Thursday, March 10, 2016

የተሸጠ ብኩርና!

(መነሻ ሃሳብ በደግፌ ጃክሰን)

  ነጠላ ያስረዘሙ ፈሪሳዊ ሰልፈኞች ከመጻሕፍቱ ጀርባ በኦርቶዶክሳዊ አቋቋም አደግድገው ቆመዋል። ከድንኳኑ ውጨኛው ክፍል "5ኛው የማኅበረ ቅዱሳን የመጻሕፍት ኤግዚቢሽን"የሚል ጽሑፍ በጉልህ ተጽፎ ተሰቅሏል። ሰይጣንም፣ ክፉውም፣ ጠማማውም፣ ነፍሰ ገዳዩም፣ ወንበዴውም፣ ሟርተኛውም ሰው "ቅዱስ ነኝ"ቢል በዚህ ዘመን የሚጠይቀው ስለሌለ (አሁን ጥያቄ የለም ማለት እስከመጨረሻው ጥያቄ የለም ማለት አይደለም) በቅድስና ማኅበር ስም የተጻፈውን ማስታወቂያ ካነበብኩ በኋላ ስለቅድስናው የሚመሰክር ፍንጭ ፍለጋ ወደድንኳኑ ጎራ አልኩ።  እዚህ ላይ አንባቢን ላስገነዝብ የምፈልገው ነገር እኛ ለራሳችን የምንሰጠው ስም ሳይሆን የምንሰራው ሥራ ነው የዋጋችንን ሚዛን ሊወስን የሚችለው። ጠንቋይ ቤት የሚካኤልና የማርያም ስዕል ተሰቅሎ መገኘቱ ወይም የገብርኤልን ዝክር እንድትደግስ በማለት ባለሀድራው በማጓራቱ ጠንቅ ዋይነቱን ወደቅድስና ማዕረግ አይለውጠውም።
ወደፍሬ ነገሩ ስመለስ፣ ከቅዱሳኑ ማኅበር ድንኳን ጎራ ብዬ የእግዚአብሔርን ቅድስና የሚያውጁ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን መድኃኒትነት የሚናገሩ፣ ዓይን ሁሉ ወደቀራንዮ እንዲመለከት የሚያሳስቡ መጻሕፍት ፍለጋ አማተርኩ። ጠላታችሁ ይፈር፣ አንድም መጽሐፍ በማጣቴ አፈርኩ። ይልቁንም እልክ የተጋቡ በሚመስል መልኩ ከዚህ በተቃራኒ የሰዎችን እይታ ከቀራንዮ በማስኮብለል ወዳልሆነ ቦታ የሚነዱ፣ ክርስቶስን በሰዎች ማንነትና ትልቅነት የሚጋርዱ ሆነው አገኘኋቸው። ካየሁት የመጻሕፍት ዐውደ ርእይ የተረዳሁት ነገር የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ ብቸኛ አዳኝነት፣ መንገድና ሕይወትነት ከመስበክ ይልቅ ቅጠልም፣ አፈርም፣ ዳቦም፣ ንፍሮም፣ ጠላም፣ ቅራሪም፣ አተላም፣ ተራራ ለተራራ መዞርም ሳማ ሰንበትም፣ አርሴማም፣ የግሼኗ ማርያምም፣ ኩክየለሽ ማርያምም፣ ግንድ አንሳውም፣ ሺህፈጁም፣ ጭሱም፣ ጠበሉም፣አመዱም፣የባህር ዛፍ ቅጠሉም፣ ጥንጁቱም፣ ቅርንፉድ መታጠንም፣ ቅማልና አይጥ ስእለት ማድረስም ገነት፣ መንግሥተ ሰማያት ሰተት አድርገው ያስገባሉ ትባላለህ። በቃ ያስገባሉ ከተባልክ አሜን ብለህ መቀበል ነው።  የኢየሱስስ ማዳን ምን ሊሆን ነው? ብሎ መጠየቅ፣ ማጉረምረም አይቻልም። መናፍቅ፣ ተሀድሶ፣ ጴንጤ ገለመሌ ካልሆንክ በስተቀር በክርስቶስ ላይ ተጨማሪ ልዩ ልዩ ተስፋዎች ሲቀርቡልህ አልቀበልም ማለት አትችልም።  "መንፈስን ሁሉ አትመኑ፣ ነገር ግን መንፈስ ከእውነት እንደሆኑመርምሩ"  የሚለውን ትምህርት ከማንበብ ውጪ ወደተግባር መለወጥ ክህደት ነው። ይህንን በመቃወም ፉከራው የገፋው ሰይጣን፣ አሹልኮ ያስገባቸውና በዘመናት ሂደት ጠፍተውና ቁጥራቸው ተመናምኖ የቆዩ መጻሕፍትን ይኼ ቅዱስ ነኝ የሚለው ማኅበር በባትሪ ፈልጎ በማሰባሰብ አራብቶና አባዝቶ አገልግሎቱን ማጠናከሩን በአግራሞት ተመለከትኩ። ሰይጣን በዚህ አገልግሎት ከመቼውም በላይ ደስተኛ ሳይሆን አይቀርም።  ማንነቱን መርምረው እንዳያውቁ በዘመቻ እየደፈቀ፣ ክህደቱን ለማግነን የሰራባቸው እንደዚህ የሰራባቸው ዘመናት አልታዩም። ኢየሱስ ክርስቶስ የንፍሮ ውሃ የጠጣልህን እስከ ዐሥር ትውልድ እምርልሃለሁ የሚል ቃል በ33 ዘመነ መዋዕለ ሥጋዌው ለማንም አላስተማረም። ይልቁንም ሌላ የመዳኛ መንገድ እንደሌለ አስረግጦ መናገሩን እናውቃለን።
ዮሐንስ 14፣6
"ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም"
ማኅበረ ቅዱሳን ግን የለም፣ ወደአብ መግባት የሚቻልባቸውንና ሰዎች በቀላሉ ከፈፀሟቸው የሚድኑባቸው ልዩ ልዩ ብልሀቶች አሉኝ የሚሉ መጻሕፍትን በአደባባይ ይሸጣል።  በዚያ ኤግዚብሽን ላይ ከተደረደሩት መጻሕፍት መካከል  “ወናሁ ትመውት በሕማመ ብድብድ እኩይ ሞት፣ ወእሬሲ ለከ ኪያሃ ከመ ስቅለትየ ወከመ ደመ ሰማዕት እለ እምቅድሜከ አኮ ለባሕቲትከ አላ ደቂቅከኒ እለ ይወውቱ በሕማመ ብድብድ በውስተ ዛቲ ገዳም እኌልቆሙ ምስለ ሰማዕታት ወአወፍዮሙ ለከ መንግሥተ ሰማያት”
ትርጉም፦ “እነሆ በክፉ ሞት በተቅማጥ ትሞታለህ፣ እሷንም እንደ ስቅለቴና ከአንተ በፊት እንደነበሩት ሰማዕታት ደም እቆጥርልሃለሁ ነገር ግን ለብቻህ አይደለም በዚች ገዳም በተቅማጥ በሽታ የሚሞቱትን ልጆችህንም ቁጥራቸውን ከሰማዕታት ጋራ አደርጋለሁ፣ መንግሥተ ሰማያትንም እሰጣቸዋለሁ” የሚለው ገድለ ተክለ ሃይማኖትን ገለጥ አድርጌ እንደገዢ ሰው አየሁት። ስድስት ክንፍ እንደተተከለለት የተቆረጠ እግር አለፍ ብሎ ወድቆ በስዕል ይታይ ነበር።
አቡነ አረጋዊ በዘንዶ ሲንሸራሸሩ፣ ለማርያም ድግስ የተቆላ አሻሮ የሸተተው ገነት እንደገባ፣ የሴት ብልት ስሞ ማርያም አፈወርቅ እንዳለችው የሚያትት፣ እግዚአብሔርን ክዶ በማርያም እንደዳነ የሚተርክ፣ ሰይጣን መነኮሰ፣ 30 ትውልድ ተማረ፣ ሎጥን ያዳነችው ማርያም ናት፣ መርቆሬዎስ ፀሐይና ፈረቃን ፈጠረ፣ ገብርኤልና ሚካኤል ሠለስቱ ደቂቅን አዳኑ፣ ሲኦልን የሞሉት ጋላና ሻንቅላ፣ የአርሴማ ድንግል ድንጋይ መካን አስወለደ፣ የአድዋን ጦርነት ጊዮርጊስ አሸነፈ ወዘተ ወጎችን የሚጠርቁ መጻሕፍት እንደጉድ ሲቸበቸቡ ተመለከትኩ። የሆኖስ ሆኖ ጊዮርጊስ አድዋ ላይ ከተዋጋ ጀግኖች አርበኞች ምን ሰሩ ሊባል ነው? የሞቱትና የቆሰሉት ምን ሲያደርጉ ኖሯል? ነው ወይስ መቁሰልና መሞት አልነበረም?
"የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል" እንዲሉ ሰዎቹ ጊዮርጊስ ባይኖር ጣልያንን ባላሸነፍንም ነበር ይሉናል። ኢህአዴግ ደርግን ያሸነፈው ማንን ይዞ ይሆን?
ማኅበሩ እያራባ ከሚሸጣቸው መጻሕፍት አብዛኛዎቹ ወንጌልን የሚቃወሙ፣ ባዶ ተስፋ የሚሰጡ፣ ሰው ከወንጌል ይልቅ እነዚያን እንዲያነብ የሚገፋፉ፣ የክርስቶስ ኢየሱስን የማዳን ሥራ አስትተው በትርኪ ምርኪ ቃል ኪዳን ላይ እንዲታመኑ የሚያበረታቱ መጻሕፍት ብቻ ድንኳኑን ሞልተው አይቻለሁ። ታዲያ ይህንን የስሁታንን ሥራ የሚሸጠው ማኅበር ራሱን "የቅዱሳን" ሲል ያሞካሸዋል።
ሰይጣን አስርጾ ያስገባቸውና በዘመናት ብዛት ተቀዳደውና ተመናምነው የሚያባዛለት አጥቶ በደነገጠበትና ተስፋ በቆረጠበት ሰዓት ማኅበሩ ድንገት ደርሶ እንደታደገው ማረዳት አይከብድም። ሊወገዙ የሚገባቸው የባዶ ተስፋ መጻሕፍትን ከወንጌል በላይ አሳትሞ ማሰራጨት ከቶ ምን ይባላል?
ከኤግዚቢሽኑ መጻሕፍት እንዲህ የሚል ቃል ያለበት መጽሐፍም ነበር።
«ወሶቤሃ አውስአ  ወይቤላ ንስኢ ወሐብኩኪ ዐሥራተ ብዙኀ ነፍሳተ መጠነ ነጠብጣብ ዝናም ዘ፬ቱ አውራኅ ለእለ አሐዱ ዕለት»
ትርጉም «ጌታም እንዲህ አላት። በዐራት ወራት ውስጥ በየቀኑ የሚወርደውን የዝናም ነጠብጣብ ያህል ነፍሳትን ዐሥራት አድርጌ ሰጥቼሻለሁ» ገድለ ክርስቶስ ሰምራ
 በዓለም ላይ በየቀኑ የሚዘንበውን የአራት ወራት ያህል የዝናብ ነጠብጣብ ውሃ ያህል ሰው ከአዳም ጀምሮ አልተፈጠረም። ገድሉ የተፈጠረውንም፣ ያልተፈጠረውንም ክርስቶስ ሰምራ ታድን ዘንድ ቃል ተገብቶላታል ይለናል።  በዚህ ቃል መሠረት ኦርቶዶክስ በክርስቶስ ሰምራ በኩል የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ናት ማለት ነው።
በሮሜ 10፣3 እንደተመለከተው
"የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም" የሚለው ቃል ከሚፈፀም በቀር እንኳን ለዓለሙ አዳኝ ልትሆን ቀርቶ ራሷም ከቆመችበት የአበው አስተምህሮ ተንሸራታ ተስፋ በሌለው ተረታ ተረት ተሸፍናለች።  ማኅበሩ የመጋረጃውን አገልግሎት በማስፋት ሰዎችን ወደጥፋት እንዳይነዳ  እንደሄሜዎስና እስክንድሮስ ለሰይጣን ተላልፎ የተሰጠ ይሁን! ብኩርናውን ለጥቅም፣ ትጋቱን ለስሁት አገልግሎት፣ ሐዋርያትም ከሰበኩት ስብከት የተለየውን የሰበከ የተረገመ ይሁን! አሜን።

Saturday, February 27, 2016

የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም!

