Wednesday, September 19, 2012

የማኅበረ ቅዱሳን የጥናት እና ምርምር ማእከል ባዘጋጀው በ፬ኛው የኢትዮጵያ ቤተ- ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ላይ የተደረገ አጭር ደሰሳ፡፡



   ፍቅር ለይኩን ለደጀ ብርሃን የላከው ጽሁፍ
[fikirbefikir@gmail.com/befikir12@yahoo.com

‹‹ሁሉን መርምሩ የተሻለውን ያዙ!›› የሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ሕያው ቃል ባለ አእምሮ የሆነ ሰው ሁሉ በማስተዋልና በጥበብ መንፈስ ሆኖ መልካሙን ከክፉ ለመለየት ጥናት እና ምርምር በእጅጉ አሰፈላጊ መሆኑን የሚያሳስበን ኃይለ ቃል/ምክር ይመስለኛል፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በአይሁድ ምኩራብ ተገኝቶ በተደጋጋሚ ስለ ጌታችን፣ አምላካችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ ጌትነት እና አዳኝነት የሰበከላቸው ልበ ሰፊዎቹ የቤሪያ ሰዎች፡- ‹‹ነገሩ እንዲህ ይሆንን በማለት መጻሕፍትን በመመርመር ቃሉን በሙሉ ልብ ተቀበሉ ይለናል፡፡›› (ሐዋ  ፲፯፣፲፩)   
የሥልጣኔ ምንጭ፣ የሺህ ዘመናት ባለ ታሪክ እና የበርካታ ቅርሶች ባለቤት ለሆነችው ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት እና ምርምር ሥራ ታላቅ ፋይዳ ያለው መኾኑ አያጠራጥርም፡፡ በኢትዮጵያ ባሕልና ቱሪዝም ሚ/ር በቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ባለሥልጣን አዳራሽ ጳጉሜን ፫ እና ፬ ለሁለት ቀናት በተካሄደው ‹‹ኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ›› አንገብጋቢ እና ወቅታዊ በሆኑ ሀገራዊና ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ምሁራን፣ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በመጡ፣ ከተለያዩ መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ካልሆኑ መሥሪያ ቤቶች በተጋበዙ እንግዶች በአማርኛ እና በእንግሊዝኛ ቋንቋ ሰባት የጥናት ወረቀቶች የቀረቡበት ጉባኤ ነበር፡፡
ጥናት እና ምርምር በሳይንሳዊ ዘዴ ለችግር መፍትሔ ለማፈላለግ፣ አዳዲስ ግኝቶችን ለመፍጠር፣ ተጨማሪ እውቀትን ለማግኘት፣ አስፈላጊውን መረጃ ተገቢውንሳኔ ለመስጠት የሚያስችል ዐቢይ ተግባር ነው፡፡ ዛሬ አንቱ የተባሉ፣ ዓለምን ያስደመሙ ጥበባት ኹሉ የጥናትና ምርምር ውጤቶች ናቸው፡፡ በዘመናችን በዓለም ላይ የተጋረጡ በርካታ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ አካባቢያዊ፣ ፖለቲካዊ እና መሰል ችግሮችን ለመፍታት ዋነኛው መንገድ ጥናት እና ምርምር መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
ስለሆነም በሀገራችን ይህን የሚያስፈጽሙ አያሌ የጥናት እና ምርምር ተቋማት ተመሥርተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን የረጅም ዘመን የሥነ መንግሥት/ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊ ኑሮ፣ ታሪክ፣ ባሕል እና ሥልጣኔ እንዲሁም ፍልስፍና፣ ሕግ፣ ሥነ ጹሑፍ፣ ኪነ ጥበብ እና ሥነ ሕንጻ/አርክቴክቸር ሰፊ እና ጉልህ አሻራ ያላት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ሰፊ የሆነ ምርምር እና ጥናት በማድረግ ረገድ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሀገራችን ለትምህርት መጀመር ከተጫወተችው ግንባር ቀደም ሚና እንዲሁም ጥንታዊት፣ ሐዋርያዊት እና ወንጌላዊት እና በበርካታ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ምእመናን ያሏት ተቋም የመሆኗን ያህል በበቂ ሁኔታ የተደራጀ የጥናት እና የምርምር ማእከል የላትም፡፡
