Wednesday, June 27, 2012

"...መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ" ማቴ. 5፥16

በመምህር ሙሴ ኃይሉ

ምንጭ፤ የሰንበት ት/ቤቶች ማ/መ/ ድረ ገጽ

 መድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ማር እንደ ወተት የሚጣፍጠውን ትምህርቱ ለመስተማርና በተለያዩ ምክንያቶች (ተአምራትን ለማየት፣ ምግበ ሥጋን ለመመገብ፣ ሐሰት አግኝተው ለመፈተን...) ከአምስት ገበያ በላይ ሕዝብ ተሰብስበው በተመለከተ ጊዜ ከፍ ወዳለ ተራራ ወጥቶ በወርቃማ አምላካዊ አንደበቱ በተራራማ ስብከቱ ካስተማራቸው የመንፈሳዊነት፣ የሐዋርያዊነት፣ የአገልግሎት፣ የምግባርና የትሩፋት ትምህርት አንዱ ነው፡፡ ይኸው ትምህርት ቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያትና በሐዋርያት እግር ሥር የሚተኩ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ምዕመናንና ምዕመናትን የሕይወት መርህ በማድረግ እስከ መጨረሻ ህቅታ ድረስ አጽንተው እንዲጠብቁ የተሰጠ የምግባርና የትሩፋት (የሥነ ምግባር) አስተምህሮ ነው፡፡ ብርሃን በተለያዩ ዓይነት የትምህርት ዘርፎች የተለያዩ ትርጉም ቢኖረውም መጽሐፍ ቅዱስ መሠረተ ዕውቀታችን አድርገን ለምናምን ለኛ ግን ብርሃን የእግዚአብሔር የባሕርይ መገለጫው ነው፡፡ ከዚህም በመነሳት ብርሃን ፈጣሬ ዓለማት፣ ሠራዔ ዓለማት፣ መጋቤ ዓለማት እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለሆነም ብርሃን ሀሉን ያስገኘ፣ ሁሉን የፈጠረ እንጂ በዚህ ዘመን ተገኘ፣ ከዚህ ዘመን በኋላ ያልፋል ተብሎ የማይነገርለት ምሥጢረ መለኮት ነው፡፡ እውነተኛ ዘለአለማዊ ብርሃን እግዚአብሔር መሆኑ ዘመነ መርገም አብቅቶ የዘመነ ምሕረት የምሥራች በተነገረበት ጊዜ ድኅነት ሰጪው፣ አዳኙም ሆነ ድኅነት ተቀባዩ ራሱ የሆነ የባሕርይ ዘለአለማዊ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሯል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ (ነባቤ መለኮት) ስለ እውነተኛ ብርሃን ምሥጢር በመጀመሪያ ምዕራፉ ሲጽፍ፡-"...ብርሃን በጨለማ ይበራል ጨለማም አላሸነፈውም፡፡ ...ለሰው ሁሉ የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር፡፡ በዓለም ነበረ ዓለሙም በእርሱ ሆነ ዓለሙም አላወቀውም'' (ዮሐ. 1፡1-10) በማለት ጀምሮ የረቀቁ የሥነ መለኮት ትምህርቶችን በምጥቀት ያትታል፡፡


ይህ ማለት አማናዊ ብርሃን እግዘአብሔር መሆኑንና በዚሁ አማናዊ ብርሃንም ሁሉን እንደተገኘ እንረዳለን፡፡ መምህረ ወንጌል ኢየሱስ ክርስቶስ ስለዚህ እውነተኛ አስተምህሮ በግልጽ ሲያስረዳ ማለት እውነተኛ (አማናዊ) ዘለአለማዊ ብርሃን ራሱ "ወልደ አብ ወልደ ድንግል" ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ ለደቀ መዛሙርቱና በወቅቱ ለተሰበሰቡት ሕዝብ በግልጽ በአደባባይ አስተምሮአል፡፡ "ደግሞም ኢየሱስ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም ብሎ ተናገራቸው" ዮሐ. 8፥12 "በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ" ዮሐ. 12፥36 "የብርሃን ልጆች እንድትሆኑ ብርሃን ሳላችሁ በብርሃን እመኑ" ዮሐ. 12፥46 እንዲል፡፡ የዓለም ሕዝብ በተለይ ደግሞ ሕግ ተሠርቶላቸው፣ ጽላት ተቀርጾላቸው፣ ነቢያት ተልኮላቸው የነበሩ እስራኤላውያን ሕግን እንጠብቃለን ሲሉ ሕግን እየሻሩና ወደ ራሳቸው (ወደ ሥጋዊ ፍላጎታቸው) ብቻ እየተረጐሙ በኃጢአት ጨለማ ውስጥ ሲኖሩ የጨለማ ጠላት የሆነው እውነተኛ ብርሃን መምጣቱንና ሰዎቹም አለመቀበላቸውን ቅዱስ ዮሐንስ ሲገልጽ፣ "ብርሃን ወደ ዓለም ስለመጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ ፍርዱ ይህ ነው" (ዮሐ. 3፥19) በማለት ይገልጽልናል፡፡ የመድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃንነት ከነቢያት ጀምሮ "በጨለማ የተቀመጠው ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ በሞት አገርና በጥላ ለተቀመጡትም ብርሃን ወጣላቸው" (ማቴ. 4፥14-16) በማለት ሲገልጽ የመጣ ሲሆን ይህንኑ አማናዊ ብርሃን አንቀበልም ብለው ኃጢአት ሳይኖርበት እንደ በደለኛ በብርሃኑ ላይ ማመጻቸውም ነቢያት በመንፈሰ እግዚአብሔር ተመርተው አስቀድመው ተነብየውታል፡፡ "እነዚህ በብርሃን ላይ የሚያምጹ ናቸዉ፡፡ መንገዱን አያውቅም በጐዳውም አይጸኑም" (ኢዮብ.24፥13) እንዲል እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነታዎች መረዳት የሚችለው አማናዊ (እውነተኛ) ብርሃን እግዚአብሔር መሆኑን ነው፡፡ የፀሐይና ጨረቃ እንዲሁም የክዋክብት ተፈጥሮስ? አንዳንድ ሊቃውንት ብርሃንን ሲተረጉሙ የተፈጠረ ብርሃንና ያልተፈጠረ ብርሃን በማለት ይተረጉማሉ፡፡