አንዳንዶች ከአበው የተረከብነው አስተምሕሮና ሕግ በማለት ሁሉን ነገር እንደወረደ እንድንቀበለው ይፈልጋሉ። አዎ፣ አበው ብዙ ነገር አስተላልፈውልናል። ነገር ግን የተላለፈልን ነገር ሁሉ ጠቃሚ ነው ማለት አይደለም። ለእግዚአብሔር ይቀርብ የነበረ የቤተመቅደሱ መስዋእት በመቅደሱ ሚዛን ይለካ እንደነበረው ሁሉ የተላለፈልን የአበው አስተምሕሮ ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል ሚዛን መሰፈር አለበት። ምክንያቱም ከኛ በፊት ያለፉ ሁሉ በእድሜ አበው ቢሆኑም በአስተምሕሮ ግን በአበው ከለላ የስሕተት አስተምህሮ በስማቸው ሊገባ ይችላልና ነው። ስለሆነም በጅምላ አባቶቻችን ማለት ብቻውን ከስሕተት አያድንም። የአባቶች ትምሕርት ከመጻሕፍት ውጪ እንዳይኾኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በአንድ ወቅት አይሁዳውያን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምሕርት እንዲኽ እንደዛሬው የተቃወሙት እኛስ ከአባታችን ከአብርሃም ነን እያሉ ነበር። አብርሃም አባታቸው መሆኑን ቢናገሩም በአብርሃም ስም ከመነገድ በስተቀር የአብርሃምን ስራ የማይከተሉ ነበሩ ተግባራቸው ይመሰክር ነበር።

ዮሐንስ 8፣39
መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው፡ አሉት። ኢየሱስም፦ የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር፣ ብሏቸዋል።
ዛሬም ከሙሴ የተቀበልነው የታቦት ሕግ አለን የሚሉ አሉ። ነገር ግን ለሙሴ የተሰጠውንና ያደረገውን ሥራ አያደርጉም። ግን በሙሴ ስም ይነግዳሉ፣ ያታልላሉ፣ ይዋሻሉ። ሙሴን አውቀውትማ ቢኾን ኖሮ ሙሴ ያደረገውን ባደረጉ ነበር። ሙሴ የታዘዘውና ያደረገውን ይኽንን ነበርና።

ዘጸአት 25፣10
ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን።
ሙሴ ለጽላቱ ማኅደር ይሆን ዘንድ እንዲሰራ የታዘዘውና የሰራውም ታቦት ልኩ ይኼው የተጠቀሰው ሆኖ ቤተመቅደሱ ፈርሶ አገልግሎቱ እስከተቋረጠበት እስከ 70 ዓ/ም ድረስ ለ 2000 ዘመን ይህ ልኬታ ተሻሽሎና ተቀይሮ ስለመገኘቱ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ላይ አልተጻፈም። ነገር ግን ዛሬ የጽላቱ ማደሪያ የሆነው ታቦት አለን የሚሉ ወገኖች በሙሴ ሽፋን የሚሰሩት ታቦት ርዝመቱም፣ ቁመቱም፣ ወርዱም እንደጠራቢው ችሎታና እንደአስጠራቢው ፍላጎት እንጂ የተወሰነ መጠን በሌለው ልቅ ፍላጎት ሲጠቀሙ ይታያሉ። የእግዚአብሔርን የመሥፈሪያ ሚዛን ሊጠቀሙ ይቅርና ለሚሰሩት የስሕተት ሥራ እንኳን አንድ ወጥ የሕግ ሚዛን ለራሳቸው የላቸውም። ጠራቢዎቹም የእግዚአብሔር መንፈስ እንደሞላባቸው በሙሴ እንደተመረጡት አልያብና ባስልኤል ሳይሆን ቤተክርስቲያን አነውራ የምትጠራቸው፣ ቆብና ቀሚስ የጣሉ መነኮሳት፣ ያፈረሱ ቄሶችና ደጋሚ ደብተራዎች፣ የሚያስገኘውን ገቢ የቀመሱ አወዳሾች መሆናቸው የአደባባይ ምስጢር ነው።   በመኖሪያ ቤቱ የእንጨት ማሽን ተክሎ፣ ከጣውላ አቅራቢዎች ምንነቱ ያልታወቀ ጥርብ እየገዛ በሚቀርቡለት የፈላጊዎች ትእዛዝ መሠረት ጽላት የሚባለውን የዘመኑን የሰዎች መሻት እየቀረጸ የሚያከፋፍል ሰው የዚኽ ጽሑፍ አቅራቢ ያውቃል። ከሥራዎቹም የተወሰነውን ለማየት ችሏል። ከታች በገብርኤል ስም ከጣውላው የተቀረጸ ምስል ለአብነት ይመለከቷል።   እግዚአብሔር በሚሰራውና ጥንት ባደረገው ነገር ሁሉ ከመረጣቸው ሰዎች ማንነት ጀምሮ የተለዩና በሚሰሩትም ሥራ ጥንቃቄና ትእዛዙን የጠበቀ ስለመሆኑ ለአፍታ የሚዘነጋ ጉዳይ አይደለም።  ዛሬስ? በ 0% የቀደመ ሥርዓት ላይ ሆነው በሙሴ ሕግ ሥር የመደበቅ ዘመን አብቅቷል። በትውልዱም የተሸፈነው መገለጡ አይቀርም። በስተመጨረሻም የእግዚአብሔርም ትእግስት ሲሞላ ውርደት መከተሉ ሳይታለም የተፈታ ነው። በዋጋ መሸጪያ ተመን ገበያ ወጥቶለት በገንዘብ የሚገዛ ጽላት በጭራሽ ሊኖር አይችልም።
እንደእውነቱ ከሆነ በዚህ ዘመን በአባቶች እያሳበቡ የእግዚአብሔርን ቃል በመቀየር በትውልድ ላይ ለመጫን መሞከር ማብቃት አለበት።
 ሙሴ የዕንቁውን ጽላት አሮን ባሰራው የጥጃው ጣኦት ላይ ከሰበረ በኋላ አስመስለኽ ቅረፅና አምጣ ተብሎ በእግዚአብሔር ሲነገረው ለጽላቱ ማደሪያ ተብሎ አስቀድሞ የተሰጠው የታቦቱ ርዝመት፣ ቁመትና ወርድ ላይ የተሰጠ የለውጥ ትእዛዝ አልነበረም። ምክንያቱም የተሰበረው ጽላቱ እንጂ ታቦቱ አይደለምና።  ስለዚህ "ቀር ከመ ቀዳሚ"  የተባለው ጽላቱን እንጂ ማደሪያውን ታቦት ካልሆነ ሙሴ ያላሻሻለውን ታቦት ዛሬ ያሻሻሉት ከየት ባገኙት አምላካዊ ትእዛዝ ነው?  ውሸታቸውን ለማጽደቅ የፈረደበት የሙሴን ስም አቅርበው ሊሞግቱን ይዳዳሉ።
ስለማኅደሩ መሻሻል የተነገረ ካልነበረ እነዚህኞቹ በራሳችን ሥልጣን አሻሽለናል ይበሉን እንጂ ሙሴን ለሐሰት ምስክርነት አይጥሩብን።
ከዚያም ሌላ ሙሴ የፊተኞቹን ጽላቶች አስመስሎ ከቀረጸ በኋላ ይዞ የሄደው ወደሲና ተራራ ነው። በዚያም እግዚአብሔር በጣቶቹ 10ቱን ትእዛዛት ጻፈባቸው እንጂ ሙሴ በጭራሽ አልጻፈም።

ዘዳግም 10፣3-4
ከግራርም እንጨት ታቦትን ሠራሁ፥ እንደ ፊተኞችም ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረብሁ፤ ሁለቱንም ጽላቶች በእጄ ይዤ ወደ ተራራው ወጣሁ።
ስብሰባ ተደርጎ በነበረበትም ቀን እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳት ውስጥ ሆኖ የተናገራችሁን አሠርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደ ነበረ በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ።
ይለናል መጽሐፍ ቅዱሳችን።

እዚህ ላይ እንደምናነበው ጽላቶቹ ላይ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ሆኖ ሳለ ሙሴ እንደጻፈ አድርጎ በሙሴ ላይ መዋሸት ለምን አስፈለገ?  አስመስለኽ ቅረጽና አምጣ መባሉን ልክ እራስኽ እየጻፍክባቸው አባዛ የተባለ ማስመሰል በእግዚአብሔር ላይ መዋሸት አይደለምን? ያልተባለውን እንደተባለ፣ ያልተነገረውን እንደተነገረ አድርጎ በማቅረብ የራስኽንም ስሕተት እንደማጽደቂያ መሳሪያ አድርጎ መጠቀም የከፋ ክሕደትና ሕዝቡን በስሕተት መንገድ መንዳት ነው።  ሙሴን ያላደረገው ነገር አድርገኻል ማለት መሳደብ ነው፣ እግዚአብሔርንም ለሙሴ አንተው ጻፍባቸው ያላለውን እንዳለ ማስመሰልስ ዋሾ ማድረግ አይደለምን?
 ጽላቶቹ ላይ የተጻፈባቸውና ሙሴ የተቀበላቸው 10ቱን ትእዛዛት ሆኖ ሳለ የሰው ስም ወይም የሰው ምስል ያለበት አድርጎ በማቅረብ በዚህ ዘመን እኛ የምንፈልገውን የልባችን ፈቃድ ለማሳካት ማጭበርበርስ ለምን ይሆን? በየትኛውስ ቃል እንደገፋለን? የምናስደስተው ሰውን ወይስ እግዚአብሔርን? መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ያላለውን ብለኻል በሚሉ ዋሾዎች ተደስቶ አያውቅም። ሊደሰትም አይችልም። ከራሱ አንቅቶ የሚናገረው የሐሰት አባት የሆነው ዲያብሎስ ብቻ ነው።
እግዚአብሔር የሰጠውን ሕግ የሚያጸናውና የሚሽረው ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ሰው እንዴት የኪዳኑን ሕግ ራሱ ለራሱ ስሜት ያሻሽላል?
የሙሴን ታቦተ ሕግ ተከትለናል ማለት እግዚአብሔር ያላለውን በራስ ፍላጎት እንደሚመች አድርጎ ማቅረብ ነው እንዴ?
ሌላው መነሳት ያለበት ነገር፣ ዛሬ የኪዳኑን ጽላት እንጠቀማለን የሚሉ ሰዎች የኦሪቱ የጽላት ሕግ፣ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለማነው? የሚለው ነው።

 በማያከራክር መልኩ የቃልኪዳኑ ታቦት ሕግ የተሰጠው ለእስራኤል ዘሥጋ ብቻ ነው። ይኽ ሆኖ ሳለ እናንተን ያ የኪዳን የሕግ ውል የጨመራችሁ በየትኛው የብሉይ ኪዳን ቃል ላይ ነው?  እግዚአብሔር ውሉን በሙሴ ፀሐፊዎች አማካይነት በአራቱ ብሔረ ኦሪት ጽፎ ሰጥቷቸዋል። የእናንተስ ውል በነማን በኩል፣ መቼና የት ቃል ተገባላችሁ? ብለን እንጠይቃቸዋለን።
ምክንያቱም እስራኤላውያን አፋቸውን ሞልተው እንዲህ ሲሉን እናገኛቸዋለን።
ዘዳግም 5 ፣2
አምላካችን እግዚአብሔር በኮሬብ ከእኛ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ።

ያ ቃልኪዳን ከፈረሰና የመስዋእቱ አገልግሎት ከተቋረጠ 2ሺህ ዘመን አልፎታል። ከዚያ በኋላ ከእስራኤላውያን ውጪ እግዚአብሔር የታቦት ቃልኪዳን የገባላቸው ሌላ ሕዝቦች የሉም። ኧረ በጭራሽ አይኖርምም። ምክንያቱም ያ ውል የተገባው ለተወሰነ ሕዝብ ብቻ ስለሆነ ሁሉን ያካተተ አዲስ ውል ያስፈልግ ስለነበር ለተወሰነ ሕዝብ በድጋሜ ቃል የሚገባበት ምክንያት የለም።
ሮሜ 9፣4
እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና"

ነገር ግን ሕዝቤ ያልተባለን ሕዝቤ ለማለት አህዛብ ሁሉ ወደመጠራቱ እንዲገቡ አዲስ ቃል ኪዳን አስፈልጓል።
ሮሜ 9፣26 እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ስፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሔር ልጆች ተብለው ይጠራሉ፥ ይላል።

በዚህም ምክንያት ለአንድ ሕዝብ ብቻ ተሰጥቶ የነበረው ሕግ ቀርቶ ሁሉን የሚመለከት ሕግ እንዲመጣ ማስፈለጉን በአዲስ ኪዳን የኦሪቱ የመስዋእት አገልግሎት ከእንግዲህ አይታሰብም ተብሎ ትንቢት ተነግሯል።

ኤርምያስ 31፣31
እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር።

 ለምን አዲስ ቃልኪዳን መግባት አስፈለገው? ምክንያቱም፣

ኤርምያስ 31፣32
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም፤ እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር።

ስለዚህ በሰማያዊው መስዋእት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተሻለ ኪዳን ስለተገባልን አሁን ልንናገርበት ጊዜው ባልሆነ የዚህ ምድር ሥርዓት አይደለንም። ጳውሎስ ድሮ ነበረ፣ አሁን ግን የለም ይለናል።

ዕብራውያን 9፣5
በላይዋም ማስተስሪያውን የሚጋርዱ የክብር ኪሩቤል ነበሩ፤ ስለ እነዚህም ስለ እያንዳንዳቸው ልንናገር አሁን አንችልም።
ምክንያቱም፣
ዕብራውያን 7፣22
እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።
ስለዚህ አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ መሪያችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን በማለት ለስሕተት መሸፈኛ አድርጎ ማቅረብ አያድነንም። አብርሃም አባታችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን ይሉ የነበረ፣ ነገር ግን የሚነገራቸውን ቃል እኛ ከሁሉ ቀድመን ያወቅን ነን በሚል ትምክህት ለመቀበል ያልፈለጉትን ሊቃውንተ አይሁድን እንዲህ ብሏቸዋል።

ዮሐንስ 8፣47
ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።

ስለዚህ በዚህ ዘመንም የቀደመችው ሃይማኖት በማለት ራስን በመካብ ብልጫ አይገኝም። ከአይሁድ የቀደመ ሃይማኖት የለምና። ነገር ቀድሞ በመገኘት አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ ፈለጋችን ነው፣ ማለት ከስህተት አያርቅም። ምክንያቱም አብርሃምና ሙሴ የተቀበሉትንና የፈፀሙትን ሕገ እግዚአብሔር ሳይሸራርፉና ሳያሻሽሉ በማድረግ እንጂ የነሱ ተከታይ መሆን የሚቻለው በስማቸው በመነገድ ግን በሕጉ በሌሉበት ሁኔታ የሙሴ ተከታዮች በማለት ራስን ካልሆነ ማንንም ማታለል አይቻልም።
ስለሆነም የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም። እንዲቀየርና እንዲሻሻል ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሕግ አልነበረም። ፊተኛውና ኋለኛው ጸሐፊ ራሱ እግዚአብሔር፣ ጽሕፈቱም ሕግጋቶች ነበሩ። የተጻፈውም በሲና ተራራ ነጎድጓዳማ ድምጽ መካከል እንጂ በጥቃቅንና አነስተኛ የእንጨት መላጊያ ውስጥ አልፎ የዚህ ምድር በሆነች እጅ ብልሃት አይደለም።
የእጅ ብልሃት ይኽ ነው።

Tuesday, February 23, 2016

ቃል ኪዳን!


“ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” (መዝ. 88/89፥3)።
በዚህ ቃል ሽፋንነት የገባው የስሕተት ትምህርት፥ የክርስቶስን የመካከለኛነት ስፍራ ለፍጡራን አሰጥቷል። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ከተለያዩ ቅዱሳን ጋር ስለ ልዩ ልዩ ጕዳዮች የገባውን ቃል ኪዳን መነሻ በማድረግና፥ “ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” የሚለውን ቃል በመታከክ፥ በዐዲስ ኪዳንም ኀጢአተኞች ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡበትን የተለያየ ቃል ኪዳን ለቅዱሳን ሰጥቷል የሚሉ አሉ።
በቅዱሳን ስም በተደረሱት ገድላትና ድርሳናት ውስጥ፥ ከራስ ዐልፈው ሰባትና ከዚያም በላይ ያለውን ትውልድ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገቡ ቃል ኪዳኖች እንዳሉ ተገልጧል። ቃል ኪዳኖቹ የተመሠረቱትም በቅዱሳን ስም የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ ነው። ሌላው ቀርቶ የአንዱን ቅዱስ ገድል የጻፈ፥ ያጻፈ፥ ያነበበ፥ የተረጐመ፥ የሰማ፥ ያሰማ እንኳ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርስ ተስፋ የሚሰጡ ገድላት በርካታ ናቸው። ይህም በራእ. 1፥3 ላይ፥ “ዘመኑ ቀርቧልና፥ የሚያነብበው የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁ ብፁዓን ናቸው” ከሚለው የተኰረጀ ሊኾን ይችላል።
በመዝሙረ ዳዊት 88/89፥3 ላይ የተገለጠው፥ እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንጂ ሌሎችን አይወክልም። በቍጥር 4 ላይ፥ “ለባሪያዬ ለዳዊት ማልኹ፤ ዘርኽን ለዘላለም አዘጋጃለኹ፤ ዙፋንኽንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለኹ” ማለቱም ይህንኑ ያስረዳል። ቃል ኪዳን የገባው የማይዋሽ እግዚአብሔር በመኾኑ፥ “ኪዳኔንም አላረክስም፤ ከከንፈሬም የወጣውን አልለውጥም። ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልኹ። ዘሩ ለዘለዓለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሓይ ይኖራል። ለዘለዓለም እንደ ጨረቃ ይጸናል። ምስክርነቱ በሰማይ የታመነ ነው” ብሎ ነገሩን እንዳጻናለት ይናገራል (ቍጥር 34-37)።
ይህ ስለ ዙፋኑ መጽናት የተገባው ቃል ኪዳን ለጊዜው ጥላነቱ በሰሎሞን ሲታይ፥ በክርስቶስ ግን ተፈጽሟል (2ሳሙ. 7፥12-16፤ ሉቃ. 1፥32፤ ዕብ. 1፥5፡8፤ ራእ. 22፥11)። እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ አምላክ በመኾኑ፥ ዳዊት ከሞተ በኋላ ልጁ ሰሎሞን በቃል ኪዳኑ ውስጥ የነበረውን ውል አፍርሶ በመገኘቱ መንግሥቱ መቀደድ ቢኖርበትም፥ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት የገባውን ቃል ኪዳን ዐስቦ ይህን በሰሎሞን ዘመን አላደረገበትም (ዳን. 9፥4፤ 1ነገ. 9፥5-7፤ 11፥1-13)።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ (በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት) ቃል ኪዳን ከተገባላቸው መካከል ዋናዎቹ፥ አዳም፥ ኖኅ፥ አብርሃም፥ ሙሴና ዳዊት ናቸው። ለአዳም የተሰጠው ቃል ኪዳን መልካሙንና ክፉውን በሚያስታውቀው ዛፍ ምልክትነት፥ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ተስፋን የያዘ ነበር። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች አዳምና ሔዋን በኪዳኑ ስላልጸኑ ሞት ገዛቸው (ዘፍ. 2፥8-17፤ ሆሴ. 6፥7)።
ከአዳም ቀጥሎ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለኖኅ ሲኾን፥ ምድር ዳግመኛ በጥፋት ውሃ እንዳትጠፋ የቆመ ኪዳን ነው። ይህ በምድር ላይ የመኖርን ተስፋ የያዘው ኪዳን፥ በቀስተ ደመና ምልክትነት ተገልጦ ለዓለም ሕዝብ ኹሉ ያገለግላል (ዘፍ. 9፥1-17)።
እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው ቃል ኪዳን፥ በብሉይ ኪዳን ጐላ ያለ ስፍራ ከተሰጣቸውና በዐዲስ ኪዳን ፍጻሜ ካገኙት ቃል ኪዳኖች መካከል ይጠቀሳል። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች ለጊዜው ምድራዊቱን ከነዓንን የወረሱት አብርሃምና በይሥሐቅ በኩል የተቈጠሩት ዘሮቹ ኹሉ ሲኾኑ፥ ፍጻሜው ግን አይሁድ፥ አሕዛብ ሳይባል አብርሃምን በእምነት በመምሰላቸው የአብርሃም ልጆች የኾኑት ኹሉ ናቸው (ገላ. 3፥7-9፡29፤ ሮሜ 4፥11-12፤ 9፥7-8)። የዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ግዝረት፥ የቃል ኪዳኑ ተስፋ ደግሞ በዘሩ የአሕዛብ መባረክና ከነዓንን መውረስ ነው (ዘፍ. 17፥1-21፤ ሮሜ 4፥11)።
የምድር አሕዛብ ኹሉ የተባረኩበት የአብርሃም ዘር ክርስቶስ፥ የምድራዊቱ ከነዓን አማናዊት የኾነችውን ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን የሚያወርስ በመኾኑ፥ ለቃል ኪዳኑ ፍጻሜን ሰጥቷል (ገላ. 3፥16)። እግዚአብሔር በክርስቶስ ያደረገው ኹሉ ለአብርሃም በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መኾኑንም ቅዱሳን መስክረዋል (ሉቃ. 1፥54፡73)።
በመቀጠል ደግሞ ለሙሴ የተሰጠውን ቃል ኪዳን እናገኛለን (ዘፀ. 19፥5-6፤ 24፥7-8)። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች የኾኑት ሕዝበ እስራኤል፥ የአብርሃምን የቃል ኪዳን ምልክት ተከትለው ሰንበታቱን መጠበቃቸው ለዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ኾኗል (ዘፀ. 31፥13፤ ሕዝ. 20፥10-17)። በቃል ኪዳኑ የተሰጣቸው ተስፋ በአገራቸው ሕይወትን ማግኘት ነው። ይህንም ገና ከምድረ ግብጽ ሳይወጡ በነበረው ዕለት ምሽት ላይ ያረዱት የፋሲካ መታሰቢያ በግ ደም አረጋግጦላቸዋል (ዘፀ. 12፥21-28)።
ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ሲና ተራራ ሲደርሱ፥ ሕጉን በድንጋይ ጽላት ጽፎ ይጠብቁትና በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል ቃል ኪዳን ይኾን ዘንድ ለሙሴ ሰጠው። ይህም ብሉይ ኪዳን ተብሎ የተጠራው ነው (ዘፀ. 19፥20፤ 31፥18፤ 20፥1-17፤ 34፥28፤ ዘዳ. 4፥13)። በእንሰሳት ደም የቆመው ብሉይ ኪዳን ወደ ፊት ለሚመጣው ዐዲስ ኪዳን መንገድ ጠራጊ እንጂ በራሱ ቋሚነት አልነበረውም። የጽላቱ ተሰብረው መተካታቸው፥ የማደሪያው ድንኳን ሰሎሞን በሠራው ቤተ መቅደስ መተካቱ፥ የመሥዋዕት መደጋገምና የመሳሰሉት ኹኔታዎች ለጊዜያዊነቱ ምልክቶች ተደርገው ይወሰዳሉ። ይበልጥ ደግሞ ትንቢቱ ይህን አረጋግጧል (ዘዳ. 18፥15፤ ኤር. 31፥31)።
ቃል ኪዳን የሚጸናው ኹለቱም ወገኖች ሲጠብቁት ብቻ ነው። ከኹለቱ አንዱ ጠብቆ ሌላው ቢያፈርሰው ቃል ኪዳን መኾኑ ይቀራል። ብሉይ ኪዳን ጊዜያዊነቱ ሳያንስ ሕዝቡ ሊጠብቀው ባለመቻሉ ቃል ኪዳንነቱ ቀረ። እግዚአብሔርም ከዚህ በብዙ መንገድ የተሻለውን ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚገባ ተናገረ (ኤር. 31፥31-34)። ይህም ስለ ዐዲስ ኪዳን የተነገረ ትንቢት በመኾኑ፥ በዕብራውያን 8 ላይ ተፈጻሚ ኾኖ ተጠቀሰ። ዐዲስ ኪዳን የተሻለና የበለጠ ኪዳን በመኾኑ ብሉይ ኪዳን ከነጓዙ ፍጻሜ አግኝቶ እንደሚቀርና የሚጠቀምበት ቀርቶ የሚያስበው እንኳ እንደማይኖር እግዚአብሔር በአጽንዖት ተናገረ (ኤር. 3፥16)።
እግዚአብሔር እስከዚህ ድረስ ለተለያዩ ቅዱሳንና ለአጠቃላዩ የእስራኤል ሕዝብ ገብቶ የነበረውን ቃል ኪዳን ኹሉ በመጠቅለል፥ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ዐዲስና ለዘላለም የማይፈርስ፥ ተጨማሪ የማያስፈልገው ቃል ኪዳን ገባ። እርሱም በገዛ ደሙ የመሠረተው ዐዲስ ኪዳን ነው (ሉቃ. 22፥19-20፤ ኢሳ. 42፥6-7)። ይህ ኪዳን በክርስቶስ ለሚያምኑ ኹሉ የተሰጠ ሲኾን፥ የዘላለም ሕይወትን ተስፋ የያዘ ቃል ኪዳን ነው። የተስፋው ምልክቶችም ጥምቀትና ቅዱስ ቍርባን ናቸው (ማር. 16፥16፤ 1ቆሮ. 11፥23-26፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 80)።
ዐዲስ ኪዳን ብሉይ ኪዳንን በከፊል ሳይኾን ሙሉ በሙሉ ተክቷል። ዐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ክብሩ የጸናበት፥ ኹሉ የተፈጸመበት ታላቅ ቃል ኪዳን መኾኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍትም መስክረዋል፤ “ወበምክረ ዚኣከ ወልድከ ዋሕድ ኢየሱስ ዘተሰቅለ በእንተ መድኀኒትነ ዘበቃለ ኪዳንከ ቦቱ ገበርከ ሠሚረከ ቦቱ። - ለድኅነታችን በተሰቀለው በአንድያ ልጅኽ በኢየሱስ በባሕርይኽ ምክር ደስ ተሰኝተኽበት ቃል ኪዳንኽን ኹሉ በእርሱ አድርገኻል” (መጽሐፈ ቅዳሴ 1984፣ ገጽ 65)።  
እንዲሁም በእልመስጦአግያ፥
“ከመ ታእምሩ ፈቃዶ ለኢየሱስ ክርስቶስ ወትሌብዉ ምስጢረ መድኀኒትክሙ ኦ አንትሙ እደው ወአንስት ቅዱሳት እለ ሀሎክሙ ውስተ ተመክሖ በክርስቶስ፥ ወኩኑ አሐደ ምስለ ብእሲ ዘውስጥ አንትሙኬ እለ አጽንዐ እግዚአብሔር ኪዳኖ ምስሌክሙ ወሤመ መንፈሶ ውስቴትክሙ፡፡”
ትርጓሜ፥ “የኢየሱስ ክርስቶስን ፈቃድ ታውቁ ዘንድና የደኅንነታችኹን ምስጢር ታስተውሉ ዘንድ፥ በክርስቶስ ትምክሕት ያላችኹ እናንተ ወንዶችና ቅዱሳት ሴቶች ሆይ፥ ከውስጣዊ ሰውነት ጋር አንድ ኹኑ፤ እግዚአብሔር ኪዳኑን ከእናንተ ጋር ያጸና መንፈሱንም በውስጣችኹ ያሳደረ እናንተ ናችኹ እኮ” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 24)።
የእግዚአብሔር የባሕርይ ምክርና ሐሳቡ ለአንዴም ለመጨረሻ ጊዜም በክርስቶስ በኩል በገባው ዐዲስ ኪዳን በኩል ተፈጽሟል። እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ጋር ባለው ታሪክ የገባው የመጨረሻው ቃል ኪዳን ዐዲስ ኪዳን ብቻ ነው። በዚህ ኪዳን ያልተፈጸመለት ወይም የቀረው ነገር ኖሮ፥ በሌላ ቃል ኪዳን ለመፈጸም በማሰብ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ሌላ ቃል ኪዳን ገብቷል የሚለው ትምህርት ልብ ወለድ ከመኾን አይዘልም፤ ምክንያቱም የዘመን ፍጻሜ በኾነው ባለንበት ዘመን፥ እግዚአብሔር ለማድረግ ያሰበው፥ ነገሮችን ኹሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል እንጂ ሌላ ቃል ኪዳን ለመግባት አይደለም (ኤፌ. 1፥10)።
ከላይ ለማሳየት እንደ ተሞከረው፥ ለቀደሙት አበው የገባው ቃል ኪዳን፥ ከወቅቱ ኹኔታ ጋር በተያያዘ መንገድ፥ ወይም ስለ ወደ ፊቱ ተስፋ ነበር እንጂ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ቃል ኪዳን አልነበረም፤ እንዲህ ያለውን ቃል ኪዳን ከማንም ፍጡር ጋር አልገባም። ምናልባት ለአዳም የገባው ቃል ኪዳን በአዳም ባይፈርስ ኖሮ፥ ለዘላለም በሕይወት መኖርን የሚያስገኝ ቃል ኪዳን ይኾን ይኾናል። ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበትን ቃል ኪዳን የገባው ግን በክርስቶስ በኩል ብቻ ነው።
በሐሰት ለቅዱሳን በዐዲስ ኪዳን ተገባ በሚባለው ቃል ኪዳን መሠረት፥ እንዲህና እንዲያ ያደረገ ይህንና ያን ያገኛል የሚል ተስፋ በብዙ አዋልድ መጻሕፍት በስፋት ተጽፎ እናነባለን። አብዛኛው ቃል ኪዳን ተሰጠ ተብሎ የሚተረከው ቅዱሳኑ ሊሞቱ ሲሉ በመጨረሻዋ ሰዓት ላይ ነው። እንዲህ ከኾነ ታዲያ በዐዲስ ኪዳን መጥምቁ ዮሐንስ፥ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ፥ እና ያዕቆብ በግፍ የተገደሉ ቅዱሳን ናቸው፤ ሊሞቱ ሲሉም ኾነ ከዚያ በፊት ቃል ኪዳን እንደ ተገባላቸው በሐዲስ ኪዳን ውስጥ አናገኝም (ማቴ. 14፥10-12፤ ሐ.ሥ. 7፥6 12፥2)። ለነዚህ ቅዱሳን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ሰዎች ከልባቸው አንቅተው (አመንጭተው) በደረሱላቸው ድርሰትና ገድላት ውስጥ ግን፥ የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን ጻጽፈው ሊያስነብቡን ቢከጅሉም አንድም እውነትነት የለውም።
ዛሬ ብዙዎቹ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባልኾነ ቃል ኪዳን ተታለዋል። ስለዚህ በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ከመጽደቅና በእርሱ ኖረው መልካም የሥራ ፍሬን ከማፍራት ይልቅ፥ በኀጢአት ላይ ኀጢአትን በመጨመር ከእግዚአብሔር ባልኾነው ቃል ኪዳን እየተኵራሩ፥ ‘በእገሌ ቃል ኪዳን መሠረት እንዲህ ካደረግኹ አልኰነንም’ ብለው ራሳቸውን ይሸነግላሉ። የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ይላቸዋል፤ “ለዐመፀኞች ልጆች ወዮላቸው፥ ይላል እግዚአብሔር። ከእኔ ዘንድ ያልኾነ ምክር ይመከራሉ። ኀጢአትንም በኀጢአት ላይ ይጨምሩ ዘንድ ከመንፈሴ ዘንድ ያልኾነውን ቃል ኪዳን ያደርጋሉ።” (ኢሳ. 30፥1)።
ምንጭ፦ የተቀበረ መክሊት 3ኛ ገጽ 106

