Tuesday, June 19, 2012

«አዎ! ዛሬም ሰዎች የእምነት ነጻነታቸው ይታፈናል!»


    የዛሬን አያድርገውና አፄ ሱስንዮስ ኮትልከዋል/ካቶሊክ ሆነዋል/ በሚል የምታ ነጋሪት፤ ክተት ሠራዊት ዘመቻ የጎንደር አደባባይ  በደም መጨቅየቱን፤ ሰማዕትነት አያምልጥህ በሚል  ጥሪ በአንድ ቀን ብቻ ከስምንት ሺህ ሰዎች በላይ ማለቃቸውን  ከተዘገበው አንብበናል። አፄ ሱስንዮስም ካቶሊክ ከመሆናቸው የተነሳ እግዚአብሔር ተቆጥቶ ምላሳቸው አንድ ክንድ ያህል ተጎልጉሎና ወደ ቀደመ መጠኑ አልመለስ ብሎ ካስቸገረ በኋላ እያጓጎሩ እንደሞቱ በጽሁፍም፤ በአደባባይም እስከዛሬ ይተረካል። የያኔው ካቶሊክና የዛሬው የኢትዮጵያ ካቶሊክ በእግዚአብሔር ዘንድ ያላቸው ቅጣት ይለያይ እንደሆነ የአፄውን የትረካ ታሪክ ፈጣሪዎችን  እየጠየቅን፤ እኛ ግን እስከሚገባን ድረስ  ሱስንዮስ ካቶሊክ ለመሆን እምነቱን ስለለወጠ  እግዚአብሔር ምላሱን አንድ ክንድ ጎልጉሎ ገደለው የሚለው  ታሪክ የፈጠራ ውጤትና ካቶሊክነት  ከተቀበልክ ምላስህ እየተጎለጎለ ትሞታለህ የሚል  ሽብር በህዝቡ ውስጥ ለመርጨት ረበናት የፈጠሩት ተንኮል እንጂ  ዛሬ በኢትዮጵያ ያሉ ካቶሊኮች ሁሉ ምላሳቸው እየተጎለጎለ በየሜዳው ሞተው ባለቁ ነበር።  እየጨመሩ እንጂ እየጠፉ መሆናቸውን አላየንም።

የሚያሳዝነው ነገር እግዚአብሔርን  ጨካኝና  ርኅራኄ የለሽ አድርጎ በመሳል ይኼው ተረት እስከ ዛሬ በአደባባይ እየተነገረ መገኘቱ ነው።  ሰዎች የእውነትን ወንጌል በተከታዮቻቸው መካከል በማዳረስ ከእምነታቸው ሳይናወጡ፤ ጸንተው ከአምላካቸው ጋር ያላቸው ግንኙነት የጠበቀ እንዲሆን ማድረግ ሲያቅታቸውና ሌላ ተገዳዳሪ እምነት ብቅ ብሎ ቀዬና መንደሩን ሰፈርና ሀገሩን በትምህርቱ ሲበጠብጠው፤  ወዮልህ! ኮንትሮባንድ ሃይማኖት መጣልህ፤ ከእነሱ አዳራሽ ከገባህ አትመለስም፤ ምናምን ያቀምሱሃል! ወደሚል የጭራቅ ሊበላህ ነው ማስፈራሪያ ጩኸታቸው ይገባሉ። ወንጌሉን በሰዎች ልቡና ዘርተው መልካም ፍሬ ማፍራት ሲሳናቸው ከማስፈራሪያው ባሻገር መጤ የተባሉትን ቤተ እምነቶች ወደማፍረስና አማኞቹንም ወደ መግደል ይወርዳሉ። ዛሬ ወንጌላውያን የሚባሉት ኢትዮጵያውያን ቤተ እምነቶች አሁን ላሉበት ደረጃ የደረሱት ተገድለው፤ ተሰደው፤ ታስረው፤ ተገርፈው፤ ተቃጥለው ስለመሆኑ ማንም ኅሊና ያለው ሰው የሚዘነጋው ነገር አይደለም። 

Monday, June 18, 2012

«ፍቅር ለይኩን ያቀረበው ትችት ውሃ የማይቋጥር ወንፊት ነው»

