Saturday, March 15, 2014

«ቅዱስ ኤልያስ ይዞት የመጣውን መጽሐፍ” ቤተ ክርስቲያን እንድትቀበል ተጠየቀ»

 (ምንጭ፤አዲስ አድማስ)
መጽሐፉ ለአቡነ ማትያስና ለጠ/ሚ ኃይለማርያም እንዲደርሳቸው ተደርጓል
ደብዳቤው ለእስራኤሉ ጠ/ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታናሁ እና ለተመድ ተልኳል

       ከተፃፈ ከ2 ሺህ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል የተባለውንና ስለ ቅዱስ ኤልያስ መምጣት ምስጢር የሚተነትነውን መጽሐፍ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተቀብላ ወደተለያዩ ቋንቋዎች በማስተርጎም ምዕመናኖችን እንድታስተምር፣ “ማህበረ ሥላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” ለቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በጻፈው ደብዳቤ ጠየቀ፡፡
ማህበሩ፤የመጽሐፉን ኮፒዎች ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ እና ለብፁዕ አቡነ ማትያስ  ህዝቡን እንዲያስተምሩበት ከሚያሳስብ ደብዳቤ ጋር መላኩን አስታውቋል፡፡
አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን አባል የሆነችበት ማህበረ ሥላሴ፤“ቅድስት ቤተ-ክርስቲያን ለሁለት ሺህ ዘመን ስትጠብቀው የቆየችውን ምስጢራዊ መጽሐፍ በአደራ የመረከብና ለዓለም ሁሉ የማሳወቅ ፅኑ ኃላፊነትን ይመለከታል” በሚል ርዕስ ለፓትርያርኩ፣ በግልባጭ ደግሞ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዲሁም ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔትናሁ እና ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት በፃፈው  ደብዳቤ “ማህፈድ ብርህት ዘዲዮስቆሮስ አንበሳ” በሚል ርዕስ በግዕዝ ቋንቋ የተፃፈውን መጽሀፍ፣ የቤተ-ክርስቲያኗ ሊቃውንት ተቀብለው ምእመናኑን ስለ ቅዱስ ኤልያስ እና ትክክለኛይቱ ሰንበት እንዲያስተምሩበት አሳስቧል፡፡
ደብዳቤው ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር የተላከው ኢትዮጵያና እስራኤል በመንፈሣዊ አሰራር አንድ ስለሚሆኑበት ሁኔታ ለማመልከት ነው ያሉት የማህበሩ አመራሮች፤ለተባበሩት መንግሥታት የተላከውም መልእክቱ ለዓለም ሁሉ እንዲዳረስ ስለሚፈለግ ነው ብለዋል፡፡
ከ2 ሺህ ዓመታት በፊት እንደተፃፈ የሚነገርለት መጽሐፉ፤ ስለ ቀዳሚት ሰንበት ምንነትና ዘለዓለማዊነት በግልፅ እንደሚያብራራ እንዲሁም የኢትዮጵያና የእስራኤልን አንድነትና ትንሳኤ ምስጢር ተንትኖ እንደሚያስረዳ ተጠቁሟል፡፡
ማህበሩ በላከው መልዕክት፣ ቅዱስ ኤልያስ ከብሄረ ህያዋን ይዞት የመጣውን መጽሀፍ፣ የቤተ-ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት እንዲመረምሩት፣ በተለያዩ ቋንቋዎች እንዲተረጎምና እንዲታተም፣ ምዕመናንም እንዲያነቡት የማድረግ ግዴታ ፓትርያርኩ እንዳለባቸው ያሳስባል፡፡ “ይህ ሳይሆን በእንቢተኝነትና በቸልታ ለዘመናት በተስፋ የተጠበቀውን ይህን መጽሀፍ እንዳይቀርብ ቢያደርጉ፣ ከብሄረ ህያዋን የመጣው ቀናኢ ነቢይ ዓለምን ሁሉ እየገሰፀ ባለበት ኃያል፣ ስልጣኑ ፅኑ ፈራጅነቱና ቁጣው