Wednesday, January 9, 2013

እውነቱ የቱ ነው? (ከዚህ በፊት የቀረበ)

መነሻ ሃሳብ «ገመና 81» መጽሐፍ

  ሀተታ

በኦርቶዶክሳውያን  ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከታች ጀምሮ እስከላይኛው እርከን ድረስ ያለው ሰው ስህተት ይኖርብናል ወይም ልንሳሳት እንችላለን ብሎ የሚያስብ ማግኘት አዳጋች ነው። በክርስቶስ ደም የተመሰረተችው ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗን በመቀበል እንዳለ መሪውና ተመሪው ራሱንም በዚያው ዓይን እያየ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በሚል ከለላ ስር ራሱን በማስጠለል፤ ስህተትን አምኖ ለመቀበል አይፈልግም። የስህተት አስተምህሮ አለ፤ በእግዚአብሔር ቃል ሲመረመር አደጋው የከፋ ነው፤ የክፉ መንፈስ አሰራር ወደማወቅ እንዳንደርስ ቃሉን በክሏል ሲባል የሚሰጠው ምላሽ፤ 2000 ሺህ ዘመን የኖረችን ቤተክርስቲያን ዛሬ የተነሱ አፍቃሬ ተሐድሶ መናፍቃን ሊያርሟትና ሊበርዟት ይፈልጋሉ በማለት ታፔላ መለጠፍ ይቀናቸዋል። የስም ታፔላ መለጠፍ ብቻ ሳይሆን ሽልማት የሚያሰጥ ቢሆን ኖሮ የተመረጡና ለመስማት የሚዘገንኑ ስድቦችና ዛቻዎች ይዥጎደጎዳሉ።
በእርግጥ የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ፍጽምትና ንጽሕት መሆኗ አያጠራጥርም። ምክንያቱም የመሠረታት በዓለቱ ላይ በፈሰሰው ደሙ ነውና። ይህ እውነት ቢሆንም በክርስቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ አባል ሆነው የሚኖሩት የአዳም ልጆች መሆናቸውንም በመዘንጋት የቤተክርስቲያኗን መንፈስና ባህርይ እንዳለ ወደሰዋዊ ማንነት በመውሰድ እኛ ፍጹማንና ንጹሐን ነን በማለት ከስህተት አልባነት የቤተክርስቲያን ማንነት ጋር ራስን መቁጠር ትኩረት የሚያሻው መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል። በእርግጥም የተጠራነው ፍጽምት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹማን እንድንሆን ነው። ነገር ግን ሰው ከተፈጠረበት ማንነት የተነሳ በፍጽምቷ ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍጹም ሆኖ መኖር የሚችል ማንነት የለውም።
ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሊሆኑን የሚችሉት የገላትያ ሰዎች ማንነት ነው። የገላትያ ሰዎች በክርስቶስ አዳኝነት አምነው ወደ ሕይወት መንገድ የተመለሱ ሕዝቦች ነበሩ። ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተጨምረው የቆዩ ሆነው ሳለ ሰብአዊ ማንነታቸው አሸንፎአቸው ወደስህተት መንገድ በመግባታቸው በሐዋርያው ጳውሎስ እጅግ የተወቀሱ ሕዝቦች ሆነዋል።
«የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነውገላ 31
ክርስቶስ ኢየሱስ በፊታቸው የተሰቀለ ሆኖ በእምነት ይታያቸው የነበሩት ሕዝቦች ከዚያ የቅድስና ማንነት ወርደውና እውነትን በመተው፤ የጠላት አዚም የወረደባቸው  ሕዝቦች እስከመሆን መድረሳቸውን ሲናገር እናያለን። ሥራቸውን ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የጀመሩ ሆነው ሳለ ቁልቁል ተመልሰው የሥጋን ሃሳብና እውቀት ወደማመን መመለሳቸው በእርግጥም አሳዛኝ የሰው ልጆች ማንነት ማሳያዎች እንደሆኑ የሚያስገነዝበን  ነገር ነው።
«እንዲህን የማታስተውሉ ናችሁ? በመንፈስ ጀምራችሁ አሁን በሥጋ ትፈጽማላችሁንገላ 33 ይላል።
እንግዲህ ክርስቲያኖች ፍጽምትና ንጽሕት በሆነች ቤተክርስቲያን ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እምነታቸውን ሊጀምሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ይህንን ፍጽምና ወደአለማወቅ መመለስም ሊታይባቸው ይችላል። ምን ጊዜም ቢሆን የስህተት መንፈስ አገልግሎቱ፤ የእውነቱን መንፈስ ከሰው ልቡና ላይ በመውሰድ ወደስህተት መንገድ መምራት ስለሆነ በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ ሰዎች ውስጥ የስህተት አስተምህሮ እንደሚገባ እናረጋግጣለን።
ብዙዎች የአብያተ ክርስቲያናት አባላት በክርስቶስ ፍቅር ላይ ጸንተው ከመቆም ይልቅ ወደ ምድራውያንና ሰማያውያን ፍጥረቶች ፍቅራቸውን ስለለወጡ የሕይወት መንገድን ስተው መገኘታቸው እውነት ነው።
ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ልጁን ወደ ተሰሎንቄ የላከበት ዋናው ምክንያትም ተሰሎንቄዎች  ከእምነት ጽናታቸው ወደኋላ እንዳይመለሱ በመንፈስ ያበረታታቸው ዘንድ ነበር። ምክንያቱም ፈታኝ የምንጊዜም አዚሙን የሚያፈሰው  የአማኞችን ልቡና በማደንዘዝ ወደ አልሆነ አቅጣጫ መመለስ  ሥራው ስለሆነ ከዚህ ፈታኝ ይጠበቁ ዘንድ እንደላከላቸው ቅዱሱ ወንጌል ይነግረናል።
«ስለዚህ እኔ ደግሞ ወደ ፊት እታገሥ ዘንድ ባልተቻለኝ ጊዜ። ፈታኝ ምናልባት ፈትኖአቸዋል ድካማችንም ከንቱ ሆኖአል ብዬ እምነታችሁን ለማወቅ ላክሁ» 1 ተሰ 35