ለቤተ ክርስቲያኒቱ አንድ ለእናቱ ሊባል የሚችለው በዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ደረጃ አለ የሚባለው የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅም በብዙ አካዳሚያዊ እና አስተዳደራዊ ችግሮች የተተበተበ በመሆኑ እንደ አንድ አካዳሚያዊ ተቋም በበቂ ሁናቴ የተደራጀ እንኳን ቤተ መጻሕፍት የለውም፡፡ በየጊዜው በአኀተ አብያተ ክርስቲያናትም ሆነ በክርሰቲያኑ ዓለም የሚወጡ አዳዲስ መጻሕፍቶች፣ የጥናት እና የምርምር ጆርናሎች እና ፐሮሲዲንጎች በዚህ ተቋም ውስጥ እጅጉን ብርቅ ናቸው፡፡ እናም ይህ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ብቸኛ እና አንድ የሆነ የሥነ መለኮት ተቋም የሚጠበቅበትን ያህል ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ ለሀገር መፍትሔ አመላካች የሚሆኑ ብቁ እና ወዳዳሪ የሆኑ ምሁራንን በብዛት እና በጥራት ለማፍራት ቀርቶ ተቋም እራሱ በበርካታ ችግሮች ተተብትቦ የሌሎችን ብርቱ እገዛ ወደሚፈልግበት ደረጃ የደረሰ ይመስላል፡፡
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ማለት ይቻላል የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን በማጥናት በኩል ከእኛ ይልቅ ምዕራባውያኑ እና አሜሪካውያን ምሁራን ሰፊውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ ይህ ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ስለ ችግሮቻችን አጥንተው መፍትሔ አሳብ የሚያቀርቡልን ፈረንጆቹ መሆናቸው ነገሩን እንቆቅልሽ ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ደግሞ በተለይም በቤተ ክርስቲያናችን ጥናት እና ምርምርን የሚያበረታቱ አመቺ ሁኔታዎች እና ተቋማት አለመኖራቸውና ለረጅም ዘመናት የቆየው የቤተ ክርስቲያኒቱ ባሕላዊ የሆነ የትምህርት ሥርዓትም ያለውን ከማስጠበቅ አልፎ አዲስ እውቀት ለማምረት (Knowledge Production) የሚያስችል የጥናት እና ምርምር በር ለመክፈት አለመቻሉ እንደ አንድ ምክንያት ሊወሰድ የሚችል ይመስለኛል፡፡
ፊደል ቀርፃ፣ ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ የድንቁርና እና የአለማወቅን ጨለማ ለመግፈፍ ገና ከጥንት ከጠዋቱ ታጥቃ የተነሳች ቤተ ክርስቲያናችን በጀመረችው ፍጥነት መጓዝ ተስኗት እና ይባስም ሲል በምርምር እና በጥናት እጅጉን የተራቀቁ እና የመጠቁ የሥነ መለኮት እና የፍልስፍና ሊቃውንቶችን ያፈራች ቤተ-ክርስቲያን በዘመናችን በብዙ ችግሮች ተተብትባ መንገዷ ሁሉ ባለህበት እርገጥ መሆኑ ሁላችንንም ሊያስቆጨን የሚገባ ጉዳይ መሆኑን መዘንጋት አይኖርብንም፡፡
ይህን ቤተ ክርስቲያኒቱ እና የትምህርት ተቋማቶቿ ኅብረተሰቡ ከእነዚህ ተቋማት የሚጠብቀውን ያህል አለመንቀሳቀሳቸው፣ ያሉባቸውን እና የተጋረጡባቸውን ሁለተናዊ እንቅፋቶች እና ቤተ-ክርስቲያኒቱ በዚህ ረገድ እጅግ ወደ ኋላ መንደርደሯን የታዘቡ አንድ ምሁር እና ፖለቲከኛ በአንድ ወቅት ‹‹ነፃነትን የማያውቅ ነፃ አውጭ›› በሚል በመጽሐፋቸው ላይ፡-
በአንድ ወቅት በምድረ አውሮፓ እና በአረቢያ ከነበሩ ተመሳሳይ የመንፈሳዊ እውቀት ተቋማት ጋር መወዳደር የሚችል የትምህርት ዓይነቶች ያስተምር የነበረ ቤተ ክህነት፣ አውሮፓውያኑ እነዚህን ተቋማት ወደ ትላልቅ እና ዝነኛ የጥናት እና የምርምር ማእከላት እና ዩኒቨርስቲዎች መቀየር ሲችሉ የእኛው ቤተ ክህነት ተቋማት እንዴት ከነ ከፍተኛ ሕዝባዊ ተቀባይነታቸው እና ክብራቸው ጋር የእርግማን ሰባኪ ተቋም ብቻ ሆኖ እንደቀረ እኔም ሆነ ትውልዴ ለማወቅ አልጣርንም፣ አልፈለግንም በማለት ቁጭታቸውን ገልጸው ነበር፡፡