የሚፈርድ መሆኑን አረጋግጠን እንነግርዎታለን” ብሏል፡፡ “ለቤተ-ክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ እና ካህናት ጥፋትና የመጨረሻው ውድቀት ነው” ሲልም ለመፅሃፉ ትኩረት እንዲሰጥ ማህበሩ  አበክሮ አሳስቧል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ የፓትርያርኩን ጽ/ቤት እና የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጽ/ቤት በስልክ አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

Wednesday, March 12, 2014

የደብረ ምጥማቅ ሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የሰንበቴ ማኅበራት ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተወከለውን ኦዲተር የኦዲት መርኃ ግብር በመቃወም ህገወጥ ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ

በአዲስ አበባ የደብረ ምጥማቅ ሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የሰንበቴ ማኅበራት ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተወከለውን ኦዲተር የኦዲት መርኃ ግብር በመቃወም ህገወጥ ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ፡፡ በተለያየ መጥፎ ሥነ ምግባርና ድርጊት ከካቴድራሉ ሰንበት ትምህርት ቤት የተባረሩ ሁለት አባላትን ይዘው በካቴድራሉ ሁለተኛ ሰንበት ትምህርት ቤት ለማቋቋም ከጉርድ ሾላ እና አካባቢ የሰበሰቧቸው ወጣቶች ስለ ሰንበት ትምህርት ቤት አመሰራረት ግንዛቤ የሌላቸው በመሆናቸው የአዲሱ ሰንበት ትምህርት ቤት ምስረታ አልተሳካም፡፡  ቀደም ሲል የሰንበቴ ማኅበራቱ ከሀገረ ስብከቱም ሆነ ከካቴድራሉ አስተዳደር እውቅና ውጪ የሚሸጡትንና በወር እስከ 300.000.00 (ሦስት መቶ ሺህ ብር) ገቢ የሚያገኙበት የቀብር ፉካ ሽያጭ እና የአዳራሽ ኪራይ ንግድ ወይ ለቤተክህነቱ ፈሰስ እንዲያደርጉ አልያም ንግድ ፈቃድ አውጥተው ለመንግሥት ግብር እንዲከፍሉ በሀገረ ስብከቱ የቀረበውን ሐሳብ አልተቀበሉትም፡፡ እናም በመስከረም ወር 2006 ዓ.ም ከጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ፤ የቅዱ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በተገኙበት ተመርጦ ሥራ የጀመረውን ሰበካ ጉባዔ አይመራንም፤ እነርሱ ባቀረቡት ጥቆማ መነሻነት ከመንግሥት እና ከገለልተኛ አካላት የተዋቀረው የኦዲት  ኮሚቴ እኛን (የሰንበቴ ማኅበራቱን እና እንደ አቶ ወልዴ የሺጥላ አይነት በሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ ገንዘብ ጉድለት የተገኘባቸውንና በቤተክርስቲያኑ ግቢ በቤተልሔሙ ጎን 26 ፉካ በመስራት መናፍቅ ልጆቻቸውን ወራሽ በማድረግ ሕገ ወጥ ሰነድ ያዘጋጁትን) ኦዲት ሊያደርጉ አይገባም በሚል ነጻና ገለልተኛ ቤተክርስቲያን እንመሰርታለን የሚል ፖስተር በመያዝ  እሑድ የካቲት 2 ቀን ጠዋት በቅዳሴ ሰዓት የቅዳሴ ሥነ ሥርዓቱን ለማስተጓጎል ሞክረዋል፡፡
በዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የሴት ሰባኪ የሆነችውና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሕጋዊ ባሏን ጥላ   ወልዴ የሺጥላ የተባለውን የቀድሞ የህንጻ ኮሚቴ ሊቀ መንበር የወሸመችው እራሷን የዘመኑ የወንጌል አብሳሪ በመንፈስ ቅዱስ የተቀባሁ ጳውሎሳዊት ነኝ በማለት ጸሎተ ፍትሐት አያስፈልግም እኔ በፍትሀቱ ፋንታ ጸሎት አድጋለሁ አስተምራለሁ በማለት ምንፍቅና የምታስፋፋው  ቅድስት አሳልፍ ወደ ቤተክርስቲያኑ ድንጋይ እንዲወረውሩ ተሰብሳቢዎቹን ስታግባባ ነበር፡፡
ከካቴድራሉ ሰንበት ትምህርት ቤት ሴት አባላትን በመተናኮልና ወሲባዊ ጥቃት በማድረስ በሕግ ተከሶ የተቀጣውና ከሰንበት ትምህርት ቤት በዚህ ቅሌት የተባረረው ሰለሞን አጥሌ የተባለው የታክሲ ሾፌርና የሰንበት ትምህርት ቤቱን ገንዘብ በተለያየ ወቅት በመውሰድ በሌብነት ወንጀል ተከሶ ከሰንበት ትምህርት ቤት የተባረረውና ዲቃላ ልጁን ደብቆ ሁለተኛ ሚስት በተክሊል ያገባው የሰለሞን አጥሌ ወያላ የሆነው ሲሳይ አፈወርቅ የተባሉት ሁለት ግለሰቦች መናፍቃንን በማሰባሰብ ሁለተኛ ሰንበት ትምህርት ቤት ለማቋቋም ያደረጉት እንቅስቃሴ አልተሳካላቸውም፡፡
ከዚህ ቀደም በዋነኛነት የሰንበቴ ማኅበራቱንና በመንግሥት ላይ ያኮረፉትን እንደነ ታዋቂውና ጨካኙ የደርግ የምስራቅ  ጎጃም ክፍለ ሀገር አስተዳዳሪና የደርጉ አባል አንሙት ክንዴን አይነት ሰዎችን በማሰባሰብ የደርግ ሥርዓተ ማኅበርን በቤተክርስቲያን ለመመስረት የሚታገለው የደርግ የስለላ ሹም የመቶ አለቃ አባቡ ታከለው በአጣዳፊ ህመም ከሰልፉ ላይ ወጥቶ ወደ ሆስፒታል የተወሰደ ሲሆን ህመሙ ጊዜ የማይሰጥ በመሆኑ እለቱን ኦፕራሲዎን መደረጉንና እስካሁን ከሰመመን እንዳልነቃ ታውቋል፡፡
የካቴድራሉ አስተዳደር በሰንበቴ ማኅበር ስም ተደራጅተው የሚነግዱትን አንዳንድ የደርግ ጡረተኞችና የሰንበቴ አላማ ጠላ ማንቃረርና ቆሎ ማሸርደም የሚመስላቸው ሥራ ፈት አባወራዎችንና የሚገስጻቸው ያጡ ባሎቻቸው የዘነጓዋቸውን እንደነ ቅድስት አይነት መናፍቃንን በቅጡ በመቃወሙና በፍርድ ቤት በተወሰነ ቤተክርስቲያኒቱ  ባወጣችው ሕግ ሕገወጥ ንግድ እና የቦታ ወረራ በመቃወሙ በመረጃ ባልተረጋገጠ ሙስና እና ስም ማጥፋት ሆ ብለን በመጮህ  ከሰን እናስወግዳለን ከሚመጣውም ጋር በመደራደር የፉካ ንግዳችንን እንቀጥላለን በማለት  ለሀገረ ስብከቱ ቅሬታቸውን በሕጋዊ ሽፋን ቢያቀርቡም ሀገረ ስብከቱ በቦታው ያለውን ችግር በዘላቂ ሁኔታ ለመፍታት ከመንግሥትና ከገለልተኛ አካላት  የተመደበው አጣሪ ግን በተጨባጭ በደረሰው መረጃ  እና በተለያዩ ጊዜያት በሰንበቴ ማኅበራቱ በቤተክርስቲኗ የድንጋይ  መአድን ሽያጭ  ባገኙት ገንዘብ በገዟቸው የቢራ አክስዮኖች ባለቤትነት ጉዳይ እንዲሁም እነ ወልዴ የሺጥላ የህንጻ ኮሚቴ ሊቀመንበር መሆናቸውን ሽፋን በማድረግ በሌሎች አብበያተክርስቲያናት ባልተለመደ መልኩ በቤተክርስቲያኗ ግቢ መኖሪያ ቤት በመገንባት እና ለግላቸው 26 ፉካ በመገንባት ለፈጸሙት ምዝበራ ከ1994 ዓ.ም ጀምሮ ኦዲት ለማድረግ በማሰብ ያዘጋጀውን የጊዜ አጠቃቀም መመሪያ በመቃወም ሰልፉን አደራጅተዋል፡፡