Sunday, February 14, 2016

የቫላንታይን ዴይ ከክርስትና አንፃር!


ስንቶቻችን ይሆን የቫለንታይን ቀን (የፍቅረኞች ቀን ብለን የምናከብረው) የሚከበርበት ምክንያትና መነሻው የምናውቀው? ወይስ ሰው ስለ አከበረውና የስልጣኔ መገለጫ መስሎን ነው የምናከብረው? ክርስቶስ ከመወለዱ ከብዙ ክፍለ ዘመናት በፊት አረማዊ ሮማውያን የካቲት 14 ማታና የካቲት 15 "የተኩላ አዳኙ" ለሚሉት ሉፐርኩስ (Lupercus) ክብር በማለት በጣኦት አምልኮ ያከብሩት ነበር። ሮማውያን ይህ በዓል ሉፐርካልያ (Lupercalia) ይሉታል።
ንጉሥ ቆንጠንጢኖስ ክርስትና የሮማውያን ይፋዊ ሃይማኖት መሆኑ በማወጁ ማንኛውም የጣኦት አምልኮ እንዲቀር ቢያስጠነቅቅም የተወስኑ ሮማውያን ሰዎች ግን በዓሉን ማክበር አልተዉም።
ይህንን አረማዊ በዓል ማለትም ሉፐርካልያ የሮማው ጳጳስ ገላስዮስ ክርስትያናዊ በዓል ሆኖ እንዲከበር አደረጉ። ጳጳስ ገላስዮስ ለካቲት 15 ሲከበር የነበረው በዓል የቅዱስ ቫለንታይን ቀን በሚል አዲስ ስያሜ የካቲት 14 እንዲከበር አደረጉ።
እንዴት ይህ አረማዊ በዓል የቅዱስ ቫለንታይን ቀን የሚል ስያሜ ተሰጠው?
ቫለንታይን የሚል ስም በሮማውያን ዘንድ የተለመደ ስያሜ ነው። ቫላንታይን ጥንታዊው ታዋቂው ሉፐርኩስ ነው። ሉፐርኩስ በግሪካውያን ፓን (pan) ተብሎ ይጠራል። በጥንታውያን አይሁድ ደግሞ ይህ ፓን በአል (Baal) በሚል ስያሜ ይታወቃል። በአል በመጽሓፍ ቅዱስ ዘፍጥረት 10-9 ላይ ታላቁ አዳኝ ተብሎ ለተገለጸው ኒምሮድ ሌላኛው መጠርያው ነው። ኒምሮድ የሮማውያን የተኩላ አዳኙ ሉፐርኩስ ነበር። በዚህ መሠረትም የቅዱስ ቫለንታይን ቀን የአረማውያን ለኒምሮድ ክብር የሚያከብሩት የጣኦት አምልኮ ነው።
ቫለንታይን የሚል ቃል ቫለንቲኑስ (valentinus) ቫለንስ ከሚል የላቲን ቃል የመጣ ነው። ቀጥተኛ ትርጉሙ ጠንካራ፣ሃይለኛ ታላቅ ማለት ነው። ዘፍጥረት10-9 ላይ እንደምናነበው " እርሱም በእግዚአብሔር ፊት አዳኝ ነበረ። ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት ሃያል አዳኝ እንደ ኒምሮድ ተባለ።  ኒምሮድ የሮማውያን ጀግና ሃይለኛ ሰው ቫለንታይን ነበር።
ሌላኛው የኒምሮድ ስም ሳንክቱስ (Sanctus) ወይ ሳንታ (santa) ነው። ሳይንት (saint) የሚል የእግሊዝኛ ትርጉም አለው ማለትም ቅዱስ። የሮማውያን ሉፐርካልያ በመጨረሻ ቅዱስ ቫለንታይን የሚል ስያሜ ያዘ ማለት ነው።
ጥንታውያን ሮማውያን ከባቢሎናውያን በቀዱት አረማዊ የልብ (heart) ምልክት ይጠቀማሉ። በባቢሎናውያን በአል (baal) ልብ የሚል ፍቺ ነው ያለው። በአሁኑ ጊዜ ይህ አረማዊ የልብ ምልክት ለቫለንታይን ቀን (የፍቅረኛሞች ቀን የምንለው) መገለጫ እንጠቀምበታለን። በአል የባቢሎናውያን የጣኦት ጌታ ነበር። በሌላ መንገድም ኒምሮድ ወይም ቅዱስ ቫለንታይን ሳተርን ተብሎ ይጠራል። ሳተርን የሮማ-ባቢሎን ከአባራሪዎቹ ለመሸሽ በምስጥራዊ ቦታ የሚደበቅ ጣኦት ነው። ሳተርን የሚል የላቲን ቃል ሴሜቲክ (አይሁድ) ቋንቋ ከሚናገሩ ባቢሎናውያን የተገኝ ነው። መደበቅ፣ ራስን መደበቅ የሚል ፍቺ አለው።
በጥንታዊ እምነትም ኒምሮድ (ሳተርን) ከአባራሪዎቹ በመሸሽ ወደ ጣልያን እንደተጓዘ ይነገራል። የአፐኒን ተራራ ስያሜው ወደ ኔምብሮድ ወይም ኒምሮድ ተቀየረ።ይህ ተራራ ኒምሮድ በጣልያን የተሸሸገበት ቦታ ነበር። ሮማም በዚህ ተራራ ላይ እንደ ተመሰረተች ይታወቃል። ሮም ፈርሳ እንደገና ከመሰራትዋ 753 ዓ/ዓ በፊት ሳቹርንያ (ሳተርን፡ኒምሮድ የተደበቀባት ቦታ) የሚል ስያሜ ነበራት። ኒምሮድ በዚህ ቦታ ተይዞ በፈጸመው ወንጀል ተገደለ። በንጉሥ ቆስንጠንጢኖስ ጊዜም ክርስቲያናዊ ሰማዕት የሚል የውሸት ክብር ተሰጥቶት በሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስትያን መዘከር ጀመረ። ኒምሮድ፣ ባል፣ ቫለንታይን፣ ታላቁ አዳኝ፣ ፋውኑስና ሉፐርክስ 31ኛ፣ 32ኛና 33ኛና ደረጃ (ዲግሪ) ላይ ያሉ ፍሪማሶኖሪዎች ከሚያመልኩት ባፎሜት (የሜንደዝ ፍየል) አምልኮ አጋንንት ጋር የሚስተካከል ነው።
እንግዲህ በሰላቢ እጆች (ኢሉሚናቲ) ሴራ ዘመናዊነት ተላብሶ ድብቅ ጣኦት የሚመለክበት የቅዱስ ቫለንታይን ቀን እኛ ደግሞ የፍቅረኛሞች ቀን በማለት እያከበርን ማለትም እያመለክን ነው። አንድ በአል የሚከበርበትን ምክንያትና አስፈላጊነት ሊኖረው ግድ ነው። ሆኖም የምናከብረውን በአል የምናከብርበትን ምክንያትና አስፈላጊነት ሳናውቅ ከሴረኞች ድብቅ አላማ ማስፈጸሚያ ከመሆን መቆጠብ ይበጀናል፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር ነዉ!

Saturday, January 30, 2016

ፓትርያርክ ማትያስ ስለማኅበረ ቅዱሳን የጻፉት ደብዳቤ ከመዘግየቱ በስተቀር ሀቅነቱ ጥያቄ የሚያስነሳ አይደለም!

ማኅበረ ቅዱሳን ማለት ለተረት፤ ለእንቆቅልሽ፤ ለልማድና ለባህል እምነት ጥብቅና የሚቆም፤ የወንጌል ቃል ጆሮውን የሚያሳክከው፤ በኢየሱስ ክርስቶስ የእውነት መንገድ ላይ ቆሞ እንዳይገለጥ መጋረጃ የሚጋርድ የጠላት መልእክተኛ ማለት ነው። ማኅበረ ቅዱሳን በሀገሪቱ ላይ የብርሃን ወንጌል እንዳይበራ የጭለማ ሥራ የሚሰራ፤ ሰዎች በእጃቸው ያለውን እውነት እንዳያዩ ወደገደል የሚመራ እውር መሪ ማለት ነው።
ማኅበረ ቅዱሳን ማለት በአንድ ወቅት የእግዚአብሔር ሕዝብ የተባለው እስራኤል በእግዚአብሔር ላይ ያለውን እምነት ትቶ የራሱን የልብ መሻትና ምኞት በተከተለበት ወቅት እንደሆነው ዓይነት በተመሳሳይ መልኩ በሀገራችን በኢትዮጵያም ከፊት ሆኖ በሀሰት እየመራ በእውነት የሚፈርድ እንዲታጣ ያደረገ፤ በሀሰትም የሚያስተምር እንዲበዛ የፈለፈለ፤ ልቡን ያደነደነ ትውልድ እንዲበረከት ሚና የተጫወተ ማኅበር ነው።
ያንን የእስራኤል ዐመጽ ነቢዩ ኤርምያስ እንዲህ ሲል ተናግሮት ነበር።

«እናንተ ሰነፎች ልበ ቢሶች፥ ዓይን እያላችሁ የማታዩ፥ ጆሮም እያላችሁ የማትሰሙ ሕዝብ ሆይ፥ ይህን ስሙ። በውኑ እኔን አትፈሩምን? ከፊቴስ አትደነግጡምን? ይላል እግዚአብሔር፤ እንዳያልፍ አሸዋን በዘላለም ትእዛዝ ለባሕር ዳርቻ አድርጌአለሁ፤ ሞገዱም ቢናወጥ አያሸንፍም፥ ቢጮኽም አያልፍበትም። ለዚህ ሕዝብ ግን የሸፈተና ያመፀ ልብ አላቸው፤ ዐምፀዋል ሄደውማል። በልባቸውም፦ የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ በጊዜው የሚሰጠውን፥ ለመከርም የተመደቡትን ወራት የሚጠብቅልንን አምላካችንን እግዚአብሔርን እንፍራ አላሉም። በደላችሁ እነዚህን አስቀርታለች፥ ኃጢአታችሁም መልካምን ነገር ከለከለቻችሁ። በሕዝቤ መካከል ክፉዎች ሰዎች ተገኝተዋል፤ እንደ አጥማጆችም ያደባሉ፥ ወጥመድንም ይዘረጋሉ ሰዎችንም ያጠምዳሉ»           ኤር 521-26

ማኅበረ ቅዱሳን በዘመናት ብዛት ማን እንደጻፋቸውና ማን እንዳስገባቸው የማይታወቁ የተረትና የእንቆቅልሽ መጻሕፍት እንዳይነኩ ዘብ የቆመ የጠላት ወታደር ነው። ብዙዎች እውነት በመናገራቸውም ያወገዘና ያስወገዘ ማኅበር ነው። ለምሳሌ አንድ አስረጂ እናንሳ!

