Monday, February 18, 2013

ኢትዮጵያን የእስልምና ሀገር ለማድረግ ከሃሳብ ያለፈ እንቅስቃሴ አለ!

( ክፍል ሁለት )

አንዳንድ ግለሰቦችና ማኅበራት ማለትም ማኅበረ ቅዱሳንና አፈቀላጤው ዳንኤል ክብረትን  ጨምሮ ባለፉት ጊዜያት በኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው የእስልምና አክራሪ እንቅስቃሴ የምስል፤የጽሁፍና  የድምጽ መረጃ ለማቅረብ ሞክረው ነበር። እነዚህ ክፍሎች የቆሙበትን ዓላማ ወደጎን ትተን በወቅቱ ስለአክራሪ እንቅስቃሴ  የአስጊነት ደረጃ መናገራቸውንም ደግፈነዋል። ቤተክህነቱ ዝምታን በመምረጡና መንግሥትም ለማዳመጥ ባለመፈለጉ በሎሌችም ወገኖች ጭምር ሲነገር የቆየው ችግር ዛሬ ላይ ለያዥ ያስቸገረ እስከመሆን ባልደረሰም ነበር።

  መንግሥት አብዛኛውን ጊዜ እሱን የሚጠቅም መስሎ እስከታየው ድረስ  ሊያስከትሉ የሚችሉ ጉዳቶችን ከኢምንት ይቆጥራቸዋል ወይም ይንቃቸዋል።  የማንም ስስ ስሜት ተጎዳ አልተጎዳ፤  የራሱ ጉዳይ  እስከማይመስለው ድረስ የሚሰሙ ድምጾችን ወደጎን ትቶ ረጅም መንገድ  በመሄድ  ዓላማውን ሲተገብር  የሌሎች መንጫጫት ግድ የሚሰጠው  አይደለም።  በዚህ የተነሳ ጠቃሚ የልማት እንቅስቃሴዎች ሳይቀሩ እንደጉዳት የሚታዩበትን አጋጣሚ እየፈጠሩ ይገኛሉ።

  ኢትዮጵያ ውስጥ የእስልምና አክራሪ እንቅስቃሴ ስለመኖሩ ሲነገር የቆየው ረጅም ጊዜ አስቆጥሯል። ችግሮች ገዝፈው የስጋት ደረጃቸው ከማደጉ በፊት አስፈላጊውን እርምት በወቅቱ መውሰድ ሲገባው አሁን ተበጠበጥኩኝ ብሎ ዛሬ ላይ ተነስቶ «ሐረካት» በሚል ድምጽ እሱም በተራው ቢጮህ  ማን ይስማው?  ለዓመታት በአክራሪዎች ጉዳት ያለቀሱ ወገኖችን እምባ ማበስ አቅቶት  ዛሬ ምን አገኘ? የሚሉ ጥያቄዎች የሚሰሙት ለዚህ ይመስለናል። በአጭሩ በወቅቱ የእኛ የተጎጂዎችን  ድምጽ ለመስማት ባለመፈለግህ አሁን በተራችን ያንተን ድምጽ አንሰማም ነው እየተባለ ያለው። ችግሩ አክራሪዎች የሉም ማለት ሳይሆን በአክራሪዎች ላይ መወሰድ የነበረበት የእርምት እርምጃ ዘግይቷል ነው የሚሰማው ድምጽ።  ይህንን የጊዜ መተላለፍን አጋጣሚ ደግሞ የፖለቲካ ነጋዴዎች ይጠቀሙበታል። አክራሪ፤ ተጎጂ፤ መንግሥትና ፖለቲካ በየራሳቸው መንገድ ሄደዋል።

