Monday, March 10, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የፓትርያርኩን እጅ የመጠምዘዝ፤ እምቢ ካሉም የማስወገድ ትግሉን አጠናክሮ ቀጥሏል!! (ከማን ጋር ሊሰሩ ነው? » አባ ኤልሳዕ


የአሀዳዊ መዋቅር ምንጭ በሆነው ሲኖዶስ የምትተዳደር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን ምኗ ነው? 
በአንድ ወቅት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ «በመንግሥት ሌቦች እጃችን ታስሯል» ማለታቸው አይዘነጋም። ከትንሹ በቀቀን ካድሬ አንስቶ እስከ ትልቁ ዓሳ ነባሪ/አንበሪ/ ሹመኛ ድረስ የመዋጥ፤ የመሰልቀጥ ተግባሩን ተመልክተው «የመንግሥት ሌባ እጃችንን አስሯል» ማለታቸው ይህንን ሁሉ በአንዴ ለማስቆም አለመቻላቸውን መግለጻቸው ብቻ ሳይሆን ከስፋቱ አንጻር ለማስቆም መሞከር ውጤቱ አደገኛ ሊሆን መቻሉን ለማመልከት« እጃችን ታስሯል» በማለት የችግሩን ስር መስደድ በአጭር ዐረፍተ ነገር ለመግለጽ ሞክረዋል። እዚያ አደገኛ ደረጃ ላይ የተደረሰው ግን በአንድ ጀምበር ሳይሆን ቀስ በቀስ አንዱ አንዱን እየዋጠና እየፋፋ እንደመሆኑ መጠን እጅ ከመታሰሩ በፊት አስቀድሞ ትንሽ በትንሹ እርምጃ ቢወሰድ ኖሮ አስጊነቱ ያን ያህል ባላሳሰበ ነበር።  ስርቆት ምንጊዜም ከክፉ ሰዎች ልቡና በሚመነጭ ሃሳብ የሚፈጸም ተግባር ነው። ክፉ ሰዎች ደግሞ ሰውን ከመግደል ወደኋላ አይመለሱም። እግዚአብሔርን ማወቅ ከሰዎች ኅሊና ውስጥ ሲጠፋ ጭካኔ ይስፋፋል። እርግማን፤ ግዳይ፣ ስርቆት፤ ደም ማፍሰስ ይበዛል።
በአንድ ወቅት የእስራኤል ልጆች ኃጢአት በመብዛቱና የካህናቱ ርኩሰት መጠን ከማጣቱ የተነሳ እግዚአብሔር አዝኖ የሥራቸውን ዋጋ ይቀበሉ ዘንድ ጥፋት እንደተዘጋጀባቸው መጽሐፍ ቅዱሳችን ይነግረናል።( ሆሴዕ ምዕ 4 እና 5) ሌብነትን መዋጋት ህግን እንደማስከበር ብቻ ሳይሆን መታየት ያለበት ደም ለማፍሰስ የማይመለሱ ሰዎችን ከኅብረተሰቡ ውስጥ እንደማውጣት ይቆጠራል።
እንደዚሁ ሁሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አጥቢያው አገልጋይ ካህን ድረስ እጃቸውን ወደኋላ አስሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም እየነገደ የፈረጠመውና በመዋቅሩ የዓሳ ነባሪ ያህል የገዘፈው ማኅበረ ቅዱሳን መሠረታዊ ጥቅሙን ለማስከበር ሲል ብቻ ከዚህ በፊት ለፓትርያርኩ ይሰጥ የነበረውን የምስጋና ካባ አውልቆ እጃቸውን ወደመጠምዘዝ ተግባር መሸጋገሩን እየተመለከትን እንገኛለን። የዚህ ሁሉ ዋናው ምክንያት በጥቅሙ መስመር ላይ የሚቆም ማንም ሰው የጥቅሙ ጠላት በመሆኑ አስቀድሞ እጁን በመጠምዘዝ ወደቀድሞ አስተሳሰቡ ለመመለስ በየትኛውም መልኩ መታገል፤ ካልተቻለ ደግሞ ከቆመበት የጥቅሙ መስመር ላይ ማጥፋትና ማስወገድ የጥቅመኛ መዳረሻ ግቡ ነው። ምን ጊዜም በማግበስበስ የበለጸጉ ሰዎች ጥቅማቸውን የማያስጠብቀውን አመራር ለማስወገድ እረፍት የሌላቸው መሆኑ ታሪክ ያስተምረናል። ሰሞኑን  የማኅበረ ቅዱሳንና የተባባሪ ጳጳሳቱ ጩኸት አቶ መለስ እንዳሉት የፓትርያርኩን እጅ የመጠምዘዝና ወደኋላ በማሰር ወደቀድሞ የማኅበሩን ጥቅም የማስከበር መስመር የመመለስ ትግል ተጠናክሮ መቀጠሉን እያየን ሲሆን ችግሩ በዚህ የማይፈታ ከሆነና ከቀጠለ ፓትርያርኩን የማስወገድ እርምጃ እንደሚከተል ሳይታለም የተፈታ ነው። እንዴት ይፈጸማል? የሚለውን ወደፊት የምናየው ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ግን ክፉ ሰዎች / ክፉ መሪዎች/ ክፉ ሀገራት/ ወዘተ ምን ጊዜም የማይስማማቸውን ከመግደል እንደማይመለሱ በእርግጠኝነት ልንናገር እንችላለን።
«ክፉ ካላደረጉ አይተኙምና፤ ካላሰናከሉም እንቅልፋቸው ይወገዳልና» ምሳሌ 4፤16
በዚሁ አጋጣሚ የምናሳስበው ነገር እውነተኛን የሚጠብቅ እግዚአብሔር እንደማያንቀላፋ ቢታወቅም  በተሰጠን ልቡና ራሳቸንን እንዳንጠብቅ የሚያዘናጋን ባለመሆኑ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በሚበሉት፤ በሚጠጡትና በሚለብሱት ሁሉ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸው ማስገንዘብ እንወዳለን።  እውነት ነው! «ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ» ማቴ 10፤28 በማለት እንደተናገረው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብቻ በሕይወታችን በማስቀደም ማገልገል እንደሚገባ እንጂ የሚያሳስበን በስጋ መሞት እንደማያስፈራን ይታወቃል።
ፓትርያርክ ማትያስ ከማኅበረ ቅዱሳን እስራት ነጻ ሰው መሆናቸውን መግለጽ በጀመሩ ማግስት፤ እስራታቸውን አምነው እንዲቀበሉ የማኅበሩ እስረኝነታቸውን ያረጋገጡ ጳጳሳት ቢቻል በምክር ሽፋን እጃቸውን እንዲሰጡ አለሳልሰው በማባበል፤ ፓትርያርኩ የአቋም ሰው በመሆን ከቀጠሉ ግፋ ሲል ደግሞ ወደፊት በማስፈራራት፤ አድማ በመምታትና በስመ ድምጽ ብልጫ የፓትርያርክነቱን ሥልጣን በመቀማት እግር ተወርች የማሰሩ ዘመቻ በእርግጥ ይቀጥላል። አባ ጳውሎስንም እንዲሁ ነበር ያዋከቡት።
ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ እንጂ የማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ የመሆን ግዴታና ውል የለባቸውም። እኛም እንደተለመደው የምንጠይቀው ነገር ቢኖር አንድና አንድ ብቻ ነው።
የአሀዳዊ መዋቅር ምንጭ በሆነው ሲኖዶስ የምትተዳደር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን ምኗ ነው? የሲኖዶስ አባላት ጳጳሳቱ የሚያገለግሉት ለማኅበረ ቅዱሳን ወይስ ለቤተ ክርስቲያን?