መስተብቍእ ዘመስቀል በተባለው የቤተክርስቲያን የጸሎት ክፍል ውስጥ እንዲህ የሚል ክህደት ተሰንቅሮ ይገኛል። 
«ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን/ለማርያም ወለመስቀል/ ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ፤ እስመ ተዐረዮሙ በክብሮሙ»
ለነዚህ ሁለቱ ፍጡራን  (ለማርያምና ለመስቀል) ለፈጣሪ የሚሰጠው  ምስጋና ይገባቸዋል። በክብር ፈጣሪያቸውን ተካክለዋልና!

 እግዚአብሔር ቢከብር ክብር የባህርይው እንጂ አክባሪ የሚጨምርለትና የሚቀንስለት ነገር የለም። ማንም የቱንም ያህል ቢከበር ከእግአብሔር ፈቃድ አንጻር እንጂ በራሱ ብቃት በሚያመጣው ችሎታ አይደለም። ደግሞም በክብር እግዚአብሔርን የሚስል፤ የሚያክልና አቻ የሚሆን ፍጥረት ፈጽሞ የለም። «በልዑል እመሰላለሁ» ካለው ከሰይጣን በስተቀር ከፍጥረታት ውስጥ በክብር እግዚአብሔርን የሚተካከል የለም።
«ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፥ በልዑልም እመሰላለሁ አልህ» ኢሳ 1414

ነገር ግን እግዚአብሔርን የሚመስለው ማንም የለም? በማንም ልንመስለውና ከማንም ጋር ልናስተካክለው አይገባም። ራሱ እግዚአብሔር በነቢዩ አንደበት እንደዚህ ሲል ተናግሮናልና።

«እንግዲህ እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ? ይላል ቅዱሱ። ኢሳ 4025»
  
ማኅበረ ቅዱሳን ማለት እንደነዚህ ዓይነት ተረቶችና ክህደቶች እንዳይነኩ ለእውነት ሁሉ ጠላት ለሆነው ለሰይጣን ጥብቅና ቆሞ የሚከራከር ማኅበር ነው። መንፈሳዊ ኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች የእውቀትና የማስተዋል ተቋማት እንደመሆናቸው መጠን ጥያቄ የሚጠይቁና ከእግዚአብሔር ቃል የተገናዘበ አሳማኝ ምላሽ እንዲሰጣቸው የሚተጉትን በክህደትና በምንፍቅና እየወነጀለ መቆሚያና መቀመጫ የሚያሳጣ፤ ወይ ከእውቀቱ ወይ ከእውነቱ አንዱንም ያልያዘ ድርጅት በመሆኑ ነው።
ስለዚህ ፓትርያርክ ማትያስ ለመንፈሳዊ ኮሌጆች ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ ደብዳቤ ለመጻፍ የተገደዱት ከኮሌጆቹ ተማሪዎች ጥያቄ አንጻር ብቻ ሳይሆን ፓትርያርኩ ለሚያደርጉት ትግል የሊቃነ ጳጳሳቱ ድጋፍ አናሳ ሆኖ በመገኘቱ ቢያንስ የትግላቸው አጋር የተማረውን ክፍል ለመያዝ ከመፈለግ የተነሳ ይመስላል።
በዚህ አጋጣሚ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎችና የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ግድ የሚለው ሁሉ ከፓትርያርኩ ጋር በመቆም የያዙትን ትግል ከግብ ለማድረስ በጸሎትና በሃሳብ እንዲያግዝ ለማሳሰብ እንወዳለን።
ደብዳቤዎቹን ለማንበብ ሊንኩን ከከፈቱ በኋላ ለማስፋትና በደንብ ለማንበብ ጽሁፉን ይጫኑት!
እዚህ ይጫኑ 1

እዚህ ይጫኑ 2

እዚህ ይጫኑ 3

እዚህ ይጫኑ 4

Monday, January 25, 2016

ተሐድሶ ወደቀደመ የወንጌል ቃል መመለስ ማለት ነው!

(ተሐድሶ ተስፋዬ)

ለኦርቶዶክስ የተከለከለ ፅሑፍ !!
ድንገት እንኳ ብታነቡም እንዳትጨርሱት !!

በሰላም አለቃ በክርስቶስ ኢየሱስ ስም ሰላም ብያለሁ፣ሰላሙ ይብዛላችሁ !! እስኪ ደግሞ ትንሽ ለክርስቶስ ብዬ ልሰደብ !!

የኦርቶዶክስ ህዳሴ በኛ በልጆቿ ከግብ ይደርሳል !! አሜን የምትሉ ለምልሙልን !! እንደምንም አንብቧት ።
ከተሀድሶ እንቅስቃሴዎች ዉስጥ በትንሹ ላካፍላችሁ...

1.1. ""ማርታን ወደ ማርያም የመቀየር ተሐድሶ""

ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ቃል ካልተመለሱ ወደ እግዚአብሔር አይመለሱም፤ ጌታ እንዳለው
“የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች፤ ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት ።” (ሉቃ.10፥42)፡፡ እነማርታ ቤተ ክርስቲያኑን ሞልተውታል፤ ዳቦ ጋግሩ፤ ወጥ ሥሩ፤ልብስ እጠቡ፤ከበሮ ምቱ ሲባሉ አይሰለቻቸውም፤ የክርስቶስን ወንጌል ተማሩ ሲባሉ ግን እንኳንስ ሊማሩ የሚማሩ እኅቶችና ወንድሞችን እንኳን ማየት አይፈልጉም፡፡ በዓመት አንድ ቀን የጥምቀት በዓል ሲመጣ ለማይሰማ ታቦት መንገድ ይጠርጋሉ፤ ምንጣፍ ያነጥፋሉ፤ ጉልበታቸውን ሳይሰስቱ ያገለግላሉ፤ የሚሰሙት ወንጌል ግን የለም፤ የእነዚህ ሰዎች አገልግሎት የቅናት እንጅ የእምነት አይደለም፡፡
ለእግዚአብሔር ቃል ቅድሚያ ካልሰጡ ደግሞ ለማይሰማና ለማያይ ታቦት ምንጣፍ እንዳነጠፉ፣ ግብር እንደገበሩ ይኖራሉ እንጅ ዕረፍትን አይገኙም፡፡ እነዚህ ሰዎች ለጊዜው ደስተኞች ናቸው፡፡ ዐሥር ዐመት በዚህ መልኩ ካገለገሉ በኋላ “አሁን ለመዳናችሁ እርግጠኞች ናችሁን?” ብለን ብንጠቃቸው እንኳንስ እርግጠኞች ሊሆኑ እንዲያውም ፍርሐታቸው ጨምሮ እናገኛቸዋለን፤ ስንጠይቃቸው የሚሰጡን መልስ “ማንም ከመሞቱ በፊት ለመዳኑ እርገጠኛ መሆን አይችልም” የሚል ነው፡፡
እነዚህ ሰዎች ይንም አይነቱን ወንጌል ከየት እንዳገኙት እናውቃለን፡፡ አዲሱ ትምህርት ነው፤ ሐዋርያት ያወገዙት፣ “ማንም እኔ ካስተማርኋችሁ የተለየ ወንጌል ቢያስተምራችሁ የተወገዘ ይሁን” (ገላ.1፡8) ብለው ያስጠነቀቁን ትምህርት ይህ ነው፡፡
ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ክርስቶስ ለመሄድ መናፈቅ አልሰሙም ማለት አንችልም፤ የሰሙትን እንዳላመኑት ግን እናያለን፡፡ ክርስቶስ በቃሉ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረው እንጅ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወድዶአልና፤ በእርሱ የሚያምን አይፈረድበትም ፤ በእርሱ የማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስላላመን አሁን ተፈርዶበታል ” (ዮሐ.3፡16-17) ያለው ቃል ዕረፈት ካልሰጠና እርግጠኛ ካላደረገን በምን እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን? ከዚህ ከጸና እውነት ያንሸራተተንና ከዓለቱ ነቅሎ በአሸዋ ላይ የሠራን ማነው? ይህን ከእግዚአብሔር እውነት የሚነቅል ትምህርት በእግዚአብሔር ቃል መዋጋት ተሐድሶ ነው፡፡
ብዙዎቻችን “የአገልግሎት ማኅበራት አባላት ነን” እያልን ከበሮ ለመምታት፣ ለመዘመር፣ ታቦት ለማክበር፣ ምንጣፍ ለማንጠፍ፣ የቤተ ክርስቲያን ቅጥረ-ግቢ ለማጽዳት፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ታቦት የሚሄድባቸውን መንገዶች ተከትሎ ለማጽዳትና ሰንደቅ ዓላማ ለመስቀል እንጅ የእግዚአብሔርን ቃል ለመስማት ጊዜ የለንም፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል ነው ብለን የምናምን ስንቶቻችን ነን? ማርታ ማርያምን ለምን ተቃወመቻት? ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እግዚአብሔርን ማገልገል እንደሆነ ስላልገባት ነበር፡፡ ክርስቶስ ግን ለሁሉ የሚበቃውን አንድ ታላቅ አገልግሎት አከበረ፤ እርሱም ቃሉን መስማት ነው፡፡ ተሐድሶ የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት የመታደስ አገልግሎት ነው፡፡
የጸጋ ስጦታዎቻችን የተለያዩ ናቸው፤ ለአንዱ የተሰጠው ለሌላው ላይኖረው ይችላል፤ የሚዘምር ላይሰብክ፣ የሚሰጥ ላያስተምር ይችላል፤ ለሁላችንም የተሰጠን ጸጋ ግን የእግዚአብሔርን ቃል የመስማት አገልግሎት ነው፤ በዚህ አገልግሎት ውጤታማ ያልሆነ ሰው ደግሞ በሌላ አገልግሎት ውጤታማ መሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን ስለማያውቀው የሚያገለግለው የሚያውቀውን ራሱን፣ አለቃውን፣ ታቦቱን፣ ገንዘብን፣ ክብርንና እውቅና መፈለግን፣ ተቃውሞን፣ ሥርዐትንና ታሪክን፣ እኔ ብቻ ትክክል ነኝ ማለትን እንጂ እግዚአብሔርን ሊያገለግል አይችልም፡፡ ተሐድሶ ከዚህ አይነት እስራት ነጻ ወጥቶ እግዚአብሔርን እንደቃሉ በእውነትና በመንፈስ ማምለክ (ማገልገል) ነው፡፡
.
1.2. የሚያስፈልገን ጸበል ወይስ ወንጌል?

ለነማርታ እነርሱ ካልደከሙ የእግዚአብሔር ጸጋ አይበቃም፡፡ የእነርሱ ማሰሮ የምትሞላው የእግዚአብሔር ጸጋ ሲፈስስባት ሳይሆን እነርሱ የፈጩት ዱቄት ሲጨመር ብቻ ነው፡፡ ቃሉን መማር መሥዋዕት አይደልም፤ ጸበል ካልጠጡ፣መክፈልት ካልበሉ እግዚአብሔርን አላገለገሉትም፡፡ ቃሉን ካልሰሙ ቤተ ክርቲያን መሳለም ምንድን ነው? ጸበል ውሃ አይደለምን? ህሊናችንን ከሞተ ሥራ ሊያነጻ የሚችል መለኮታዊ ጸበል የእግዚአብሔር ቃል ነው፤(ዕብ.9፡14) ዲያቆናት በኩስኩስት ጸበል ከሚቀዱ ይልቅ ከመለኮታዊው ጸበል ከቃሉ ለምእመናን የማጠጣት አገልግሎት ቢጀምሩ ምናለበት? እስከመቼ ምእመናን በውሃ እየተታለሉ ይኖራሉ? የሕይወት ውሃ መጽሐፍ ቅዱስ ተከድኖ ወይም አልባሌ ቦታ ተጥሎ ዘወትር የውሃ መቅጃ ኩስኩስት ስናጥን የምንኖረው እስከ መቼ ነው? ኧረ ተዉ ጎበዝ የእግዚአብሔር ፍርድ ሳይገለጥ ወደ ቃሉ እንመለስ! ተሐድሶ ከውሃና ከመክፈልት ወደ ሕይወት ውሃ ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ ነው፡፡
እግዚአብሔር የሕይወት ምግብ አዘጋጅቶ እየጠበቀን እኛ እግዚአብሔር የሰበሰበውን ሕዝብ የሚያልፍ ምግብ ያውም ውሃ አጠጥተን የምንልከው እስከመቼ ነው? ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ ምን ተሐድሶ አለ? ሰውን ወደ እግዚአብሔር ቃል ከመመለስ የበለጠ አገልግሎትስ የት ይገኛል? ተሐድሶ አዲስ ነገር አይደልም፤ እግዚአብሔር ተረስቷልና ይታሰብ፤ እግዚአብሔር ክብሩንና ቦታውን ተነጥቋልና ወደ ክብሩ ይመለስ የሚል ተጋድሎ ነው፡፡ ክብሩን ለማንም እንደማይሰጥ የተናገረው እግዚአብሔር ያስነሳው አገልግሎት እንጂ አንዳች የሰው ፍላጎት የለበትም፡፡ እናውቃልን ስንዴ፣ ሰልባጅ፣ ብር ፈልገው የሚሠሩ፣ የፕሮቴስታንት ተላላኪዎች እንደምንባል፡፡ እኛ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱ መቆሳቆል፤ የነገሮች ቅጥ ማጣት፣ በእግዚአብሔር ቦታ የማይሰሙና የማያዩ ታቦታት መቀመጥና መክበር፣ ንስሓ መግባት አለመቻላችን ቤተ ክርስቲያናችንን እየጎዳ ያለ መሆኑ፣ ያሳሰበን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንጂ በምንም ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ላይ ክፉ አሳብ ያለን ሰዎች አይደለንም፡፡ እንዲውም በአመንነው እውነት ምክንያት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር የሚጠቅም ልዩ ሸክም (ራእይ) ያለን ሰውች ነን፤ ራእያችን እንዳይዘገይ፣ መባረካችን እንዲፈጥን በመንገዳችን እንቅፋት አትሁኑብን እንላለን እንጂ በፍጹም እግዚአብሔር የማይፈልገው፣ ቤተ ክርስቲያንንም ሆነ ሀገርን የሚጎዳ አጀንዳ የለንም፡፡ አገልግሎታችን ሰማያዊና የከበረ መሆኑን እናውቃለን፤ ለዚህም ነው በነገር ሁሉ ስንፈተን “የማምነውን አውቀዋለሁ” ብለን ጸንተን እየተጓዝን፣ በየጊዜው ደግሞ እየበዛን ያለነው፡፡ የሚያበዛን የሕይወት ቃል የሆነው የእግዚአብሔ ቃል ነው፡፡ በተሐድሶ ያለ ሕዝብ በውሃ ዳር የተተከለ ዛፍ ነው፤ ቅጠሉ አይጠወልግም፤ ዘወትር ያፈራል እንጂ የመድረቅ ሥጋት የለበትም፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው!
.
1.3. የምንሰብከው እግዚአብሔርን ወይስ የእኛን ሥነ ምግባር?