 ቁጥራቸው 60 የሚደርሱት እነዚሁ ሰልፈኞች ከያዟቸው መፈክሮች መካከል መንግሥትን የሚተቹ እና አመጹን በማስፋፋት ልክ በእስልምና እምነት በመስኪዶች አካባቢ እንዳለው አይነት ውጥረት ለመፍጠር ቢያስቡም ፖሊስ ደርሶ ሰልፉ እንዲበተን አድርጓል፡፡ በቅርቡ ከአሜሪካ የመጣውና የደህንነት አባል ነኝ በማለት አመጹን የሚያስተባብረው አለማየሁ ከልል  ክሰ ቢመጣ አዘጋላችኋለሁ በማለት ቃል እንደገባላቸው የሰንበቴ ማኅበራቱ አመራሮች አስታውቀዋል፡፡ በዚህ ድርጊት ውስጥ የተሳተፉት ዋናዎቹ ግለሰቦች የተለያየ ችግር ያለባቸው ሲሆኑ አንዳንዶቹ በአጫሽነት ፤ ሰካራምነት ፤ በቃሚነት የሚታወቁ እና በአካባቢ ማኅበረሰብ የእንጨት ሽበት ተብለው የተናቁ ሽማግሌዎች ናቸው፡፡ ይህን አጋጣሚ እንደ መልካም የቆጠሩት አንዳድ ፖለቲካ ኃይሎች ሰልፉን ለማጠናከርና ወደ ውጪ በመውጣት ህዝብን ቀልብ ለመሳብ ቢያስቡም ፖሊስ ግን ይህንን ሊፈቅድ አልቻለም፡፡ ከትግራይ የተመረጠ ፓትርያርክ ቤተክርስቲያኗን ሊመራ አይችልም መንግሥት እጁን ከቤተክርስቲያናችን ላይ ያንሳ ትግሬ ተወላጅ ሰራተኞች ይውጡ በማለት በዋናነት መፈክር ሲያሰሙ የዋሉት አንሙት ክንዴ፤ አስማረ ዋሴ ፤ ባዬ ባዘዘው፤ወልሴ የሺጥላ፤ አበበ ደስታ ፤ መልአከ ኃይሌ ፤ ታደሰ  ፤ ቅድስት አሳልፍ፤ ደሳለኝ ፋንታቢል፤ ወልደኢየሱስ በሻህ ፤ሙሉ በለጠ ሲሆኑ ከወጣቶቹ ደግሞ ሴሰኛው ታክሲ ሾፌር  ሰለሞን አጥሌ እና ሌባው ሲሳይ አፈወርቅ ሲሆኑ እነዚህ የግል ጥቅም ያሳወራቸውና እምነትና ፖለቲካ የተቀላቀለባቸው ግለሰቦች በፖሊስ ክስ እንደተመሰረተባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
በሰአሊተ ምህረት ያለው የሰንበቴ አካሄድ ገና ከጅምሩ በ34ኛው አጠቃላይ መንፈሳዊ ሰበበካ ጉባዔ ታላቅ ተቃውሞ የገጠምውና ሲኖዶሱ እልባት እንዲሰጠው በተሰብሳቢዎቹ አቋም የተያዘበትቤተክርስቲያን የምትመዘበርበት መንገድ ነው፡፡ የሰንበቴ ማኅበራቱ ወደ እድርነትና እክስዮን ማኅበርነት በመለወጣቸው እና ከቀብር ፉካና ከአዳራሽ ኪራይ ያገኙትን ገቢ የቢራ አክስዮኖችን በመግዛት ከመንፈሳዊ ተግባት ውጪ የሚያውሉት ሲሆን ለረፈደበት የፖለቲካ ዓላማ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያንቀሳቅሱ ማወቅ ተችሏል፡፡ የዚህ ድርጊት ዋነኛ መሪ ወልዴ የሺጥላ በኢትዮ ቴሌኮም ሲሰራ በጽዳት ሰራተኞች ላይ በፈጸመው የወሲብ ትንኮሳ በአስተዳደር ተከሶ ከቅርንጫፍሥ አስኪጅነት ወደ ሽያጭ ሰራተኛነት የወረደ ግለሰብ መሆኑ ስለርሱ የሚያውቁት ሁሉ ይመሰክራሉ፡፡
በካቴድራሉ ጉብኝት ያደረጉት ቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁአን ሊቃነጳጳሳት በሰንበቴ ማኅበራ የተወረረውንና ለብዝኃኑ ጥቅም መስጠት ያለበትን ቦታ እና ግንባታ ተመልክተው ማዘናቸው ታውቋል፡፡ የደብረ ምጥማቅ ሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል ሰፊ የልማት ቦታና በሰንበቴ የተወረረ የቀብር ስፍራ እንዲሁም በሰንበቴ ማኅበራ ቁጥጥር ሥር የሆነ በብዙ ሚሊዮን ብር የሚገመት የድንጋይ ማእድን ሐብት እና ከ100.000 በላይ አማንያን ያሉበት ሲሆን በሰንበቴ የጥቅም ሰንሰለት የተደራጁ ከ60 የማይበልጡ ግለሰቦች ምክንያት ሰላሙን አጥቶ የቆየ ደብር ነው፡፡

Monday, March 10, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የፓትርያርኩን እጅ የመጠምዘዝ፤ እምቢ ካሉም የማስወገድ ትግሉን አጠናክሮ ቀጥሏል!! (ከማን ጋር ሊሰሩ ነው? » አባ ኤልሳዕ


የአሀዳዊ መዋቅር ምንጭ በሆነው ሲኖዶስ የምትተዳደር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን ምኗ ነው? 