Monday, January 7, 2013

«በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም» ፩ኛ ቆሮ ፭፤፰


ጨለማ አስቸጋሪ ነገር ነው። የሰው ልጆች የሌሊቱን ጨለማ ማሸነፍ ባይችሉ ማየት የተከለከለ የዓይናቸውን ብርሃን ለማገዝ የተለያዩ የብርሃን ምንጮችን ሰርተዋል። እንደዚያም ሆኖ የሰው ልጆች የብርሃን ምንጮች  ጨለማን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠር አይችሉም። ይልቁንም በእንከንና በችግር የተሞሉ በመሆናቸው በሌሊቱ ጨለማ ውስጥ አንዳንዴ በጨለማው ሊሸነፉ ይችላሉ። እንኳን የሰው ልጆች የብርሃን ስሪቶች ይቅርና የሰማይ አምላክ የፈጠራት የፀሐይ ብርሃን እንኳን ዓለሙን ሙሉ በአንድ ጊዜ እንድትሸፍን ተደርጋ አልተስራችም። ከዚህም የተነሳ በክልል ያልተወሰነ፤ ብቃቱ ምሉዕ የሆነና በጨለማ መተካት የማይችል ብርሃን እስከዛሬ ዓለማችን አልተሰራላትም።   ስለዚህ ለዓይናችን የሚታየው የብርሃን ምንጭ ውሱንነት የዚህን ያህል ግልጽ ከሆነ በሰዎች ውስጣዊ ሕይወት ውስጥ ያለውን የማንነት ብርሃን ከጨለማ ማውጣት የሚችል ማነው?  