የሚያስፈልገው ነገር አንድ ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል፡፡ የእኛ ገድልና ድርሳን፣ የእኛ አመለካከትና ዕወቀት፣ የእኛ ቅኔና ትርጓሜ በቦታው ጠቃሚ ቢሆንም በእግዚአብሔር ክብር ላይ መጋረጃ ሲሆን ግን ጉዳት እንጂ ጥቅሙ አይታየንም፤ የሕይወት መንገድ የተገለጠበት መጽሐፍ “መጽሐፍ ቅዱስ” ነው፡፡ ይህን እውነት ማንም ማስተባበል እንደማይችል እናምናለን፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቃል እንመለስ! (Back to the word of God!) ምንም ብንሰብክ፣ ምንም ብንቀኝ፣ ምንም ብናከማች የእግዚአብሔር ቃል ካልሆነ ይበተናል፡፡
ይህ ነገር ለምን ያሳስበናል? ሰዎች እንዲለወጡ፣ ንስሓ እንዲገቡ፣ እንደእግዚአብሔር ቃል እንዲመላለሱ እግዚአብሔር ይፈልጋል፤ ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ እግዚአብሔርን በቃሉ መሠረት ስናውቀው ብቻ ነው፡፡ የግብፅ ፓትርያርክ የነበሩት አቡነ ሺኖዳ የተናገሩትን ምሳሌ አድረገን እንመልከት፤ “I confess before You, O Lord that I ought to have changed my trend of writing. I confess-in shame-that I often talked to people about virtue but little did I talk to them about you, though you are all in all” (The release of the spirit p.14) መልእክቱ ወደ አማርኛ ሲመለስ እንዲህ የሚል ነው፡፡ “ከአሁን በፊት ስጽፍበት የነበረውን ልማዴን መለወጥ እንደነበረብኝ አቤቱ በፊትህ እናዘዛለሁ፤ ለሕዝቡ ስለ ምግባራት (ስለመልካም ምግባር) ዘወትር ብዙ እንደ አስተማርሁ፣ ብንም እንኳን አንተ ሁሉ በሁሉ ብትሆንም ስለአንተ ግን ጥቂት እንደነገርኋቸው በሐፍረት እናዘዛለሁ፡፡” ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ ሥነ ሥርዐት ስንሰብክ ከኖርን የምናልመውን ለውጥ ማምጣት አንችልም፤ የሚለውጠው እግዚአብሔር እንጅ የእኛ ቃል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ በቃሉ እንጅ በእኛ የስብከት ጥበብ አይሠራም፡፡ እግዚአብሔር በቃሉ እንጂ በእኛ ተረት ለመጽናት ቃል ኪዳን የለውም፡፡
ዛፉን እየነቀልንና እያደረቅን ፍሬ የምንፈልገው ከየት ነው?
እስኪ ልብ በሉ! እግዚአብሔርን ከሰው ልብ የሚያፈናቅል (እንደዛፍ ተክል የሚነቅል) ትምህርት እያስተማርን በጎ ምግባር የምናገኘው ከምኑ ነው? አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት ስለ እግዚአብሔር ሳይሆን ስለ በጎ ሥራ ስንሰብክ የምንኖረው እስከመቼ ነው? መቼም ቢሆን የሰይጣንን አሳብ አንስተውም፤ ዛሬስ ብሎ ብሎ ተሐድሶ መልካም ሥራን መቃወም ጀመረን? ተመልከቱ! ተሐድሶ ለየለት! የሚል ሰው አይጠፋም፡፡ እያልን ያለነው በዛፉ የማይኖር ፍሬ አያፈራም፤ ሰውን ከዛፉ የሚቆርጥና የሚያደርቅ ለመጥፋትና ለመቃጠል የሚያዘጋጅ የሐሰት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ይራቅ፤ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ትታደስ ነው፡፡ይህ ነው ተሐድሶ!
በክርስቶስ የምንኖረው በቃሉ ስንኖር ብቻ ነው፤ ቃሉን እየተቃወምን ወይም ቃሉን ከአትሮንስ አውርደን የእኛን ተረት አትሮንስ ላይ የምንሰቅል ከሆነ፣ ዐውደ ምሕረቱን እንደ ስሙ የምሕረት ማወጃ አደባባይ ሳይሆን የሚያስር ትብትብ መስበኪያ ካደረግነው፣ እግዚአብሔር በቃሉ ነጻ ሊያወጣው የሚፈልገውን ሕዝብ የበለጠ የእስራት ቀንበር ከጫንንበት የት አለ የእኛ የክርስቶስ መልእክተኞች መሆን? የምንሟገተው ለማን ነው? ለራሳችን ወይስ ለክርሰቶስ? ለክርስቶስ ከሆነ ቃሉን ለምን አናጠናም/አንሰብክም? ዓለምን መቃወም የምንችለው በቃሉ ብቻ ነው፡፡ ለእኛ የተለየ ጥበብ የለንም፤ያለን ማረጋገጫ ቃሉ ብቻ ነው፡፡ ተሐድሶ ይህ ነው! ወደ እግዚአብሔር ቃል መመለስ! እግዚአብሔር ይመልሰን! የቤተ ክርስቲያናችንን የተሐድሶ ተስፋ በቃሉ እንደገና ወደ ክብሯና ቅድስናዋ የመመለስዋን ትንሣኤ ለማየት ነው!!!
ኢየሱስ ያድናል !!

Sunday, January 24, 2016

"ቅድስና ለእግዚአብሔር"


(ተረፈ አበራ)
ሰው በክርስቶስ ሲያምን ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርለታል ።ሮሜ 4:25 ይህ ማለት በታረሰ መሬት ላይ ተተክሎ እንደ ጸደቀ ወይን ይሆናል።ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል እንደ ሊባኖስ ዝግባ ይለመልማል እንደሚል መጽሐፍ ፍሬ ያፈራል።መዝ 29:92 ፍሬው ቅድስና ይባላል።ጽድቅና ቅድስና እምነትና ሥራ ይባላሉ ።ያዕ 2:14 ቅድስና መለየት ማለት ሲሆን ሰው በክርስቶስ ጸጋ መጽደቁን የሚያረጋግጥበት የመንፈስ ፍሬ ነው ።ይህም ማለት ውስጣዊ ጤንነት እና ንጹህነት ወይም ከእንከን መራቅን ያመለክታል።እግዚአብሔር በባህሪው ቅዱስ ነው ።ሰዎችን በጸጋው ይቀድሳል።
  ቅድስና የሚያስፈልገን ነገር ግን ያልፈለግነው የሕይወት ውበት ነው።ደስታን፣ብልጽግናን፣ሰላምንና ስኬትን በምንፈልግበት መጠን ቅድስናን ፈልገን እናውቅ ይሆን? ቃሉ፦'ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ፥ያለ እርሱ ጌታን ሊያይ የሚችል የለምና።' ይላል።ዕብ.12፥14 ቅዱሱን ጌታ ለማየት የቅድስና ጥሪውን በመቀበል፣በደሙ በመታጠብ ከዓለም፣ ከኀጢአት፣ ከርኩሰትና ከሥጋ ሀሳብ በመለየት መኖር ያስፈልጋል።'እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።'1ኛ ጴጥ. 1፥15-16።ክርስትና ለእግዚአብሔር የመለየት ኑሮ ነው።ልዩነቱ የበጎ ተጽዕኖ አቅም ነው።በተራራው ጌታ የሰበከንን የአማኝ ኑሮ ብናጠና ብልጫችንን እንረዳለን። ለሚበልጠው ታጭተን በሚያንስ አኗኗር እንዳንገኝ እናስተውል። በቅዱሱ ፊት በተጣለ ማንንነት መቆም አይቻልም።በሰው ፊት እንኳ ቆሽሾ መቅረብ ምን ያህል ይከብዳል? 'እኔ ኤልሻዳይ ነኝ፤ በፊቴ ተመላለስ፥ ፍጹምም ሁን፤' ዘፍጥረት 17፥1 ያለውን ጌታ ነው የምናመልከው። እግዚአብሔር የምንቀደስበትን መስዋእት አዘጋጅቷል። የተዘጋጀው መስዋእት ልጁ ነው።ህሊናችንን ቀድሶ መንፈሳችንን አንጽቶ በደላችንን አጥቦ ሊያቆመን ወደሚችለው እንቅረብ።አሮጌ(ያደፈ ልብስ)አልብሶ የሚከሰንን በደሙ ኀይል በስሙ ስልጣን ጥሎአል።ራእይ 12፥11 ቀዳሹ እኛን መቀደስ ፈቃዱ ነው እኛ መቀደስ እንፈልጋለን?ብሉይ ኪዳን 'ቅዱሳን ሁኑ'(ዘሌ 19፥2) ያለን ቅዱሱን ልጁን ላከ።ቀዳሹ ጌታም እኛን ተቀዳሾቹን በደሙ አነፃ።ከኀጢአታችን አጠበን(ራእይ 1፥6) ቀደሰን(1ቆሮ 6፥11) ክብሩን እንድናበራ ለየን።በመሆኑም እኛ ለርስቱ የተለየን ቅዱስ ሕዝብ ነን።(1ጴጥ 2፥9)።ለለየን ተለይተን መኖር ይጠበቅብናል።ቅድስና የሕይወት ዘመን ኑሮ ነው፡፡ስለዚህ ሁልጊዜ ሀሳባችንን ልናነፃ፣ንግግራችንን ልንገራ፣ ሰውነታችንን ከርኩሰት በጸጋው ኀይል ልንጠብቅ ይገባል። ቅዱሳን ለመሆን መጠራታችንን አንርሳ።(ሮሜ 1፥7)። የተጠራነው ለርኩሰት አይደለም።'ለርኵሰት ሳይሆን እግዚአብሔር በቅድስና ጠርቶናልና።"1ኛ ተሰሎንቄ 4፥7። ስለዚህ አባታችንን ለመምሰል በአንደበት ብቻ ሳይሆን በሕይወትም በቅድስና ማደግ አለብን።አባታችን መልኩን በኛ ሕይወት ውስጥ የማየት ናፍቆት አለው።የጠራን በባሕርይው ቅዱስ እንደሆነ እኛም በኑሯችን ሁሉ ከአለም እድፍ ራሳችንን በመጠበቅ በቅድስና መኖር አለብን። የቀደሰንን እንድንመስል ተወስኗል።'ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኵር ይሆን ዘንድ፥ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና።'ሮሜ 8፥29።አስቀድሞ ወደታሰበልን ያድርሰን፤ካላደረሰን መድረስ የለምና። ይቀጥላል! እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን !!


Wednesday, January 20, 2016

ተቀባይነት ያጣ እውነት!



