Thursday, March 10, 2016

የተሸጠ ብኩርና!

(መነሻ ሃሳብ በደግፌ ጃክሰን)

  ነጠላ ያስረዘሙ ፈሪሳዊ ሰልፈኞች ከመጻሕፍቱ ጀርባ በኦርቶዶክሳዊ አቋቋም አደግድገው ቆመዋል። ከድንኳኑ ውጨኛው ክፍል "5ኛው የማኅበረ ቅዱሳን የመጻሕፍት ኤግዚቢሽን"የሚል ጽሑፍ በጉልህ ተጽፎ ተሰቅሏል። ሰይጣንም፣ ክፉውም፣ ጠማማውም፣ ነፍሰ ገዳዩም፣ ወንበዴውም፣ ሟርተኛውም ሰው "ቅዱስ ነኝ"ቢል በዚህ ዘመን የሚጠይቀው ስለሌለ (አሁን ጥያቄ የለም ማለት እስከመጨረሻው ጥያቄ የለም ማለት አይደለም) በቅድስና ማኅበር ስም የተጻፈውን ማስታወቂያ ካነበብኩ በኋላ ስለቅድስናው የሚመሰክር ፍንጭ ፍለጋ ወደድንኳኑ ጎራ አልኩ።  እዚህ ላይ አንባቢን ላስገነዝብ የምፈልገው ነገር እኛ ለራሳችን የምንሰጠው ስም ሳይሆን የምንሰራው ሥራ ነው የዋጋችንን ሚዛን ሊወስን የሚችለው። ጠንቋይ ቤት የሚካኤልና የማርያም ስዕል ተሰቅሎ መገኘቱ ወይም የገብርኤልን ዝክር እንድትደግስ በማለት ባለሀድራው በማጓራቱ ጠንቅ ዋይነቱን ወደቅድስና ማዕረግ አይለውጠውም።
ወደፍሬ ነገሩ ስመለስ፣ ከቅዱሳኑ ማኅበር ድንኳን ጎራ ብዬ የእግዚአብሔርን ቅድስና የሚያውጁ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን መድኃኒትነት የሚናገሩ፣ ዓይን ሁሉ ወደቀራንዮ እንዲመለከት የሚያሳስቡ መጻሕፍት ፍለጋ አማተርኩ። ጠላታችሁ ይፈር፣ አንድም መጽሐፍ በማጣቴ አፈርኩ። ይልቁንም እልክ የተጋቡ በሚመስል መልኩ ከዚህ በተቃራኒ የሰዎችን እይታ ከቀራንዮ በማስኮብለል ወዳልሆነ ቦታ የሚነዱ፣ ክርስቶስን በሰዎች ማንነትና ትልቅነት የሚጋርዱ ሆነው አገኘኋቸው። ካየሁት የመጻሕፍት ዐውደ ርእይ የተረዳሁት ነገር የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ ብቸኛ አዳኝነት፣ መንገድና ሕይወትነት ከመስበክ ይልቅ ቅጠልም፣ አፈርም፣ ዳቦም፣ ንፍሮም፣ ጠላም፣ ቅራሪም፣ አተላም፣ ተራራ ለተራራ መዞርም ሳማ ሰንበትም፣ አርሴማም፣ የግሼኗ ማርያምም፣ ኩክየለሽ ማርያምም፣ ግንድ አንሳውም፣ ሺህፈጁም፣ ጭሱም፣ ጠበሉም፣አመዱም፣የባህር ዛፍ ቅጠሉም፣ ጥንጁቱም፣ ቅርንፉድ መታጠንም፣ ቅማልና አይጥ ስእለት ማድረስም ገነት፣ መንግሥተ ሰማያት ሰተት አድርገው ያስገባሉ ትባላለህ። በቃ ያስገባሉ ከተባልክ አሜን ብለህ መቀበል ነው።  የኢየሱስስ ማዳን ምን ሊሆን ነው? ብሎ መጠየቅ፣ ማጉረምረም አይቻልም። መናፍቅ፣ ተሀድሶ፣ ጴንጤ ገለመሌ ካልሆንክ በስተቀር በክርስቶስ ላይ ተጨማሪ ልዩ ልዩ ተስፋዎች ሲቀርቡልህ አልቀበልም ማለት አትችልም።  "መንፈስን ሁሉ አትመኑ፣ ነገር ግን መንፈስ ከእውነት እንደሆኑመርምሩ"  የሚለውን ትምህርት ከማንበብ ውጪ ወደተግባር መለወጥ ክህደት ነው። ይህንን በመቃወም ፉከራው የገፋው ሰይጣን፣ አሹልኮ ያስገባቸውና በዘመናት ሂደት ጠፍተውና ቁጥራቸው ተመናምኖ የቆዩ መጻሕፍትን ይኼ ቅዱስ ነኝ የሚለው ማኅበር በባትሪ ፈልጎ በማሰባሰብ አራብቶና አባዝቶ አገልግሎቱን ማጠናከሩን በአግራሞት ተመለከትኩ። ሰይጣን በዚህ አገልግሎት ከመቼውም በላይ ደስተኛ ሳይሆን አይቀርም።  ማንነቱን መርምረው እንዳያውቁ በዘመቻ እየደፈቀ፣ ክህደቱን ለማግነን የሰራባቸው እንደዚህ የሰራባቸው ዘመናት አልታዩም። ኢየሱስ ክርስቶስ የንፍሮ ውሃ የጠጣልህን እስከ ዐሥር ትውልድ እምርልሃለሁ የሚል ቃል በ33 ዘመነ መዋዕለ ሥጋዌው ለማንም አላስተማረም። ይልቁንም ሌላ የመዳኛ መንገድ እንደሌለ አስረግጦ መናገሩን እናውቃለን።
ዮሐንስ 14፣6
"ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም"
ማኅበረ ቅዱሳን ግን የለም፣ ወደአብ መግባት የሚቻልባቸውንና ሰዎች በቀላሉ ከፈፀሟቸው የሚድኑባቸው ልዩ ልዩ ብልሀቶች አሉኝ የሚሉ መጻሕፍትን በአደባባይ ይሸጣል።  በዚያ ኤግዚብሽን ላይ ከተደረደሩት መጻሕፍት መካከል  “ወናሁ ትመውት በሕማመ ብድብድ እኩይ ሞት፣ ወእሬሲ ለከ ኪያሃ ከመ ስቅለትየ ወከመ ደመ ሰማዕት እለ እምቅድሜከ አኮ ለባሕቲትከ አላ ደቂቅከኒ እለ ይወውቱ በሕማመ ብድብድ በውስተ ዛቲ ገዳም እኌልቆሙ ምስለ ሰማዕታት ወአወፍዮሙ ለከ መንግሥተ ሰማያት”
