Showing posts with label ትምህርት. Show all posts
Showing posts with label ትምህርት. Show all posts

Sunday, June 8, 2014

«የዓላማ ሰው ከመሆን የሚከለክል ማንነትና መፍትሄው»

[«ከዓላማ መር መጽሐፍ» ለንባብ እንዲመች ተደርጎ የተወሰደ]

ማንኛውም ሰው ሕይወት በአንድ ነገር ግፊት ይመራል። ብዙ መዝገበ ቃላት «አንቀሳቀሰ» ለሚለው ግሥ፦ መራ፤ ተቆጣጠረ ወይም አቅጣጫን ወሰነ» የሚል ፍቺ ይሰጡታል። መኪናም ነዳህ፤ ሚስማር በመዶሻ መታህ ወይም ኳስ አንከባለልህ፤ በዚያን ወቅት ያንን ነገር እየመራህ፤ እየተቆጣጠርክና አቅጣጫውን እየወሰንክ ነው። ታዲያ ልክ እንዲሁ ሕይወትህን የሚመራው ኃይል ምንድነው?
   በአሁኑ ጊዜ በአንድ በሆነ ችግር በሆነ ጫና፤ ወይም ማለቅ ያለበትን ሥራ ለመጨረስ በጥድፊያ በመራመድና በመንቀሳቀስ ላይ ትገኝ ይሆናል። በክፉ ትዝታ፤ በአስበርጋጊ ፍርሃት ወይም በቅጡ ባልገባህ አንድ ኅሊናዊ እምነት ትመራ ይሆናል። ሕይወትህን ሊያንቀሳቅሱና ሊመሩ የሚችሉ ብዙ ሁኔታዎች፤ የሕይወት ፋይዳዎችና ስሜቶች አሉ። ቀጥሎ የተዘረዘሩት አምስቱ /5/ በጣም የተለመዱና የታወቁ ናቸው።

1/ ብዙ ሰዎች በበደለኛነት ስሜት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ዘመናቸውን ሁሉ ጸጸትና ቁጭት ከወለደው ሃፍረታቸው ለመሸሸግ ሲሸሹ ይኖራሉ። ቁጭትና ጸጸት የሚመራቸው ሰዎች የትዝታ ተጠቂዎች ናቸው። ያለፈው ሕይወታቸው መጪውን ህይወታቸውን እንዲቆጣጠረው ይፈቅዱለታል። ብዙውን ጊዜ ሳያውቁት የሕይወት ስኬታቸውን እያበላሹ እራሳቸውን ይቀጣሉ። ቃየል ኃጢአትን በሠራ ጊዜ በደሉ ከእግዚአብሔር ህልውና ለየው፤ እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፦ «በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ» ዘፍ 4፤12። ይህ ቃል በዘመናችን ያለ ዓላማ በሕይወት ጎዳና የሚንከራተቱ ብዙ ሰዎችን ይገልጣል።
  ምንም እንኳን የዛሬ ኑሯችን የትናንት ውጤት ቢሆንም፤ የትናንት ኑሯችን ግን የዛሬ እስረኞች ሊያደርገን አይገባም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓላማ ባለፈው ሕይወትህ የሚወሰን አይደለም። እግዚአብሔር ሙሴ የተባለውን ሰው ገዳይ የነበረ ወደ ሕዝብ መሪነት፤ ጌዴዎን የተባለው ፈሪ ደግሞ ወደ ደፋር ጀግና ለውጧቸዋል። በአንተ ቀሪ ሕይወትም እንዲሁ አስደናቂ ነገሮችን ሊያደርግ ይችላል። እግዚአብሔር ለሰዎች አዲስ የሕይወት ጅማሬ በመስጠት የተካነ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል። «መተላለፉ የተከደነለት፤ ኃጢአቱም የተሸነፈችለት እንዴት ብሩክ ነው» መዝ 32፤1

2/ ብዙ ሰዎች በቂምና በቁጣ ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ደረሰብን የሚሉትን ጉዳት ከማስወገድ ይልቅ አቅፈውት ይኖራሉ። የጉዳታቸውን ስቃይ በይቅርታ ከማስወገድ ይልቅ በመደጋገም ያብሰለስሉታል። አንዳንዶቹ ደግሞ ዝም በማለት ንዴታቸውን ውስጣቸውን  «አምቀው» ይይዙታል። የቀሩት ደግሞ የታመቀ ቁጣቸውን «በማፈንዳት» በሌሎች ላይ ያምባርቃሉ። እነዚህ ሁሉ አጸፋዎች ጤናማ ያልሆኑ የማይጠቅሙ ናቸው።
  የአንተ ቂም መያዝ፤ ቂም በያዝክበት ሰው ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ይበልጥ የሚጎዳው አንተን ነው። የጎዳህ ወይም ያስቀየመህ ሰው ድርጊቱን ረስቶ የራሱን ኑሮ እየመራ ይሆናል፤ አንተ ግን ያለፈውን ቂም አምቀህ በመያዝ በብስጭት ትብሰለሰላለህ።
 ልብ በል! ከዚህ በፊት የጎዱህ ሰዎች አልጥል ባልከው የገዛ ቂምህ ካልሆነ በቀር እየጎዱህ ሊኖሩ አይችሉም። ያለፈው ነገርህ አልፏል። ማንም ሊቀይረው አይችልም። በመራርነትህ ራስህን ብቻ ነው የምትጎዳው። በቃ ለራስህ ስትል ካለፈው ተማርና ተወው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ «ሞኙን ሰው ብስጭት ይገድለዋል፤ ቂሉንም ቅናት ያጠፋዋል» ኢዮብ 5፤2

3/ ብዙ ሰዎች በፍርሃት ይመራሉ።

   እንዲህ ላሉ ሰዎች የሥጋታቸው ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉት ነገሮች በሕይወታቸው ያሳለፉት አስፈሪ ጉዳት በእውነት ላይ ያልተመሠረተ ምኞትና ጉጉት፤ ቁጥጥር ባለበት ቤተሰብ ውስጥ ማደግ፤ ወይም በተፈጥሮ የመጣ ፍርሃት ያለባቸው ይሆኑ ይሆናል። ምክንያቱም ምንም ሆነ ምን በፍርሃት የሚኖሩ ሰዎች ድፍረት ከማጣታቸው የተነሳ ሁኔታዎችን ስለማይጋፈጡ ብዙ እድሎች ያመልጧቸዋል። ፍርሃትን በድፍረት ከማሸነፍ ይልቅ ችግር ካለበት ሁኔታ መሸሽንና ባሉበት ሁኔታ ውስጥ መቆየትን ይመርጣሉ።
ፍርሃት እግዚአብሔር ያቀደልህን እንዳትሆን የሚያደርግህና እራስህን ያስገባህበት እስር ቤት ነው። በፍቅርና በእምነት መሣሪያነት ልትጋፈጠው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «በፍቅር ፍርሃት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሃት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።

4/ ብዙ ሰዎች ለመበልጸግ ባላቸው ምኞት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉት ሰዎች የሕይወታቸው ዋና ግብ ሀብት ማግኘት ነው። እንዲህ ያለው ሁልጊዜ ሀብት የመፈለግ ግፊት የሚመነጨው ብዙ ሀብት ሲኖረኝ ይበልጥ ደስተኛ፤ ይበልጥ ታዋቂና ዋስትና ያለኝ እሆናለሁ ከሚል የተሳሳተ አመለካከት ነው። እነዚህ ሦስቱም አስተሳሰቦች ስህተት ናቸው። ሀብት ሊያስገኝ የሚችለው ጊዜያዊ ደስታን ነው። ምክንያቱም ቁሳዊ ነገሮች ስለማይለወጡ ያሰለቹናል። በመሆኑም አዳዲስ ትልልቅና የተሻሉ ነገሮችን እንደገና እንፈልጋለን።
   ብዙ ሀብት ካለኝ ይበልጥ የተከበርኩና ተፈላጊ ሰው እሆናለሁ የሚልና የማይጨበጥ እምነትም አለ። እኛ እራሳችንን የተመንበት ዋጋ ከትክክለኛ ዋጋችን ጋር ተመሳሳይ አይደሉም። ዋጋህ አንተ አሉኝ ከምትላቸው ውድ ነገሮች አይወሰንም። በሕይወት እጅግ ዋጋ ያላቸው ቁሳዊ ነገሮች እንዳልሆኑ እግዚአብሔርም ይነግረናል።
  ስለ ገንዘብ በጣም የተለመደው የማይጨበጥ እምነት ብዙ ገንዘብ ካለኝ በሁሉ ነገር ዋስትናዬ በጣም የተጠበቀ ይሆናል የሚለው ነው። አይሆንም! በተለያዩና ከአቅም በላይ በሆኑ ምክንያቶች ሀብት ወይም ገንዘብ በቅጽበት ይጠፋል። እውነተኛ ድነት ወይም ዋስትና የምታገኘው ፈጽሞ ማንም ሊወስድብህ ከማይቻለው ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ካለህ ግንኙነት ነው።

5/ ብዙ ሰዎች በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት በመፈለግ ማንነት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ወላጆቻቸው ወይ ልጆቻቸው  ወይ ደግሞ አስተማሪዎቻቸው አለዚያም ሌሎች ወዳጆቻቸው ከእነርሱ የሚጠብቁትን ነገር ለማሟላት የሚያደርጉት ጥረት ሕይወታቸውን እንዲቆጣጠር ይፈቅዳሉ። አንዳንድ ሰዎች ከጎለመሱ በኋላም እንኳን ለማስደሰት አስቸጋሪ በሆኑ ወላጆቻቸው ተቀባይነትን ለማግኘት ይፈልጋሉ። ሌሎች ደግሞ ሰዎች ስለ እነርሱ የሚያስቡት ነገር እያስጨነቃቸው በእኩዮቻቸው ተጽእኖ ይመራሉ። የሚያሳዝነው  ግን ብዙዎችን ለማስደሰት የሚሞክሩ ሰዎች በሂደቱ ራሳቸውን ያጣሉ።
ለስኬት የሚያበቁ ቁልፍ ነገሮችን በሙሉ ባላውቅም ለውድቀት የሚያበቃው ዋነኛ፤ ነገር ግን ሁሉን ለማስደሰት መሞከር ነው። በሌሎች አስተሳሰብ መመራት እግዚአብሔር ለሕይወትህ ያለውን ዓላማ እንድትስት የሚያደርግህ መንገድ ነው። አላስፈላጊ ጭንቀት፤ እርካታ ያጣ ሕይወት ጥቅም ላይ ያላዋልከው ችሎታና ሌሎች ብዙ ነገሮች ሕይወትህን ሊያሸከረክሩት ይችላሉ። ሁሉም ግን የትም የማያደርሱ ናቸው።

ማጠቃለያ፤

ከላይ የተዘረዘሩትን አስወግደህ በዚህ ምድር ላይ የምትኖርበትን ዓላማ ያወቅህ ከሆንህ፤
1/ ኑሮህን እያጨናነቅህ አትመራውም።
2/ ትኩረት ማድረግ የሚገባህን ለይተህ ታውቃለህ።
3/ ለዓላማህ ትጋት ትቆማለህ።
4/ ለዘላለም ሕይወት ዋጋ ትሰጣለህ።
5/ የዚህ ዓለም መሪህ፤ አሳብህ ወይም የሌሎች ጫና ሳይሆን እግዚአብሔር ብቻ እንዲሆን ትፈቅዳለህ።


ስለሆነም በዚህ ምድር ላይ የምትኖረው ለምን እንደሆነ አስቀድመህ እወቅ! የምትኖረው እንደሰው በልተህና ጠጥተህ ቀንና ሌሊትን በማንነትህ ላይ እያፈራረቅህ ለመኖር አይደለም። ይህንንማ ሌሎች እንስሳትም ያደርጉታል። አንተ ግን በእግዚአብሔር ዓላማ የተፈጠርክ፤ ለእግዚአብሔር ዓላማ የተሰራህ ነህና በዚህ ዓላማ ላይ ቆመህ መገኘት አለብህ!

በዚህ ምድር ላይ የተፈጠረከው ለየትኛው ዓላማ እንደሆነ ታውቃለህ? እርምጃህን እየወሰንክ ያለኸውስ እንዴት ነው?

Thursday, May 22, 2014

ግዝት(ውግዘት)…ኑፋቄ….መናፍቅነት…ግዝት-ዘበከንቱ… እና ወፈ-ገዝት መሆን!


 ( በአማን ነጸረ )
1. ግዝት(ውግዘት)፡ ማለት አንድ ምዕመን(አማኝ) በአፉ ክርስቲያን ነኝ ቢልም በተግባር ከሃይማኖት ወጥቶ ከበጎ ምግባር አድጦ(ተዛንፎ) ሲገኝ ከማኅበረ ምዕመናን እንዲለይ በስልጣነ-ክህነት የሚፈጸም መንፈሳዊ ቅጣት ነው፡፡
2. የውግዘት ዓላማ፡(ሀ)ቤ/ክ እንዳትረክስ፣(ለ)ኑፋቄው ወደ ሌሎች እንዳይዛመት፣(ሐ)ተወጋዡ በንስሐ እንዲመለስ እድል ለመስጠት ነው፡፡
3. የውግዘት ቅድመ-ሁኔታዎች፡(ሀ)ተጠርጣሪው ከሃይማኖት እና/ወይም ከበጎ ምግባር መውጣቱን ማረጋገጥ፣(ለ)ከጥፋቱ/ከክህደቱ እንዲመለስ ደጋግሞ መገሰጽና መምከር፣(ሐ)ተመክሮ ካልተመለሰ በስልጣነ-ክህነት አውግዞ መለየት፣(4)ውግዘቱ እንደጥሰቱ ዓይነት ከማዕረግ ዝቅ ማድረግ ወይም ስመ-ክርስትናን ነጥቆ መለየት ሊሆን ይችላል፡፡ከዚህ በኋላ ድርጊቱ-ኑፋቄ ተወጋዡም-መናፍቅ ይባላሉ፡፡በነገራችን ላይ ምንፍቅና የሚል ቃል በየመጻህፍቱ አላየንም፡፡በግእዙ ኑፋቄ ነው የሚባለው፡፡በአማርኛ መናፍቅነት፡፡
4. ግዝት-ዘበከንቱ እና ወፈ-ገዝት መሆን፡ ከላይ ያሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ያላሟላ ግዝት ግዝት-ዘበከንቱ ሲባል ገዛቹም ወፈ-ገዝት ይባላል፡፡ነገር ግን ተጠርጣሪው በግልጽ የተወገዘ ሃይማኖትንና ምግባርን ሲያራምድ ያገኘነው እንደሆነ መናፍቅ ብንለው ፍርድ የለብንም፡፡
5. ከንቱ እና ከንቱ አንድ ወገን ብለን ስለመርገም ዘበከንቱም እንናገር፡ ሀቅ ላይ ያልተመሰረተና የሚረገመውን ሰው ህሊና የመውቀስ አቅም የሌለው ከንቱ እርግማን በመጽሐፈ ምሳሌ 26 ቁ 2 እንደተገለጸው….እንደሚተላለፍ ድንቢጥ፣ወዲያና ወዲህም እንደሚበር ጨረባ እንዲሁም ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም፡፡ፍትሐ ነገስቱም በአንቀጽ 11 እንዲህ አይነቱን ረጋሚ “ወኩሎ ዘይረግም ይረግም ነፍሶ” ይለዋል::
ምንጭ፡ (1) መርሐጽድቅ ባህለ ሃይማኖት በ1988 ዓ.ም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የታተመ ገጽ 157 እስከ 161 ፣ (2)የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ-237፣ (3) ጥቅሶች፡ ማቴ 18 ቁ 15-18፣2ተሰ 3ቁ14፣ቲቶ 3 ቁ 11፣1ጢሞ 1ቁ 19፣2ጢሞ 2 ቁ 17፣1ቆሮ 5 ቁ 5፣2ቆሮ 2 ቁ 6
መነሻ፡ በ40 ቀን ያገኘነውን ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ባልተሰጠ ስልጣነ-ክህነት ሊነጥቁ የሚሞክሩ ወፈ-ገዝት ወንድሞቻችን!!