በአንድ ወቅት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ «በመንግሥት ሌቦች እጃችን ታስሯል» ማለታቸው አይዘነጋም። ከትንሹ በቀቀን ካድሬ አንስቶ እስከ ትልቁ ዓሳ ነባሪ/አንበሪ/ ሹመኛ ድረስ የመዋጥ፤ የመሰልቀጥ ተግባሩን ተመልክተው «የመንግሥት ሌባ እጃችንን አስሯል» ማለታቸው ይህንን ሁሉ በአንዴ ለማስቆም አለመቻላቸውን መግለጻቸው ብቻ ሳይሆን ከስፋቱ አንጻር ለማስቆም መሞከር ውጤቱ አደገኛ ሊሆን መቻሉን ለማመልከት« እጃችን ታስሯል» በማለት የችግሩን ስር መስደድ በአጭር ዐረፍተ ነገር ለመግለጽ ሞክረዋል። እዚያ አደገኛ ደረጃ ላይ የተደረሰው ግን በአንድ ጀምበር ሳይሆን ቀስ በቀስ አንዱ አንዱን እየዋጠና እየፋፋ እንደመሆኑ መጠን እጅ ከመታሰሩ በፊት አስቀድሞ ትንሽ በትንሹ እርምጃ ቢወሰድ ኖሮ አስጊነቱ ያን ያህል ባላሳሰበ ነበር።  ስርቆት ምንጊዜም ከክፉ ሰዎች ልቡና በሚመነጭ ሃሳብ የሚፈጸም ተግባር ነው። ክፉ ሰዎች ደግሞ ሰውን ከመግደል ወደኋላ አይመለሱም። እግዚአብሔርን ማወቅ ከሰዎች ኅሊና ውስጥ ሲጠፋ ጭካኔ ይስፋፋል። እርግማን፤ ግዳይ፣ ስርቆት፤ ደም ማፍሰስ ይበዛል።
በአንድ ወቅት የእስራኤል ልጆች ኃጢአት በመብዛቱና የካህናቱ ርኩሰት መጠን ከማጣቱ የተነሳ እግዚአብሔር አዝኖ የሥራቸውን ዋጋ ይቀበሉ ዘንድ ጥፋት እንደተዘጋጀባቸው መጽሐፍ ቅዱሳችን ይነግረናል።( ሆሴዕ ምዕ 4 እና 5) ሌብነትን መዋጋት ህግን እንደማስከበር ብቻ ሳይሆን መታየት ያለበት ደም ለማፍሰስ የማይመለሱ ሰዎችን ከኅብረተሰቡ ውስጥ እንደማውጣት ይቆጠራል።
እንደዚሁ ሁሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አጥቢያው አገልጋይ ካህን ድረስ እጃቸውን ወደኋላ አስሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም እየነገደ የፈረጠመውና በመዋቅሩ የዓሳ ነባሪ ያህል የገዘፈው ማኅበረ ቅዱሳን መሠረታዊ ጥቅሙን ለማስከበር ሲል ብቻ ከዚህ በፊት ለፓትርያርኩ ይሰጥ የነበረውን የምስጋና ካባ አውልቆ እጃቸውን ወደመጠምዘዝ ተግባር መሸጋገሩን እየተመለከትን እንገኛለን። የዚህ ሁሉ ዋናው ምክንያት በጥቅሙ መስመር ላይ የሚቆም ማንም ሰው የጥቅሙ ጠላት በመሆኑ አስቀድሞ እጁን በመጠምዘዝ ወደቀድሞ አስተሳሰቡ ለመመለስ በየትኛውም መልኩ መታገል፤ ካልተቻለ ደግሞ ከቆመበት የጥቅሙ መስመር ላይ ማጥፋትና ማስወገድ የጥቅመኛ መዳረሻ ግቡ ነው። ምን ጊዜም በማግበስበስ የበለጸጉ ሰዎች ጥቅማቸውን የማያስጠብቀውን አመራር ለማስወገድ እረፍት የሌላቸው መሆኑ ታሪክ ያስተምረናል። ሰሞኑን  የማኅበረ ቅዱሳንና የተባባሪ ጳጳሳቱ ጩኸት