ትርጉም፦ “እነሆ በክፉ ሞት በተቅማጥ ትሞታለህ፣ እሷንም እንደ ስቅለቴና ከአንተ በፊት እንደነበሩት ሰማዕታት ደም እቆጥርልሃለሁ ነገር ግን ለብቻህ አይደለም በዚች ገዳም በተቅማጥ በሽታ የሚሞቱትን ልጆችህንም ቁጥራቸውን ከሰማዕታት ጋራ አደርጋለሁ፣ መንግሥተ ሰማያትንም እሰጣቸዋለሁ” የሚለው ገድለ ተክለ ሃይማኖትን ገለጥ አድርጌ እንደገዢ ሰው አየሁት። ስድስት ክንፍ እንደተተከለለት የተቆረጠ እግር አለፍ ብሎ ወድቆ በስዕል ይታይ ነበር።
አቡነ አረጋዊ በዘንዶ ሲንሸራሸሩ፣ ለማርያም ድግስ የተቆላ አሻሮ የሸተተው ገነት እንደገባ፣ የሴት ብልት ስሞ ማርያም አፈወርቅ እንዳለችው የሚያትት፣ እግዚአብሔርን ክዶ በማርያም እንደዳነ የሚተርክ፣ ሰይጣን መነኮሰ፣ 30 ትውልድ ተማረ፣ ሎጥን ያዳነችው ማርያም ናት፣ መርቆሬዎስ ፀሐይና ፈረቃን ፈጠረ፣ ገብርኤልና ሚካኤል ሠለስቱ ደቂቅን አዳኑ፣ ሲኦልን የሞሉት ጋላና ሻንቅላ፣ የአርሴማ ድንግል ድንጋይ መካን አስወለደ፣ የአድዋን ጦርነት ጊዮርጊስ አሸነፈ ወዘተ ወጎችን የሚጠርቁ መጻሕፍት እንደጉድ ሲቸበቸቡ ተመለከትኩ። የሆኖስ ሆኖ ጊዮርጊስ አድዋ ላይ ከተዋጋ ጀግኖች አርበኞች ምን ሰሩ ሊባል ነው? የሞቱትና የቆሰሉት ምን ሲያደርጉ ኖሯል? ነው ወይስ መቁሰልና መሞት አልነበረም?
"የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል" እንዲሉ ሰዎቹ ጊዮርጊስ ባይኖር ጣልያንን ባላሸነፍንም ነበር ይሉናል። ኢህአዴግ ደርግን ያሸነፈው ማንን ይዞ ይሆን?
ማኅበሩ እያራባ ከሚሸጣቸው መጻሕፍት አብዛኛዎቹ ወንጌልን የሚቃወሙ፣ ባዶ ተስፋ የሚሰጡ፣ ሰው ከወንጌል ይልቅ እነዚያን እንዲያነብ የሚገፋፉ፣ የክርስቶስ ኢየሱስን የማዳን ሥራ አስትተው በትርኪ ምርኪ ቃል ኪዳን ላይ እንዲታመኑ የሚያበረታቱ መጻሕፍት ብቻ ድንኳኑን ሞልተው አይቻለሁ። ታዲያ ይህንን የስሁታንን ሥራ የሚሸጠው ማኅበር ራሱን "የቅዱሳን" ሲል ያሞካሸዋል።
ሰይጣን አስርጾ ያስገባቸውና በዘመናት ብዛት ተቀዳደውና ተመናምነው የሚያባዛለት አጥቶ በደነገጠበትና ተስፋ በቆረጠበት ሰዓት ማኅበሩ ድንገት ደርሶ እንደታደገው ማረዳት አይከብድም። ሊወገዙ የሚገባቸው የባዶ ተስፋ መጻሕፍትን ከወንጌል በላይ አሳትሞ ማሰራጨት ከቶ ምን ይባላል?
ከኤግዚቢሽኑ መጻሕፍት እንዲህ የሚል ቃል ያለበት መጽሐፍም ነበር።
«ወሶቤሃ አውስአ  ወይቤላ ንስኢ ወሐብኩኪ ዐሥራተ ብዙኀ ነፍሳተ መጠነ ነጠብጣብ ዝናም ዘ፬ቱ አውራኅ ለእለ አሐዱ ዕለት»
ትርጉም «ጌታም እንዲህ አላት። በዐራት ወራት ውስጥ በየቀኑ የሚወርደውን የዝናም ነጠብጣብ ያህል ነፍሳትን ዐሥራት አድርጌ ሰጥቼሻለሁ» ገድለ ክርስቶስ ሰምራ
 በዓለም ላይ በየቀኑ የሚዘንበውን የአራት ወራት ያህል የዝናብ ነጠብጣብ ውሃ ያህል ሰው ከአዳም ጀምሮ አልተፈጠረም። ገድሉ የተፈጠረውንም፣ ያልተፈጠረውንም ክርስቶስ ሰምራ ታድን ዘንድ ቃል ተገብቶላታል ይለናል።  በዚህ ቃል መሠረት ኦርቶዶክስ በክርስቶስ ሰምራ በኩል የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ናት ማለት ነው።
በሮሜ 10፣3 እንደተመለከተው
"የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም" የሚለው ቃል ከሚፈፀም በቀር እንኳን ለዓለሙ አዳኝ ልትሆን ቀርቶ ራሷም ከቆመችበት የአበው አስተምህሮ ተንሸራታ ተስፋ በሌለው ተረታ ተረት ተሸፍናለች።  ማኅበሩ የመጋረጃውን አገልግሎት በማስፋት ሰዎችን ወደጥፋት እንዳይነዳ  እንደሄሜዎስና እስክንድሮስ ለሰይጣን ተላልፎ የተሰጠ ይሁን! ብኩርናውን ለጥቅም፣ ትጋቱን ለስሁት አገልግሎት፣ ሐዋርያትም ከሰበኩት ስብከት የተለየውን የሰበከ የተረገመ ይሁን! አሜን።