ዛሬ በዓለማችን ያሉ ትላልቅ የሃይማኖትም ሆኑ ዓለማዊ ተቋማት ከፍተኛ የሆነ ወጪ የሚመድቡት ሰፊ እና ጥልቅ በሆነ ጥናት ለታገዙ የምርምር ስራዎች እና አማካሪዎች/መማክርት ነው፡፡ በሀገራችንም ሆነ በቤተ ክርስቲያናችን ለተጋረጡብን ሁልቆ መሣፍርት ለሌላቸው ችግሮቻችን በዚህ ዘመን ጥልቅ የሆኑ በእግዚአብሔር ጥበብ እና ማስተዋል መንፈስ የተቃኙ ጥልቅ የሆኑ አሳቢዎች/ተመራማሪዎች (Great Thinkers) በእጅጉ ያሰፍልጉናል፡፡
በቀደመው ታሪካችን ዘመን በሀገራዊ እና በቤተ ክርስቲያን አጀንዳዎች ላይ ሰፊ ጊዜ በመውሰድ የሚያሰላስሉ፣ የሚጸልዩ፣ በጽሞና መንፈስ ሆነው በእግዚአብሔር ፊት በጽናት እና በትዕግስት የሚቆዩ አባቶች እንደነበሩን የታሪክ ድርሳናቶቻችን ይመሰክራሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ተጋድሎ እና መንፈሳዊነት ዛሬ በታሪክ ብቻ በነበር የምናወሳው የሩቅ ዘመን ትዝታችን ሆኖ መቅረቱ ሁላችንንም ሊያንገበግበን ይገባል፡፡ አውሮፓውያን እና አሜሪካውያን ዛሬ ለደረሱበት እጅግ ለመጠቀ ሥልጣኔ፣ የአስተሳሰብ ምጥቀት፣ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እድገቶች እና ለውጦች ትልቅ መሠረት የጣሉ በሃይማኖት ተቋማቶቻቸው የነበሩ ጥልቅ አሳቢዎች እና ተመራማሪዎች እንደ ነበሩ የታሪክ ድርሳናት ይመሰክራሉ፡፡
በአውሮፓውያኑ ዘንድ ስለ ኢትዮጵያ ጥንታዊ ሥልጣኔ፣ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ቅርስ፣ ፍልስፍና፣ ኪነ ህንፃ እና ኪነ ጥበብ በሰፊው እንዲጠና በመካከለኛው ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያውን መነኮሳት እና ሊቃውንት በተለይ በአውሮፓ ለኢትዮጵያ ጥናት እና ምርምር መከፈት ምክንያት መሆናቸውን ታሪካችን ያወሳል፡፡ በተለይ አባ ጎርጎሪዎስ ዘመካነ ሥላሴ የተባሉት መነኩሴ ጀርመናዊውን ሉዶልፍን የግዕዝን ቋንቋ፣ የሀገራችን እና የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በማስተማር በመካከለኛው ዘመን በአውሮፓ ምድር የኢትዮጵያ ጥናት እንዲጀመር በቀደምትነት መሠረትን የጣሉ  ኢትዮጵያዊ ሊቅ እንደሆኑ የሀገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ሀገር ምሁራን ይመሰክራሉ፡፡
በእነዚህ ኢትዮጵያውያን መነኮሳትና ሊቃውንት በአውሮፓ የተጀመረው ጥናት እስከ አሁን ዘመን ድረስ ቀጥሎ በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ ትላልቅ ዩኒቨርስቲዎች፣ የጥናት እና ምርምር ማእከሎች በኢትዮጵያ ጥንታዊ ቋንቋ በሆነው በግዕዝ፣ በሀገሪቱ የረጅም ዘመን ታሪክ እና ሥልጣኔ ዙሪያ ሰፋ ያለ ጥናት በማካሄድ ላይ ናቸው፡፡ ለአብነትም ያህል በፈረንሳይ፣ በኢጣሊያን ፍሎረንስ እና ኔፕልስ ዩኒቨርስቲዎች፣ በጀርመን ሀምቡርግ ዩኒቨርስቲ፣ በለንደን School of Oriental and African Studies እና በአሜሪካ በሚገኙ ታላላቅ ዩኒቨርስቲዎች በጥንታዊው የኢትዮጵያ ቋንቋ በግዕዝ እና በሀገራችን ጥንታዊ ሥልጣኔ እና ታሪክ፣ ባሕል እና ቅርስ ዙሪያ ጥናቶች ይደረጋሉ፡፡
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በአብዛኛው በኢትዮጵያ ዙሪያ ጥናት እና ምርምር የሚያካሂዱ የውጭ ሀገር ምሁራን መሆናቸው ቀስ በቀስ እየተለወጠ ቢገኝም እኛ ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ስለ እራሳችን በጥናት እና በምርምር በተደገፈ ሁኔታ በልበ ሙሉነት ለመናገርም ሆነ በተለያዩ ቋንቋዎች የዳጎሱ የጥናት መጻሕፍቶችን በማቅረብ ረገድ ገና ብዙ የሚቀረን ይመስለኛል፡፡ ምናልባትም የዚህ የማኅበረ ቅዱሳን የምርምር እና የጥናት ማእከል በየዓመቱ የሚያዘጋጀው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ዓመታዊ ጉባኤም በከፊል የዚህ ቁጭት እና ቅናት ውጤት የወለደው ነው ለማለት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