Saturday, July 6, 2013

የካህናቱ የ«እናውቃለን» እና «አናውቅም» እውቀት!



ካህናቱ ከተራው ሕዝብ በቃለ እግዚአብሔር የተሻለ እውቀት እንዳላቸው ይታመናል። ይጠበቃልም። ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ መጻሕፍቱ ላይ «እያዩ የማያስተውሉ» ተብሎ የተነገረባቸው ደግሞ እነዚህ የእውቀት ማዕድ ያካፍሉ ዘንድ በክህነት አገልግሎት የተሰለፉትን ሆኖ ስናይ እጅግ ያስገርመናል። ካህናቱ እያዩ የማያስተውሉ ከሆነ የሚመሩት ሕዝብ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አይከብድም።
አይሁዳውያኑ ካህናትና የመጻሕፍቱ መምህራን ስለብሉያት መጻሕፍት በቂ እውቀት እንዳላቸው ከመገመቱም በላይ ራሳቸውም በቂ እውቀት እንዳላቸው ስለራሳቸው ሲመሰክሩ እናነባለን። ይሁን እንጂ እውቀታቸው ሲመዘን ብዙውን ጊዜ አውቀን ተናገረናል የሚሉት አንደበት እርስ በእርሱ ከመጋጨቱ አልፎ ተርፎም ሰዎቹ ራሳቸውም ጭምር እርስ በእርሳቸው የሚጋጩበትም አጋጣሚ ታይቷል።
ለዚህም ጥሩ ማሳያ የሚሆነን ከላይ በርዕሱ ላይ ያስቀመጥነው ነጥብ ጥሩ መነሻ ይሆነናል። እነዚህ የእውቀት ማዕድ አደላዳዮች እንደሆኑ የሚታሰብላቸው ካህናት በአንድ ወቅት በአንድ ምላስ ሁለት ቃል በመናገር አንዴ «እናውቃለን» ያሉትን አንደበት ሽረው ወዲያው ደግሞ «አናውቅም» በማለት ሲናገሩ እናገኛቸዋለን።
ካህናቱ ይኸንን ቃል የተናገሩት ጌታ ኢየሱስ ከደብረ ዘይት ተራራ መልስ በቤተ መቅደስ ብዙ ካስተማረ በኋላ በድንጋይ ሊወግሩት በፈለጉና በመካከላቸው ተሰውሮ በወጣ ጊዜ ነበር።  ከዚያ አልፎ እንደወጣ ዘመኑን ሁሉ ዓይነ ስውር የነበረና በልመና የሚተዳደር አንድ ሰው ባገኘ ጊዜ «ደቀ መዛሙርቱም መምህር ሆይ፥ ይህ ሰው ዕውር ሆኖ እንዲወለድ ኃጢአት የሠራ ማን ነው? እርሱ ወይስ ወላጆቹ? ብለው ጠየቁት» ዮሐ 9፤2
ጌታም ሲመልስ፤ «በራሱም ይሁን በቤተሰዎቹ ኃጢአት ሳይሆን የእግዚአብሔር ሥራ ይገለጽ ዘንድ» እንደዚያ መሆኑ ከገለጸላቸው በኋላ የመጣበትን የማዳን ስራ በማሳየት በምራቁ ጭቃ ለውሶ ዓይኑን በመቀባትና በሰሊሆም መታጠቢያ በመታጠብ ዓይነ ብርሃኑ እንዲመለስ እንዳደረገለት እናነባለን።
የሚገርመው አስደናቂ ነገር የሚጀምረው እዚህ ላይ ነው። ዓይነ ብርሃኑ የጠፋው ይህ ሰው ዓይኑ ከበራለት በኋላ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ከመወለዱ አንስቶ እውር የሆነን ሰው ዓይን ያበራ ሰው ስለመኖሩ እንዳልተሰማ በመሰከረ ጊዜ ካህናቱ በተቃራኒው ሃሳቡን በመቃወም «ይህ ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» በማለት የመጀመሪያ ቃለ ጽርፈት ሲሰነዝሩ ታይተዋል። ዮሐ 9፤24
ዓይነ ስውር የነበረው ሰው የተደረገለትን ነገር አድንቆ ለካህናቱ ሲመልስ «ኃጢአተኛ መሆኑን አላውቅም፤ ዕውር እንደ ነበርሁ አሁንም እንዳይ ይህን አንድ ነገር አውቃለሁ አለ» ዮሐ 9፤25
ካህናቱ የማያውቁትን የብርሃን ጌታ እንደሚያውቁት አድርገው በላዩ ላይ የሀሰት አንደበት ሲከፍቱ፤ እውር ሆኖ መወለዱንና አሁን ግን ብርሃን እንደተሰጠው የተግባር ምስክር ሆኖ የራሱን ሕይወት ስለቀየረው ስለኢየሱስ ማንነት ከካህናቱ በተሻለ ማወቅ መቻሉ በእርግጥም አስገራሚ ነገር ነው። ምናልባትም ራሱ ባለቤቱ እንደተናገረው « የማያዩ እንዲያዩ የሚያዩም እንዲታወሩ እኔ ወደዚህ ዓለም ለፍርድ መጣሁ አለ» ያለው ቃል እንደተፈጸመባቸው የሚያስረዳን ነገር ይሆናል። ዓይነ ስውሩ የሥጋ ብርሃንም፤ የልቡና ዓይንም ሲገለጥለት የልቡናቸውን ብርሃን በእውቀት እንደሞሉ የሚያስቡና ዓይነ ሥጋቸውም ከልደታቸው ጀምሮ ምሉዕ እንደሆነ የሚተማመኑት ካህናት ግን በሁለቱም ወገን መጋረዳቸውን አንደበታቸው ያረጋግጣል። ይኸውም ከእናቱ ማኅጸን አንስቶ እውር ሆኖ የተወለደን ሰው ብርሃን መስጠት የቻለ ስለመኖሩ ከዚህ ቀደም እንዳልተሰማና ይህንን ለማድረግም ከእግዚአብሔር ካልሆነ በስተቀር ኃጢአተኛ ሰው ብርሃን መስጠት እንደማይችል ልቡናቸው እያወቀ የለም! ይህ ሰው «ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» ሲሉ በቃለ ሀሰት ምስክርነት እስከመስጠት ያደረሳቸው ነገር እያዩ የማያዩ ሰዎች ስለሆኑ ነበር።
 እነዚህ ልበ ዕውራን ካህናት የዕውርነታቸው መጠን የለሽነት የሚገለጸው ደግሞ የተነገራቸውን እውነት ለመቀበል አለመፈለጋቸው ብቻ ሳይሆን እየተነገራቸው የሰሙትን ለመሸከም የሚችል ልቡና የሌላቸው መሆናቸው ደግሞ ሌላው አስገራሚ ነገር ነው።
ካህናቱ ዓይኑ ስለበራለት ሰው በቅድሚያ ጥያቄ ያቀረቡት ለወላጆቹ ነበር። «እናንተ ዕውር ሆኖ ተወለደ የምትሉት ልጃችሁ ይህ ነውን? ታድያ አሁን እንዴት ያያል? ብለው ጠየቁአቸው» ዮሐ 9፤19
ወላጆቹም፤ ዓይነ ስውሩ ልጃቸው አሁን ዓይኑ እንደበራለት ከመሰከሩ በኋላ ማን እንዳበራለትና እንዴት እንደበራለት እንደማያውቁ በተናገሩ ጊዜ ካህናቱ ሁለተኛ ማረጋገጫ በመሻት ወደ ጉዳዩ ባለቤት በመሄድ ጥያቄያቸውን ዓይነ ስውር ለነበረው ሰው አቅርበዋል። እሱም ሲመልስ «ያበራለት ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን እንደማያውቅ፤ ነገር ግን ዓይኑን እንዳበራለት እንደሚያውቅ ሊገባቸው በሚችል ቋንቋ በግልጽ ተናግሮ ሳለ መልሰው በጥያቄ ሲያደርቁት ይታያሉ። ዳኅጸ ልሳን በመፈለግ ለመክሰስና ሸንጎ አቁሞ ለማስወገዝ ወይም ለማስደብደብ ካልሆነ በስተቀር ወደእውነት ለመመለስ ለቀና ነገር ቀና ልብ መቼም የሌላቸው ናቸው።
«ደግመውም። ምን አደረገልህ? እንዴትስ ዓይኖችህን ከፈተ? አሉት» ዮሐ 9፤26 ዓይኑ የበራለትም ሰው ነገረ ስራቸው ሁሉ አስገርሞትና እንደዚህ አብዝተው ጥያቄ መጠየቃቸው በተደረገው ተአምር ተስበውና በኢየሱስ የማዳን ፍቅር ተሸንፈው ደቀ መዛሙርቱ ለመሆን የፈለጉ መስሎት በመሰላቸት ስሜት እንዲህ ሲል መለሰላቸው።
«እርሱም መልሶ፦ አስቀድሜ ነገርኋችሁ አልሰማችሁምም፤ ስለ ምን ዳግመኛ ልትሰሙ ትወዳላችሁ? እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን? አላቸው» ዮሐ 9፤26
ካህናቱ ነገረ መጻሕፍትን አዋቂዎች ናቸው፤ እድሜአቸውን ሁሉ በመቅደሱ ሲያገለግሉ ኖረዋል፤ በዚያ ላይ ዓይናቸው አልታወረም። በእርግጥም መጠየቃቸው ደቀመዛሙርት ለመሆን ከመፈለግ የተነሳ ሊሆን እንደሚችል ቢገመት ስህተት ላይሆን ይችላል። ስህተቱ ግን ካህናቱ ክርስቶስን ለማወቅ አለመቻላቸው ብቻ ሳይሆን ለማወቅም አለመፈለጋቸውን አለመረዳት ነው። ልበ ዕውራኑ ካህናትም ሲመልሱ እንዲህ አሉ።
«ተሳድበውም። አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ፥ እኛ ግን የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን፤ እግዚአብሔር ሙሴን እንደ ተናገረው እኛ እናውቃለን፥ ይህ ሰው ግን ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት» ዮሐ 28-29
ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው ዓይኑ ብርሃን ስለማግኘቱ ለማወቅ አንድም ቦታ መፈለጋቸውን አናነብም።  ዓይነ ብርሃኑ የተመለሰለትን ሰው በጥያቄ ከማሰለችታቸው በላይ ተመጣጣኝ መልስ ቢሰጣቸው ካህናት ሆነው ሳለ የምላሻቸው ማሟሺያ ስድብ ጭምር ማከላቸው በእርግጥም እውቀት በተለይም መንፈሳዊ እውቀት ከላይ ከሰማይ ካልተሰጠ በስተቀር በትምህርትና በክህነት ማዕርግ ሊገኝ እንደማይችል ያረጋግጥልናል። ይህንንም እውነት ጌታችን ራሱ እንዲህ ሲል መናገሩ የታሪኩን እውነታ ያሳያል። «የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም» ዮሐ 6፤44  ለሰው ልጅ ትምህርትና እውቀት አስፈላጊ የለውጥ መሣሪያዎቹ እንደሆኑ ባይካድም  ከላይ ካልተሰጠ በስተቀር ይህ በራሱ ወደእውነተኛ መገለጥ ሊያደርስ አይችልም። ብዙ አዋቂዎች ባለማወቅ ደመና ተሸፍነው መገኘታቸው ዘወትር የምንመለከተው ሐቅ ነው።
ካህናቱ ዓይነ ስውሩን ከሰደቡት በኋላ «አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ፤ እኛ ግን የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን» አሉት።  የኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆን የተናቀ ደረጃ ሲሆን የሙሴ ደቀ መዝሙር መሆን መቻል በካህናቱ ዘንድ ትልቅ እድገትና እውቀት መሆኑ ነው። ዛሬም «የእርቃችን መንገድና እውነት፤ መድኃኒትና በር ኢየሱስ ብቻ» ብሎ መጥራት ያስነቅፋል። በዚህ ላይ ልዩ ልዩ የመዳኛ መንገዶችን፤ ብዙ ብዙ አማላጆችን ካልያዝክ በስተቀር  «ኢየሱስ» በሚለው ስም ላይ ብቻ መታመን ዋስትና እንደሌለው የሚያስተምሩ ካህናት አሉ። «ፊት የማያስመልሱ፤ አንገት የማያስቀልሱ» ብዙ የቃል ኪዳን ባለቤቶችን ከፊትህ ካላደረክ ገነትን በኢየሱስ ይቅር ባይነት ላይ ብቻ ታምነህ እንዲህ በቀላሉ አታገኝም! የሚሉ መምህራንና ካህናት አሉ። «ስድስቱን ቃላተ ወንጌልንና ዐሠርቱ ቃላተ ኦሪትን» ለመፈጸም ከመፈለግ ይልቅ «ተአምሯን ለመስማት ተሽቀዳደሙ» የሚለውን ማደንዘዣ ዘወትር የሚያነበንቡ ልበ እውራን ካህናት አሉ። «ኢየሱስ ጌታ ነው»  (1ኛ ቆሮ 12፤3) ብሎ መጥራት ይህ የመናፍቅ አባባል ነው የሚሉና ይህንንም በመፍራት በአፋቸው የማስገቡ ካህናት አሉ።
ካህናተ ቤተ መቅደስ፤ ዓይነ ብርሃኑ የተመለሰለትን ሰው ከሰደቡ በኋላ «አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ» ብለው ለእነሱ ጸያፍ የመሰላቸው፤ ነገር ግን የኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆን ከመቻል የተሻለ እድል እንደሌለ ስለማያውቁ ራሳቸውን የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ከመሆን አግልለው «እኛ የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን» ማለታቸው ትልቁንና የተሻለው መጣላቸው መሆኑን አላወቁትም። እናውቃለን ይላሉ፤ አያውቁም፤ እናያለን ይላሉ እውራን ናቸው። አብ ስለወልድ ማንነት የገለጠላቸው ግን «ኢየሱስ ጌታ ነው» ሲሉ አያፍሩም። «በሩ እኔ ነኝ» ስላለ ዕለት ዕለት ያንን በር ብቻ ያንኳኳሉ። «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» ያለው ቃል ስለማይታበል ተስፋቸው እሱ ነው።  የሌሎችን በር በመደብደብ፤ እባካችሁ ሂዱና ያንን «በሩ እኔ ነኝ» ያለውን ጌታ አስከፍቱልን ብለው በማስቸገር ባልተነገረ ድካም ውስጥ ራሳቸውን ሲያሽከረክሩ አይገኙም። እሱን በቀጥታ ለለመኑት አምላካችን የማያሳፍር በቃሉ የታመነ ተለማኝ ነውና።
«እኔም እላችኋለሁ። ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል»   ሉቃ 11፤9
የሚገርመውና የሚደንቀው ነገር ካህናተ ሌዋውያኑ «ይህ ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን እናውቃለን» ሲሉ ቆይተው የደቀ መዝሙርነት ጉዳይ ሲነሳ የተናገሩትን ቃል ሸምጥጠው በመካድ «ይህ ሰው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም» ሲሉ መገኘታቸው ነው። «እግዚአብሔር ሙሴን እንደ ተናገረው እኛ እናውቃለን፥ ይህ ሰው ግን ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት» ዮሐ 9፤29  ከወዴት እንደሆነ ካላወቁት ከምን ተነስተው ነው « ይህ ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እናውቃለን» ብለው ለመናገር ድፍረት ያገኙት?  ለዚህ ሁሉ ያላዋቂ ሳሚ ዓይነት ምላሻቸው ዋናው ምክንያት ካህናቱ ራሳቸውን የሚስሉት ከሌላው የተሻለ እውቀትና ማንም ያልደረሰበት ትምህርት እንዳላቸው ስለሚያስቡ ብቻ ነው። እውነትና ከአብ ዘንድ ስለወልድ ያለው መገለጥ ከሌላ ከማንም ዘንድ ሊኖር ይችላል ብለው በፍጹም አያስቡም። ቢኖር እንኳን ከእነሱ የተለየውን ሁሉ እንደኑፋቄና ክህደት ይቆጥሩታል።
በዘመናችን የወልድን መሲህነት፤ ብቸና አዳኝነትና ከምድር እስከሰማይ የተዘረጋውን ሕያው መሰላል በማንሳት ሌሎችን በምትክነት አበጅተው፤ ለምትክነቱም የሚጠቅም መከላከያ ምሽግ ቆፍረው የሚሟገቱ ካህናትና አዘጭዛጭ ማኅበራት አሉ።  «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ አለው» ዮሐ 1፤52  የሚለውንና ከባለቤቱ ከራሱ የሰማነው ቃል አይበቃንም፤ የግብጻዊው መነኩሴ የህርያቆስም ይጨመርልን፤ አብሮም ይዳበል በማለት «አንቲ ውእቱ ሰዋስዊሁ ለያዕቆብ» መላእክት የሚወጡባትና የሚወርዱባት መሰላል አንቺ ነሽ (ቅዳሴ ማርያም) የሚሉ ካህናትና አዘጭዛጮች አሉ። ይህንን የቃል ልዩነት ለማስማማት ሲሉ አንዴ እናውቃለን፤ አንዴ ደግሞ አናውቅም የሚሉ ልበ እውራን አሉ። ራሳቸውን ከክርስቶስ ደቀ መዝሙርነት ሰልፍ አውጥተው እኔ የተክልዬ ልጅ፤ የሳማ ሰንበት፤ የዜና ማርቆስ፤ የአርሴማ፤ የሙሴ…………..የሚሉ አሉ። የአጵሎስና የኬፋ ዓይነት መሆኑ ነው።
«ጻፎችና ፈሪሳውያን በሙሴ ወንበር ተቀምጠዋል። ስለዚህ ያዘዙአችሁን ሁሉ አድርጉ ጠብቁትም፥ ነገር ግን እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደ ሥራቸው አታድርጉ። ከባድና አስቸጋሪ ሸክም ተብትበው በሰው ትከሻ ይጭናሉ፥ እነርሱ ግን በጣታቸው ስንኳ ሊነኩት አይወዱም። ለሰውም እንዲታዩ ሥራቸውን ሁሉ ያደርጋሉ፤ ስለዚህ አሽንክታባቸውን ያሰፋሉ ዘርፉንም ያስረዝማሉ፥ በምሳም የከበሬታ ስፍራ፥ በምኵራብም የከበሬታ ወንበር፥በገበያም ሰላምታና። መምህር ሆይ መምህር ሆይ ተብለው እንዲጠሩ ይወዳሉ» ማቴ 23፤2-7 ዛሬም በተግባር አለ። ካህናቱ ያውቃሉ ግን እውነትን አያውቁም!!

Sunday, June 23, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ (ክፍል ሦስት )



ከባለፈው ክፍላችን የቀጠለውን በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን ጠላት አስርጎ ያስገባውን የስህተት መንፈሱን አሰራር በቀጣይነት እንመረምራለን። ጥንተ ጠላታችን በእግዚአብሔር ዋና ቃል ውስጥ ጥቂት የስህተት ቃላትን ሰንቅሮ ማስገባት መቻሉ ጠቅላላ የአምልኮ ሥርዓታችንን እንደፈለገ ለማናጋት በር ስለሚያገኝ በዚህ ዙሪያ አጥብቆ ይሰራል። ይህንን እስትንፋሰ እግዚአብሔር የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ከአበው ሲወርድ እዚህ ዘመን የደረሰውን ጠብቆና ጠንቅቆ በማቆየት፤ ስህተት ሲገኝ በማቃናት፤ የጎደለውን በማረም፤ የሁል ጊዜ አዲስነቱን እንደያዘ፤ ትውልዱን እያደሰ መቀጠል እንዲችል የማድረግ ኃላፊነቱ የቅዱስ ሲኖዶስና የሊቃውንት ጉባዔው ሥልጣን ቢሆንም ምሁራኑ በዐረፍተ ዘመን በሞት ጥላ ሥር አርፈው ቦታቸውን በመልቀቅ ለጊዜው ጥሬ ትርጉሙን እንኳን ለመረዳት አቅሙ በሌላቸውና «ከተንስኡ ለጸሎት» በዘለለ ቃለ እግዚአብሔርን ለመመርመር ድክመት ቤቱን የሰራባቸው ወንበሩ ላይ ያለአቅማቸው በመቀመጣቸው ቅዱሱ መጽሐፍ ሊበረዝ ችሏል። ሊቃውንቱ ወደዳር ተገፍተው በደጀ ጠኝነት ያንጋጥጣሉ።፤ ገሚሱም በጋዜጣ አዟሪነት ያለቦታቸው ተሰማርተዋል። እነ «በአፍ ጤፍ ይቆሉ»  በሊቃውንት ስም የቤተክህነትን ገበያ ያደራሉ። መጋቤ ብሉይ ሠይፈ ሥላሴን የመሳሰሉ ሊቃውንት የደረሱበትን እውቀትና እውነት እንዳይተነፍሱ በድንቁርና መዶሻ ተመትተው እስከወዲያኛው አሸለቡ። ድኩማነ አእምሮዎች ሲያዋክቧቸው የቆዩት ብፁዕ አቡነ መርሐ ክርስቶስ እንኳን በዚህ በጎጋ ጉባዔያተኛ መካከል ባገኙት መንገድ ሁሉ ያካፈሉት ቃለ እውነት ብዙ ዘር ያፈራ ቢሆንም የተመኙትን ያህል ሳይሰሩ ያንን ሁሉ እውቀት ይዘውት የሄዱት ለቤተክርስቲያን ትልቅ ጉዳት መሆኑን እያየነው ነው። 
   እንደው ለመሆኑ ከእሳቸው ወዲያ በነገረ መጻሕፍትና ትርጉም አዋቂነት የሚጠራ ጳጳስ ማን ይሆን? ከተረትና ከእንቆቅልሽ በዘለለ ቃለ እግዚአብሔርን በምልዓትና በስፋት ማስተማር፤ ማረቅ፣ ማቃናት የሚችል አንድም ጳጳስ በዚህ ዘመን አለመኖሩ ብቻ ሳይሆን የሚቆጨውም ሰው አለመገኘቱ በጣም አሳሳቢ ነው። ሊቃውንት ጉባዔ የተባለው የእነ ክንፈገብርኤል አልታዬና የሊቀ ሥዩማን  ራደ መሥሪያ ቤት ሊቅነቱን ሳናይለት ዘመኑን ፈጠመ።  የሚብሰው ደግሞ ትልቁንና ዋናውን ቃለ እግዚአብሔር/መጽሐፍ ቅዱስ/ ጥንታዊውን የአበው ትርጉምና ሕግጋት ጠብቆ እንደንጹህ የምንጭ ውሃ ኮለል ብሎ የምእመናን የልቡና ጥማት እንዲያረካ ማድረግ አለመቻሉ ብቻ ሳይሆን የነበረውን መጽሐፍ አደፍርሰው፤ በጥብጠውና ከመርዝ ጋር ደበላልቀው በማቅረብ ሊቃውንት የሚባለውን ክብር ትቢያ ላይ ወድቆ እንዲቀር ማድረጋቸው ሌላው አሳዛኙ ገጽታቸው ነው። 
የሊቃውንት ጉባዔነትን ሥልጣን ተሸክመው የራሳቸውን ግዙፍ ድክመትና ስህተት በማየት ከማረም ይልቅ  የመንደር ላይ ጽሁፎችንና በራሪ ወረቀቶችን እየለቀሙ  አብረዋቸው የሌሉ ሰዎችን በማውገዝ መጠመዳቸው የሊቅነት ስያሜ  አቅጣጫው የጠፋ ይመስለናል። በየተአምሩ፤ በየድርሳኑ፤ በየገድላቱ፤ በየመጽሐፍ ቅዱሱ የተሰነቀረውንና ማን እንዳስገባው የማይታወቀውን ከእግዚአብሔር ቃል ሃሳብና ትርጉም የማይስማማውን እየመረመሩ ማስተካከል ሲገባ ሊቃውንት ጉባዔው የተኛበትን ሥራ በፈቃዳቸው ተረክበው «ይህ፤ ይህ ግድፈት ነው፤ ሊታረም ይገባል፤ የቀደምት አበው አስተምህሮ ሥፍራውን ይያዝ » በማለት በማስረጃ አስደግፈው የጠቆሙ ሰዎችን ጽሁፍ እየለቀሙ አውግዘናል ማለቱ ሊቃውንት ጉባዔው ኮምፓስ እንደሌለው መርከብ ውቅያኖስ ላይ መንሳፈፉን ራሱ አረጋግጧል። ሰዎቹ ይታረም ያሉት የተጻፈውን ስህተት አንስተው እንደ ወንጌል ቃልና እንደአበው አስተምህሮ ይታረም ማለታቸው ወንጀል ሆኖ ሊያስወግዝ ቀርቶ እኛ መሥራት ያቃተንን ስለሰራችሁልን እናመሰግናለን ሊባሉ ይገባ ነበር።
እኛም አቅማችንና ችሎቻን የፈቀደውን ያህል በመረጃና በማስረጃ አስደግፈን  ሁሉም እንዲያውቀው በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን ጠላት አስርጎ ያስገባውን የስህተት ቃል ለማሳየት እንሞክራለን። 

1/ የብቻችን መጽሐፍ እንዴት?

በባለፈው ክፍል ሁለት ጽሁፋችን ለመጠቆም እንደሞከርነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በፊት እንደትርፍ የቀኖና መጻሕፍት ትቆጥራቸው የነበሩትና ከ2000 ዓ/ም መጽሐፍ ቅዱስ ህትመት በኋላ ግን እንደዋና  የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የደመረችው የመቃብያን መጻሕፍት ሦስት ክፍሎች ከአይሁዳውያን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ቁጥር ውስጥ የሌለ መሆኑን ለማሳየት ሞክረናል። በ3ኛውና በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበሩት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከኦሪት ዘፍጥረት እስከ ትንቢተ ሚልክያስ ያሉትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በ39 ክፍል መድበው ትክክለኛ የእግዚአብሔር ቃል የሆኑ የአይሁዳውያን መጻሕፍትን ሙሉ በሙሉ መቀበላቸውም ታሪክ ያስተምረናል። ከዚህ ውጪ የአይሁዳውያን መጻሕፍት ያልነበሩትን የኦሪት መጻሕፍት እንደብሉይ ኪዳን ለመቀበል የሚያስችል ሌላ ምክንያት የለም። ለእስራኤል ዘሥጋ የተሰጡ የእግዚአብሔር ቃል መጻሕፍት ሙሉ በሙሉ በአዲስ ኪዳን ዘመን ተቀባይነት አግኝተዋል። እነዚህንም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ብለን እንጠራቸዋለን። ነገር ግን ለሕዝበ እስራኤል ያልተሰጡና በብሉይ ኪዳን መጻሕፍትነት ያልተመዘገቡ መጻሕፍት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከየት አምጥታ እንደብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ቆጠረቻቸው? ምንጫቸው ከየት ነው?  እነዚህንም በትርፍነት የያዘቻቸው በእርግጥ ለዚህ ጥያቄ መልስ የሚሰጥ የለም። ስማቸውን ዘወትር የምታነሳቸው ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን/ እነአትናቴዎስ/ የማያውቋቸውና ዛሬም ድረስ እናቴ የምንላት የኮፕት ቤተ ክርስቲያን የማታውቃቸውን መቀበላችን ለምን? ብለን መጠየቅ አግባብነት አለው። ደግሞም በዓለማችን ላይ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት በአንዱም ውስጥ የሌለ መጽሐፈ መቃብያን ለኢትዮጵያ ብቻ የተሰጠው ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር? መቼና እንዴት? ለሚሉት ጥያቄዎች በእርግጥ በቂ መልስ የሚሰጥ የለም።

2/ዲያብሎስ ከክብሩ የወደቀው ለአዳም ስገድ ተብሎ አልሰግድም በማለቱ ነው። 

መጽሐፈ መቃብያን ምንጩ ያለመታወቁ አንዱ ምክንያት የያዘው ሃሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አለመሆኑ ነው። ዲያብሎስ ከክብሩ የወረደው እግዚአብሔር ለአዳም ስገድ ባለው ጊዜ ለሚዋረድልኝ ለአዳምስ አልሰግድም ብሎ እምቢተኛ በመሆኑ ነው ይለናል። ዲያብሎስ ራሱ ይህንን ቃል ሲናገር ያዳመጠው ሰው ማን እንደሆነ ለጊዜው ባይገለጽም መቃብያን ግን የዲያብሎስን ንግግር የሰማ ያህል እንዲህ ሲል አስፍሮታል።
«የሚጠፉ በኔም የሚስቱ ሰዎች ፈጽመው ይበዙ ዘንድ የአዳምም ልጆች ይጠፉ ዘንድ ይህንን በተናገሩ ጊዜ እኔ ደስ ይለኛል። ለሚዋረድልኝ ለአዳም አልሰግድም በማለቴ እግዚአብሔር ስለአባታቸው ስለአዳም ከማዕረጌ አዋርዶኛልና« 3ኛ መቃ 1፤15

ዲያብሎስ ራሱን ከፍ ከፍ ስላደረገና አምላክነትን ስለፈለገ ከማዕረጉ እንደተዋረደ የምታስተምር ቤተ ክርስቲያን፤ የለም ዲያብሎስ የወደቀው ለአዳም ስገድ በተባለ ጊዜ አልሰግድም በማለቱ ነው የሚለውን የመቃብያን መጽሐፍ፤ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለበት የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ነው በማለት ከ 81 ዱ ጋር አዳብላ ልትቆጥረው እንዴት ቻለች? ጥያቄአችን ነው። አይሁዶቹም እንደብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ያልቆጠሩት፤ ኮፕቶችና ሌሎቹም አብያተ ክርስቲያናት የማያውቁትን ይህንን መቃብያንን ከብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ጋር እንድንደምረው የሚያስገድደን መንፈሳዊ ይዘቱ ምንድነው? ስለ ሰማንያ ወአሀዱ መጽሐፍ ቅዱስ ስንናገር አሰሱንና ገሠሡን ሁሉ በመቆጠር ሊሆን አይገባውም። የአንድ መንፈሳዊ መጽሐፍ ልኬታ ምንጩ፤ መንፈሳዊነቱ፤ ተቀባይነቱና አገልግሎቱ ካልተመዘነ የጠላት አሰራር መግባቱ አይቀሬ ይሆናል። 

3/ ሳምራውያን ትንሣዔ ሙታን የለም ብለው ያምኑ ነበር ወይ?