Saturday, February 27, 2016

የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም!

አንዳንዶች ከአበው የተረከብነው አስተምሕሮና ሕግ በማለት ሁሉን ነገር እንደወረደ እንድንቀበለው ይፈልጋሉ። አዎ፣ አበው ብዙ ነገር አስተላልፈውልናል። ነገር ግን የተላለፈልን ነገር ሁሉ ጠቃሚ ነው ማለት አይደለም። ለእግዚአብሔር ይቀርብ የነበረ የቤተመቅደሱ መስዋእት በመቅደሱ ሚዛን ይለካ እንደነበረው ሁሉ የተላለፈልን የአበው አስተምሕሮ ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል ሚዛን መሰፈር አለበት። ምክንያቱም ከኛ በፊት ያለፉ ሁሉ በእድሜ አበው ቢሆኑም በአስተምሕሮ ግን በአበው ከለላ የስሕተት አስተምህሮ በስማቸው ሊገባ ይችላልና ነው። ስለሆነም በጅምላ አባቶቻችን ማለት ብቻውን ከስሕተት አያድንም። የአባቶች ትምሕርት ከመጻሕፍት ውጪ እንዳይኾኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በአንድ ወቅት አይሁዳውያን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምሕርት እንዲኽ እንደዛሬው የተቃወሙት እኛስ ከአባታችን ከአብርሃም ነን እያሉ ነበር። አብርሃም አባታቸው መሆኑን ቢናገሩም በአብርሃም ስም ከመነገድ በስተቀር የአብርሃምን ስራ የማይከተሉ ነበሩ ተግባራቸው ይመሰክር ነበር።

ዮሐንስ 8፣39
መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው፡ አሉት። ኢየሱስም፦ የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር፣ ብሏቸዋል።
ዛሬም ከሙሴ የተቀበልነው የታቦት ሕግ አለን የሚሉ አሉ። ነገር ግን ለሙሴ የተሰጠውንና ያደረገውን ሥራ አያደርጉም። ግን በሙሴ ስም ይነግዳሉ፣ ያታልላሉ፣ ይዋሻሉ። ሙሴን አውቀውትማ ቢኾን ኖሮ ሙሴ ያደረገውን ባደረጉ ነበር። ሙሴ የታዘዘውና ያደረገውን ይኽንን ነበርና።