የጥናት እና ምርምር ፋይዳውን የተረዱ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፍሬዎች የሆኑ እና በተለያዩ የትምህርት መስክ እስከ ፒ ኤች ዲ የተማሩ ልጆቿ ጥረት ለአራተኛ ጊዜ በማኅበረ ቅዱሳን የምርምር እና ጥናት ማእከል የተዘጋጀው አራተኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ፣ በጥናት እና በምርምር በመታገዝ በቤተ ክርስቲያናችን ያሉትን ችግሮች በሚገባ አጥንቶ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ ተያያዥ በሆኑ፣ በወቅታዊ የሀገራችን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ መፍትሔ ለማፈላለግ የበኩሉን ድርሻ ለማበርከት በሚል ከአራት ዓመታት በፊት የተጀመረ ጉባኤ መሆኑን የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የሆኑት ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም በመክፈቻ ንግግራቸው ገልጸዋል፡፡
ለአራተኛ ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ ለሁለት ቀናት በተደረገው የኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ ላይ በቀረቡት የጥናት ወረቀቶች እና ከተሳታፊያን በተነሱ ጥያቄዎች፣ አስተያየቶች እና ውይይቶች ዙሪያ መጠነኛ የሆነ አጭር ደሰሳ በማድረግ ይህችን አጠር ያለች ጹሑፍ ለአንባቢያን ለማቅረብ ወደድሁ፡፡
ይህ ጹሑፍ እግረ መንገዱንም በተለይ በማኅበረ ቅዱሳን እና ከማኅበረ ቅዱሳን በተቃራኒ በቆሙ ማኅበራት እና ግለሰቦች ደጋግመው ማኅበረ ቅዱሳንን ስለሚከሱበት፡- ‹‹ማኅበሩ የወንጌል ጠላት ነው፣ ማኅበረ ቅዱሳን የፖለቲካ ድ/ት ነው፣ ማኅበሩ በመንፈሳዊነት መጋረጃ ጀርባ የለየለት ዘራፊ እና ነጋዴ ሆኗል፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ላለፉት ሃያ ዓመታት ለገባችበት ቀውስ በከፊልም ቢሆን የማኅበሩ ተጠያቂ ነው…ወዘተ፡፡›› በማለት ማኅበሩን የሚከሱትን ቡድኖችንም ሆነ ግለሰቦች በሩቅ ቆመው ከመካሰስ እና እርስ በርስ ከመፈራረድ ይልቅ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል አሉ የሚሏቸውን ችግሮች እና ትዝብታቸውን በተጨባጭ መረጃ፣ በጥናት እና በምርምር በማስደገፍ ማቅረብ ቢችሉ እንዴት መልካም በሆነ ነበር፡፡ እንዲሁም በእንዲህ ዓይነቶቹ እና በተመሳሳይ የጥናት ጉባኤ መድረኮች ላይ በመገናኘት፣ በመቀራረብ እና በግልጽ በመነጋገር ልዩነቶችን አሰውግዶ በአንድነት መሥራት የሚቻልበት መንገድ እንዲኖር በሚል በቅንነት መንፈስ ያቀርብኩት ደሰሳ እንደሆነ ከወዲሁ ለአንባቢዎቼ በአክብሮት ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡
በዚህ አራተኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ላይ ከቀረቡት እና በጨርፍታ ዳሰሳ ላደርግባቸው ከመርጥኳቸው የጥናት ወረቀቶች መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፕሬስ ባልደረባ፣ የታሪክ ምሁር እና ተመራማሪ እንዲሁም በሀገራችን በሚታተሙ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና የታሪክ ነክ መጽሐፎች ላይ ሰፊ እና ጥልቅ የሆኑ ዳሰሳዎችን (Book Reviews and Critics) በማድረግ የሚታወቀው አቶ ብርሃኑ ደቦጭ፡-