 ይህንን የሕይወት ጨለማ፤ በብርሃን መሙላት የሚቻለው ከሰው ልጆች መካከል አንድም ቅዱስና ጻድቅ የሆነ፤ ከሰማያት መላእክት መካከል  ማንም የለም።  ይህንን የሰው ልጆች ሕይወት በጨለማ ውስጥ ከመኖር ወደብርሃን መቀየር የግድ ያስፈለገው ጉድለቱን መሙላት የሚችል ባለመኖሩ ነበር። እሱም ጨለማ የማያሸንፈው፤ ብርሃኑን ለተቀበሉ ሁሉ በውስጣቸው ዘላለማዊ ብርሃን ማኖር የሚችል፤ የብርሃናት ሁሉ ጌታ ለመሆን  የተገባው  መገኘት ነበረበት። በጨለማ የሚሄድን ሕዝብ ወደብርሃን እንዲመጣና በሞት ጥላ ስር የወደቁ ሁሉ ዘላለማዊ ሕይወትን እንዲያገኙ፤ ነፍስና ሥጋን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር ሌላ ማን ይችላል? ፍጹም የሆነ መታመኛ እርሱ ብቻ ነውና! ዳዊት በዝማሬው « እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው» እንዳለው መዝ ፳፯፤፩ ይህንን የሕይወት ጨለማ በብርሃን መግለጥ የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነበር።

የሰው ልጆች ብርሃን የጨለማ  ዓለምን በሙላት መግለጥ የማይችል ከመሆኑም በላይ የነፍስን ጨለማ ደግሞ በብርሃን መሙላት ይችላል ተብሎ ስለማይታሰብ፤  መታመኛ ብርሃን የሆነው እግዚአብሔር፤ ከዘላለማዊ ብርሃኑ የወጣ ብርሃን፤ ከአምላክነቱ የወጣ አምላክ፤ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፤ ጨለማን በመግለጥ ብርሃንን  የሚሰጥ፤ በሞት ጥላ ስር ላሉ ሕይወትን የሚያድል፤ አንድያ ብርሃን ልጁን ለጨለማው ዓለም ላከ። ይህም ብርሃን ወደዓለም መጣ።
«በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ»  ዮሐ ፲፤፵፮ በማለት እውነተኛው ብርሃን እንደተናገረው።
ይህ ብርሃን ወደዓለም የመጣው ጨለማውን ዓለም በማይጠፋ ብርሃን ሊሞላ ነው። በሞት ጥላ ስር ላሉትም ሕይወትን ሊሰጥም ጭምር ነው።«በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው» ኢሳ 9፤2 እንዳለው።  የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ለዓለሙ ሁሉ ሆነ።
«ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል» ኢሳ ፱፤፮

Saturday, January 5, 2013

ምንኩስናና ጋብቻ!

በንጽህናና በድንግልና እየኖሩ የክርስቶስን የማዳን ሥራ ዘወትር እያሰቡ መኖር የእውነተኛ ክርስቲያን አንዱ ገጽታ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስም ይህንን ሲገልጸው  «ነገር ግን ያለ አሳብ ልትኖሩ እወዳለሁ። ያላገባው ጌታን እንዴት ደስ እንዲያሰኘው የጌታን ነገር ያስባልና» በማለት ሳያገቡ የክርስቶስን  መከራ ሞት እያሰቡና የሕይወታቸው መመሪያ አድርገው ለሚኖሩ ትልቅ ሥፍራ ሰጥቷቸው ይገኛል። (1ኛ ቆሮ 7፤32)

ይህ ማለት ግን ያገቡ ሰዎች ክርስቶስን ማገልገል አይችሉም  ማለት አይደለም። እንዲያውም  የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲሉ በትግልና በትልቅ ፈተና ስር ራሳቸውን ጥለው ሥጋቸውን በመጨቆን የሚያሰቃዩትን ሰዎች በድንግልና ያለመቀጠል ብቃታቸውን እንዲህ ሲል ከፈተናቸው እንዲላቀቁ በጌታ መንፈስ ይመክራቸዋል።
«ነገር ግን በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ» 1ኛ ቆሮ 7፤ 9
ክርስቲያን መኖር የሚገባው በተሰጠው ጸጋ እንጂ የሌለውንና ያልተጠራበትን ጸጋ በጥረቱ ለማግኘት በመፈለግ ባለመሆኑ አንዳንዶች በድንግልና እንኖራለን ብለው ሲያበቁ አዳማዊ ማንነታቸው ከሔዋን ጋር የሚያጣምር ሲሆንባቸውና ከቁጥጥር ውጪ በሆነ ምኞት ስር ሲጥላቸው የሥጋ ብልቶቻቸውን በቢላዋ ጎምደው እስከመጣል ይደርሳሉ። ይሁን እንጂ የሥጋ ብልታቸው መቆረጡ የልብ ምኞታቸውም ቆርጦ ሊያስቀረው የማይችል ስለሆነ ዘወትር እንደተቅበዘብዙ ይናራሉ።
«ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፥ አንዱ እንደዚህ ሁለተኛውም እንደዚያ»  1ኛ ቆሮ 7፤7