ዘጸአት 25፣10
ከግራር እንጨትም ታቦትን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን።
ሙሴ ለጽላቱ ማኅደር ይሆን ዘንድ እንዲሰራ የታዘዘውና የሰራውም ታቦት ልኩ ይኼው የተጠቀሰው ሆኖ ቤተመቅደሱ ፈርሶ አገልግሎቱ እስከተቋረጠበት እስከ 70 ዓ/ም ድረስ ለ 2000 ዘመን ይህ ልኬታ ተሻሽሎና ተቀይሮ ስለመገኘቱ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ላይ አልተጻፈም። ነገር ግን ዛሬ የጽላቱ ማደሪያ የሆነው ታቦት አለን የሚሉ ወገኖች በሙሴ ሽፋን የሚሰሩት ታቦት ርዝመቱም፣ ቁመቱም፣ ወርዱም እንደጠራቢው ችሎታና እንደአስጠራቢው ፍላጎት እንጂ የተወሰነ መጠን በሌለው ልቅ ፍላጎት ሲጠቀሙ ይታያሉ። የእግዚአብሔርን የመሥፈሪያ ሚዛን ሊጠቀሙ ይቅርና ለሚሰሩት የስሕተት ሥራ እንኳን አንድ ወጥ የሕግ ሚዛን ለራሳቸው የላቸውም። ጠራቢዎቹም የእግዚአብሔር መንፈስ እንደሞላባቸው በሙሴ እንደተመረጡት አልያብና ባስልኤል ሳይሆን ቤተክርስቲያን አነውራ የምትጠራቸው፣ ቆብና ቀሚስ የጣሉ መነኮሳት፣ ያፈረሱ ቄሶችና ደጋሚ ደብተራዎች፣ የሚያስገኘውን ገቢ የቀመሱ አወዳሾች መሆናቸው የአደባባይ ምስጢር ነው።   በመኖሪያ ቤቱ የእንጨት ማሽን ተክሎ፣ ከጣውላ አቅራቢዎች ምንነቱ ያልታወቀ ጥርብ እየገዛ በሚቀርቡለት የፈላጊዎች ትእዛዝ መሠረት ጽላት የሚባለውን የዘመኑን የሰዎች መሻት እየቀረጸ የሚያከፋፍል ሰው የዚኽ ጽሑፍ አቅራቢ ያውቃል። ከሥራዎቹም የተወሰነውን ለማየት ችሏል። ከታች በገብርኤል ስም ከጣውላው የተቀረጸ ምስል ለአብነት ይመለከቷል።   እግዚአብሔር በሚሰራውና ጥንት ባደረገው ነገር ሁሉ ከመረጣቸው ሰዎች ማንነት ጀምሮ የተለዩና በሚሰሩትም ሥራ ጥንቃቄና ትእዛዙን የጠበቀ ስለመሆኑ ለአፍታ የሚዘነጋ ጉዳይ አይደለም።  ዛሬስ? በ 0% የቀደመ ሥርዓት ላይ ሆነው በሙሴ ሕግ ሥር የመደበቅ ዘመን አብቅቷል። በትውልዱም የተሸፈነው መገለጡ አይቀርም። በስተመጨረሻም የእግዚአብሔርም ትእግስት ሲሞላ ውርደት መከተሉ ሳይታለም የተፈታ ነው። በዋጋ መሸጪያ ተመን ገበያ ወጥቶለት በገንዘብ የሚገዛ ጽላት በጭራሽ ሊኖር አይችልም።
እንደእውነቱ ከሆነ በዚህ ዘመን በአባቶች እያሳበቡ የእግዚአብሔርን ቃል በመቀየር በትውልድ ላይ ለመጫን መሞከር ማብቃት አለበት።
 ሙሴ የዕንቁውን ጽላት አሮን ባሰራው የጥጃው ጣኦት ላይ ከሰበረ በኋላ አስመስለኽ ቅረፅና አምጣ ተብሎ በእግዚአብሔር ሲነገረው ለጽላቱ ማደሪያ ተብሎ አስቀድሞ የተሰጠው የታቦቱ ርዝመት፣ ቁመትና ወርድ ላይ የተሰጠ የለውጥ ትእዛዝ አልነበረም። ምክንያቱም የተሰበረው ጽላቱ እንጂ ታቦቱ አይደለምና።  ስለዚህ "ቀር ከመ ቀዳሚ"  የተባለው ጽላቱን እንጂ ማደሪያውን ታቦት ካልሆነ ሙሴ ያላሻሻለውን ታቦት ዛሬ ያሻሻሉት ከየት ባገኙት አምላካዊ ትእዛዝ ነው?  ውሸታቸውን ለማጽደቅ የፈረደበት የሙሴን ስም አቅርበው ሊሞግቱን ይዳዳሉ።
ስለማኅደሩ መሻሻል የተነገረ ካልነበረ እነዚህኞቹ በራሳችን ሥልጣን አሻሽለናል ይበሉን እንጂ ሙሴን ለሐሰት ምስክርነት አይጥሩብን።
ከዚያም ሌላ ሙሴ የፊተኞቹን ጽላቶች አስመስሎ ከቀረጸ በኋላ ይዞ የሄደው ወደሲና ተራራ ነው። በዚያም እግዚአብሔር በጣቶቹ 10ቱን ትእዛዛት ጻፈባቸው እንጂ ሙሴ በጭራሽ አልጻፈም።

ዘዳግም 10፣3-4
ከግራርም እንጨት ታቦትን ሠራሁ፥ እንደ ፊተኞችም ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረብሁ፤ ሁለቱንም ጽላቶች በእጄ ይዤ ወደ ተራራው ወጣሁ።
ስብሰባ ተደርጎ በነበረበትም ቀን እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳት ውስጥ ሆኖ የተናገራችሁን አሠርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደ ነበረ በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ።
ይለናል መጽሐፍ ቅዱሳችን።

እዚህ ላይ እንደምናነበው ጽላቶቹ ላይ የጻፈባቸው እግዚአብሔር ራሱ ሆኖ ሳለ ሙሴ እንደጻፈ አድርጎ በሙሴ ላይ መዋሸት ለምን አስፈለገ?  አስመስለኽ ቅረጽና አምጣ መባሉን ልክ እራስኽ እየጻፍክባቸው አባዛ የተባለ ማስመሰል በእግዚአብሔር ላይ መዋሸት አይደለምን? ያልተባለውን እንደተባለ፣ ያልተነገረውን እንደተነገረ አድርጎ በማቅረብ የራስኽንም ስሕተት እንደማጽደቂያ መሳሪያ አድርጎ መጠቀም የከፋ ክሕደትና ሕዝቡን በስሕተት መንገድ መንዳት ነው።  ሙሴን ያላደረገው ነገር አድርገኻል ማለት መሳደብ ነው፣ እግዚአብሔርንም ለሙሴ አንተው ጻፍባቸው ያላለውን እንዳለ ማስመሰልስ ዋሾ ማድረግ አይደለምን?
 ጽላቶቹ ላይ የተጻፈባቸውና ሙሴ የተቀበላቸው 10ቱን ትእዛዛት ሆኖ ሳለ የሰው ስም ወይም የሰው ምስል ያለበት አድርጎ በማቅረብ በዚህ ዘመን እኛ የምንፈልገውን የልባችን ፈቃድ ለማሳካት ማጭበርበርስ ለምን ይሆን? በየትኛውስ ቃል እንደገፋለን? የምናስደስተው ሰውን ወይስ እግዚአብሔርን? መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ያላለውን ብለኻል በሚሉ ዋሾዎች ተደስቶ አያውቅም። ሊደሰትም አይችልም። ከራሱ አንቅቶ የሚናገረው የሐሰት አባት የሆነው ዲያብሎስ ብቻ ነው።
እግዚአብሔር የሰጠውን ሕግ የሚያጸናውና የሚሽረው ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ሰው እንዴት የኪዳኑን ሕግ ራሱ ለራሱ ስሜት ያሻሽላል?
የሙሴን ታቦተ ሕግ ተከትለናል ማለት እግዚአብሔር ያላለውን በራስ ፍላጎት እንደሚመች አድርጎ ማቅረብ ነው እንዴ?
ሌላው መነሳት ያለበት ነገር፣ ዛሬ የኪዳኑን ጽላት እንጠቀማለን የሚሉ ሰዎች የኦሪቱ የጽላት ሕግ፣ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለማነው? የሚለው ነው።