‹‹የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች በቤተ ክርስቲያን እና በሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ያላቸውን የአዘጋገብ ሂደት›› በተመለከተ ባቀረቡት የጥናት ወረቀት ላይ በተለይ በስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ ርዕሰ አንቀጾች፣ ዜናዎች እና ሐተታዎች ላይ አጥኚው ሰፋ ያለ ትንታኔ ለመስጠት ሞክረዋል፡፡ ጋዜጣዋ በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባዎች፣ ሂደቶች እና ውሳኔዎች ላይ፣ በሃይማኖታዊ ግጭቶች መንስኤዎች ዙሪያ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ በሆኑ ወቅታዊ እና ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ የሚወጡ ዘገባዎች በአብዛኛው ፍርሃት የሚንጸባረቅባቸው ቢሆኑም ስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉትን ችግሮች በማሳየት ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳላት ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን ተግባራዊ የሚሆን መፍትሔን በማቅረብ ረገድ ግን ጋዜጣዋ ድካም እንደሚታይባት ገልጸዋል፡፡
አቶ ብርሃኑ ባቀረቡት የጥናት ወረቀት ላይ አንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት እና በቅርስ ጥናት እና ጥበቃ የሥራ ባልደረባ የሆኑ ሰው በሰጡት አስተያየት፡- ‹‹ስምዓ ጽድቅ ጋዜጣ እንደ ስሟ እውነትን በመናገር ረገድ ብዙም የተዋጣላት አይደለችም፡፡›› የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመት ውጤቶች፡- ‹‹የቤተ ክርስቲያን ዋና ተልእኮ የሆነው ወንጌልን ገሸሽ ያደረጉና የወንጌሉ ዐቢይ መልእክት እውነት፣ መንገድ እና ሕይወት የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን በሚገባ የማይገልጽ ነው በሚል አስተያየታቸውን አጠናክረዋል፡፡›› በሌላ በኩል ደግሞ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች፡- ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባዎች እና ውሳኔዎች ላይ እንዲሁም ሀገራዊ በሆኑ ወቅታዊ እና አንገብጋቢ ፖለቲካዊ አጀንዳዎች ላይ ግልፅነት እና ተጠያቂነት የሚያንሰው ነው ሲሉ…›› ሌሎች በግል ያነጋገርኳቸው ተሳታፊዎች ደግሞ በዋነኝነት፡-
‹‹በቤ/ን እና በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች መንፈሳዊ ወኔ እና ድፍረት የሚጎድለው አዘጋገብ እንደ ሚንጸባረቅበት…›› አስተያየታቸውን ሰጥተውኛል፡፡ 