ሐዋርያው እንዳለው በድንግልና የጌታን ነገር ብቻ እያሰቡ መኖር የተሻለ መሆኑ አይካድም።  ይህ ጸጋ ለሁሉም የሚሰጥ ባለመሆኑ አንዳንዶች ጸጋቸውን ሳያውቁ ሰዎች በደነገጉት የድንግልና ሕግ ሥር ወድቀው የራሳቸውን የጽድቅ መንገድ ለማቆም እየታገሉና  እየተቃጠሉ መኖራቸው እርግጥ ነው። የሥጋ ብልቶቻቸውን ከመቁረጥ አንስቶ አስገድዶ እስከመድፈር ፤ እንስቶችን አባብሎ ከመዳራትና የስርቆሽ ዝሙት እስከመፈጸም መድረሳቸው  የሰውኛ ጥረት ውጤት ነው። አንዳንዶቹ የሥጋው ፈተና የመጨረሻው ጣሪያ ላይ ሲደርስባቸው ለክፉ መንፈስ ተጋልጠው ግብረ ሰዶም እስከመፈጸም ይደርሳሉ።
«የእግዚአብሔርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ፥ ለእግዚአብሔር ጽድቅ አልተገዙም» ሮሜ 10፤3
 የተባለው  የእግዚአብሔርን ጽድቅ  ሳያውቁ ለመጽደቅና የራሳቸውን ጽድቅ ለማቆም  ሲታገሉ ከጽድቁ ሥራ ወጥተው የቀሩትን ይህ ቃለ እግዚአብሔር ተፈጽሞባቸዋል ማለት ይቻላል።

ከዓለማውያን ሰዎች ባልተሻለ መልኩ አባ እገሌ እገሊትን ደፍረው ተያዙ፤ አቡነ እገሌ ልጅ ወለዱ፤ እነአባ እገሌም  ግብረ ሰዶም ፈጸሙ እየተባለ ለሰሚ የሚቀፍ ዜና የሚሰማው እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ የሌላቸውን ጸጋ ለማግኘት ሲታገሉ ቆይተው የጭናቸው እሳት እየፈጀ መቆሚያና መቀመጫ ስለሚያሳጣቸው ነው። በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ በሰው ሚስት ላይ የተያዙ፤ አስገድደው የደፈሩ፤ አልፎ ተርፎም ግብረ ሰዶም ፈጽመው የተገኙ የብዙ አባዎች ጉዳይ አሳሳቢነት ለሲኖዶስ ጉባዔ መወያያ  ሆኖ  መቅረቡ አይዘነጋም።
ይህ እንግዲህ የምናውቃቸውንና የምንሰማቸውን አስጸያፊ ተግባራት ሳይጨምር መሆኑ ነው። ይህን ማንሳት በሥጋ ድካም መነኮሳት የሰሩትን ኃጢአት ለማውራት ሳይሆን የጋብቻን ክቡርነት የሚናገረውን የእግዚአብሔርን ቃል በመጋፋት የራሳቸውን ሕግ ለማቆም በመታገል መካከል በሚፈጠረው ሽንፈት የተነሳ ኢ-ሞራላዊ፤ ኢ- ምግባራዊና ጸረ ሃይማኖታዊ አድራጎት እየተስፋፋ በመገኘቱ ምክንያት እንደሆነ መታወቅ አለበት። የማይቻለውን ለመቻል ሲታገሉ ሽንፈታቸው መረን የለሽ ወደመሆን አድርሷቸው  የመገኘታቸው ነገር ግልጽ ወጥቶ በመነጋገር  አንድ  እልባት ላይ መድረስ ካልተቻለ ድርጊቱ ማቆሚያ የሌለው ሆኖ ይቀጥላል። ይህም በተጎጂው ላይ፤ በእምነቱ ተከታይ ውስጥ እና በማኅበረሰቡ ውስጥ አሉታዊ አስተሳሰብ እንዲኖር የማድረጉ ነገር ማብቂያ የለውም።