 በማያከራክር መልኩ የቃልኪዳኑ ታቦት ሕግ የተሰጠው ለእስራኤል ዘሥጋ ብቻ ነው። ይኽ ሆኖ ሳለ እናንተን ያ የኪዳን የሕግ ውል የጨመራችሁ በየትኛው የብሉይ ኪዳን ቃል ላይ ነው?  እግዚአብሔር ውሉን በሙሴ ፀሐፊዎች አማካይነት በአራቱ ብሔረ ኦሪት ጽፎ ሰጥቷቸዋል። የእናንተስ ውል በነማን በኩል፣ መቼና የት ቃል ተገባላችሁ? ብለን እንጠይቃቸዋለን።
ምክንያቱም እስራኤላውያን አፋቸውን ሞልተው እንዲህ ሲሉን እናገኛቸዋለን።
ዘዳግም 5 ፣2
አምላካችን እግዚአብሔር በኮሬብ ከእኛ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ።

ያ ቃልኪዳን ከፈረሰና የመስዋእቱ አገልግሎት ከተቋረጠ 2ሺህ ዘመን አልፎታል። ከዚያ በኋላ ከእስራኤላውያን ውጪ እግዚአብሔር የታቦት ቃልኪዳን የገባላቸው ሌላ ሕዝቦች የሉም። ኧረ በጭራሽ አይኖርምም። ምክንያቱም ያ ውል የተገባው ለተወሰነ ሕዝብ ብቻ ስለሆነ ሁሉን ያካተተ አዲስ ውል ያስፈልግ ስለነበር ለተወሰነ ሕዝብ በድጋሜ ቃል የሚገባበት ምክንያት የለም።
ሮሜ 9፣4
እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና"

ነገር ግን ሕዝቤ ያልተባለን ሕዝቤ ለማለት አህዛብ ሁሉ ወደመጠራቱ እንዲገቡ አዲስ ቃል ኪዳን አስፈልጓል።
ሮሜ 9፣26 እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ስፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሔር ልጆች ተብለው ይጠራሉ፥ ይላል።

በዚህም ምክንያት ለአንድ ሕዝብ ብቻ ተሰጥቶ የነበረው ሕግ ቀርቶ ሁሉን የሚመለከት ሕግ እንዲመጣ ማስፈለጉን በአዲስ ኪዳን የኦሪቱ የመስዋእት አገልግሎት ከእንግዲህ አይታሰብም ተብሎ ትንቢት ተነግሯል።

ኤርምያስ 31፣31
እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር።

 ለምን አዲስ ቃልኪዳን መግባት አስፈለገው? ምክንያቱም፣

ኤርምያስ 31፣32
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም፤ እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር።

ስለዚህ በሰማያዊው መስዋእት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተሻለ ኪዳን ስለተገባልን አሁን ልንናገርበት ጊዜው ባልሆነ የዚህ ምድር ሥርዓት አይደለንም። ጳውሎስ ድሮ ነበረ፣ አሁን ግን የለም ይለናል።

ዕብራውያን 9፣5
በላይዋም ማስተስሪያውን የሚጋርዱ የክብር ኪሩቤል ነበሩ፤ ስለ እነዚህም ስለ እያንዳንዳቸው ልንናገር አሁን አንችልም።
ምክንያቱም፣
ዕብራውያን 7፣22
እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል።
ስለዚህ አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ መሪያችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን በማለት ለስሕተት መሸፈኛ አድርጎ ማቅረብ አያድነንም። አብርሃም አባታችን፣ እግዚአብሔር አምላካችን ይሉ የነበረ፣ ነገር ግን የሚነገራቸውን ቃል እኛ ከሁሉ ቀድመን ያወቅን ነን በሚል ትምክህት ለመቀበል ያልፈለጉትን ሊቃውንተ አይሁድን እንዲህ ብሏቸዋል።

ዮሐንስ 8፣47
ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።

ስለዚህ በዚህ ዘመንም የቀደመችው ሃይማኖት በማለት ራስን በመካብ ብልጫ አይገኝም። ከአይሁድ የቀደመ ሃይማኖት የለምና። ነገር ቀድሞ በመገኘት አብርሃም አባታችን፣ ሙሴ ፈለጋችን ነው፣ ማለት ከስህተት አያርቅም። ምክንያቱም አብርሃምና ሙሴ የተቀበሉትንና የፈፀሙትን ሕገ እግዚአብሔር ሳይሸራርፉና ሳያሻሽሉ በማድረግ እንጂ የነሱ ተከታይ መሆን የሚቻለው በስማቸው በመነገድ ግን በሕጉ በሌሉበት ሁኔታ የሙሴ ተከታዮች በማለት ራስን ካልሆነ ማንንም ማታለል አይቻልም።
ስለሆነም የዛሬ ታቦትና ጽላት ከሙሴ ዘመን ጋር በጭራሽ አይገናኝም። እንዲቀየርና እንዲሻሻል ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሕግ አልነበረም። ፊተኛውና ኋለኛው ጸሐፊ ራሱ እግዚአብሔር፣ ጽሕፈቱም ሕግጋቶች ነበሩ። የተጻፈውም በሲና ተራራ ነጎድጓዳማ ድምጽ መካከል እንጂ በጥቃቅንና አነስተኛ የእንጨት መላጊያ ውስጥ አልፎ የዚህ ምድር በሆነች እጅ ብልሃት አይደለም።
የእጅ ብልሃት ይኽ ነው።

Tuesday, February 23, 2016

ቃል ኪዳን!


“ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” (መዝ. 88/89፥3)።
በዚህ ቃል ሽፋንነት የገባው የስሕተት ትምህርት፥ የክርስቶስን የመካከለኛነት ስፍራ ለፍጡራን አሰጥቷል። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ከተለያዩ ቅዱሳን ጋር ስለ ልዩ ልዩ ጕዳዮች የገባውን ቃል ኪዳን መነሻ በማድረግና፥ “ከመረጥኹት ጋራ ቃል ኪዳኔን አደረግኹ” የሚለውን ቃል በመታከክ፥ በዐዲስ ኪዳንም ኀጢአተኞች ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡበትን የተለያየ ቃል ኪዳን ለቅዱሳን ሰጥቷል የሚሉ አሉ።
በቅዱሳን ስም በተደረሱት ገድላትና ድርሳናት ውስጥ፥ ከራስ ዐልፈው ሰባትና ከዚያም በላይ ያለውን ትውልድ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገቡ ቃል ኪዳኖች እንዳሉ ተገልጧል። ቃል ኪዳኖቹ የተመሠረቱትም በቅዱሳን ስም የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ ነው። ሌላው ቀርቶ የአንዱን ቅዱስ ገድል የጻፈ፥ ያጻፈ፥ ያነበበ፥ የተረጐመ፥ የሰማ፥ ያሰማ እንኳ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርስ ተስፋ የሚሰጡ ገድላት በርካታ ናቸው። ይህም በራእ. 1፥3 ላይ፥ “ዘመኑ ቀርቧልና፥ የሚያነብበው የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁ ብፁዓን ናቸው” ከሚለው የተኰረጀ ሊኾን ይችላል።
በመዝሙረ ዳዊት 88/89፥3 ላይ የተገለጠው፥ እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንጂ ሌሎችን አይወክልም። በቍጥር 4 ላይ፥ “ለባሪያዬ ለዳዊት ማልኹ፤ ዘርኽን ለዘላለም አዘጋጃለኹ፤ ዙፋንኽንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለኹ” ማለቱም ይህንኑ ያስረዳል። ቃል ኪዳን የገባው የማይዋሽ እግዚአብሔር በመኾኑ፥ “ኪዳኔንም አላረክስም፤ ከከንፈሬም የወጣውን አልለውጥም። ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልኹ። ዘሩ ለዘለዓለም፥ ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሓይ ይኖራል። ለዘለዓለም እንደ ጨረቃ ይጸናል። ምስክርነቱ በሰማይ የታመነ ነው” ብሎ ነገሩን እንዳጻናለት ይናገራል (ቍጥር 34-37)።
ይህ ስለ ዙፋኑ መጽናት የተገባው ቃል ኪዳን ለጊዜው ጥላነቱ በሰሎሞን ሲታይ፥ በክርስቶስ ግን ተፈጽሟል (2ሳሙ. 7፥12-16፤ ሉቃ. 1፥32፤ ዕብ. 1፥5፡8፤ ራእ. 22፥11)። እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ አምላክ በመኾኑ፥ ዳዊት ከሞተ በኋላ ልጁ ሰሎሞን በቃል ኪዳኑ ውስጥ የነበረውን ውል አፍርሶ በመገኘቱ መንግሥቱ መቀደድ ቢኖርበትም፥ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት የገባውን ቃል ኪዳን ዐስቦ ይህን በሰሎሞን ዘመን አላደረገበትም (ዳን. 9፥4፤ 1ነገ. 9፥5-7፤ 11፥1-13)።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ (በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት) ቃል ኪዳን ከተገባላቸው መካከል ዋናዎቹ፥ አዳም፥ ኖኅ፥ አብርሃም፥ ሙሴና ዳዊት ናቸው። ለአዳም የተሰጠው ቃል ኪዳን መልካሙንና ክፉውን በሚያስታውቀው ዛፍ ምልክትነት፥ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ተስፋን የያዘ ነበር። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች አዳምና ሔዋን በኪዳኑ ስላልጸኑ ሞት ገዛቸው (ዘፍ. 2፥8-17፤ ሆሴ. 6፥7)።
ከአዳም ቀጥሎ ቃል ኪዳን የተሰጠው ለኖኅ ሲኾን፥ ምድር ዳግመኛ በጥፋት ውሃ እንዳትጠፋ የቆመ ኪዳን ነው። ይህ በምድር ላይ የመኖርን ተስፋ የያዘው ኪዳን፥ በቀስተ ደመና ምልክትነት ተገልጦ ለዓለም ሕዝብ ኹሉ ያገለግላል (ዘፍ. 9፥1-17)።
እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው ቃል ኪዳን፥ በብሉይ ኪዳን ጐላ ያለ ስፍራ ከተሰጣቸውና በዐዲስ ኪዳን ፍጻሜ ካገኙት ቃል ኪዳኖች መካከል ይጠቀሳል። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች ለጊዜው ምድራዊቱን ከነዓንን የወረሱት አብርሃምና በይሥሐቅ በኩል የተቈጠሩት ዘሮቹ ኹሉ ሲኾኑ፥ ፍጻሜው ግን አይሁድ፥ አሕዛብ ሳይባል አብርሃምን በእምነት በመምሰላቸው የአብርሃም ልጆች የኾኑት ኹሉ ናቸው (ገላ. 3፥7-9፡29፤ ሮሜ 4፥11-12፤ 9፥7-8)። የዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ግዝረት፥ የቃል ኪዳኑ ተስፋ ደግሞ በዘሩ የአሕዛብ መባረክና ከነዓንን መውረስ ነው (ዘፍ. 17፥1-21፤ ሮሜ 4፥11)።
የምድር አሕዛብ ኹሉ የተባረኩበት የአብርሃም ዘር ክርስቶስ፥ የምድራዊቱ ከነዓን አማናዊት የኾነችውን ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን የሚያወርስ በመኾኑ፥ ለቃል ኪዳኑ ፍጻሜን ሰጥቷል (ገላ. 3፥16)። እግዚአብሔር በክርስቶስ ያደረገው ኹሉ ለአብርሃም በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መኾኑንም ቅዱሳን መስክረዋል (ሉቃ. 1፥54፡73)።
በመቀጠል ደግሞ ለሙሴ የተሰጠውን ቃል ኪዳን እናገኛለን (ዘፀ. 19፥5-6፤ 24፥7-8)። የቃል ኪዳኑ ተቀባዮች የኾኑት ሕዝበ እስራኤል፥ የአብርሃምን የቃል ኪዳን ምልክት ተከትለው ሰንበታቱን መጠበቃቸው ለዚህ ቃል ኪዳን ምልክት ኾኗል (ዘፀ. 31፥13፤ ሕዝ. 20፥10-17)። በቃል ኪዳኑ የተሰጣቸው ተስፋ በአገራቸው ሕይወትን ማግኘት ነው። ይህንም ገና ከምድረ ግብጽ ሳይወጡ በነበረው ዕለት ምሽት ላይ ያረዱት የፋሲካ መታሰቢያ በግ ደም አረጋግጦላቸዋል (ዘፀ. 12፥21-28)።
ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ሲና ተራራ ሲደርሱ፥ ሕጉን በድንጋይ ጽላት ጽፎ ይጠብቁትና በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል ቃል ኪዳን ይኾን ዘንድ ለሙሴ ሰጠው። ይህም ብሉይ ኪዳን ተብሎ የተጠራው ነው (ዘፀ. 19፥20፤ 31፥18፤ 20፥1-17፤ 34፥28፤ ዘዳ. 4፥13)። በእንሰሳት ደም የቆመው ብሉይ ኪዳን ወደ ፊት ለሚመጣው ዐዲስ ኪዳን መንገድ ጠራጊ እንጂ በራሱ ቋሚነት አልነበረውም። የጽላቱ ተሰብረው መተካታቸው፥ የማደሪያው ድንኳን ሰሎሞን በሠራው ቤተ መቅደስ መተካቱ፥ የመሥዋዕት መደጋገምና የመሳሰሉት ኹኔታዎች ለጊዜያዊነቱ ምልክቶች ተደርገው ይወሰዳሉ። ይበልጥ ደግሞ ትንቢቱ ይህን አረጋግጧል (ዘዳ. 18፥15፤ ኤር. 31፥31)።
ቃል ኪዳን የሚጸናው ኹለቱም ወገኖች ሲጠብቁት ብቻ ነው። ከኹለቱ አንዱ ጠብቆ ሌላው ቢያፈርሰው ቃል ኪዳን መኾኑ ይቀራል። ብሉይ ኪዳን ጊዜያዊነቱ ሳያንስ ሕዝቡ ሊጠብቀው ባለመቻሉ ቃል ኪዳንነቱ ቀረ። እግዚአብሔርም ከዚህ በብዙ መንገድ የተሻለውን ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚገባ ተናገረ (ኤር. 31፥31-34)። ይህም ስለ ዐዲስ ኪዳን የተነገረ ትንቢት በመኾኑ፥ በዕብራውያን 8 ላይ ተፈጻሚ ኾኖ ተጠቀሰ። ዐዲስ ኪዳን የተሻለና የበለጠ ኪዳን በመኾኑ ብሉይ ኪዳን ከነጓዙ ፍጻሜ አግኝቶ እንደሚቀርና የሚጠቀምበት ቀርቶ የሚያስበው እንኳ እንደማይኖር እግዚአብሔር በአጽንዖት ተናገረ (ኤር. 3፥16)።
እግዚአብሔር እስከዚህ ድረስ ለተለያዩ ቅዱሳንና ለአጠቃላዩ የእስራኤል ሕዝብ ገብቶ የነበረውን ቃል ኪዳን ኹሉ በመጠቅለል፥ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ዐዲስና ለዘላለም የማይፈርስ፥ ተጨማሪ የማያስፈልገው ቃል ኪዳን ገባ። እርሱም በገዛ ደሙ የመሠረተው ዐዲስ ኪዳን ነው (ሉቃ. 22፥19-20፤ ኢሳ. 42፥6-7)። ይህ ኪዳን በክርስቶስ ለሚያምኑ ኹሉ የተሰጠ ሲኾን፥ የዘላለም ሕይወትን ተስፋ የያዘ ቃል ኪዳን ነው። የተስፋው ምልክቶችም ጥምቀትና ቅዱስ ቍርባን ናቸው (ማር. 16፥16፤ 1ቆሮ. 11፥23-26፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 80)።
ዐዲስ ኪዳን ብሉይ ኪዳንን በከፊል ሳይኾን ሙሉ በሙሉ ተክቷል። ዐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ክብሩ የጸናበት፥ ኹሉ የተፈጸመበት ታላቅ ቃል ኪዳን መኾኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት የቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍትም መስክረዋል፤ “ወበምክረ ዚኣከ ወልድከ ዋሕድ ኢየሱስ ዘተሰቅለ በእንተ መድኀኒትነ ዘበቃለ ኪዳንከ ቦቱ ገበርከ ሠሚረከ ቦቱ። - ለድኅነታችን በተሰቀለው በአንድያ ልጅኽ በኢየሱስ በባሕርይኽ ምክር ደስ ተሰኝተኽበት ቃል ኪዳንኽን ኹሉ በእርሱ አድርገኻል” (መጽሐፈ ቅዳሴ 1984፣ ገጽ 65)።  