Sunday, September 16, 2012

«ሰምና ወርቅ»


 ከካሳሁን ዓለሙ ድረ ገጽ ተመርጦ የተወሰደ ቅኔ፤
*********************
እንኳን ደኅና ገባህ ከሄድክበት አገር፣

ጠላቶችህ ሁሉ ይቅር ብለው ነበር፡፡

***************

‹ትግራይ› አይደለም ወይ መለስ ትውልድህ፣

የጁ ነው በማለት የደበደቡህ፡፡
*****************

‹መለስ ዜናዊ› ታላቅ መስፍን፣

ነበሩ ሲሉ ባገራችን፣

እንዲያ ሳያጡ ሰገነት፣

ምነው አደሩ ፈረስ ቤት፣

ሞከሩት እንጂ አልኖሩም፣

ከዳሞት አልቀሩም፡፡

***************
በዓለ ድባብ ንጉሥ ባለ ጥና አቡን፣

እየዞሩ ፈቷት አገራችንን፡፡
****************

አሁን ምን ያደርጋል ሱሰኛ መሆን፣

ብዙ ቤት ፈረሰ ትላንት በዚያ ቡን፡፡
***************

ይድናል እያልን ዓይን ዓይኑን ስናይ፣

እንዲያ እንደፈራነው እውነት ሞተ ወይ?
************

የዛሬ ዘመን ወዳጅም፣

ከሽሕ አንድ አይገኝም፣

አንቱ ብትለው ይኮራል፡

አንተ ያልከው ግን ይኖራል፡፡
*********

አሻግሬ ባይ መንገዱን፣

ኧረ ሰው ምናምን፡፡
************
ተስቦ ገብቶ ከቤቴ፣

አልወጣ ካለኝ ዓመቴ፡፡
**************

ወደ አደባባይ ወጥተህ፣

ከባላጋራህ ተሟግተህ፣

ክርክር ገጥመህ ወደ ማታ፣

ዓለም አፈር ነው ስትረታ፡፡
***************
‹ዋልድባ› ወርጄ ቀስሼ፣

ልብሰ ተክህኖ ለብሼ፣

ታዩኛላችሁ እኔን

ነገ ገብቼ ሣጥን፡፡
**************

ክፉ ቢናገር ተቆጥቶ፣

ጠላትህ ደሙ ፈልቶ፤

እሱም እንዳንተ ሰው ነው

ኧረ ተው ሰብቀህ አትውጋው፡፡

Friday, September 14, 2012

ከተማን በመግዛትህ ሁሉን እገዛለሁ አትበል!


ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ ምእራፍ ከተባለ መፅሄት ጋር ያደረጉትቃለመጠይቅ፣
           በጣም የሚወዱትን መዝሙር ይንገሩኝ?
           አቶ ኃ/ማርያም፡- ‹‹እኔም እንደ ዳዊት ጨርቄን ልጣልልህ›› የሚለውን
           ጉባዔ ገብተው ሲያመልኩ ግን እንደ ባለሥልጣን የፕሮቶኮል ነገር አለ፡፡ የጥበቃ ጉዳይ አለ፡፡ ሌላም ሌላም፡፡ ይሄን ሁሉ ረስተው በነጻነት ለማምለክ አይቸገሩም?
አቶ ኃ/ማርያም፡ ምንም አልቸገርም፡፡ ጉባዔ ውስጥ ካለሁ እኔ ስለ ራሴ ጨርሶ አላስብም፡፡ እነ ንጉሥ ዳዊት በእግዚአብሔር ፊት ጨርቃቸውን ጥለው ያመልኩ ነበር፡፡ እኔስ የማመልከው እግዚአብሔር ፊት እንደሆንኩ እንጂ የማስበው ሌላ ነገር አላስብም ማልቀስ ካለብኝ አለቅሳለሁ፣ መንበርከክ ካለብኝ እንበረከካለሁ፡፡ ጌታ ሁን ያለኝን ሁሉ ለመሆን ዝግጁ ሆኜ ነው የማመልከው፡፡
ልጆችዎ በቤተክርስቲያን ውስጥ የመክሊት (የአገልግሎት) ሥራ ውስጥ ሲሳተፉ ይታያል፡፡ የእከሌ ልጅ ነኝ እኮ ብለው ሳይኩራሩ ወንድሞችና እህቶች የጠጡባቸውን የሻይ ብርጭቆዎች እየዞሩ ሲለቅሙ እንዳየ ወንድሜ ፍጹም ነግሮኛል፡፡ በቤት ውስጥ ምን ብለው ቢያስተምሯቸው ነው?
አቶ ኃ/ማርያም፡- እኔም ባለቤቴም ቤት ውስጥ ሁሉም የምንነግራቸው ነገር እኛ ጋር ምንም እንደሌለ እኛ ምንም እንዳልሆንን ሀብታችን ኢየሱስ እንደሆነ የማወርሳቸውም አምላኬን እግዚአብሔርን ብቻ እንደሆነ ነው የምንነግራቸው፡፡ አንተ የራስህ መኪና እንኳን የለህም፡፡ ቤት የለህም፣ አሁን እናንተ አንድ ነገር ብትሆኑ እኛ ምን አለን? ሲሉኝ እንኳን የምመልስላቸው መልስ የለንም ግን መኪና አጥተን እናውቃለን ወይ? ቤትስ አጥተን ማደሪያ አጥተን እናውቃለን ወይ? መኪና ብገዛም ቤት ቢኖረንም የእኛ አይደለም፡፡ ሁሉንም ትተነው ነው የምናልፈው፡፡ ሀብታችን ጌታ ብቻ ነው እላቸዋለሁ፡፡ በአገልግሎት እንዲበረቱም እንመክራቸዋለን፡፡
ለአገልግሎትና የክርስቶስን አካል ለማነጽ ልዩ ልዩ ጸጋ ይሰጣል፡፡ ለእርሶ የተሰጦት የጸጋ ዓይነት ምንድነው?
አቶ ኃ/ማርያም፡ እንግዲህ ጥሪ የተለያየ ነው፡፡ ሁላችንም መሰዊያ ላይ ቆመን አንሰብክም፡፡ እኔን ደግሞ የሰጠኝ የሚመስለኝ ጸጋ ሕዝብን እና አገርን በመልካም አስተዳደር ማገልገል ነው፡፡ ስለዚህ ለእኔ ሥራዬ ስራ ብቻ ሳይሆን አገልግሎትም ጭምር ነው ብዬ የተቀበልኩት፡፡
አቶ ኃ/ማርያም ጠዋት ከመኝታዎ ስንት ሰዓት ይነሳሉ?
አቶ ኃ/ማርያም፡/ሳቅ ብለው/ መመለስ አለብኝ እኔ ሁልጊዜ ከእንቅልፌ ምነሳው ከለሊቱ 11 ሰዓት ነው፡፡ ጉዞ፣ እንደዚህ አይነቱ ነገር ካልረበሸኝ በስተቀር 11 ሰዓት እነሳለሁ፡፡ ከ11 ሰዓት እስከ 12 ድረስ የፀሎት ጊዜዬ ነው፡፡ ከ12 እስከ 12፡30 ትንሽ ‹‹ኤክሰርሳይስ›› (ስፖርት እሰራለሁ፡፡ በቀሪው ጊዜ የዕለቱን የቢሮ ስራ አዘጋጅቼ 1፡30 አካባቢ ወደ ቢሮዬ እሄዳለሁ፡፡
አዘውትረው የሚጸልዩባቸው ጉዳዮች አሉ ካሉ ቢያስታውቁን?