 
በአባ ሰላማ ድረ ገጽ ላይ «ፍቅር ለይኩን» የተባለ ሰው ስለየትኞቹ  ስም አጥፊ ብሎጎች ለመናገር እንደፈለገ ስማቸውን  ባይገልጽም እሱን ደስ ያላሰኘውን ነጥብ በማመልከት፤ የሰዎችንም ኃጢአት መዘርዘር ጥሩ እንዳልሆነ  መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥቅሶችን በማስረጃ አቅርቦ ምክርና ተግሳጽ ለመስጠት ሲሞክር ተመልክተናል።
ይህ በአባ ሰላማ ድረ ገጽ ላይ ጽሁፉን ያቀረበው «ፍቅር ለይኩን» የተባለው ሰው ፤ በፖለቲካው ዓለም ደከመን፤ ሰለቸን  ሳይሉ የኢሕአዴግን መንግሥት በማጥላላትና በመቃወም ሌሊትና ቀን በሚደክሙት ድረ ገጾች ላይ የተለያዩ ፖለቲካዊ መጣጥፎችንና አንዳንዴም መንፈሳዊ መሰል የነቀፋ ጽሁፎችን  የሚያቀርበው የደቡብ አፍሪካው «ፍቅር ለይኩን»  መሆኑን የምናውቀው ከስሙ ባሻገር «ሻሎም፤ ሰላም» በሚለው የጽሁፉ ማሰረጊያ  ቃል የተነሳ እሱነቱን ብንገምት ከእውታው የራቅን አይመስለንም።
ከዚህ ተነስተን ስለአቶ ፍቅር ለይኩን  ጽሁፍ ጥቂት ለማለት እንወዳለን።
 አቶ ፍቅር ስለአባቶች መዋረድና አለመከበር ተገቢ መሞገቻ ይሆነው ለመከራከሪያነት የተጠቀመበትን ዐውደ ጥቅስ  በማስቀደም እንጀምር።
‹‹ደፋሮችና ኩሩዎች ሆነው ሥልጣን ያላቸውን ሲሳደቡ አይንቀጠቀጡም፣ ዳሩ ግን መላእክት በኃይልና በብርታት ከእነርሱ ይልቅ ምንም ቢበልጡ በጌታ ፊት በእነርሱ ዘንድ የስድብን ፍርድ አያመጡም…፡፡›› ፪ጴጥ ፪፣፲፩፡፡
ይህን ጥቅስ አቶ ፍቅር ለይኩን ያቀረበው ምንም ይስሩ ምንም፤ ምንም ያድርጉ፤ የቱንም ያህል ይበድሉ፤  ስለ ጳጳሳት አትናገሩ፤ ምክንያቱም ወንጌል አትናገሩ ብሏልና ሲል የአፍ መዝጊያ ጥቅስ በማቅረብ ሊሞግተን ይፈልጋል። ጥቅሱ ስለማን እና ስለምን እየተናገረ እንደሆነ ግን አያብራራም። መቼም ምግባረ ብልሹና የጥፋት ኃይል ለሆኑ ሹመኞች ሁሉ እንድንገዛ የተነገረ ነው  እንደማይለን ተስፋ እናደርጋለን። እንደዚያማ ከሆነ አቶ ፍቅር የኢህአዴግ መንግሥት ክፉና መሰሪ ነው፤ የአባ ጳውሎስ አስተዳደር አጥፊና ከፋፋይ ነው እያሉ ለኢህአዴግ ውድቀት በሚሰሩ ድረ ገጾች ላይ ጽሁፎቹን ሲለቀልቅ ባልዋለም ነበር። ምክንያቱም ወንጌል እንደዚህ ሲል ያስጠነቅቀዋልና።
ስለ ጌታ ብላችሁ ለሰው ሥርዓት ሁሉ ተገዙ፤ ለንጉሥም ቢሆን፥ ከሁሉ በላይ ነውና፤
ለመኳንንትም ቢሆን፥ ክፉ የሚያደርጉትን ለመቅጣት በጎም የሚያደርጉትን ለማመስገን ከእርሱ ተልከዋልና ተገዙ። 1ኛ ጴጥ 2፤13-14
ኢህአዴግን መቃወምም ሆነ መደገፍ መብት በመሆኑ ጸረ ኢህአዴግ ድረ ገጾች አቋማቸውን ግልጽ አድርገዋል። የማያሻማ ሆኖ «ለንጉሥም ቢሆን ተገዙ፤ ክፉ የሚያደርጉም ቢሆኑ መኳንንቱ ከላይ ተልከዋልና» የሚለውን የወንጌል ቃል ጨቋኞች፤ አምባገነኖችንና አላውያን መሪዎችን ሁሉ አሜን ብለን እንድንሸከም የሚናገር ቃል አይደለም ከሚል ጽንሰ ሃሳብ የተነሳ እየታገሉ ይገኛሉ። አቶ ፍቅር ደግሞ በነዚያው ድረ ገጾች ስሜቱን በጽሁፍ እየገለጸ ሲያበቃ  ከወንጌል ቃል ጠቅሶ ለምግባረ ብልሹዎችና ለሥርዓት አፍራሾችም ቢሆን ተገዙ በማለት ሊያስተምረን ይፈልጋል። ምነው ጽሁፎቹን ለሚያቀርብባቸው ድረ ገጾች የእናንተ ተቃውሞ ቃለ እግዚአብሔርን የተጻረረና ሕገ እግዚአብሔርን ያፈረሰ ስለሆነ አርፋችሁ ተቀመጡ፤ ዝም ብላችሁም ለኢህአዴግ ተገዙ! የሚል ምክርና ጽሁፍ ያላቀረበላቸው? ብለን ስንጠይቅ የምናገኘው መልስ እኔና መሰሎቼ የምንጠላው ሲጻፍበት እንጂ የምናወዳቸው ሲነኩብን ያመናል የሚል ቃና ይሰጠናል።