አቶ መለስ እንዳሉት የፓትርያርኩን እጅ የመጠምዘዝና ወደኋላ በማሰር ወደቀድሞ የማኅበሩን ጥቅም የማስከበር መስመር የመመለስ ትግል ተጠናክሮ መቀጠሉን እያየን ሲሆን ችግሩ በዚህ የማይፈታ ከሆነና ከቀጠለ ፓትርያርኩን የማስወገድ እርምጃ እንደሚከተል ሳይታለም የተፈታ ነው። እንዴት ይፈጸማል? የሚለውን ወደፊት የምናየው ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ግን ክፉ ሰዎች / ክፉ መሪዎች/ ክፉ ሀገራት/ ወዘተ ምን ጊዜም የማይስማማቸውን ከመግደል እንደማይመለሱ በእርግጠኝነት ልንናገር እንችላለን።
«ክፉ ካላደረጉ አይተኙምና፤ ካላሰናከሉም እንቅልፋቸው ይወገዳልና» ምሳሌ 4፤16
በዚሁ አጋጣሚ የምናሳስበው ነገር እውነተኛን የሚጠብቅ እግዚአብሔር እንደማያንቀላፋ ቢታወቅም  በተሰጠን ልቡና ራሳቸንን እንዳንጠብቅ የሚያዘናጋን ባለመሆኑ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በሚበሉት፤ በሚጠጡትና በሚለብሱት ሁሉ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸው ማስገንዘብ እንወዳለን።  እውነት ነው! «ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ» ማቴ 10፤28 በማለት እንደተናገረው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብቻ በሕይወታችን በማስቀደም ማገልገል እንደሚገባ እንጂ የሚያሳስበን በስጋ መሞት እንደማያስፈራን ይታወቃል።
ፓትርያርክ ማትያስ ከማኅበረ ቅዱሳን እስራት ነጻ ሰው መሆናቸውን መግለጽ በጀመሩ ማግስት፤ እስራታቸውን አምነው እንዲቀበሉ የማኅበሩ እስረኝነታቸውን ያረጋገጡ ጳጳሳት ቢቻል በምክር ሽፋን እጃቸውን እንዲሰጡ አለሳልሰው በማባበል፤ ፓትርያርኩ የአቋም ሰው በመሆን ከቀጠሉ ግፋ ሲል ደግሞ ወደፊት በማስፈራራት፤ አድማ በመምታትና በስመ ድምጽ ብልጫ የፓትርያርክነቱን ሥልጣን በመቀማት እግር ተወርች የማሰሩ ዘመቻ በእርግጥ ይቀጥላል። አባ ጳውሎስንም እንዲሁ ነበር ያዋከቡት።
ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ እንጂ የማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ የመሆን ግዴታና ውል የለባቸውም። እኛም እንደተለመደው የምንጠይቀው ነገር ቢኖር አንድና አንድ ብቻ ነው።
የአሀዳዊ መዋቅር ምንጭ በሆነው ሲኖዶስ የምትተዳደር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን ምኗ ነው? የሲኖዶስ አባላት ጳጳሳቱ የሚያገለግሉት ለማኅበረ ቅዱሳን ወይስ ለቤተ ክርስቲያን?