አቶ ኃ/ማርያም፡እኔ ዘወትር በአራት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ እጸልያለሁ፡፡ አንደኛ ሰላምና በረከት ለዚህች አገር እንዲበዛ እጸልያሁ፡፡ ለመሪዎቿ፣ ለመንግሥት፣ ባለሥልጣናት ጥበብና ማስተዋልን እንዲሰጥ እጸልያሁ፡፡ ሁሉም ሃይማኖቶች ያለ አድልዎ እና ልዩነት በእኩልነት እና በመቻቻል እንዲኖሩ እመኛለሁ፡፡ ሁለተኛ የእግዚአብሔር ቃል ‹‹ሰው ሁሉ ወደ መዳን እንዲመጣ›› ይላል፡፡ ስለዚህ ሰው ሁሉ እንዲድን እጸልያለሁ፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነውና፡፡ ሶስተኛ እናቴ አልዳነችምና ለወላጅ እናቴ በተለይ እጸልያለሁ፡፡ አራተኛ ለልጆቼና ለቤተሰቤ ዘወትር እጸልያለሁ፡፡
እንደው በግልጽ ለመጠየቅ ያህል ወደ ሥልጣን ሲመጡ አብረው የሚመጡና ለመሥራትም የሚመቹ የኃጢአት ፈተናዎች ይኖራሉ፡፡ እርስዎ እስካሁን ድረስ የገጠምዎትን ፈተና በምን መንገድ አልፈውታል?
አቶ ኃ/ማርያም፡ የእውነት ለመናገር እስካሁን እግዚአብሔር ረድቶኛል፡፡ በፈተናዎቹ አልፌአለሁ እላለሁ፡፡ ይሄን ከልቤ ነው የምልህ፡፡ ንጉሥ ዳዊት የተከበረ በእግዚአብሔር ዘንድም የተወደደ በብዙ ነገር በጣም የተመሰገነ ንጉሥ ነበር፡፡ እስራኤልን የሚመስል ትልቅ ሕዝብ መግዛት የቻለ ዳዊት ግን ራሱን መግዛት አልቻለም ነበር፡፡ ለዚህ ነው መጽሐፍ ቅዱስ ከተማን ከመግዛት ይልቅ ራስን መግዛት ይበልጣል ያለው፡፡ ነገር ግን መጽሐፉ የሚመክረው ራስን ቤተሰብን መግዛት እንድንችል ነው፡፡ አለ አይደል ከተማን በመግዛትህ ሁሉን እገዛለሁ አትበል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ውስጣዊ ሰብዓዊ ውድቀት ሊኖርብህ እንደሚችል አስበህ ጥንቃቄ አድርግ፡፡ ጥንቃቄ ይጠብቅሃል አይደል የሚለው መጽሐፍ ቅዱስ፣ ዝሙት ሊያታልህ ይችላል፡፡ ዝሙት እንዳይጥልህ ጥንቃቄ አድርግ፡፡ የሥጋ ምኞት፣ ገንዘብ ፍቅርና የዓይን አምሮት የሚባሉት አይደሉም ሰውን የሚጥሉት፡፡ ስለዚህ ከተማን የገዛ ሰው፣ በተለይ እነዚህ ሶስት ነገሮች ላይ መጠንቀቅ አለበት፡፡ እኛ ኢህአዴጎች ስኳር ነው የምንለው፡፡ ስኳሩ እንዳያታልልህ ጥንቃቄ መደረግ አለበት ነው ሀሳቡ፡፡ ፓርቲዬን በጣም የምወድበት ትልቁ ምክንያት ሙስናን፣ ያለ አግባብ፣ ጥቅም ለማግኘት የሚደረግን ጥረት ፓርቲዬ የኪራይ ሰብሳቢ አመለካከት የሚላቸው በሙሉ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተወገዙ ናቸው፡፡ እነዚህ መሰረታዊ መርሆች ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮት ጋር ይጣጣሙልኛል፡፡ አይቃረኑም፡፡ ስለዚህ ሙስና፣ አላስፈላጊ ጥቅማጥቅሞች፣ ውሸት ውስጥ ሳትገባ ሕዝብን ማገልገል አለብህ ስለሚል የኔ ፓርቲ እነዚህን መርሆዎች ስለሚያራምድ ይህ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ስለሆነ በጣም ደስ ብሎኝ ነው የምሰራው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ አንተ ራስህ ከእግዚአብሔር ጋር ንስሐ በመግባት የምትፈታው ነገር ከተገኘ ተገምግመህ እንድትስተካከል ይሆናል ወይም ደግሞ ልትባረርም ትችላለህ፡፡ ስለዚህ ፓርቲዬ በዚህ ጉዳይ ላይ በጣም በጣም ጠንካራ አቋም አለው፡፡ እና በዚህ ዓይነት ነው፡፡
የሚጸጸቱበትን ውሳኔ አስተላልፈው ያውቃሉ?