የዔደን ገነቱ እባብ “ማኅበረ ቅዱሳን”


                                               ምንጭ፤ ዓውደ ምሕረት ብሎግ
ይህ ጽሁፍ አራት ኪሎ አካባቢ ሲበተን የተገኘ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ እየተዘጋጀ ያለ ተከታታይ ጽሁፍ ዘጠነኛው ክፍል ነው። ከዚህ ጽሁፍ በፊት ያሉትን ጽሁፎችን ለማግኘት ሙከራ አድርገን የነበረ ቢሆንም የጽሁፉን አዘጋጅ ማወቅ ስላልተቻለ ጽሁፎቹ አልተገኙም። በዚህ ጽሁፍ የማኅበረ ቅዱሳንን ምስረታ አስመልክቶ እስካሁን ድረስ ከሰማናቸው ሀሳቦች ለየት ያለሀሳብ ይዞ የቀረበ ነው። ማኅበረ  ቅዱሳን ከእውነተኛ የቤተክርስቲያን ልጆች ጋር መግባባት ሲገባው እኔ ያልኩትን ተቀበል አሊያ አንተም አትኖርም በሚል ደካማ አስተሳሰብ የቤተክርስቲያን ልጆች እያሸማቀቀ ያለ ሲሆን ስጋ እንጂ መንፈስ  የሌለበት መሆኑም ታውቋል። የማኅበሩ ሃሳብ ዓላማና አካሄድ ከአመሰራረቱና ከስም አወጣጡ ጀምሮ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው መሆኑን የሚያስረዳው ይህ ጽሁፍ አቡነ ገብርኤል የማኅበሩን ስም ማኅበረ ቅዱሳን ያሉበትን ምክንያት የዋህ አባላቱና ሌሎች ሰዎች ከሚያስቡት እጅግ በተለየ መንገድ ያቀርባል። ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ኤደን ገነቱ እባብ ስቶ የሚያስት ወድቆ የሚጎትት ታውሮ ልምራ የሚል መሆኑን የሚያውቁ ሁሉ የኤደን ገነት እባብ መባሉን ተገቢነት ይስማማሉ። (መልካም ንባብ)

Tuesday, June 26, 2012

ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል ከቀረበባቸው የስም ማጥፋት ክስ ነጻ መሆናቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ ገለጸ!

                          ምንጭ፤ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ድረ ገጽ
መምህር አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል (ቆሞስ) ከሳሹ በአግባቡ በማይታወቅ መልኩ የቀረበባቸውን የስም ማጥፋት ክስ በጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ስለቀረበ ቅዱስ ሲኖዶስም በወቅቱ የክሱን እውነተኝነት ለማጣራት ኮሚቴ እንዲቋቋም መወሰኑ ይታወቃል።
የተቋቋመው ኮሚቴም የተባለው ነገር እውነት ወይም ውሸት እንደሆነ በአግባቡ አጣርቶ ለቅዱስ ሲኖዶስ ለማቅረብ በተደጋጋሚ የክሱ ባለቤት ቀርቦ እንዲያስረዳ ጥሪ ቢያቀርብም የዚህ ክስ ባለቤት እኔ ነኝ ባይ ስለጠፋ የቀረበውን የሐሰት ክስ ወደ ሊቃውንት ተልኮ ሊቃውንቱ ነገሩን አጣርተውና ቃላቸውን ተቀብለው (በአካል ጠይቀው) የደረሱበትን እውነት ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያቀርቡ በታዘዙት መሠረት ጽሑፉን በሚገባ አጣርተው አለ የተባለውን መረጃና ማስረጃ አገናዝበው በተከሰሱበት ሁኔታ አቋማቸውን ጠይቀው ካጠናቀቁ በኋላ ከቀረበባቸው የሐሰት ውንጀላ ነጻ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ሰነድ ለቅዱስ ሲኖዶስ አቅርበው እልባት አግኝቷል።
በመሆኑም ከጉባኤው ፍጻሜ ማግስት ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል በጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በቀረበብኝ የስም ማጥፋት ክስ አጣሪ ኮሚቴ ተሰይሞ በማጣራት ነጻ ስላደረገኝ የማስረጃ ወረቀት እንዲሰጠኝ ብለው ለቅዱስ ፓትርያርኩ አመልክተው ስለተፈቀደላቸው የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ነጻ እንደሆኑ የሚገልጽ ማስረጃ መስጠቱን ይፋ አድርጎአል፡፡ ይህንን ቅዱስ ሲኖዶስ የሰጣቸው ማስረጃ ከዚህ ቀጥለን አቅርበነዋል።

የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ነጻ እንደሆኑ የሚገልጽ ማስረጃ [ እዚህ ይጫኑ ]
መምህር አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል (ቆሞስ)አቋማቸውን ተጠይቀው የሰጡት መልስ[እዚህ ይጫኑ]