ሌላው ችግር ልማት የሚባለው ነገር ነው። በመሠረቱ ልማት ለአንድ ሀገር እድገት ወሳኝ ነው። ለድህነታችንም  ዋናው ምክንያት ልማት አለመኖሩ ነው። ይህንን ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ቢሰራ የሚጠላ የለም።  በእርግጥ መንግሥትን የሚጠሉ አካሎች ልማቱን በአሉታዊ ጎኑ በመፍታት ለትርፍ አይሰሩበትም አይባልም። መንግሥት አሉታዊ ጎኖችን ለመቀነስ የልማቱን ሃሳብ በሕዝብ ልብ ውስጥ ከማስቀመጡ በፊት በራሱ ጉልበት ለመወጣት ይፈልጋል። ከዚህ ውስጥ የዛሬማ ወንዝ የስኳር ልማት ተጠቃሽ ነው። ከዋልድባ ገዳም ጋር የሚዋሰነውን የስኳር ልማት ለማስፋፋት መንግሥት አስቀድሞ ወደሕዝብ ማወያየት መግባት ያልፈለገው ፤ አወያይቶ የሚመጣውን  የእምቢታና የተቃውሞ ድምጽ ከማስተናገድ ይልቅ ሥራውን ጀምሮ የሚመጣውን ተቃውሞ ማቃለል ይሻላል ከሚል እሳቤ የተነሳ ይመስለኛል።  ይህ  የልማት ስልት ከእስልምናው የሰለፊ እንቅስቃሴ ጋር በተመሳሳይ ጊዜ በመደረጉ ዋልድባ ተነካብን ከሚሉ ሰልፈኞች ጋር በአንድ ጎራ የማይስማሙትን እንዲስማሙ እድል ከፍቷል። ጳጳሳት ነን የሚሉቱ ሳይቀር «አላህ አክባር» የሚል አዛን እስከማሰማት የደረሱት የፍቅር መጠናቸው ዛሬ ድንገት ስለጨመረ ሳይሆን መንግሥት ሁለቱንም  ወገኖች ምን ያመጣሉ? በሚል ስንጥር  በአንድ ወቅት ስለወጋቸው ብቻ ነው። ይህ ደግሞ ለፖለቲካ ነጋዴዎች ጥሩ የትርፍ ጊዜ ነው። ንግድ ደግሞ አዋጭ ቦታና ሰዓት ይጠብቃል። እውነት ለመናገር በዚህ የተነሳ «ጂሐዳዊ ሐረካት» የተባለው ፊልም ከቀልድ ጫወታነቱ ያለፈ አልሆነም።  

Sunday, February 17, 2013

የኢትዮጵያ ሲኖዶስ ያለው የት ነው?



የ6ኛው ፓትርያርክ ምርጫ እርግጥ መሆኑ ከተነገረበት በፊት አንስቶ ብዙ ተወርቷል፣ ብዙም ተብሏል። ግማሹ ከምርጫው ይልቅ እርቁ ይቅደም ይል ነበር። ገሚሱም በተለይ ከሀገር ቤት እርቅ ማለት አንድ ማኅበር፤ አንድ መንጋ ማለት እንጂ ያረጀ ስልጣን ማደስ አይደለም ማለቱም አይዘነጋም። ከምርጫው ይልቅ እርቁ ይቅደም ከሚለው ወገን የሚመጣው ሃሳብ አብዛኛው በቅንነትና ለቤተክርስቲያን አንድነት ከማሰብ ልባዊ ስሜት እንደሆነ ይገመታል። አንዳንዱም እርቅ የሚለው ነገር ከግቡ እንደማይደርስ እያወቀ ወይም ስውር ዓላማውን ከኋላው አድርጎ ሐቀኛ መስሎ ለመታየት የሚያደርገው ጫወታም እንደሆነ ካለፉት እንቅስቃሴዎች ተነስቶ ግምት ማስቀመጥ ይቻላል። በዚህም ይሁን በዚያ እርቅ የተባለውን ነገር ገቢር ለማድረግ ከስሜትና ከቅናት በፊት ግንዛቤ ውስጥ ሊገቡ የሚገባቸው ብዙ ሥረ ነገሮች መኖራቸውን አለመረዳት ቅን ሃሳቦች ሁሉ ትክክለኞች ቢሆኑ እንኳን  አፈጻጸማቸውን አርቆ መመልከት አለመቻል በራሱ ችግር ነው። እንደምንሰማው የውጪው ሲኖዶስ መፈንቅለ ፓትርያርክ ያደረገው ወያኔ ነው እያለ ወያኔ በሚመራው ሀገር እንዴት ሆኖ ነው ተመልሶ ፓትርያርክ መሆን የሚችለው ለሚለው ግዙፍ ጥያቄ ምላሽ የሚያሻው ይመስለኛል። የውጪው ሲኖዶስ መፈንቅለ ፓትርያርክ አድርጎብኛል ካለው መንግሥት ጋር የእርቅ ድርድር ያደርጋል ወይስ መንግሥት ጥፋቱን አምኖ እንዲመለሱ በመፍቀድ ዋስትና ይሰጣል? ብለንም ተጨማሪ ጥያቄ ለማቅረብ እንገደዳለን።
    የአቡነ ጳውሎስ ኅልፈት ብቻውን ፈነቀለኝ ባሉት መንግሥት ሀገር ለመመለስ የሚያስችል አዲስ ግኝት ነው ወይ? እርቅ ለም? ከማን ጋር? እንዴት? ለሚሉት ጥያቄዎች ምላሽ ሳያገኝ እየተጠራሩ መነጋገር ብቻውን መፍትሄ እንደማይሆንና ከሚጠየቁት ነጥቦች አንጻር መሳካት አለመቻሉን አስቀድመን በመገመት  በዚህ ዙሪያ ጽፈንበት ነበር። ወደፊትም የውጪ ሲኖዶስ ሳይሆን  የውጪ ጳጳሳት ተብሎ ወደሀገር ቤት ተመልሶ ባለው አንድ ሲኖዶስ ስር ከሚኖሩ በስተቀር እንደአቻ ሲኖዶስ የሚደረግ ድርድር ሊኖር እንደማይችል ከመጻዒ አመለካከቶች አንጻር አስቀድሞ መተንበይ ይቻላል።  የሚነሳው እውነታ ሲኖዶስ ያለው የት ነው? የሚለው ጥያቄ ነው። እልህና ቁጣ በሚፈጥረው ስሜት እስካልተመራን ድረስ  የኢትዮጵያ ሲኖዶስ ያለው አዲስ አበባ ነው። ኢትዮጵያውያን አሜሪካ በመኖራቸው ብቻ አሜሪካ፤ ኢትዮጵያ ልትባል አትችልም።
     ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት አንባ ገነን ይሁን ዲሞክራሲያዊ ሀገሪቱ ከዓለም ካርታ ላይ እስካልጠፋች ድረስ የኢትዮጵያ መንግሥት ይባላል። ሲኖዶሱም መንግሥት ባለበት ሀገር የኢትዮጵያ ሲኖዶስ ይባላል። እውነታውን ለመቀበል ባንፈልገውም እንኳን አለመቀበላችን እውነታውን አይለውጠውም። አንዳንዶች ታሪክ እያጣቀሱ ስለስደት ሲኖዶስ ስነሞገት ለመግጠም ይዳዳሉ።
 ከ50 ሚሊዮን በላይ ኦርቶዶክሳዊ ምእመናንን የሚመራው ማነው? ብንል ምድር ላይ ያለው እውነታ የሚናገረው በሀገረ ኢትዮጵያ ውስጥ ሲኖዶስ መሆኑን ነው።