ብዙ ብለናል፤ ብዙ ተብሏል።  ችግሩ ያለው የሚነገር እውነት አለመኖሩ ሳይሆን እውነቱን የሚቀበል መጥፋቱ ላይ ነው። ተቀባይነት ያጡ እውነቶችን መጽሐፍ ቅዱስን ዋቢ አድርገን እናቀርባለን።

1/ ታቦት

ታቦት ማለት ማደሪያ፤ማኅደር ማለት ነው።  ቃልኪዳናዊ አሠራሩም ከዚህ የሚከተለውን ይመስላል።
«እኔ እንደማሳይህ ሁሉ፥ እንደ ማደሪያው ምሳሌ እንደ ዕቃውም ሁሉ ምሳሌ፥ እንዲሁ ሥሩት። ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን። በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት። አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፥ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች፥ በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ። መሎጊያዎችንም ከግራር እንጨት ሥራ፥ በወርቅም ለብጣቸው። ለታቦቱ መሸከሚያ በታቦቱ ጐን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ። መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፥ ከቶም አይውጡ። በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጣለህ። ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ። ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፥ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ» ዘጸ 25፤10-18
ይህንን የእግዚአብሔር መመሪያ ያላሟላ ታቦት፤ ታቦት ሊባል አይችልም። ከዚህ የሚጨመርም፤ የሚቀነስም ከእግዚአብሔር  ቃል ያፈነገጠ ነው። ይህ አንዱ ታቦት ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ይይዛል። ካህናቱ ሲሸከሙም በመሎጊያዎቹ ጽላቱ ውስጥ እንዳለ አራት ሰዎች በአንድ ጊዜ ይሸከሙታል እንጂ አናት ላይ ቁጢጥ የሚል ጽላት የለም። ይህ ያፈጠጠ ያገጠጠ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ነው። ይህ የእግዚአብሔር ቃል እንዲሻሻል የተነገረበት ጊዜ የለም። ዛሬ ታቦት የሚባለው ከየት የመጣ ነው? ዓላማው፤ አሰራሩ፤ እቅድና ግቡ ምንድነው? ብዙ ሰዎች ስለተከተሉት ወይም እድሜ ጠገብ ስለሆነ ውሸት መቼም ቢሆን እውነት ሊሆን አይችልም። ታቦትን የተመለከተ የእግዚአብሔር ዓላማ በዚህ ዘመን ለማንም አልተሰጠም።

2/ጽላት፤

 ጽላት ሁለቱ የኪዳን ሰሌዳዎች ናቸው። 10ቱ የእግዚአብሔር ትዕዛዛት የተጻፈባቸው ሰሌዳዎች ስለሆኑ ጽላት ተብለዋል። ሙሴ ጽላቶቹን ሊቀበል ሁለት ጊዜ ወደተራራ ወጥቷል። የመጀመሪያውን ጽላት የቀረጸውና በጣቱ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ነው። «እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው» ዘጸ 31፤18
የመጀመሪያዎቹ ከተሰበሩ በኋላ ጽላቱን ከእብነ በረድ ዳግመኛ የቀረጸው ሙሴ ራሱ ሲሆን በላዩ ላይ ትዕዛዛቱን በጣቱ የጻፈባቸው ግን እግዚአብሔር ነው።
 «ሙሴን አለው፦ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች እንደ ፊተኞች አድርገህ ጥረብ፤ በሰበርኻቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃሎች እጽፍባቸዋለሁ» ዘጸ 34፤1   ዘዳ10፤4
መጽሐፍ ቅዱስ ስለጽላት በተናገረበት የትኛውም አንቀጽ ውስጥ ሙሴ ጽላቶቹ ላይ ጻፈ የሚል ገጸ ንባብ የለም። ከእብነ በረድ አስመስለህ ቅረጽ የተባለውን ትዕዛዝ አንተው ጻፍባቸው የተባለ በማስመሰል ራሳቸው የሚጽፉባቸው ከየት በተገኘ ትዕዛዝ ነው? በወቅቱም ጽላቶቹ ላይ እግዚአብሔር ራሱ የጻፈባቸው ትዕዛዛት እንጂ ምስል ወይም ስዕል አይደለም። ይህስ ከማን የተገኘ ትምህርት ነው? ስንት ጽላት? ስንት ታቦትስ? እግዚአብሔር ሰጥቷል?

3/ ምልጃና ማስታረቅ

«አማላጅ» የሚለው ቃል የተገኘው «ማለደ» ከሚል ግስ ሲሆን «ማለደ» ማለት ደግሞ «ለመነ» ወይም «ጸለየ» ማለት ይሆናል። « መማለድ ፤ ማማለድ… » ማለት  «መለመን ፣ ማስታረቅ» ሲሆን «አማላጅ» ደግሞ ይህን ተግባር የሚያከናውን ነው፡፡ ተግባሩ ደግሞ «ምልጃ» ይባላል፡፡
አዳም ከእግዚአብሔር ፊት በኮበለለ ጊዜ ወዴት ነህ? ሲባል እነሆ በዚህ ተሸሽጌአለሁ አለ።                         «እግዚአብሔር አምላክም አዳምን ጠርቶ፦ ወዴት ነህ? አለው።እርሱም አለ፦ በገነት ድምፅህን ሰማሁ፤ ዕራቁቴንም ስለ ሆንሁ ፈራሁ፥ ተሸሸግሁም» ዘፍ 3፤9-10
ይህ የኮበለለው ሰው፤ አዳም ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነበረበት። መቼ? ማንስ? ያስታርቀዋል?
በዘመነ ብሉይ የማስታረቅ አገልግሎት የተሰጠው ለካህናቱ ወገን ብቻ ነበር። የኃጢአት ማስተሰሪያ መስዋዕትም ዕለት ዕለት ይቀርብ ነበር።
« ዕለት ዕለትም ስለ ማስተስረይ ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈኑን ታቀርባለህ፤ ማስተስረያም ባደረግህ ጊዜ መሠዊያውን ታነጻዋለህ ቅዱስም ይሆን ዘንድ ትቀባዋለህ» ዘጸ29፤36 ይህ የማስታረቅ አገልግሎት ፍጹማዊ አገልግሎት አይደለም። በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የተጋረደውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የማይችል ጊዜአዊ አገልግሎት ነበር። ስለዚህም በአዳምና በልጆቹ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነበረ። ይህ የበደል ቁጣ ሊመለስ የሚችለው ይህንን መሸከም የሚችል መስዋዕት ሲኖር ብቻ ነው። ለዚህም አገልግሎት ብቁ መሆን የሚችለው ደግሞ ከኃጢአት በቀር በሁሉ የተፈተነ ሊሆን ይገባዋል።
«ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም» ዕብ 4፤15
ስለዚህም ሰማያዊ ሊቀካህን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ፊት ለኮበለልነው ለአዳም ልጆች ሁሉ አስታራቂ መስዋዕት ሆነ። ይህንንም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ አለ።«ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ»ኢሳ53፤12
ኢየሱስ ክርስቶስ አስታራቂና ማላጅ ባይሆን ኖሮ ሥጋ ከለበሰ ከሰው ልጅ ማንም ቢሆን የማስታረቅ አልገልግሎትን ሊፈጽም አይችልም ነበር። የክርስቶስ ኢየሱስን አስታራቂነት ልዩ የሚያደርገው የማማለድ ብቃቱ ብቻ ሳይሆን ዕለት ዕለት የሚደረገውን የማስታረቅ አገልግሎት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስቀረት መቻሉ ነበር።
«ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ኃጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መሥዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ» ዕብ 10፤11-12
ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስ የማስታረቅ አገልግሎት አንዴ የተፈጸመ፤ ነገር ግን ዕለት ዕለት ወደእግዚአብሔር የሚመጡትን ሁሉ የሚያድን የዘላለም መስዋዕት ስለሆነ ዛሬ አዲስ የሚፈጸም የልመናና የማስታረቅ አገልግሎት የለም። አንዳንዶች ዛሬም የሚለምን ያለ የሚመስላቸው አሉ። አንዳንዶች ደግሞ አንዴ የፈጸመው አገልግሎት አብቅቷል፤ ከእንግዲህ አይሰራም የሚሉ አሉ።  አማላጅነትን ለሰዎች ያስረከቡ ሁሉ የክርስቶስን ዘላለማዊ ብቃት ይክዳሉ። በሌላ መልኩም የሰዎችን አማላጅነት ለመከላከል ሲሉ ኢየሱስን ዛሬም የሚማልድ አድርገው የሚስሉም አሉ። ሁለቱም ጽንፎች የኢየሱስን ማንነት ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።እውነቱ ግን ዕብራውያን መጽሐፍ እንዳለው፤
«እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ቅዱስና ያለ ተንኮል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባልና፤ እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና» ዕብ 7፤23-27
ስለዚህ በአጸደ ነፍስ ያሉ ቅዱሳን፤  ሰዎች ከበደል ወደ ጽድቅ፤ ከኃጢአት ወደቅድስና ሰዎች እንዲመለሱ ይማልዳሉ፤ ይለምናሉ ማለት ለኃጢአተኛው ምትክ ሆነው ያድኑታል ማለት አይደለም። አንዴ የተፈጸመው የማማለድና የማስታረቅ አገልግሎት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው።

Friday, January 1, 2016

ስለአንዳንድ በኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ ላይ…ከአንዳንድ የኦሮሞ ጸሐፍት የተሰነዘሩ…ያስቀየሙኝ ክታቦች!!


 (በአማን ነጸረ ክፍል 4)