ስለሰዱቃውያንና ስለፈሪሳውያን ትምህርተ ሃይማኖት የምናገኘው ማስረጃ ያለው በአዲስ ኪዳን ውስጥ ብቻ ነው። ሁለቱም የካህናተ ኦሪት ወገን ቢሆኑም  ሰዱቃውያን ከሞት በኋላ ስላለው ትንሣዔም ሆነ ዘላለማዊነት በፍጹም እምነት የላቸውም። ትንሣዔም፤ መላዕክትም የለም ባዮች ናቸው። ፈሪሳውያን ግን መላእክትም፤ ትንሣዔ ሙታንም መኖሩን  ቢያምኑም ይህ የሚሆነው ለአይሁዳውያን ብቻ ነው የሚል የትምክህት አስተምህሮ ስለነበራቸው ኢየሱስ ለክርስቲያኖች እንዲህ ሲል አስጠንቅቋል።
«ኢየሱስም፦ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ አላቸው። ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ እንድትጠበቁ ብዬ ስለ እንጀራ እንዳልተናገርኋችሁ እንዴት አታስተውሉምን? እነርሱም ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን ትምህርት እንጂ ከእንጀራ እርሾ እንዲጠበቁ እንዳላላቸው ያን ጊዜ አስተዋሉ» ማቴ 16፤6-12 የአዲስ ኪዳን የትንሣዔ አዋጅ ለተወሰነ ሕዝብ ስላይደለ የፈሪሳውያንን አስተምህሮ ክርስቲያኖች መቀበል ስለሌለባቸው ከዚህ ክፉ እርሾ እንዲጠበቁ አሳስቧል። እንደሰዱቃውያንም ትንሣዔ የለም ከሚል ትምህርትም ራሳቸውን እንዲጠብቁ ጳውሎስ  ሲያስረዳ የስንዴ ቅንጣት እንዴት ፈርሳና በስብሳ  ፍሬ እንደምታፈራ ትንሣዔውን በምሳሌ ሲያስተምር «አንተ ሞኝ፥ አንተ የምትዘራው ካልሞተ ሕያው አይሆንም» 1ኛ ቆሮ 15፤36 ይለናል።
እዚህ ላይ ስለሰዱቃውያንና ስለፈሪሳውያን የትንሣዔ ሙታን እምነት ማንሳት ያስፈለገው ከላይ በቁጥር 3 ላይ ላመለከትነው የጥያቄ ኃይለ ቃል መንደርደሪያ እንዲሆነን ነው። ሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ስለትንሣዔ ሙታን ያላቸው እምነት ከላይ እንደገለጽነው የአዲስ ኪዳን አስረጂ ከሆነ ሳምራውያን የሚባሉት ሕዝቦች ትንሣዔ ሙታን የለም ያሉት መቼ ነው? ብለን እንጠይቃለን። ምክንያቱም መጽሐፈ መቃብያን ሳምራውያን ትንሣዔ ሙታን የለም ብለዋል ይለናልና። 

አጭር ታሪክ፤

ሴኬም የያዕቆብ ምንጭ ያለባት የዐሥሩ ነገድ ሰሜናዊው እስራኤል መቀመጫ ከተማ ነበረች። የሰሎሞን መንግሥት በልጁ በሮብዓም/ ሁለት ነገድ/ በኢየሩሳሌም እና በአገልጋዩ በናባጥ ልጅ በኢዮርብዓም /ዐሥር ነገድ/ በሴኬም ከተከፈለ ( 1ኛ ነገ 12፤20) በኋላ ቆይቶ የሰማርያ ታሪክ ይጀምራል። እሱም የአክአብ አባት ዘንበሪ ሳምር ከሚባለው ሰው ላይ ከሴኬም ከተማ በስተቀኝ ያለውን ተራራ በሁለት መክሊት ከገዛ በኋላ በባለቤቱ በሳምር ስም ተራራ ላይ ቤት ሰርቶ ቦታውን ሰማርያ ማሰኘቱን መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። 1ኛ ነገ 16፤24 ከተማው እያደገ፤ ሀገሩም እየሰፋ ሰማርያ ስያሜውን ይዛ ዛሬም ድረስ አለች። ሰማርያ ገሪዛንና ጌባል የሚባሉ የአምልኮ ኮረብታዎቿን ይዛ በመገኘቷ ከሁለቱ ነገድ መዲና ከሆነችው ከኢየሩሳሌም ጋር ኅብረት ያልነበራቸው ከዚያን ጊዜ አንስቶ ነበር። ስለዚህም ጌታችን ከኢየሩሳሌም ወደሰሜናዊ የገሊላ አውራጃ ለመሄድ አማራጭ መንገዱ ሩቅ ስለሆነና የመጣበትም ዓላማ ስለነበረው በዚህች ከይሁዳውያን ጋር ኅብረት ባልነበራት በሰማርያ ማለፉን እናነባለን። (ዮሐ 4፤4)

ሰማርያውያን የእግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ ስፍራ ገሪዛን ተራራ እንጂ ኢየሩሳሌም አይደለችም ከማለታቸው በስተቀር፤ የትንሣዔ ሙታንና የገነትንም መኖር ያምናሉ። ይሁን እንጂ መጽሐፈ መቃብያን የተባለው የአዲስ ኪዳኑን ታሪክ እንደብሉይ ኪዳን ዘመን ትረካ ወደኋላ ጎትቶ የሌለውን ነገር ያስነብበናል።
«ሳምራውያን ግን ሥጋችን ትቢያ ይሆናል፣ አይነሳም ይላሉ» (2ኛ መቃ 14፤1-3) እዚህ ላይ ጥያቄ የሚያስነሳው መቃብያን የተባለው መጽሐፍ በአዲስ ኪዳን የተጻፈውንና ጌታችን ያስተማረውን ታሪክ ስለሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ይዞ መገኘቱ አንዱ ነጥብ ሲሆን ትንሣዔ ሙታን የለም ያላሉትንና የማይሉትን ሳምራውያንን ከሰዱቃውያን ጋር አብሮ መጨፍለቁ ታሪኩን አስገራሚ ያደርገዋል። ምክንያቱም ሰዱቃውያንና ፈሪሳውያን ስለትንሣዔ በጠየቁት ጊዜ ሳምራውያን ያልነበሩ ሆነው ሳለ መቃብያን ግን ልክ እንዳሉ ቆጥሮ፤ ያልተናገሩትን ስለመናገራቸው መዘገቡ ምን ይባላል? ሳምራውያን የብሉይ ኪዳን እምነት ተከታዮች ስለትንሣዔ ሙታን ያላቸው እምነት ግልጥ ነው። መቃብያን ግን የትም ያልተጻፈውን አንስቶ ይለጥፍባቸዋል።
ዛሬ በቁጥር ከ 800 የማይበልጡ ሳምራውያን በትንሣዔ ሙታንም በመላእክትም መኖር የማመን ጥንታዊ እምነታቸውን ያልተዉ የ10ሩ ነገድ ዘሮች በሰማርያ ይኖራሉ። መቃብያን ግን ይዋሽባቸዋል። ለምን?
(ይቀጥላል)

Wednesday, June 12, 2013

ጥያቄ፤ በክርስትና ሕይወቴ ኃጥአትን እንዴት ማሸነፍ እችላለሁ?






       ምንጭ፤    (michaelyemane.blogspot.com) 


ጥያቄ፤ በክርስትና ሕይወቴ ኃጥአትን እንዴት ማሸነፍ እችላለሁ?
መልስ፤ በጥረታችን ኃጥአትን ለማሸነፍ ይረዳን ዘንድ መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ የተለያዩ መንገዶችን ያቀርባል፡፡ በዚህ ዕድሜ በኃጥአት ላይ ፍጽሞ በሚገባ ባለድል አንሆንም (1ኛ ዮሐንስ 1፡8)፤ ነገር ግን ያ አሁንም የእኛ ግብ ሊሆን ይገባል፡፡ በእግዚአብሔር ዕርዳታ እና የቃሉን መርሆች በመከተል በሂደት ኃጥአትን ማሸነፍ እና በበለጠ ክርስቶስን መምሰል እንችላለን፡፡
በጥረታችን ኃጥአትን ለማሸነፍ መጽሐፍ ቅዱስ የሚጠቅሰው የመጀመሪያው መንገድ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን ሰጥቶናል ስለዚህም በክርስትና ህይወታችን ባለድል መሆን እንችላለን፡፡ እግዚአብሔር ወደ ገላትያ ሰዎች 5፡16-25 ውስጥ የሥጋ ሥራዎችን ከመንፈስ ፍሬዎች ጋር ያነጻጽራል፡፡ በዚያ ምንባብ ውስጥ በመንፈስ እንድንሄድ ተጠርተናል፡፡ ሁሉም አማኞች አስቀድሞ መንፈስ ቅዱስ አላቸው፤ ነገር ግን ይህ ምንባብ ለእሱ ቁጥጥር እየተገዛን በመንፈስ መሄድ እንደሚገባን ይነግረናል፡፡ ይህ በቋሚነት መንፈስ ቅዱ በህይወታችን ውስጥ ሥጋን ከመከተል ይልቅ በተከታታይ የመንፈስ ቅዱስን ምሪት መከተል መምረጥ ማለት ነው፡፡
መንፈስ ቅዱስ ማድረግ የሚችለው ልዩነት፤ በመንፈስ ቅዱስ ከመሞላቱ በፊት ኢየሱስን ሦስት ጊዜ በካደው በጴጥሮስ ህይወት ታይቷል፤ እናም ከዚህ በኋላ ክርስቶስን እስከሞት ድረስ እንደሚከተለው ተናግሮ ነበር፡፡ በመንፈስ ከተሞላ በኋላ በጴንጤቆስጤ በዓል ላይ በአደባባይ በድፍረት ለአይሁዶች ነገራቸው፡፡
የመንፈስን ምሪት ላለማጥፋት ለመሞከር በመንፈስ እንሄዳለን (በ1ኛ ተሰሎንቄ 5፡19 እንደተነገረው) እና በምትኩ በመንፈስ መሞላትን እንፈልግ (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡18-21)፡፡ አንድ ሰው በመንፈስ ቅዱስ እንዴት ይሞላል? በብሉይ ኪዳን ውስጥ እንደነበረው ከሁሉ በፊት የእግዚአብሔር ምርጫ ነው፡፡ እሱ እንዲከወን የፈለገውን ሥራውን የሚያስፈፅሙ ግለሰቦችን መረጠ እና በመንፈሱም ሞላቸው (ኦሪት ዘፍጥረት 41፡38፤ ኦሪት ዘፀአት 31፡3፤ ኦሪት ዘዳግም 24፡2፤ 1ኛ ሳሙኤል 10፡10) በእግዚአብሔር ቃል ራሳቸውን እየሞሉ ያሉትን እነዚያን ሊሞላቸው እንደሚመርጥ ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡18-21 እና ወደ ቆላስያስ ሰዎች 3፡16 ውስጥ ማረጋገጫ አለ፡፡ ይሄ ወደ ሁለተኛው መንገድ ይመራናል፡፡
የእግዚአብሔር ቃል፤ መጽሐፍ ቅዱስ፤ እግዚአብሔር ለየትኛውም በጎ ሥራ ሁሉ እኛን ለማስታጠቅ ቃሉን ሰጥቶናል ይላል (2ኛ ጢሞቴዎስ 3፡16-17)፡፡ እንዴት መኖር እንዳለብን እና ምን ማመን እንዳለብን ያስተምረናል፣ የተሳሳቱ ጎዳናዎችን በመረጥን ጊዜ ይገልጥልናል፣ ወደ ትክክለኛውም ጎዳና እንድንመለስ እና በዚያ ጎዳና እንድንቆይም ይረዳናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሕያው እና የሚሰራ እንደሆነ፣ ሥር ለመስደድ ወደ ልቦቻችን ዘልቆ ለመግባት እና ጥልቅ የሆኑትን የልባችንን ኃጥአቶች እና አመለካከቶችን ማሸነፍ እንደሚችል ወደ ዕብራውያን ሰዎች 4፡12 ይነግረናል፡፡ ዘማሪው በመዝሙረ ዳዊት 119 ውስጥ ስለ እሱ የህይወት ቀያሪነቱ ኃይል በጥልቀት ይናገራል፡፡ ኢያሱ ጠላቶቹን የማሸነፍ ውጤታማነት ቁልፉ ይህንን መንገድ ያለመርሳት እንዳልሆነ ነገር ግን በምትኩ በቀን እና በማታ ማሰላሰል እና እሱን መታዘዝ እንደሆነ ተነግሮታል፡፡ እግዚአብሔር ባዘዘ ጊዜ እንኳ በውትድርናው ስሜት የማይሰጥ ነገር ባይሆንም ይህን አደረገ፤ እና ይሄ ለተስፋይቱ ምድር ላደረገው ጦርነት የድሉ ቁልፍ ነበር፡፡
እኛ ራሳችን ብዙውን ጊዜ በቀላሉ የምናየው መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ወደ ቤተክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱሶቻችንን በመሸከም ወይም የቀን ጥሞና ወይም በቀን አንድ ምዕራፍ እያነበብን ምልክታዊ አገልግሎት እንሰጣለን፣ነገር ግን እሱን ማሰቡን ፤ እሱን ማሰላሰሉን ወይም በኑሮዎቻችን ላይ ተግባራዊ ማድረጉን ትተናል፣ እሱ የሚገልጣቸውን ኃጥአቶቻችንን መናዘዝ ወይም ለእኛ ለሚገልጣቸውን ስጦታዎች እግዚአብሔርን ማመስገን ትተናል፡፡ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ በሚመጣበት ጊዜ እኛ ብዙውን ጊዜ ምግብ ያስጠላቸው ወይም አመጋገባቸው የተዛባብን ነን፡፡ ከቃሉ በመመገብ በመንፈሳዊው እንዲያው በህይወት እንዲያቆየን ያህል (ነገር ግን ጤናማ እና የሚፋፉ ክርስቲያኖች እንድንሆን ፈጽሞ የሚበቃንን ያህል አንበላም) ወይም ብዙ ጊዜ ልንመገብ እንመጣለን ነገር ግን መንፈሳዊ ምግብን ከእሱ ለማግኘት ለረጅም ጊዜ በፍጹም አናሰላስለውም፡፡
እሱ ጠቃሚ ነው፣የእግዚአብሔርን ቃል በየቀኑ የማጥናትና የማሰላሰል ልምድ ካላደረግህ ያን ማድረግ ትጀምራለህ፡፡ ጥቂቶች የሚረዳ ጅማሬ ሆኖ አግኝተውታል፡፡ ከእሱ ያገኘኸውን አንድ ነገር እስከምትጽፍ ድረስ ቃሉን ላለመተው ልምድ አድርገው፡፡ ጥቂቶች እነርሱን በተናገራቸው ዙሪያ ይለወጡ ዘንድ እንዲረዳቸው በመጠየቅ ወደ እግዚአብሔር የሚደረጉትን ፀሎቶች ይመዘግባሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ መንፈስ የሚጠቀምበት መሳሪያ (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡17)፤ እግዚአብሔር መንፈሳዊ ውጊያዎቻችንን እንድንዋጋ የሰጠን ጠቃሚ እና ዋነኛ የጦር ዕቃ አካል (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡12-18) ነው፡፡
በኃጥአት ላይ ለምናደርጋቸው ውጊያዎቻችን ሦስተኛው ዋነኛ መንገድ ፀሎት ነው፡፡ አሁንም ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች የከንፈር አገልግሎት የሚሰጡበት መንገድ ነው ነገር ግን ጥቅሙን ደካማ ያደርጋል፡፡ የፀሎት ስብሰባዎች፣ የፀሎት ጊዜያቶች ወ.ዘ.ተ. አሉን ነገር ግን ጸሎትን የጥንቷ ቤተክርስቲያን በምትጠቀምበት መንገድ አልተጠቀምንበትም (የሐዋርያት ሥራ 3፡1፣4፡31፣6፡4፣13፡1-3)፡፡ ጳውሎስ ያገለግላቸው ለነበሩት እንዴት ይፀልይ እንደነበር በተደጋጋሚ ይጠቅሳል፡፡ እግዚአብሔር ጸሎትን በተመለከተ የሚያስደንቁ ተስፋዎችን ሰጥቶናል (የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-11፣ የሉቃስ ወንጌል 18፡1-8፣ ዮሐንስ ወንጌል 6፡23-27፣ 1ኛ ዮሐንስ መልዕክት 5፡14-15)፣ እና ጳውሎስ ለመንፈሳዊ ውጊያ በመዘጋጀት ምንባቡ ውስጥ ፀሎትን ያካትታል (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡18)፡፡
በኑሮዎቻችን ኃጥአትን በማሸነፉ ፀሎት እንዴት ጠቃሚ ነው? ልክ ከጴጥሮስ ክህደት በፊት በጌተሰማኔ የአትክልት ሥፍራ ለጴጥሮስ የክርስቶስ የሆኑ ቃላቶች አሉን፡፡ ኢየሱስ እየጸለየ ጴጥሮስ እየተኛ ነው፡፡ ኢየሱስ አነቃውና እናም አለው “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው።”(የማቴዎስ ወንጌል 26፡41) እኛ እንደ ጴጥሮስ ትክክል የሆነውን ማድረግ እንፈልጋለን ነገር ግን ጥንካሬውን እያገኘን አይደለም፡፡ መፈለጋችንን ፣ ማንኳኳታችንን፣ መጠየቃችንን ለመቀጠል የእግዚአብሔርን ተግሳጽ መከተል ያስፈልገናል እናም ያ የምንፈልገውን ጥንካሬ ይሰጠናል (የማቴዎስ ወንጌል 7፡7)፡፡ ጸሎት ምትሃታዊ ዘይቤ አይደለም፡፡ ጸሎት በቀላሉ የእኛን የራሳችንን ድክመትና የእግዚአብሔርን የማይወሰነውን ኃይል ማረጋገጥ እና እኛ ማድረግ የምንፈልገውን ሳይሆን እሱ እንድናደርገው የሚፈልገውን ለማድረግ ለዚያ ጥንካሬ ወደ እሱ መዞር ነው (1ኛ ዮሐንስ መልዕክት 5፡14-15)
ኃጥአትን ለመማረክ በምናደርገው ጦርነታችን ውስጥ አራተኛው መንገድ፤ የሌሎች አማኞች ህብረት፤ ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ኢየሱስ ደቀመዛሙርቱን በላከበት ጊዜ ሁለት ሁለት አድርጎ ላካቸው (የማቴዎስ ወንጌል 10፡1)፡፡ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ ያሉ ሚሲዮኖች በአንድ ጊዜ አንድ ሆነው አልወጡም ነበር ነገር ግን ሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆነ ማህበር ነበር፡፡ ኢየሱስ አንድ ላይ መሰብሰባችንን እንዳንተው ነገር ግን ያን ጊዜ በፍቅር እና በመልካም ሥራዎች እርስ በራሳችንን ለማበረታታት እንድንጠቀምበት አዞናል (ወደ ዕብራውያን ሰዎች 10፡24)፡፡ አንዳችን ለአንዳችን ስህተታችንን እንድንናዘዝ ይነግረናል (የያዕቆብ መልዕክት 5፡16) በብሉይ ኪዳን በጥበብ መጽሐፍ ውስጥ ብረት ብረትን እንደሚስል ተነግሮናል፥ ስለዚህ አንድ ሰው ሌላውን ይስላል (መጽሐፈ ምሳሌ 27፤17)። በቁጥሮች ውስጥ ጥንካሬ አለ (መጽሐፈ መክብብ 4፡11-12)፡፡
ብዙ ክርስቲያኖች የሚከብዱ ኃጥአቶችን በማሸነፉ ረገድ ኃላፊነትን የሚወስድ ወዳጅ መኖር በጣም ትልቅ ጥቅም መሆን እንደሚችል ያን አግኝተዋል፡፡ ከአንተ ጋር ሊያወራ፤ ሊፀልይ፣ ሊያበረታታህ፤ እና እንዲያውም የሚገጽህ የሚችል ሌላ ሰው ማግኘት ትልቅ ዋጋ አለው፡፡ ፈተና ለሁላችንም ያለ ነው (1ኛ ቆሮንቶስ 10፡13) ኃላፊነትን የሚወስድ ወዳጅ ወይም ኃላፊነትን የሚወስድ ማህበር መኖሩ እንዲያውም በጣም ከባድ የሆኑትን ኃጥአቶችን ለማሸነፍ የሚያስፈልገንን የመጨረሻውን የማበረታቻ እና የመነሳሳት መጠን ሊሰጠን ይችላል፡፡
አንዳንድ ጊዜ በኃጥአት ላይ ድል መንሳት በፍጥነት ይመጣል፡፡ ሌላ ጊዜ ድል በጣም በዝግታ ይመጣል፡፡ እግዚአብሔር የእሱን መንገዶች ስንጠቀም ለውጥን በህይወታችን በሂደት እንደሚያመጣ ቃል ገብቷል፡፡ ኃጥአትን ለማሸነፍ ጥረታችንን በቀጣይነት መቀጠል እንችላለን ምክንያቱም እሱ በቃሉ ታማኝ እንደሆነ እናውቃለን፡፡