እንዲሁም በእልመስጦአግያ፥
“ከመ ታእምሩ ፈቃዶ ለኢየሱስ ክርስቶስ ወትሌብዉ ምስጢረ መድኀኒትክሙ ኦ አንትሙ እደው ወአንስት ቅዱሳት እለ ሀሎክሙ ውስተ ተመክሖ በክርስቶስ፥ ወኩኑ አሐደ ምስለ ብእሲ ዘውስጥ አንትሙኬ እለ አጽንዐ እግዚአብሔር ኪዳኖ ምስሌክሙ ወሤመ መንፈሶ ውስቴትክሙ፡፡”
ትርጓሜ፥ “የኢየሱስ ክርስቶስን ፈቃድ ታውቁ ዘንድና የደኅንነታችኹን ምስጢር ታስተውሉ ዘንድ፥ በክርስቶስ ትምክሕት ያላችኹ እናንተ ወንዶችና ቅዱሳት ሴቶች ሆይ፥ ከውስጣዊ ሰውነት ጋር አንድ ኹኑ፤ እግዚአብሔር ኪዳኑን ከእናንተ ጋር ያጸና መንፈሱንም በውስጣችኹ ያሳደረ እናንተ ናችኹ እኮ” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 24)።
የእግዚአብሔር የባሕርይ ምክርና ሐሳቡ ለአንዴም ለመጨረሻ ጊዜም በክርስቶስ በኩል በገባው ዐዲስ ኪዳን በኩል ተፈጽሟል። እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ጋር ባለው ታሪክ የገባው የመጨረሻው ቃል ኪዳን ዐዲስ ኪዳን ብቻ ነው። በዚህ ኪዳን ያልተፈጸመለት ወይም የቀረው ነገር ኖሮ፥ በሌላ ቃል ኪዳን ለመፈጸም በማሰብ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ሌላ ቃል ኪዳን ገብቷል የሚለው ትምህርት ልብ ወለድ ከመኾን አይዘልም፤ ምክንያቱም የዘመን ፍጻሜ በኾነው ባለንበት ዘመን፥ እግዚአብሔር ለማድረግ ያሰበው፥ ነገሮችን ኹሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል እንጂ ሌላ ቃል ኪዳን ለመግባት አይደለም (ኤፌ. 1፥10)።
ከላይ ለማሳየት እንደ ተሞከረው፥ ለቀደሙት አበው የገባው ቃል ኪዳን፥ ከወቅቱ ኹኔታ ጋር በተያያዘ መንገድ፥ ወይም ስለ ወደ ፊቱ ተስፋ ነበር እንጂ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባ ቃል ኪዳን አልነበረም፤ እንዲህ ያለውን ቃል ኪዳን ከማንም ፍጡር ጋር አልገባም። ምናልባት ለአዳም የገባው ቃል ኪዳን በአዳም ባይፈርስ ኖሮ፥ ለዘላለም በሕይወት መኖርን የሚያስገኝ ቃል ኪዳን ይኾን ይኾናል። ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበትን ቃል ኪዳን የገባው ግን በክርስቶስ በኩል ብቻ ነው።
በሐሰት ለቅዱሳን በዐዲስ ኪዳን ተገባ በሚባለው ቃል ኪዳን መሠረት፥ እንዲህና እንዲያ ያደረገ ይህንና ያን ያገኛል የሚል ተስፋ በብዙ አዋልድ መጻሕፍት በስፋት ተጽፎ እናነባለን። አብዛኛው ቃል ኪዳን ተሰጠ ተብሎ የሚተረከው ቅዱሳኑ ሊሞቱ ሲሉ በመጨረሻዋ ሰዓት ላይ ነው። እንዲህ ከኾነ ታዲያ በዐዲስ ኪዳን መጥምቁ ዮሐንስ፥ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ፥ እና ያዕቆብ በግፍ የተገደሉ ቅዱሳን ናቸው፤ ሊሞቱ ሲሉም ኾነ ከዚያ በፊት ቃል ኪዳን እንደ ተገባላቸው በሐዲስ ኪዳን ውስጥ አናገኝም (ማቴ. 14፥10-12፤ ሐ.ሥ. 7፥6 12፥2)። ለነዚህ ቅዱሳን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ሰዎች ከልባቸው አንቅተው (አመንጭተው) በደረሱላቸው ድርሰትና ገድላት ውስጥ ግን፥ የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን ጻጽፈው ሊያስነብቡን ቢከጅሉም አንድም እውነትነት የለውም።
ዛሬ ብዙዎቹ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባልኾነ ቃል ኪዳን ተታለዋል። ስለዚህ በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ከመጽደቅና በእርሱ ኖረው መልካም የሥራ ፍሬን ከማፍራት ይልቅ፥ በኀጢአት ላይ ኀጢአትን በመጨመር ከእግዚአብሔር ባልኾነው ቃል ኪዳን እየተኵራሩ፥ ‘በእገሌ ቃል ኪዳን መሠረት እንዲህ ካደረግኹ አልኰነንም’ ብለው ራሳቸውን ይሸነግላሉ። የእግዚአብሔር ቃል ግን እንዲህ ይላቸዋል፤ “ለዐመፀኞች ልጆች ወዮላቸው፥ ይላል እግዚአብሔር። ከእኔ ዘንድ ያልኾነ ምክር ይመከራሉ። ኀጢአትንም በኀጢአት ላይ ይጨምሩ ዘንድ ከመንፈሴ ዘንድ ያልኾነውን ቃል ኪዳን ያደርጋሉ።” (ኢሳ. 30፥1)።
ምንጭ፦ የተቀበረ መክሊት 3ኛ ገጽ 106