(7.1) ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ በጻፉት በመጀመሪያው ‹‹ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ›› መጽሐፋቸው ገጽ-137 ይሕንኑ ሁኔታ (የቶፋ ሥርዓት) በጥቁምታ ያመላክቱናል፤እንዲህ ሲሉ ‹‹በኢትዮጵያ የካሕናት ቁጥር እጅግ ብዙ ነው፡፡ለነዚሁም ሁሉ መንግሥት ከያውራጃው ከግማሽ እስከ አንድ ጋሻ መሬት ለእያንዳንዱ ካሕን ርስት እያደረገ ሰጥቷቸዋል፡፡ይኸውም ርስት እየሆነ የተሰጠው መሬት ለልጅ ልጅ የሚያልፍ [በመሆኑ] ቤተክርስቲያን ልታዝዝበት አትችልም፡፡በዚህም ላይ ከንጉሠ-ነገሥቱ ዠምሮ መሳፍንቱ መኳንንቱም ሌላውም እነሱን የመሰለው ሁሉ ወይዛዝርት እንኳ ሳይቀሩ የቤተክርስቲያን ገበዞች እየሆኑ ከ200 እስከ 700 ጋሻ መሬት ንጉሠ-ነገሥቱ ርስት እያደረገ ይሰጣቸዋል...›› በማለት ይዞታው በወሬ የኢኦተቤክ እየተባለ ስመ-ንብረቱ (title deed) ግን በተግባር በንጉሡ፣በመሳፍንትና ወይዛዝርት እጅ እንደነበረ፤እነዚህ መሳፍንትና ወይዛዝርት ሲያልፉም ልጆቻቸው የቤ/ክ ትምህርት ባይማሩም ‹ገበዝ› በሚል መጠሪያ ርስቱን ወርሰው ደሃ ካሕናትን እያስቀደሱ በስመ ተዋሕዶ የሚያደርጉትን ብዝበዛ (የቶፋ ሥርዓት) ስሙን ሳይጠሩ ያብራሩልናል፡፡
(7.2) በ1967 ዓ.ም የመሬት-ላራሹ ዐዋጅ ሲታቀድ በካሕናት እጅ እንደዜጋ የነበረውን መሬት ሁሉ በነባሩ ‹‹የሲሶ መሬት ይዞታ›› ትረካ አጠቃሎ የመውረስ አዝማሚያ አስፈርቶ ነበር፡፡ሁኔታው ያሳሰባቸው የጊዜው የኢኦተቤክ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ በ1967 ዓ.ም ለደርግ በጻፉት ደብዳቤ ተቃውሞአቸውን ሲገልጹ ‹‹...ተጋኖ ሲነገር የኖረው ጨርሶ ያልነበረ የመንግሥት ሥልጣን ድርሻና የሀገሪቱ ሲሶ መሬት ወሬ ፈጽሞ ተረት ቢሆንም ያው ያለው መጠነኛ ድጋፍ እስካሁን ድረስ ከመንግሥት ሲሰጣት ቆይቷል›› በማለት ‹‹ያው ያለው መጠነኛ ድጋፍ›› እንዲቀጥል ተማጽነው ነበር፡፡ፓትርያርኩ ጥያቄያቸውን በ7 ነጥቦች አብራርተው ነበር ያቀረቡት፡፡2ቱን ብቻ ልጥቀስላቸው ‹‹1ኛ. የኢትዮጵያ ገዳማት መሬት ያንድነት ማኅበር እንደ መሆኑ መጠን ይኸው በይዞታቸው ያለው የንፍሮ መሬታቸው በይዞታቸው ስር እንዲቆይ እንዲፈቀድላቸው፣እንዲሁም ‹በርሷ (በኢኦተቤክ) ስም ተይዘው ሌሎች ወገኖች ሲጠቀሙባቸው የኖሩ መሬቶች ቢወሰዱ የምትጎዳበት ባይኖርም› እስከ ዛሬ በቀጥታ ስትረዳባቸው የቆዩ አንዳንድ መሬቶች በይዞታዋ ስር እንዲቆዩላት፤2ኛ. በግብርና ስራ የሚተዳደሩ ካሕናት ሁሉ ካሕንነታቸው ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን ስለማይሽረው እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የመሬት ድርሻቸውን የማግኘት መብታቸው እንዳይዘነጋባቸው››ብለው ጠይቀው ነበር (መምህር ኪዳነማርያም ጌታሁን፡ገ.102)፡፡
(7.3) በደስታ ተክለወልድ የአማርኛ መዝገበ ቃላት ገጽ 1267 ‹‹ወኪል፣ምትክ፣ተጠሪ፣ገባሪ›› ተብሎ ስለተተረጎመው ‹‹ቶፍነት›› ሌላ ዋቢ እንቁጠር፡፡‹‹የኢኦተቤክ አስተዳደር በየዘመናቱ››የተሰኘው መጽሐፍ ደራሲ ብፁዕ አቡነ ገሪማ (ዶ/ር) ስለዚህ ጉዳይ ሲተርኩ ‹‹ለቤተክርስቲያን መግባት የሚገባውን የግብር ገንዘብ መሳፍንቱ፣መኳንንቱ፣ባላባቶችና ወይዛዝርት በግብዝና በእልቅና፣በመሪጌትነት፣በድብትርና፣በቅስና፣በዲቁና እና በልዩ ልዩ [የ]ክሕነት [አገልግሎት] ስም ርስት እየያዙ በግል እየተጠቀሙ በተወሰነ ክፍያ ወይም በቶፍነት ካሕናትን ያስገለግሉ ነበር›› ይሉናል፡፡አቡነ ገሪማ ታሪኩን ሲቀጥሉ ‹‹…የቤ/ክ መተዳደሪያ ብዛት ጎልቶ ከመታየቱ በቀር ለካሕናቱ መተዳደሪያ ይሆን ዘንድ የተፈቀደው ርስተ - ጉልት የሚሰጠው ጥቅም የአገልጋዮች ካሕናትን ችግር ከመሸፈን አኳያ በቂ አልነበረም፡፡…ከሚያጋጥሙት ችግሮች መካከል፡- ያልቀናውንና በረሃማውን መሬት እየሰጡ የለማውን መሬት መቀማት፣ለም የሆነውን መሬት በጠፍ መሬት መለወጥ፣የኩታ ገጠም አቀማመጥ ያለውን ርስት ወደ ግል ይዞታ ማስገባት…ይገኙበታል›› ይላሉ (አቡነ ገሪማ፡ገ.64-70)፡፡
(7.4) ከላይ ያለችውን የ“ቶፍነት” ሥርዓት ጽንሰ - ሐሳብ ለመረዳት ከመርስዔኀዘን ‹‹ትዝታዬ›› መጽሐፍ ገጽ-92 ማሳያ እንጨምር፡፡የድጓ መምህር የነበሩት ኣባታቸው ሲሞቱ የአባታቸውን መሬት ወርሰው እንደ ባለርስት መገበራቸው ቀርቶ እንዴት ወደ ቶፍነት እንደተሸጋገሩ ሲተርኩ ‹‹…እንግዲህ የምትገብረው በአባትህ ሥም አይደለም፣መሬቱ ለፊታውራሪ ጥላሁን ስለተሰጠ ሥመ - ርስቱ ተዛውሯል፤ሆኖም ለፊታውራሪ ጥላሁን በቶፍነት ልትገብር ትችላለህ…›› እንደተባሉ ይገልጻሉ፡፡ከመርስዔኀዘን አባባል እንደምንረዳው የመንግሥት ሹም የነበሩት ፊ/ሪ ጥላሁን ለድብትርና ተብሎ ለይስሙላ የተመደበውን ርስት ወርሰው ይዘው ደብተራውን (መርስዔኀዘንን) ‹‹ቶፋ›› አድርገዋቸዋል፡፡ታሪክ ግን ፊታውራሪ የያዙት ርስት ለስሙ የኢኦተቤክ ስለተባለ ብቻ ‹‹ሲሶ የቤተክሕነት ድርሻ›› ብላ ያልበላነውን ልታስተፋን ትጥራለች!!ቆዩማ ይቺን ታሪክ የሚሏትን ጉድ በጎጃምኛ ልስደባት ‹‹ኧግ!ይቦጭቅሽ!››
(7.5) ይሄን ሀቅ ጠጋ ብለው ያላዩልን እነ መኩሪያ ቡልቻ እና አባስ ሐጂም ነዋሪ ነባሪውን ስሑት የወሬ ጫፍ ይዘው <<...the clergy were....landlords,they owned Oromo peasants as Gabbars...>> ይሉናል!እርግጥ ይሕ በነአቶ አጽሜ ጸረ-ካሕናተ-ኦርቶዶክስ ጥላቻ ተከትቦ እስካሁን የሚናፈስ የታሪክ አረዳድ ኢህአዴጋውያንን ጨምሮ የብዙኃኑ ልሂቅ አረዳድ ስለሆነ እነ መኩሪያ ቡልቻንና አባስ ሐጂን ነጥሎ መውቀስ ኢ-ፍትሐዊ ሊሆን ይችላል፡፡በቁሳዊ ሀብትና በካሕናት ኑሮ ረገድ የዛሬዋ የኢኦተቤክ ያለችበትን ከቅድመ-1967 ዓ.ም የመሬት ዐዋጅ የተሻለ ኢኮኖሚያዊ አቅም ያስተዋለ ሰውማ በእርግጥም አቡነ ቴዎፍሎስ እንዳሉት በኦሮሚያም ሆነ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች የሚተረከው ‹‹የሲሶ መሬት›› ድርሻ ‹‹ፈጽሞ ተረት›› እንደነበረ ይገለጽለታል፡፡እኛማ ትናንት በተወረሱባት ሕንጻዎች ምትክ ከደርግ የ5 ሚሊዮን ብር ምጽዋት ትጠብቅ የነበረች ቤ/ክ ዛሬ ገንዘብ አያያዟ ባያስደስተንም እንኳ በጀቷ ቢሊዮን መሻገሩን አይተናል፡፡እናም የትናቱ የተረት ተረት ‹‹ሲሶ ግዛት›› ከቶም አያቃዠንም!!አባቴ እንዲህ ይል ነበር ‹‹ድሮ ካሕን ስሙና ማዕረጉ ብዙ ነው፤በቤቱ ግን ሙሉ እንጀራ ቆርሶ የሚበላ ከስንት አንድ ነው፤በነገሥታቱ ከባቢ ካሉት በቀር ድሆችን ካሕናት የሚፈቅድ የለም፤ከነተረቱም ‹የካሕን ልጅ ስም ይጠግባል፤እንጀራ ግን አይጠግብም› ይባል ነበር፤መምህራኖቻችን የኖሩት ተማሪ ለምኖ እያበላቸው ነው፤አየ!፤ተውኝማ ልጄ!››
(7.6) ትውልዱ ባይገለጽለትም እኛ መከራና ስቃይ ከካሕናት ወላጆቻችን የወረስነው ‹ምድጃ የላቀን፤አመድ የወረሰን፤ደሃ የድሃ ልጆች› ወላጆቻችንን ዘበናይ ሁላ ተማርኩ ብሎ ‹‹ሲሶ-ሲሶ!›› እያለ በእንግሊዝኛ ሲዘባነንባቸው እንገረማለን፡፡በተሳልቆ ‹‹ኡኡቴ!ድንቄም ሲሶ!›› እንላለን፡፡ትናንት በነበሩ ብዙኃን ካሕናት ወላጆቻችን ያልተጠገበ ጥጋብ የዛሬዎቹ ሕያዋን ልጆቻቸው እንድንሸማቀቅ የሚሹትን የባለቅኔውን ድንቅ አባባል ተውሰን፡-
‹‹እስመ-እንዘ-ቦ፡ሕያወ፡እሞተ-ሥጋ፡ግዙፍ፣
ሞተ-ዮሴፍ፡አኃዊሁ፡ነገርዎ፡ለዮሴፍ፡፡››እንላቸዋለን--ለቀባሪው ማርዳት!!ሁሉን ትተን የታላላቆቹን ሊቃውንት የነክፍለ ዮሐንስ መራብና መታረዝ የሚያመላክቱና ቅኔያዊ ቁዘማዎቻቸውን የገለጹባቸውን ቅኔያት እንጠቃቅሳለን፡፡እንዲህ፡-
‹‹...ልብስየሂ፡ምንንት፡መንጦላእተ-ርኅቅት፡ነፍስ፣
እስመ-አነ፡ከመ-ዶርሆ፡እምላእለ-አብራክየ፡እለብስ፡፡››
እያሉ እኒያን የመሰሉ ሊቃውንት እርቃናቸውን እንኳ በቅጡ መሸፈን አቅቷቸው እንደ ዶሮ ከጉልበት በላይ ተራቁተው በ‹‹ሲሶ ግዛት››ተረት አእጽምቶቻቸው እረፍት ሲያጡ ከማየት የሚደርስብንን ሕማም በቅኔያቱ እናስታምማለን፡፡ደግሞም የዋድላው የኔታ ሲራክ ራሳቸውን ከአህያና በቅሎ ጋር እያነጻጸሩ የ30 ብር ዓመታዊ ደሞዝ ሰቆቃዊ አኗኗራቸውን፡-
‹‹አእዱግ፡ወበቅል፡እንዘ-ያወጽኡ፡ስልሳ፣
ሲራክ፡አምላከ-ዋድላ፡ተሰይጠ፤ለሠላሳ፡፡››
እያሉ የገለጹባቸውን ቅኔያት እያስታወስን እንግሊዝኛ ተናጋሪ ደባትሮቻችን ወደ ልባቸው ተመልሰው ሚዛኑን የጠበቀ ጽሑፍ እንዲያቀርቡል እንጸልያለን፡፡አንዳንዴም እንጎተጉታለን፡፡አልፎ አልፎም ሕመማቸው ሕመማችን መሆኑን ሳንስት በተጋነነ ቅሬታና ፍረጃ መስመር ሲለቅቁብን ከወዲህ የላላውን ለመወጠር ከወዲያ የተወጠረውን እንጎትታለን--እንዲህ እንዳሁኑ!
የላላው ይወጠር፤የተወጠረው ይርገብ፡፡ወይኩን ማዕከላዌ!አሜን!ይኹን፤ይደረግ!
፡፡፡፡፡፡፡፡በአማን ነጸረ፡፡መስከረም 2008 ዓ.ም፡፡፡፡፡፡፡፡
ማጣቀሻዎቼ!
ሀ. መጻሕፍት(ሃርድ ኮፒ)
1. ብፁዕ አቡነ ገሪማ (ዶ/ር)፣የኢኦተቤክ አስተዳደር በየዘመናቱ፣ጥቅምት 2000 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
2. ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ(M.A)፣የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ታሪክ፣1986 ዓ.ም፣2ኛ እትም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
3. በኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንትና ጳጳሳት፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ እስከ ፳፻(2000 ዓ.ም)፣በ2000 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
4. አባ አንጦንዮስ አልቤርቶ (ዶ/ር) (ካፑቺን)፣የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ፡ከብፁዕ አቡነ ጉሊየልሞ ማስያስ እስከ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ጃሮሶ (1841-1941 ዓ.ም)፣1993 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
5. ታቦር ዋሚ፣የውገና ድርሰቶችና የታሪክ እውነቶች፣በ2007 ዓ.ም፣3ኛ እትም፣አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት
6. መርስዔኀዘን ወልደቂርቆስ፣ትዝታዬ፡ስለራሴ የማስታውሰው፣2002 ዓ.ም፣አስቴር ነጋ አሳታሚ ድርጅት፤ሮኆቦት አታሚዎች
7. ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ (1ኛ መጽሐፍ)፣1965 ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ወዳማዊ ኃይለሥላሴ ማተሚያ ቤት
8. አለቃ ተክለኢሱስ ዋቅጀራ (ሐተታ በዶ/ር ስርግው ገላው)፣የኢትዮጵያ ታሪክ፣2000ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት
9. በቀለ ወልደማርያም አዴሎ፣የካፋ ሕዝቦችና መንግሥታት አጭር ታሪክ፣1996 ዓ.ም፣ሜጋ ማተሚያ ድርጅት
10. ዶናልድ ሌቪን (ትርጉም በሚሊዮን ነቅንቅ)፣ትልቋ ኢትዮጵያ፣2007 ዓ.ም፣አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ
11. ቅዱስ ያሬድ፣መጽሐፈ-ድጓ፣1988 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
12. ከአባቶች ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ፣የውዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጉም፣1990 ዓ.ም፣ትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት
13. የእጅ ጽሕፈት የግእዝ መማሪያ ግስ/መዝገበ-ቃላት(በራሴ ተቀድቶ የተማርኩበት)፡፡
14. እነ አለቃ አፈወርቅ ዘውዴ፣የግእዝ ቅኔያት የስነጥበብ ቅርስ-2፣1980 ዓ.ም፣ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት
15. መምህር ኪዳነማርያም ጌታሁን፣የሐሰት ምስክርነት፣1994 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
16. ሰሎሞን ጥላሁንና ሥምረት ገ/ማርያም፣ደማቆቹ፣2000ዓ.ም፣
17. ደስታ ተክለወልድ፣ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት፣1962 ዓ.ም፣አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት
18. የኢትዮጵያ መጽሐፍቅዱስ ማኅበር፣የመጽሐፍቅዱስ መዝገበቃላት፣1992 ዓ.ም፣6ኛ እትም፣ባናዊ ማተሚያ ቤት
19. ላጵሶ ጌ.ድሌቦ (ዶ/ር)፣የኢትዮጵያ ረጅም ሕዝብና ታሪክ አንደኛ መጽሐፍ፣1982 ዓ.ም፣ንግድ ማተሚያ ድርጅት
ለ. የኢንተርኔት መጻሕፍት(ሶፍት ኮፒ) እና መጣጥፎች!
1. የመኩሪያ ቡልቻ፣የገመቹ መገርሳ እና የቶማስ ዚትልማንን ጽሑፎች ለማግኘት http://www.diva-portal.org/…/get/diva2:277262/FULLTEXT01.pdf
2. የመሐመድ ሐሰንን ጽሑፍ https://zelalemkibret.files.wordpress.com/…/jos-volume-7-nu…
3. የአባስ ሐጂን http://69.162.74.242/~iprenewi/r.php… ወይም http://69.162.74.242/~iprenewi/r.php…
4. በወለጋ ስለነበረው የሚሽኖች እንቅስቃሴ GILCHRIST, HORACE ERIC የጻፈው የ2ኛ ዲግሪ ማሙያ http://repository.lib.ncsu.edu/…/bits…/1840.16/844/1/etd.pdf
5. ፕ/ር ታምራት አማኑኤል የአለቃ ዐጽመጊዮርጊስን እና የነአለቃ ታዬ ታሪክ ጨምሮ የቀደምት ጸሐፍያንን ስራዎች ባጭሩ የዳሰሱበት መጽሐፍ http://www.ethioreaders.com/…/About-Ethiopian-Authors-Prof-…
6. ስለኦሮሞ ሕዝብ የሃይማኖት ተዋጽኦ https://en.wikipedia.org/wiki/Oromo_people#Religion
7. ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል በሶማሌ ሕዝብ ታሪክ ውስጥ ያለው የተለያየ ትርጉም https://www.yumpu.com/…/the-galla-myth-on-somali-history-or…
8. ስለ Krapf ሚሲዮናዊ ሕይወት https://en.wikipedia.org/wiki/Johann_Ludwig_Krapf
9. ‹‹ጋላ›› የሚለው ቃል ኬንያም ውስጥ በታሪክ መጻሕፍት ጥቅም ላይ ሲውል ስለመኖሩ የሚያሳይ ደብዳቤ http://yassinjumanotes.blogspot.com/…/stop-use-of-word-gall…
10. በዚች መዝሙር ላሳርግ Ethiopian Orthodox Mezmur in Afaan Oromo- Waldaa Qulqullootaa - Galanni Waaqayyoof haa ta'u https://www.youtube.com/watch?v=tER05f165A8
http://www.diva-portal.org/…/get/diva2:277262/FULLTEXT01.pdf