Tuesday, June 4, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ ( ክፍል ፪ )


( ክፍል ፪ )
ከዚህ በፊት በክፍል ፩ ለመግለጽ እንደሞከርነው ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ቅዱሳት መጻሕፍት ትርጉም ውስጥ እጁን በማስገባት የራሱን ዓላማ በእግዚአብሔር ቃል ሽፋን ሲፈጽም መቆየቱን ለማብራራት ሞክረናል። ክርስቲያኖች እውነቱን አውቀው እግዚአብሔርን ወደማምለክና በአንድያ ልጁ በኩል የተደረገውን የማዳን ሥራ በቂ እንዳልሆነና ልዩ ልዩ የድኅነት/ የመዳን/ መንገዶች መኖራቸውን በማሳየት መመለሻ ወደሌለው ጥፋት ለመውሰድ ሌሊትና ቀን የማይደክም ብርቱ ጠላት መሆኑ «የሚውጠውን የሚፈልግ አንበሳ» የተባለው ቃል ያረጋግጥልናል።

ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ የቅብጥ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ከጻፏቸው በርካታ መጻሕፍት መካከል አንዱ የሆነውና «diabolic war» /ዲያብሎሳዊ ውጊያ/ በተሰኘ መጽሐፋቸው ውስጥ ዲያብሎስን ጠንካራ የሚያደርገው መልካም ነገር አለ ብሎ ባሰበበት ቦታ ሁሉ ከፍተኛ ውጊያ ቢገጥመው እንኳን ተስፋ ቆርጦ ስለማይሄድ ክፉ ጠላት በማለት ይገልጹታል። ሲሸነፍ አሜን ብሎ እጁን የሚሰጥ ሳይሆን ጊዜ እየጠበቀ እስከመጨረሻው ድረስ ያለመታከትና ያለመሰልቸት መዋጋት መቻሉ የክፋቱን ልክ ያሳያል ይላሉ። በእርግጥ ዲያብሎስ ከክብሩ የወደቀና የተሸነፈ መልአክ ነው። ቢሆንም ያለው ከሙሉ ኃይሉ ጋር ስለሆነ  ውጊያው ቀላል ስላይደለ እምነታችንን እንዳይጥልብን አጽንተን እንጠብቅ ዘንድ ይመክሩናል። 

ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፥12
«መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ»

ስለዚህ ጠላታችን ኃይለኛ ተዋጊ እንጂ የወደቀ ነው ተብሎ የሚናቅ ስላይደለ አብያተ ክርስቲያናትን አጥብቆ መዋጋቱን መዘንጋት ተገቢ አይደለም። ግለሰቦችን ተዋግቶ ከማሸነፍ ይልቅ ግለሰቦች የተሰባሰቡባትን ቤተክርስቲያን የምትመራበትን ቃል መጠምዘዝ መቻል ሁሉንም ከእውነተኛው መንገድ ላይ ማስወጣት መቻል መሆኑ አሳምሮ ስለሚያውቅ  ይህንኑ በትጋት ይፈጽማል።ከዚህም የመዋጊያ ስልቱ መካከል ቅዱሱን የእግዚአብሔር ቃል ባደረባቸው ሰዎች በኩል ማጣመም፤ መሸቃቀጥ፤ ብዙ የመዳን መንገዶች እንዳሉ ማሳየት፤ የኢየሱስ ክርስቶስን ብቸኛና ብቁ መድኃኒትነት በልዩ ልዩ መድኃኒቶች መተካት ዋናው ስራው ነው። ይህንንም በተግባር ሲሰራ ቆይቷል። ለዛሬም ጥቂቱን በማሳየት እንዴት እንደተዋጋን ለማሳየት እንሞክራለን።

1/ የመጽሐፍ ቅዱስን ቁጥር ማዛባት የጠላት ዋነኛ ሥራው ነው..

መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው የጻፉት መሆኑ አያጠያይቅም። ቀደምት አበውም የመጽሐፍ ቅዱስን ቅደም ተከተል፤ ምዕራፍና ቁጥር የተነተኑትም በመንፈስ ቅዱስ መርምረው መሆኑንም እናምናለን። ችግሩ የሚነሳው በዚህ ዘመን ላይ እንደመጽሐፍ ቅዱስ አካል የሚቆጠሩት የቀደምት መጻሕፍት አካል የሆኑት የትኞቹ ናቸው? የሚለው ጥያቄ ነው። ለማሳየነትም በቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ለ1600 ዓመት ስትመራ ቆይታለች እየተባለ የሚነገርላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስ ቁጥርና ዝርዝር በፍጹም አይመሳሰልም። ለምን? ሁለቱን አብያተ ክርስቲያናት የመጽሐፍ ቅዱስ ቁጥርና ዝርዝር አንድ ካላደረጋቸው አንድ ነበሩ ሲያሰኝ የቆየው ታዲያ ምን ነበር? እነአትናቴዎስን ከፍ ከፍ የምታደርገው በምን መለኪያ ነው? በዋናው የእግዚአብሔር ቃል ልዩነት ካላቸው በሃይማኖት አይመሳሰሉም ማለት ነው። የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን በዕብራውያን እጅ ያሉትን 39 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንደትክክለኛ የእግዚአብሔር እስትንፋስ መጻሕፍት አድርጋ ትቀበላለች። ካርቴጅ  በተደረገው ጉባዔ መጻሕፍት አምላካውያት ላይ ቀኖና ሲደነገግ እነቅዱስ አትናቴዎስ 39ኙን የዕብራውያን መጻሕፍት አጽድቀዋል። ኮፕትም ይህንኑ ተቀብላ እስከዛሬ አለች። እንደዕብራውያን መጻሕፍት የማይቆጠሩና በተጨማሪ ቀኖናተ መጻሕፍት የተያዙ /Deutrocanonical/ መጻሕፍትን ለብቻ መዝግባለች። 
እነዚህም 1/ እዝራ ሱቱኤል (አንድና ሁለትን) እንደአንድ መጽሐፍ 2/ ጦቢት 3/ ዮዲት 4/ ጥበበ ሰሎሞን 5/ ሲራክ 6/ ባሮክ 7/ መቃብያን (አንድና ሁለት) እንደአንድ መጽሐፍ መያዟ ይታወቃል። እነዚህም መጻሕፍት ቢሆኑ ድምራቸው ከዕብራውያን መጻሕፍት አይደሉም።  መጽሐፈ ሔኖክ፤ 3ኛ መቃብያን ፤ 4ኛ መቃብያን የሚባሉትን መጻሕፍት እንደትርፍ መጻሕፍት አድርጋ አትቀበልም።  መቃብያን አንድና ሁለት ራሱ ከኢትዮጵያው መቃቢያን ጋር ምንም የሃሳብና የመንፈስ ግንኙነት የሌለው በመሆኑበሁሉም  በመጽሐፈ መቃብያን በኩል ቅብጥና ኢትዮጵያ ልዩነታቸው የሰማይና የምድር ያህል ይርቃል። ለምን?

ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንደቅዱሳት መጻሕፍት አድርገው ያልቆጠሯቸውን መጻሕፍት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከማን አግኝታ ተቀበለቻቸው? ለመቀበል ያስቻላት መመዘኛ ምንድነው? እስክንድርያ እናቴ፤ ማርቆስ አባቴ ስትል የቆየችባቸው ዘመናት የክርስትና ሕይወትና ዓምድ በሆነው የመጽሐፍ ቅዱስ አንድነት ከሌላት መነሻው ምንድነው? ኮፕት 66ቱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንደአበው ቅዱሳት መጻሕፍት ድንጋጌ ስትቀበል፤ በትርፍነት እንደሕጻናት የመንፈሳዊ ትምህርት ማጎልመሻ መጻሕፍትነት 7 በተጨማሪ ወይም በዲቃላ መልክ ይዛ ትገኛለች። 

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ግን ዲድስቅልያ፤ አብጥሊስ፤ትዕዛዝ፤ ሥርዐተ ጽዮን፤ ግጽው፤ ቀሌምንጦስ፤ ዮሴፍ ወልደኮርዮን ወዘተ ሳይቀሩ በ4ኛውና በ5ኛው ክ/ዘመን የተጻፉትን ሳይቀር የቅዱሳት መጻሕፍት አካል አድርጋ መቁጠሯ ለምን ይሆን?
ሰማንያ ወአሀዱ ተብለው በተለምዶ ቢጠሩም እነሱም እስከ 85 ይደርሳሉ። አንዳንዴ የግድ የተለመደው 81ን እንዳያልፍ ሲባል ሁለቱን በአንድ እስከመጨፍለቅ ይደረሳል። ቀሌምንጦስ የሐዋርያው ጴጥሮስ ደቀመዝሙር የእጣ ክፍሉ በነበረችው በኮፕት ቤተክርስቲያን ውስጥ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ያበረከተ ብዙ መጻሕፍትን የጻፈ ቢሆንም ኮፕት የሱን መጻሕፍት እንደመጽሐፍ ቅዱስ አካል አድርጋ ያልተቀበለችው ሆኖ ሳለ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የኔ ሰማንያ አሀዱ በማለት በግድ የምትቆጥረው ምን ቁጣ ወርዶባት ይሆን? ከዘመነ ሐዋርያት በኋላ የተጻፉ መጻሕፍት ከመማሪያነትና በመንፈሳዊ እውቀት ከማነጽ ባሻገር እንደወንጌል ቃል ሊቆጠሩ ይችላሉ? የኛ ሰማንያ ወአሀዱ ይህንን ሁሉ ግሳንግስ ይዟል። ለምን? በምን መለኪያ? ቅዱሳት መጻሕፍትን በፈለጉበት ጊዜ እያነሱ መጨመር ይቻላል?