Friday, June 15, 2012

እጃችሁን ለእግዚአብሔር ስጡ" (፪ዜና ፴፥፰)

ከዶ/ር አምሳሉ ተፈራ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፊሎሎጂ ዲፓርትመንት
ረዳት ፕሮፊሰር
ለሁሉ ፈጣሪ ለእግዚአብሔር ራስን መቀደስና ከኃጢአት መለየት ለሰው ሁሉ የቀረበ ጥሪ ነው። ይህን ዘንግተው የነበሩ ሕዝበ እስራኤል ወደ አምላካቸው እንዲመለሱና ሁለንተናቸውን ለእርሱ እንዲሰጡ የተላከላቸው መልእክት ነው ርእሳችን እኛንም ይመለከታልና እንደሚከተለው በዝርዝር እንየው።
የሚታየውንም የማይታየውንም የፈጠረ፣ በባሕርም በየብስም ያሉትን ያስገኘ፣ ሰውን ለክብሩ ወራሽነትና ለስሙ ቀዳሽነት የወሰነ፣ ዓለምን ሲፈጥር አማካሪ ያልፈለገ፣ ፍጡሩን በመመገብና በመውደድ ወደር የሌለው፣ ለሰው ልጆች ራሱን አሳልፎ የሰጠ ነው ቸሩ አምላካችን እግዚአብሔር። ይህን ጌታ በምንም ልንለውጠውና ልንተካው አንችልም። አምላክ ነውና ተወዳዳሪ የለውም (ኢሳ. ፵፣ ፲፪ - ፲፬)
የርእሳችን መነሻ የሆነው «እጃችሁን ለእግዚአብሔር ስጡ» የሚለው ትምህርት የተሰጠው፣ ሃያ ዘጠኝ ዓመታት በእስራኤል ላይ በነገሠው ንጉሥ ሕዝቅያስ ነው። ምክንያቱ ደግሞ የእግዚአብሔርን ፋሲካ ለማድረግ የሚደረግ ቅድመ ዝግጅትን ይመለከታል። እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ስለሆነ፤ ወደ እርሱ መቅረብና ማገልገል የሚቻለው በንጽሕና ሆኖ ነው፤ አገልግሎትንም የሚቀበለው ያለቸልታ በትጋት ሲሆን ነው። «ልጆቼ ሆይ በፊቱ ትቆሙና ታገለግሉት ዘንድ፥ ታጥኑለትም ዘንድ እግዚአብሔር መርጦአችኋልና ቸል አትበሉ፤ ብሎ ያዘዘን ለዚህ ነው (፪ዜና. ፳፱፣፲፩)።
«ንጉሡ ሕዝቅያስ ለእግዚአብሔር ፋሲካ እንዲደረግ ወደ እስራኤልና ወደ ይሁዳ ለዐሥራ ሁለቱም ነገደ እስራኤል መልእክት ላከ። ነገር ግን ካህናቱ ገና በሚገባ ስላልተቀደሱ፣ ሕዝቡም በኢየሩሳሌም ተጠቃለው ስላልተሰበሰቡ፤ ፋሲካው በደንብ ሲዘጋጁ በቀጣዩ ወር እንዲከበር ተወሰነ። ለቀጣዩ ወር ግን ሁሉም ከያለበት ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ድረስ እንዲሰባሰብ እንዲህ የሚል ዐዋጅ ተነገረ፣ «የእስራኤል ልጆች ሆይ ... እግዚአብሔርን እንደ በደሉ እንደ አባቶቻችሁና እንደ ወንድሞቻችሁ አትሁኑ። አባቶቻችሁም እንደ ነበሩ አንገተ ደንዳና አትሁኑ፤ እጃችሁንም ለእግዚአብሔር ስጡ፤ ለዘላለም ወደ ተቀደሰው ወደ መቅደሱም ግቡ፤ ጽኑ ቁጣው ከእናንተ እንዲመለስ አምላካችሁን እግዚአብሔርን አምልኩ። (፪ዜና ፴፣፯-፰)።