Friday, February 15, 2013

የፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴው ማምሻውን መግለጫ አወጣ




ኮሚቴው ከሳምንት በፊት በሰጠው ይፋዊ መግለጫ መሠረት ለፓትርያርክነት እጩ ሆነው የሚቀርቡትን አባቶች  ጥቆማ ከተለያየ አቅጣጫ እየቀረበለት መቆየቱን በማውሳት እግዚአብሔር ለቤተክርስቲያን የሚጠቅማትን መንፈሳዊ አባት እንዲሰጣት የጾምና የጸሎት ጊዜውን አጠናክረን መቀጠል ይገባናል በማለት ለመላው የቤተክርስቲያኒቱ ተከታዮች በመግለጫው ላይ በድጋሚ አበክሮ አሳስቧል።
በወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ዛሬ የካቲት 8/ 2005 / የእጩ ተጠቋሚዎች የመቀበያ ጊዜ ማብቃቱን በመግለጽ ከእንግዲህ የሚቀረው ሥራ  ሲኖዶሱ በሰጠው ደንብ ላይ ተመርኩዞ ከየካቲት 9 እስከ 14 2005 / ድረስ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ የሚቀርቡ 5 እጩዎችን መመልመል መሆኑን በመግለጫው ላይ አመልክቷል።
ይቀርባሉ ከተባለው ብዙ ተጠቋሚዎች መካከል ውስጥ እንዴትና በምን ስሌት መልምሎ 5ቱን እጩ ተጠቋሚዎች ብቻ እንደሚያቀርብ ኮሚቴው የዘረዘረው ነገር ባይኖርም መርጦ ለሲኖዶስ የማቅረብ ስልጣኑ የኮሚቴው መሆኑን ግን ሳይገልጽ አላለፈም።
የኮሚቴውን የምልምላ ስልት ያሟላሉ የተባሉ 5 እጩዎች ለቅዱስ ሲኖዶስ በማቅረብ ሲኖዶሱ ከየካቲት 16 ጀምሮ በሚያደርገው ጉባዔ ላይ የቀረቡለትን የእጩ ፓትርያርኮች  ዝርዝር  በይሁንታ በማጽደቅ፤ የካቲት 18/ 2005 / ለሕዝብ ይፋዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ይጠበቃል። ምርጫውም የካቲት 21 ቀን እንደሚደረግና በእለቱ ማምሻው ላይ የድምጽ ብልጫ ያገኘው አባት በይፋ ተገልጾ የካቲት 24/ 2005 / ሥርዓተ ሲመቱ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም  ከዚህ በፊት የተገለጸ መሆኑ ይታወሳል። ብዙ ጊዜ ሲባል እንደቆየው የመንግሥት ጫና አለ የሚባለው ነገር እስካሁን በኮሚቴው ላይ ስለመኖሩ የታወቀ ነገር የለም።
የአስመራጭ ኮሚቴውን የዛሬውን መግለጫ ለማንበብ (እዚህ ላይ ይጫኑ )
 
እግዚአብሔር የወደደውንና የፈቀደውን ያድርግ!