በዚህም ተባለ በዚያ አበው ሊቃውንት እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለባቸው ናቸው በማለት በቅደም ተከተል ያስቀመጧቸውን ቅዱሳት መጻሕፍት ብቻ ሳይሆን የማይታወቁ፤ ያልተመረመሩ፤ አበው በቀኖናቸው ያልያዟቸው፤ ብዙ ትርፍ መጻሕፍትን ይዛ መገኘቷ እንደቅርስ ካልሆነ በስተቀር እንደቅዱሳት መጻሕፍት ስብስብ ሊያስቆጥራቸው የሚችል አንዳችም አስረጂ አይቀርብባቸውም።
እስኪ ግብጽ/ቅብጥ/ እንደትርፍ መጻሕፍት የምትቆጥረውንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ግን እንደዕብራውያን መጻሕፍት እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያስጻፈው ነው ብላ የምታምንበትን 1ኛ መቃብያንን ምዕ 1፤1 በንጽጽር እንመልከት።

የቅብጥ ቤተክርስቲያን መቃብያን 1፤1

After Alexander son of Philip, the Macedonian, who came from the land of Kittim, had defeated Darius, king of the Persians and the Medes, he succeeded him as king. (He had previously become king of Greece.)

ተዛማጅ ትርጉም፤ «ከምድረ ኪቲም የመጣው መቄዶንያዊው የፊልጶስ ልጅ ፤ የፋርሱንና የሜዶኑን ንጉሥ ዳርዮስን አሸነፈ።ራሱንም ንጉሥ አድርጎ  ሾመ፤ ቀድሞም የግሪክ ንጉሥ ነበር»   (መቃብያን ቀዳማዊ 1፤1)

ይህ  ታሪክ ስለታላቁ እስክንድር የሚተርክ የታሪክ ክፍል ነው። ታላቁ እስክንድር ደግሞ የኖረበትን የታሪክ ዘመን ስንመረምር በ3ኛው መቶ አጋማሽ ዓመተ ዓለም የነበረ ጦረኛ ተዋጊ መሆኑን መረጃዎች ያሳዩናል። ከዚህ ተነስተን ስለ እስክንድር ታላቁ የሚተርከው ይህ የመቃብያን መጽሐፍ ታላቁ እስክንድር ካለፈ በኋላ እሱን በሚያውቁ ወይም ታሪኩን በሰሙ ሰዎች የተጻፈ ስለመሆኑ የጽሁፉ ይዘት ይጠቁመናል። ለጽሁፉም መነሻ ምክንያት የሆነው ኢየሩሳሌምን ጨምሮ ከፋርሶች እጅ ነጻ በማውጣቱ ምናልባትም የአይሁድ ታሪክ ጸሐፊዎች የጻፉት ሊሆን እንደሚችል የነገረ መለኮት ታሪክ አዋቂዎች ይገምታሉ።  ግብጻውያንም እንደቅዱሳት መጻሕፍት ያልቆጠሩበት መነሻ ምክንያትም እስክንድር ቅድመ ክርስትና የነበረ ሰው ሲሆን በእምነትም አይሁዳዊ ባለመሆኑ የተነሳ ነው። በማታትያስና አምስት ልጆቹ ያለውን በሜዲተራንያን  አካባቢ በግሪኮች ላይ የተደረገውን የዐመጽ ትርክርት የሚናገር መጽሐፍ ነው። ዛሬም አይሁዳውያን እንደመንፈሳዊ መጽሐፍ ሳይሆን ከታሪክ መጽሐፍነት የበለጠ ስፍራ አልሰጡትም።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መቃብያን በተመሳሳይ(ምዕ 1፤1) ከኮፕቱ ጋር ሲተያይ፤

«ስሙ ጺሩጻይዳን የሚባል ኃጢአትንም የሚወዳት አንድ ሰው ነበር። በፈረሶቹም ብዛት፤ ከሥልጣኑ በታች፤ በጭፍራዎቹም ጽናት ይመካ ነበር» (መቃብያን ቀዳማዊ 1፤1)

የሃሳብ፤ የመልዕክት ግንኙነት ምንም የለውም። ይህ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን መቃብያን ስለማታትያስና አምስት ልጆቹ የዐመጽ ታሪክ ምን አይናገርም። ይልቁንም የሜዶን ንጉሥ ሳይሆን ግሪኮች መካከለኛው ምሥራቅን ሲገዙ የነበሩበትን ዘመን ትቶ ወደኋላ በመሄድ ስለሜዶኖች ይተርካል። እንግዲህ ይህንን ዓይነት የመጻሕፍት ልዩነት መኖሩ መነሻው ምንድነው? ብለን ብንጠይቅ ጠላት እያሰረገ በቅዱሳት መጻሕፍት ሽፋን ያስገባው እንጂ   በሁለት አፍ የሚናገር ቃለ እግዚአብሔር ለክርስቲያኖች የተሰጠ  ሆኖ አይደለም።

2/ መጽሐፈ መቃብያን ያላቸው ተቀባይነት ፣

፩ኛና ፪ኛ መቃብያን በካቶሊክ፤ በምሥራቅ ኦርቶዶክሶችና ኮፕት ኦርቶዶክስ ዘንድ እንደተጨማሪ መጻሕፍት ሲቆጠሩ በአይሁዶችና በፕሮቴስታንቶች ዘንድ እንደ እግዚአብሔር እስትንፋስ ስለማይቆጠር ተቀባይነት አላገኘም።  ፫ኛ መቃብያን በምሥራቅ ኦርቶዶክሶች ዘንድ ብቻ ተቀባይነት ሲያገኝ በካቶሊክ፤ በኮፕት፤ በአይሁዶችና በፕሮቴስታንቶች  ዘንድ እንደ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ተደርጎ አይቆጠርም። ፬ኛ መቃብያን ደግሞ ከጆርጂያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ብቻ እንጂ በየትኞቹም አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም። 

በመቃብያን ስም የሚጠራ ነገር ግን ከላይ ከተዘረዘሩት አብያተ ክርስቲያናት መጽሐፈ መቃብያን ጋር ምንም ግንኙነት የሌለው ሦስት የመቃብያንን መጻሕፍት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስና የኤርትራ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት የራሳቸው መቃብያን ይዘው ይገኛሉ። ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት የማይቀበሉት በተለይም ከአይሁድ የኦሪት መጻሕፍት ውስጥ እንደአንዱ የማይቀጠርና ወዳጅ ቤተክርስቲያን የተባለችው የኮፕት ቤተክርስቲያን ጭምር የማትቀበለውን ይህንን የመቃብያን መጻሕፍት መቀበላችን ምክንያቱ ምንድነው?

ለኢትዮጵያውያን ለብቻችን ከሰማይ የወረደ ልዩ መጽሐፍ ስለሆነ ይሆን? በበፊቶቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ እንደመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ሳይቆጠር /Apocrypha/  ተብሎ ለብቻው የተቀመጠውን በ2000 ዓ/ም መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ግን እንደቅዱሳት መጻሕፍት ቆጥራው መዝግባው መገኘቷ አስገራሚ ሆኗል። እቀበለዋለሁ በምትላቸው የኒቂያ፤ የኤፌሶንና የቁስጥንጥንያ ጉባዔያት ውስጥ ከቅዱሳት መጻሕፍት ዝርዝር ውስጥ የሌሉትን በ2000 ዓ/ም እትም ውስጥ ማስገባትዋ የጤንነት ነው? በእርግጥም ጠላት ቤተክርስቲያኒቱን በእውነተኛው የእግዚአብሔር ቃል ውስጥ እንክርዳዱን በደንብ መዝራት መቻሉን ያረጋገጠ ሆኗል።

3/ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን መቃብያን ግልጽ ስህተቶች፤ 

መቃብያን ምንጩ ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከሰዎች ልብ መንጭቶ የተጻፈ ስለመሆኑ ብዙ ግድፈቶችን ማቅረብ ይቻላል። ለምሳሌ ያህል በ1ኛ መቃብያን 10፤ 1-2 ያለውን እስኪ እንመልከት። እንዲህ ይላል።
«ነገር ግን እንዲህ ካልሆነ የቀደሙት ሰዎች ከአዳም ጀምሮ ከሴትና ከአቤል፤ ከሴምና ከኖኅ ከይስሐቅና ከአብርሃም ከዮሴፍና ከያዕቆብ፤ ከአሮንና ከሙሴ ጀምሮ በአባቶቻቸው መቃብር ይቀበሩ ዘንድ ነው እንጂ በሌላ ቦታ ይቀበሩ ዘንድ ያልወደዱ ለምንድነው? በትንሣዔ ጊዜ በአንድነት ሊነሱ አይደለምን? አጥንታቸውስ ጣዖት ከሚያመልኩ ከክፉዎች ከአረማውያንም አጥንት ጋራ እንዳይቆጠር አይደለምን?» 

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረን አሮን የሞተው በሖር ተራራ ላይ ርስት ምድር ሳይገባ በሞዓባውያን ሀገር ነው። ዘኁል 20፤25-26 ሞዓብ ደግሞ ጣዖት አምላኪያውያን ናቸው እንጂ እስራኤላውያን አልነበሩም። መጽሐፈ መቃብያን ግን የሌለውን ታሪክ በመለፍለፍ አሮን  ከአባቶቻቸው መቃብር ከተቀበሩት አንዱ እንደሆነ ውሸት ይተርክልናል። የአብርሃምና ሚስቱ ሣራ እስከዛሬም  መቃብራቸው ያለው በኬብሮን ነው።  ዘፍ 23፤19-20  ኬብሮን ደግሞ ከደቡባዊ እስራኤል ከተማ አንዷ ናት። በአሮንና በአብርሃም መቃብር መካከል ያለው የቦታ ልዩነት ሩቅ ነው።  ሙሴ እስከዛሬ ድረስ መቃብሩ የት እንደሆነ እንደማይታወቅ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። የሞተው ግን በናባው ተራራ ላይ ነው። መቃብሩ በሞዓብ ሸለቆ ውስጥ ቢሆንም መቃብሩ አልተነገረም። ታዲያ የሙሴን መቃብር የት እንደሆነ አውቆ ነው መቃብያን ከአባቶቻቸው ጋር ለትንሣዔ ቀን እንዲያመች  አንድ ቦታ ተቀበሩ የሚለን? መቃብያን ስማቸውን በመጥራት ሁሉ አንድ ቦታ እንደተቀበሩና ይህም የሆነው መቃብራቸው ከጣዖት አምላኪዎች ጋር እንዳይቀላቀል፤ በትንሣዔ ቀንም አብረው እንዲነሱ ሲሉ ነው የሚለን ትንሣዔን የቦታ ርቀት ይከለክለዋል? 

በጣዖት አምላኪ መካከል መቀበር ሟችን የኃጢአት ተጋሪ እንዲሆን ያደርገዋል? መቃብያን አስገራሚ ትንተናና ልብወለዳዊ ትረካውን በመስጠት አንድ ላይ ያልተቀበሩትን መተረኩ ያስደንቃል። ስለዚህ መቃብያን የተጻፈው በእግዚአብሔር መንፈስ አይደለም። ቦታ አያውቅም፤ ታሪክ አያውቅም፤ የእግዚአብሔርንም የትንሣዔ አሠራር አያውቅም። ይህንን ዓይነት መዛነፍ በማስከተል በቀደምት አበው ተሸፍኖ መቃብያን ከቅዱሱ የእግዚአብሔር ቃል ጋር እንዲቆጠረው ያደረገው ጥንተ ጠላታችን መሆኑን ከመቀበል ውጪ ያፈጠጠውን እውነት መካድ የሚቻል አይደለም።
(ይቀጥላል)

Tuesday, May 21, 2013

«እግዚአብሔርን ወደማወቅ መድረስ


የሥነ አእምሮ፤ የፍልስፍናና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ሪቻርድ ፕራት ሃይማኖትን ሰዎች የሚጠቀሙት ከሚመጣባቸው ቁጣና ቅጣት በማምለጥ ሰላምና ዘላለማዊ ዋስትና አገኝበታለሁ ብለው ለመጠለያነት ነው ይላሉ። ከዚያ ተቋም ውጪ ዋስትና አለ ብለው አያስቡም። ሰላምና ዋስትና መፈለግ በራሱ ጥሩ ቢሆንም ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት በራሳቸው መንገድ የተገለጸውን ሰላምና ዋስትና መስጠት ወይም ማሰጠት አለመቻላቸው እውነት ነው። እንደሃይማኖቶቹ ልዩነት የተለያየ የደኅንነት መንገድ የለም። ምክንያቱም ዋስትናና ሰላም በተቋም ደረጃ ለተከታዮች የሚከፋፈል ስጦታ ሳይሆን  መስጠት ከሚችልና ዋስትና ካለው የሰላም ባለቤት ከራሱ ከእግዚአብሔር ለጠየቁትና ለለመኑት በቀጥታ የሚሰጥ እንጂ እግዚአብሔር ለሃይማኖት ተቋማት በተለይ አድሎ፤ እነርሱ ደግሞ በተናጠል ወደእነሱ ለመጣ እንዲያድሉ የተደረገበት መንገድ በፍጹም የለም። እግዚአብሔርን አባት ብለው ለሚጠሩት አማኞች ሁሉ አባት  የሚሆነው ልጅ የመባልን ጸጋ በነጻ ማግኘታቸውን አምነው ለተቀበሉ ብቻ ነው ይላሉ ዶ/ር ፕራት።
« በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና» ገላ 3፤26
በማመን የሚገኘውን ጸጋና ልጅነትን በሃይማኖት ተቋም በኩል መቀበል አይቻልም። ዛሬ በዚህ ዓለም ላይ የሃይማኖት ተቋማት መብዛት ዋናው ምክንያት ከሌላው የተሻለ ሰላምና ዋስትናን ለተከተለን ሁሉ እናድላለን ብለው ስለሚሰብኩ ብቻ ነው። በየድርጅቶቹ ውስጥ ያሉ ተከታዮችም በዚያ ተቋም በኩል ሰላምና ዋስትና ያገኙ ስለሚመስላቸው እኔ ኦርቶዶክስ ነኝ፤ እኔ ካቶሊክ ነኝ፤ እኔ ይሁዲ፤ እኔ እስላም፤ እኔ ፕሮቴስታንት ነኝ፤  ጴንጤ ነኝ፤ እኔ ደግሞ ሙሉ፤ ጎዶሎ፤ ቤዛ፤ መሠረት፤ሞርሞን፤ ወዘተ ነኝ እያሉ መታመኛና ዋስትና ያለበት የራሳቸውን ተቋም ትክክለኛነት ይናገራሉ። ሁሉም ራሱን ከሌላው የተሻለ የዋስትናና የሰላም ምንጭ የሆነውን ፈጣሪ ለመስጠት ብቃቱና ውክልናው አለኝ ብሎ ለራሱ ይመሰክራል።  እንዲያውም አንዱ ሃይማኖት የሌላውን ጉድለት በራሱ መንገድ እየዘረዘረ ራሱን ከማንም የተሻለ የእግዚአብሔርን ጎዳና መሪ አድርጎ በመደስኮር ወደእሱ ለመምጣት እንዲሽቀዳደሙ ሲሰብክ ይታያል። እግዚአብሔር ሰዎችን የሚመዝነው ባሉበት የእምነት ተቋም ያለውን ህግና ደንብ ማክበራቸውን በማየት ሳይሆን እግዚአብሔርን አውቀው ከእርሱ ጋር ያደረጉትን እምነትና ኅብረት በመመዘን ብቻ መሆኑ እውነት ነው። አማኞች ያሉበት ሃይማኖት የሰራላቸውን አጥር አልፈው እግዚአብሔርን ለማወቅና ለማግኘት፤ ከእኔነት አዙሪት ወጥተው ለአንዱ እግዚአብሔር መገዛት ቢችሉ ኖሮ የሃይማኖት ተቋማት ባልኖሩም ነበር።  የመጀመሪያይቱ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። ዛሬም ከድርጅትነት የተለየች የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። የየሃይማኖቶች ጥምቀት፤ ጌታና አባት የለም። ሃይማኖቶች ግን የየራሳቸውን ጌታ፤ አባትና ጥምቀት ሲሰጡ ይታያሉ። ይህም የመጽሐፉ ተቃራኒ ነው።
«አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ»  ኤፌ 4፤5-6
 ይሁን እንጂ ያለው እውነት አንድ ብቻ በመሆኑ እኔ፤ እኔ ያለው ሁሉ እውነተኛ ሊሆን አይችልም። በዚህም ይሁን በዚያ የማይናወጥና የማያጠራጥር እውነት፤ ሰላምና ዋስትና ያለው ከምንጩ ባለቤት ከኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ክርስቶስም  ሰላምና ዋስትናን በውክልና እንዲሰጥ ያቋቋመው አንድም ተቋም እና ድርጅት በዚህ ምድር ካለመኖሩም በላይ ክርስቶስ በአማኞች ልቦና ላይ ሰላምና ዋስትናን ሊመሰርት መጣ እንጂ ድርጅት ሊያቋቁም አይደለም። ክርስቶስ ያቋቋመው እኔን ነው ማለት የሚቻለው  ባለሰርቲፊኬት ተቋም ባለመኖሩ ሁሉም እኔ ከሌላው የተሻልኩ ለክርስቶስ ቅርብ ነኝ እያለ ራሱን አጽዳቂ ከመሆን ውጪ ሰላምና ዋስትናን በዚህ ምድር ማምጣት አይችልም።
ሳይካትሪስትና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ዶ/ር ሪዩበን ዴቪድ  ደግሞ እንዲህ ይላሉ። ሁሉም ሃይማኖቶች እግዚአብሔርን የሚገልጹበት የየራሳቸው ዶግማና አስተምህሮ፤ የእግዚአብሔር ወዳጅ ለመሆን የሚያስችልም የየራሳቸው ሕግና ደንብ አላቸው። ያንን ዶግማና አስተምህሮ፤ ሕግና ደንብ በመጠበቅ ብቻ ትክክለኛው እግዚአብሔር ይገኛል ስለሚሉ  እያንዳንዱ የሚያምነውና ከእርሱ ዘንድ ብቻ በትክክል እንዳለ የሚገልጽበት የራሱ እግዚአብሔር አለው  ሲሉ  ያብራራሉ።  ዶ/ር ሪዩበን ማብራሪያቸውን ሲቀጥሉ ትክክለኛው እውነት ግን እግዚአብሔር ራሱን የገለጸበትና የሚለካበት መንገድ እያንዳንዱ ሃይማኖት በጻፈው ዶግማ፤ አስተምህሮ፤ ሕግና ቀኖና መሠረት አለመሆኑ ነው።  የእስላሞች ፈጣሪ «አላህ» ይባላል። እስላሞች ራሳቸው የተረጎሙትን ያንን «አላህ» ሰው ማመን ካልቻለ አይድንም ይላሉ። አላህ የሚገኘውም ቁርአን በተባለ መጽሐፋቸው ውስጥ ነው። ከዚያ ውጪ አላህ የለም።ካቶሊኮች የራሳቸው የሆነና ካቶሊካዊ ትርጉም  የተሰጠው እግዚአብሔርን የማወቅ ዐለምዓለቀፋዊነት አስተምህሮ፤ ዶግማና ቀኖና አላቸው። ሰዎች ትክክለኛውን እግዚአብሔርን ለማግኘት እነዚያ መጽሐፍቶች ውስጥ ገብተው በተተረጎመው ተቋማዊ እምነት ውስጥ መነከር አለባቸው። ካቶሊክ መሆን ካልቻሉ እግዚአብሔርን አያገኙትም፤ ወይም በተሳሳተ ጎዳና ላይ ናቸው ይላሉ።  ገሚሱም የቀደመችው መንገድ በዚህ አለች ይላሉ። አንዳንዶቹም ኢየሱስን ከእኛ ዘንድ ተቀበሉ፣ እንደግል አዳኝ ካልወሰድክ አትድንም ይላሉ። እርግጥ ነው፤ እምነት የግል ነው። የክርስቶስ የማዳን አገልግሎት የተሰጠው ግን ለግል አይደለም። ላመኑ ሁሉ እንዲያው የተሰጠ ጸጋ ነው። አንድ ሰው በግሉ ክርስቶስን ማመኑ ክርስቶስን የግል አዳኝ አያደርገውም። ማንም ለመዳን በዚህ የግል አዳኝነቱ መስመር ውስጥ የግድ ማለፍ የሚሉ እንደብቸኛ ወኪልነት ራሳቸውን  የሚቆጥሩ ናቸው።  ዶ/ር ሪዩበን፤ በእርግጥ ማንም ሰው ስለክርስትና መሠረታዊ የመዳን ትምህርትና ሕይወት የሚገኝበትን የመንፈስ ቅዱስ ምሪት እውቀት ያስፈልጉታል። «ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል» 2ኛ ጢሞ 3፤5   «እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው» ሮሜ 10፤17
ቅዱሱን መጽሐፍ መማርና ማንበብ ሕይወት የሚገኝበትን ቃል ለማግኘት እንጂ የድርጅት አባል በመሆን ለእግዚአብሔር ያሉበትን ተቋም እንደትክክለኛ ሥፍራ የማቅረብ ዓላማ አይደለም። ሐዋርያትም ወንጌልን እየተዘዋወሩ ሕዝቡን እያስተማሩና እያጠመቁ ወደ ሕይወት መንገድ መመለስ ቻሉ እንጂ  ድርጅትና የእምነት ተቋም በመመስረት ስለማገልገል አንድም ቦታ ወንጌል ላይ አልነገሩንም በማለት ያብራራሉ ዶ/ር ሪዩበን።  ሰው በመጠየቅ፤ በማንበብ፤ በመማር፤በመጸለይና በእግዚአብሔር ፈቃድ እውነቱን ወደማወቅ  ሊያደርስ ይችላል። በአንድ ድርጅት ውስጥ ተወትፎ መኖር ግን እውነት ምን እንደሆነ ከማወቅ ይከለከላል። ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ የአይሁድ እምነት ተከታይ እንደነበረ የኦሪቱን ሕግ ሊፈጽም ኢየሩሳሌም የመገኘቱ ታሪክ ይነግረናል። ወደሀገሩ ሲመለስ ያልገባውን በመጠየቅ በሐዋርያው ፊልጶስ የኢሳይያስ መጽሐፍ ትርጉም ሲነገረው  እውነቱን ወደማወቅ ደረሰ፤ አመነ ተጠመቀም። ከአይሁዳዊ የእምነት ተቋም ወደክርስትና የመዳን ሕይወት ወዲያው ተሸጋገረ። በሕይወቱ ላይ የመጣው አዲስ ለውጥ ከአይሁድ ሕግና መመሪያ ድርጅታዊ ትእዛዝ ነጻ በመሆን ክርስቲያን የመባል የሐዋርያት እምነትጋር ኅብረት አደረገ እንጂ ከድርጅት ወደድርጅት አልተዘዋወረም። ያለኝ ኦሪታዊ ሕግና ደንብ ይበቃኛል፤ መዳን በዚያ ነው ያለው ብሎ በተቋማዊ ሕግጋቱ ላይ በድርቅናው ጸንቶ ቢሆን ኖሮ እውነቱን ወደማወቅ ባልደረሰም ነበር።  ክርስትና ማለት በክርስቶስ የተገለጠውን እውነት ማወቅና በዚያ ሕይወት ውስጥ መኖር በመሆኑ ጃንደረባው ከዚህ አዲስ እምነት ጋር ለማወቅ ባለው ትጋት ልክ ሊገባ በቃ።  የሃይማኖት ተቋማት አባል ሆኖ መቅረት ማለት በተቋሙ ጣሪያ ስር ተደፍኖ መቅረት ማለት ነው። በጣሪው ከተዘጋ ልቡና ወጣ ብሎ እውነቱን ለማወቅ ሰው ቢፈልግ ኖሮ እንደጃንደረባው ወደእውነቱ መድረስ በቻለ ነበር። ዛሬ በዓለማችን ላይ ያሉ ሃይማኖቶች ሁሉ በተለይም በክርስትናው ስም የሚንቀሳቀሱት በየራሳቸው ጣሪያ ስር ሚሊዮኖችን ነፍሳት ደፍነው በመያዝ ከዚያ እንዳይወጡ በሕግ፤ በመመሪያ፤ በደንብና በትዕዛዝ አጥር  እውነቱን ወደማወቅ እንዳይደርሱ ከልክለው ይገኛሉ።  እስልምና የተባለው እምነት ተከታዮቹን በሃይማኖት መጽሐፉ ላይ ከየትኛውም  ሌላ እምነት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርጉና በእምነት ከማይመስሏቸው ሰዎችም ጓደኝነትን እንኳን እንዳይዙ በጥብቅ ያስጠነቅቃል።  (ሱረቱ አል ኢምራን 3፤28) ከዚህ ጥብቅ መመሪያ የተነሳ ከዚህ እስር ለመውጣት አይችሉም። ከዚህም የተነሳ እውነት ምን እንደሆነ ወደማወቅ ለመድረስ ሊደርሱ አይችሉም። ኢየሱስ ክርስቶስ  በትንሣኤ ዘለሙታን ዳግም ሲመጣ በእሱ ላይ የነበረንን እምነትና ምግባር ይመዝናል እንጂ በነበርንበት የሃይማኖት ተቋም ልክና ማንነት አይፈርድልንም ወይም አይፈርድብንም።  እኔ ቀጥተኛይቱ ስላልን ቀጥተኛ አንሆንም። ቀጥተኛው የት እንዳለ በቃሉ ስንመረምር ብቻ እውነቱን ማወቅ ይቻለናል። አስተዋይ ልብም  በእውቀት፤ ጠቢብም በመሆን ሰሚ ጆሮ ካለን መንገዳችንን ያሰፋዋል፤ በታላቅም ሥፍራ ያደርሰናል። 
«የአስተዋይ ልብ እውቀትን ያገኛል፥ የጠቢባንም ጆሮ እውቀትን ትፈልጋለች፣ የሰው ስጦታ መንገዱን ታሰፋለታለች፥ በታላላቆችም ፊት ታገባዋለች» ምሳሌ 18፤15-16
መንፈሳዊ ሰው መሆን ማለትም ያሉበትን ድርጅት ዓላማ መቀበልና መፈጸም ሳይሆን እግዚአብሔርን ማወቅ፤ እንደትእዛዙና ፈቃዱ መኖር ማለት ነው። ስለዚህ ከድርጅት በላይ እግዚአብሔርን ወደማወቅ አዲስ ሕይወት ልንሻገር ይገባል ።
1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2፥3-4
ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው።

Monday, April 29, 2013

ወድቆም ያፈራል


Wedkom Yaferal Read in pdf

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ ዓርብ ሚያዝያ 18/2005 ዓ.ም.
ከጸሎት ክፍሎች አንዱ ስእለት ነው፡፡ ስእለት ለእግዚአብሔር የምንገባው ቃል ነው፣ እግዚአብሔርም የሚጠብቀው ብርቱ ነገር ነው /መክ. 5፡4-5/፡፡ በተሳልንበት ግለት እንድንፈጽመው ይጠበቅብናል፡፡ ስእለት ለእግዚአብሔር አመጣለሁ የምንለው የምስጋና መግለጫ ነው፡፡ አንዳንዶች ገንዘባቸውን፣ ሌሎች ሕይወታቸውን፣ የቀሩት ልጆቻቸውን፣ ውስኖች የሰጣቸውን ለእርሱ ለመስጠት ስእለት ይገባሉ፡፡ ስእለት መሳል ፈቃድ ነው፣ አለመፈጸም ግን ትልቅ ኃጢአት ነው፡፡ ሰው እግዚአብሔርን እንዴት ይዋሸዋል?
ስእለት እግዚአብሔር ስላደረገልን ነገር የምስጋና መግለጫ ይዘን የምንመጣበት ነው፡፡ ስእለት የውለታው ምላሽ ሳይሆን የውለታው መታሰቢያ ነው ብንል ይገልጸዋል፡፡ በብዙ ጭንቀቶች ባለፍኩባቸው ዘመናት ሁሉ ስእለትን ለእግዚአብሔር እሳላለሁ፡፡ እነዚያን የከበዱኝን ወራቶች ሳስብ መከራው ከባድ ሆኖ ነው ወይስ እኔ ደካማ ሆኜ ነው? የሚለውን እስካሁን ልመልሰው አልቻልኩም፡፡ ብዙ የሀዘንና የስብራት ዘመኖችን እግዚአብሔር አሻግሮኛል፡፡ እንደ ፈቃዱም መልስ ሰጥቶኛል፡፡ እንደ ፈቃዱ ከልክሎኛል፣ እንደ ፈቃዱ ባርኮኛል፡፡

Wednesday, April 24, 2013

ንስሐ ለማን፤ ለምንና እንዴት?


 (ከዚህ በፊት የቀረበ ጽሁፍ ነው)

«ነስሑ እስመ ቀርበት መንግሥተ ሰማያት» (መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ማቴ ፫፤፩-፪)

«ነስሐ»  ስርወ ቃሉ እብራይስጥ ሲሆን ትርጉሙም አዘነ፤ ተጸጸተ፤ ተመለሰ፤ ክፉ ዐመሉን ተወ፤ መጥፎ ጠባዩን ለወጠ ማለት ነው። የግእዙም ግስ ይህንኑ ቃል እንዳለ ወርሶ ይጠቀምበታል።
«ነስሑ እምፍኖቶሙ እኩይ፤ ወእግዚአብሔርኒ ነስሐ እምዘነበበ» ይላል በዮናስ ፫፤፲ ላይ። ከክፉ መንገዳቸው ተመለሱ፤ እግዚአብሔርም በተናገረው ተጸጸተ»  እንደማለት ነው። ሰብአ ነነዌ ከኃጢአታቸው በንስሐ በተመለሱ ጊዜ እግዚአብሔርም ሊቀጣቸው በነበረው ፍርድ አዘነና ምህረትን ሰጣቸው። የእግዚአብሔር ሀዘን ከምህረቱ ሲሆን የሕዝቡ ሀዘን ደግሞ ከበደሉ ነው።       «ነስሐ» የሚለው ቃል በሁሉም ሥፍራ ማዘንን፤ መመለስን፤ መፀፀትን፤ መተውን ያመለክታል። «እግዚአብሔር ተፀፀተ» ስንል አምላካዊ ምሕረቱን ለመቀበል በማይፈልግ የሰው እልክኛ ልብ ወይም በሌላ መልኩ ምሕረቱን በሚጠይቅ ተነሳሒ ላይ ባለው አባታዊ ፍቅር እንጂ የሚጎድለው ወይም የሚጨመርለት ስላለ ያንን ከማጣትና ከማግኘት ጋር በተያያዘ አይደለም። ሰብአ ነነዌ ከተዘጋጀው ጥፋት ለመመለስ ንስሐ ሲገቡ እግዚአብሔርም በአምላካዊ ምህረቱ አዝኖላቸው ጥፋቱን መልሶላቸዋል። በሌላ ቦታም እንዲህ የሚል አለ።
በዘመነ ኖኅ የሰው ልጅ ዐመጻ በዝቶ የጥፋት ውሃ በታዘዘ ጊዜ «እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ፥ በልቡም አዘነ» ዘፍ ፮፤፮ ይላል።
«ተጸጸተ» የሚለው ቃል «ነስሐ» የሚለው ቃል ትርጉም ነው። «እግዚአብሔር ተጸጸተ፤ አዘነ» ሲል ቀድሞ ያላወቀው ነገር በመድረሱ ወይም የማያውቀው ነገር እንደተከሰተ በማየቱ የተሰማው ስሜት ሳይሆን የሰው ልጅ ቀድሞ ከገነት ሕጉን አፍርሶ በመውደቁና ዳግመኛም በዚህ ምድር ላይ ኃጢአቱን እያበዛ በመሄዱ የተነሳ ሰው በራሱ በደል የሚመጣበት የፍርድ ቁጣ ስለሚያሳዝነው ብቻ ነው። ፻፳ የንስሐ ዘመንን ለመጠቀም ያልፈለገ ሕዝብ በውሃ ሰጥሞ ሲጠፋ ቢመለከት እግዚአብሔር መጸጸቱ አምላካዊ ባሕሪው ነው። እግዚአብሔር አባት በመሆኑ ሰዎች ይጠፉ ዘንድ ሳይፈልግ ዐመጻቸው ከሚያመጣባቸው ፍርድ የተነሳ ግን ያዝናል፤ ይጸጸታል።

Sunday, March 24, 2013

ዓለም ለእኔ ብቻ በሚሉ ስግብግቦች የተሞላች ነች!


በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ሁላችንም የዚህ ስግብግብነት ሰለባዎች ነን። ምናልባት ላይታወቀን  ቢችል ወይም በሌላው ላይ ያደረስነው የስግብግበት መገለጫ ጠባይዓት በግልጽ ባለመታየቱ ብቻ ራሳችን ነጻ እንደሆንን እናስብ ይሆናል። ነገር ግን የሰው ልጅ ከሥጋ ድካምና ከፈተናው ጽናት የተነሳ ስግብግብ ነው። ስግብግብነት ማለት ሁሉን ለእኔ በሚል ፍላጎት ዙሪያ ብቻ የሚሽከከረከር  ሳይሆን ስሱዕ /ስስታምነትን/ ፤መጠን የለሽ ጉጉነትን ይጨምራል።  ስስታምነት ለራስ ማድላትና ራስን ማዕከል ባደረገ ስሜት ስር መታጠር በመሆኑ የስግብግብነት አንድ አካል ነው። ጉጉነት ደግሞ እዚያ ጠርዝ ላይ ለመድረስ የሚጠይቀውን መስዋዕት ሁሉ ለመክፈል መሮጥ ነው። ስግብግብነት ከመጠን በላይ መብላት፤ በብዙ ወጪ ለመርካት መሞከር፤ የፍላጎት ጣሪያ መናር እና የአኗኗር ቅንጡነትንም ይጨምራል። «ሁሉ አማረሽን ገበያ አታውጧት» የሚባለው የፍላጎት ስግብግብነት ልክ ማጣት ማሳያ ነው።
ስግብግብነትን ካምብሪጅ ዲክሽነሪ በምሳሌ እንዲህ ይለዋል።
(industrialized countries should reduce their gluttonous (= greater than is needed) consumption of lifesyle)
የበለጸጉ ሀገሮች የስግብግብ ፍጆታ አኗኗራቸውን መቀነስ አለባቸው እንደማለት ነው።  ምክንያቱም የአኗኗራቸው ቅንጡነት ስግብግቦች እንዲሆኑ አድርጓቸዋል።ለልቅ ኑሮ ጉጉ ናቸው። ጉጉነት /AVID / ያላዩትን ነገር እንዲያዩ ይገፋቸዋል። ጉጉነት ምንጊዜም አንድን እርከን ከመሻገር በኋላ የሚመጣ ፍላጎት ነው።  ምንም የሌለውና በጣም የተራበ ሰው በቅድሚያ የሚታየው ወይም ከፊቱ ድቅን ብሎ የሚመጣበት ጉጉት ምንም ይሁን ምንም ረሃቡን የሚያስታግስበትን የእህል ዘር እንጂ ከትልቅ አዳራሽ ውስጥ ተሰይሞ የበግ አሮስቶ በውስኪ እያወራረደ መርካት አይደለም።  ያ ማለት ግን አይፈልግም ማለት አይደለም። ይህ የቅንጦት እሳቤ ምንም ከማጣት ችጋር ጋር ስለማይቀራረብ ብቻ ነው። የበለጸጉ ሀገሮች ግን በብዙ መልኩ ከችጋር ስለወጡ አመጋገባቸው ሁሉ ጊዜ ሰርግና መልስ ነው። እንደ ችጋር ሀገሮች የበሉት የምግብ ተረፍ ለበኋላ ተብሎ ይቀመጥ ዘንድ በፍጹም አይታሰብም። አዲስ ሞዴል መኪና፤ አዲስ የቤት እቃ፤ አዲስ ሁሉ አዲስ እንዲሆንላቸው ፍላጎታቸው ጣሪያ ነው። ለሌላው አዲስ ለእነሱ አሮጌ ነው። መሪዎቻቸው የእነዚህን ቅንጡ ሰዎች ኑሮ ላለማጓደል ከሌላው ዘርፈው ወይም ቀምተው ያመጡላቸዋል። ዘረፋው በቀጥታ ላይሆን ይችላል። ሚዛናዊ ባልሆነ ንግድ ወይም የምርት ልውውጥ፤ ሽያጭና ጥቅሞቻቸውን በሚያስከብሩ ስምምነቶች ሊሆን ይችላል። በአንዱ ቦታ የመሳሪያ ቅነሳ ወይም ማስተላለፍ እገዳ ፊርማ ቢያኖሩ  በሌላ ቦታ ደግሞ በመርከብ ጭነው ሊሸጡ ይችላሉ። ይህንን ካላደረጉ ሰማይ የደረሰውን ስግብግብ ፍላጎታቸውን መሙላት አይችሉም።

Sunday, March 17, 2013

ክርስቶስ በአምላክነቱ ቃል ማዳን ሲችል ለምን ሥጋ መልበስ አስፈለገው?


የብዙ ሃይማኖቶች መምህራን «ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ፤ ፍጹም ሰው ነው» በማለት ይመሰክራሉ። ይህም እውነት ነው። ነገር ግን ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር ወልድ በመለኮታዊ ሥልጣኑ ማዳን ሲችል ለምን ሥጋ በመልበስ በሞቱ አዳምንና ልጆቹን ማዳን አስፈለገው? ለሚለው ጥያቄ የጠራ መልስ የላቸውም። ሥጋ መልበስ ማለት አምላካዊ ስልጣኑን በመተው ራሱን ባዶ ማድረግ እንደሆነ ለመቀበል ሲቸገሩ ይስተዋላሉ። ይሁን እንጂ ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ሲል በትክክል ገልጾታል።

«እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ» ፊልጵ ፪፤፮-፯ 

ፍጹም ሰው ሆነ ስንልም መለኮታዊ ማንነቱን ተወ ማለት ሳይሆን አምላካዊ ሥልጣኑን ሸሸገ ማለታችን ነው። ከኃጢአት ብቻ በቀር እንደእኛ የተፈተነውም ለዚህ ነው። መለኮታዊ ስልጣኑን የመሸሸጉ ምክንያትም ፍጹም ሰው በመሆን ከአብ ጋር ያለውን መለኮታዊ ዕሪናውን  እንደተወ ሳይቆጥር እንደልጅ ለመታዘዝ ነው።  ብዙዎች ኦርቶዶክሳውያን የሆንን ሰዎች ልጅ ሆኖ መታዘዙን ልክ፤ ከአብ  ያነሰ አድርጎ እንደመቁጠር ስለምናስብ እንደነግጣለን። አማለደ፤ አስታረቀ፤ ታዘዘ የሚሉ ቃላትን መስማማት የወልድን ባሕርይ ህጹጽ አድርጎ  የሚያወርድ ነው በማለት ለመቀበል የማይፈልጉ አስተሳሰቦች ሞልተዋል። አምላካዊ ባህርይውን ለመጠበቅ ሲባል ፍጹም ሰው የሆነበትን ምስጢር በመሸርሸር ከማማለድ፤ ማስታረቅና መካከለኛ የመሆን ማንነቱ ለመሸሽ መሞከር  ምስጢረ ሥጋዌን በሽፍንፍኑ እንደመሻር ይቆጠራል። 

 ማማለድ፤ ማስታረቅና መካከለኛ መሆኑን አምኖ መቀበል ከሌለ ፍጹም ሰው እንደሆነ ማመን በፍጹም ሊመጣ አይችልም። በመለኮታዊ ሥልጣኑ ማዳን እየቻለ ሥጋ መልበስ ያስፈለገው በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ ማፍረስ የሚችል ከኃጢአት ሁሉ ንጹህ የሆነ የእግዚአብሔር ልጅ በመካከል እንዲገባ በማስፈለጉ እንደሆነ አምኖ መቀበል የግድ ነው። ያለበለዚያ ነገረ ድኅነት የሚባል አስተምህሮ አይመጣም።
ቀድሞ ሰውና እግዚአብሔርን ሲያገናኝ የቆየው ሕግ ነበር። ሕጉ የሚያዘውን ሁሉ የሚያስፈጽሙ መካከለኞች ደግሞ ካህናቱ ናቸው። በሕግ ተቀባዮች በሕዝቡና በሕግ ሰጪው በእግዚአብሔር መካከል ያሉት መካከለኛ የሕግ አስፈጻሚዎቹ ራሳቸው ንጹህ መሆን ይጠበቅባቸው ነበር።  ይህንንም የስርየት መስዋዕት በማቅረብ መንጻት ግዴታቸው ነው። ከዚያም የሕዝቡን ሥርየት ሕጉን በመተግባር ያስፈጽማሉ። እንግዲህ ይህ መስዋዕት ዕለት ዕለት የሚደረግ ነው። እንደዚያም ተደርጎ ለሕጉ ፈጻሚዎች  ዘላለማዊ የሆነ ስርየትን ማስገኘት አይችሉም። ይህ መስዋዕት ምድራዊ ነው። ምክንያቱም በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ትዕዛዝን የማፍረስ የጥል ግድግዳ በቀዳማዊው ሰው ጥፋት የተነሳ ተተክሎ ነበርና። 

ይህ የጥል ግድግዳ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መፍረስ ነበረበት። በሕዝቡና በእግዚአብሔር መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ በብቃት ለማፍረስ ደግሞ ኃጢአት የማያውቀው ሰው ያስፈልጋል። ክህነቱም ፍጹም ሊሆን ይገባል። ይህንንም ለማሟላት አምላክ ሰው በመሆን ያንን ደካማ ሥጋችን በመልበስ ከውድቀት ማዳን ነበረበት። በዚህም የተነሳ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ወልድ በፈቃዱ የአብ የባህርይ ልጅ ሆኖ ሥጋችንን ለመልበስ በግብረ መንፈስ ቅዱስ በመካከላችን አደረ። እንደሰውነቱ ኃጢአት አያውቀውም። እንደካህንነቱ ዘላለማዊ ካህን ነው። እንደአዳኝነቱ ሞት አያሸንፈውም። እንደልጅነቱ የአባቱን ፈቃድ የሚፈጽም ነው። እንደስርየት መስዋዕትነቱ አንዴ፤ ግን ለሁል ጊዜ  የሚሆን ነው። ይህም የነበረውን ጥል አፍርሶ በአብ የተወደደ መካከለኛና ለሕዝቡ ኃጢአት ዘላለማዊ ሥርየትን ማስገኘት የሚችል ሊቀ ካህን ሆኗል።

Thursday, March 7, 2013

«ጉዞው»


መንፈሳዊ ልቦለድ

የሀገርህን እወቅ ጉዞ ደስ ይለኛል። ባለኝ ትርፍ ጊዜ ወይም ዓመታዊ የሥራ ፈቃድ ያላየኋቸውን ታሪካዊም ይሁን ከባቢያዊ መልክዓ ምድሮች፤ የኅብረተሰብ አኗኗርና ባህል መጎብኘት በጣም ስለሚያስደስተኝ እነሆ ተሰናዳሁ። አዲስ አበባ አምስት ኪሎ ባለችው ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን መግቢያ በር አካባቢ በተለጠፈ አንድ ማስታወቂያ ላይ ባገኘሁት አድራሻ መሠረት በዓመታዊው የመርጦ ለማርያም የንግሥ በዓል ላይ ለመታደም ከተጓዦች ጋር እነሆ ታድሜአለሁ።
 
አውቶቡሱ በተቀጠረለት ቦታና ሰዓት ቆሟል። እኔም ሰዓቱን አክብሬ ከቦታው ተገኝቻለሁ። ተጓዦችም ተሰብስበዋል። ግማሹ ሀገሩን ለቆ የሚሄድ እስኪመስል ድረስ የሚያመላልሰው ጓዝ የት የለሌ ነው። ጧፉ፤ ሻማው፤ጥላው ይጫናል። ግማሹ ለስለት፤ ግማሹም ለሽያጭ ነው። ነጋዴው የሚሸቅጠውን እቃ ይጭናል፤ ያስጭናል። ከየአድባራቱ በተንሸዋረረ ጨረታ የሚገዙ ነጋዴዎች በዓላትን እየቆጠሩ ይሸቅጣሉ። የሥራ ፈጠራ ይሁን በተፈጠረው ሥራ የማትረፍ ክህሎት፤ ገንዘብ ለዋጩና ሻማ ሻጩ ብዙ ነው። ግርግሩ ለብቻው ነው። ዓለማየሁ፤ ዓለሚቱ፤ መንግሥቱ.........ከዚህም፤ ከዚያም የሰዉ ስም ይጠራል።  «ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ» የሚል መዝሙር በትልቁ የከፈተ አንድ ተጓዥም ሲንቅ ሲጭን አይቻለሁ። ጆሮው ላይ ማዳመጫውን የወተፈና በመዝሙር ምርቃና ውስጥ የሰጠመ ሌላው ተጓዥም ምናልባት መንግሥቱ፤ ሀብታሙ....... እየተባለ ሲጠራ ያልሰማው በምናቡ መንግሥተ ሰማይ የገባ መስሎት ይሆናል። ቢሆንስ? ማን ያውቃል።

የንጋት ብርድ አጥንት ሰርስሮ ስለሚገባ የለብስኩትን ጋቢ እጥፋት ዘርግቼ ወደአንድ ጥግ ቆምኩኝ። ከእጄ የቪዲዮ ካሜራ በስተቀር የያዝኩት ምንም ጓዝ ስለሌለ ራሴን ከዚህ ግርግር የሰወርኩ እድለኛ አድርጌ ቆጠርኩት።  ሲፈጥረኝ ግርግር አልወድም። በሰርግና በበዓላት ድግስ ላይ ሰዎች ሲዋከቡ ሳይ ይገርመኛል። ግርግሩ ካለፈ ወደነበረ ማንነት መመለስ ስላለ ያንን መዘንጋት መስሎ ስለሚሰማኝ ምንም አይመስለኝም።  ትንሹን ነገር አዋክበው የተዋጣለት ግርግር መፍጠር የሚችሉ ሰዎችን ሳይ ይገርመኛል። መርጦ ለማርያም ለዓመታዊ ክብረ በዓል ለመሄድ መንፈሳዊነቱ ማድላት ሲገባው ይሄ ሁሉ ግርግርና አታሞ ይገርማል።