Friday, August 29, 2025
እንዳንጠፋ ድነታችንን በጸጋው ኃይል አጽንተን እንጠብቃለን!
በጌታችንንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ አንዴ ድነናል፣ በዚህ ድነት በመንፈስ እንመላለሳለን፣ ኃጢአትን አንፈፅምም!
“ነገር ግን እላለሁ፥ በመንፈስ ተመላለሱ፥ የሥጋንም ምኞት ከቶ አትፈጽሙ።”
— ገላትያ 5፥16
የሀልዎተ እግዚአብሔር ቤተክርስቲያን መጋቢ ዘነበ ግርማ ድነታችን በሕይወት ዘመናችን በጽድቅና በቅድስና በመመላለስ ካልፈጸምነው ልንጠፋ እንችላለን ብሎ ያስተማረውን ትምህርት የሪል ስቴቱ ባለቤት ነብይ በላይ ሽፈራውና ኢየሱስ ክርስቶስ የሞተው ለተመረጡት ሰዎች ብቻ እንጂ ለዓለሙ ሁሉ አይደለም ብሎ የሚያስተምረው አማን ሻሎም የተባሉት ነብይ ዘነበን ተቃውመው የሙግት ትምህርት ሲለፈልፉ ሰማሁ። አዘንኩም፣ ገረመኝም። ያዘንኩት እነዚህ ተቃዋሚዎች ከእነሱ በስተቀር የቃል እውቀት ማንም እንደሌለው አስበው መናገራቸው ሲሆን የገረመኝ ለከት የሌለው ባዶነታቸውን በአደባባይ ሲገልጹ አለማፈራቸው ነው።
የዘነበን፣ የበላይ፣ የአማን ሻሎም እና የተመሳሳይ ሰዎች አስተምህሮ በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ከመበርበራችን በፊት እንደመግቢያ የመጀመሪያውን ሰው የአዳምን ማንነት እንደማስረጃ እንመልከት።
አዳም እንዲኖር የተሰጠው ቦታ የት ነበር ብትባሉ በገነት እንደምትሉ እርግጠኛ ነን። የሰው ልጆች ከዚህ ምድር በሞት ሲለዩ ነፍሳቸው የት ትሄዳለች ብለን ብንጠይቃችሁ መልሳችሁ ምን ሊሆን ይችላል? በገነት ልትሉ እንደምትችሉ ብንገምት የተሳሳትን አይመስለንም። ምክንያቱም ከኢየሱስ ጋር ከተሰቀለው አንዱን ፍርደኛ ኢየሱስ እንደዚህ ሲል ሰምተነዋል።
“ኢየሱስም፦ እውነት እልሃለሁ፥ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ አለው።”
— ሉቃስ 23፥43
በፊትም አዳም የኖረበት፣ በኋላም በኢየሱስ ክርስቶስ ያመንን እኛ የምንኖርበት ቦታ ገነት መሆኑን እንረዳለን። አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እስኪፈጠሩ መኖሪያችን ዔድን ገነት ነው።
“ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን።”
— 2ኛ ጴጥሮስ 3፥13
እሺ! እውነቱ ይህ ከሆነ አዳምን ለዘላለም ይኖር ዘንድ እግዚአብሔር ከሰጠው መልካም ሥፍራ ከሆነው ገነት ያስወጣው ምንድነው? እግዚአብሔር አዳምን በገነት ማኖር ስላልፈለገ ነው እንዴ ከገነት የተባረረው? አይደለም! አዳም ከሚስቱ ጋር የእግዚአብሔርን ቃል በገዛ ምርጫቸው ስላፈረሱ ነው።
ባለመታዘዝና የተሰጣቸውን ትዕዛዝ በማፍረሳቸው፣ ከእግዚአብሔር ድምፅ ይልቅ የሰይጣንን ፈቃድ ለመፈፀም ፈቃደኛ ስለሆኑ ነው የተባረሩት። ሁሉን አዋቂ እግዚአብሔር አዳም እንደሚሳሳት አያውቅም ነበር? እግዚአብሔር አስቀድሞ ያውቃል! የእግዚአብሔር ሁሉን አዋቂነት የሰውን ልጆችን ነጻ ምርጫ አይጋፋም። ማወቅና መረዳት የምንችልበትን ነፍስያ ባህርይውን ያካፈለን ለዚህ ነው። በምርጫህ ወደህ፣ አምነህ ታመልከዋለህ፣ አልፈልግህም ብለኸው ለኃጢአት ብትገዛ ከኃጢአት የሚታጨደውን ደመወዝ በምርጫህ ትቀበላለህ።
ስለሆነም አዳም በበደለ ጊዜ ዐመጽና ኃጢአት ከእግዚአብሔር አምላካዊ ባህርይ ጋር በገነት አብሮ መኖር ስለማይችል አዳም ከቅዱሱ ከእግዚአብሔር ፊት ተባረረ። የመጀመሪያው አዳም ሕይወት የተጠናቀቀው በዚህ የእውነት ፍርድ ነው።
የመጀመሪያው አዳም ከተጠናቀቀበት ፍርድ ነጻ ለመውጣት ዋጋ ከፍሎ ወደ አዳነው ወደ ሁለተኛው አዳም እንምጣ!
ሁለተኛው አዳም የመጀመሪያው አዳምንና ልጆቹን ለማዳን ከኃጢአት የነጻ፣ ለእግዚአብሔር አልታዘዝም ከሚል ዐመጽ የተለየ ንጹህ ነበር። ለዚህም የማዳን ሥራ ራሱ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ መጣ። “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።”
— ዮሐንስ 1፥14
እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ ሆኖ ሳለ በቃሉ ብቻ አዳምን ወደገነት መመለስ እየቻለ ለምን ሰው መሆን አስፈለገው? ብለን ስንጠይቅ መልሳችን እግዚአብሔር በጽድቅ ፈራጅ፣ በእውነትም ፍትህ ሰጪ ስለሆነ ነው የሚል ይሆናል። ዳዊት በመዝሙሩ እንዳለው።
“እርሱም ዓለምን በጽድቅ ይፈርዳታል፥ አሕዛብንም በቅንነት ይዳኛቸዋል።”
— መዝሙር 9፥8
ለኃጢአት ዋጋ ፍርድ ሳይሰጥ ጽድቅ የለም። ከእግዚአብሔርም ጋር እርቅ አይኖርም። የስርየት መስዋእቱም ደም ነበር። ለዚህ ነበር እግዚአብሔር ራሱ ሰው የሆነውና ስለአዳም ኃጢአት የደም መስዋእት የከፈለው።
ፊልጵስዩስ 2፣6-8
"እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ፥ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፥ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ።"
አዳም ለኃጢአት ሲታዘዝ ተባረረ። ኢየሱስ ለጽድቅ ሲታዘዝ ሕይወት ሆነልን።
እስከዚህ ድረስ መግቢያ ይሆነን ዘንድ ስለወደቀው የመጀመሪያው አዳምና የዘላለም ሕይወት ስለሆነው ስለሁለተኛው አዳም፣ ኢየሱስ ቤዛነት ይሄንን ያህል ካልን ስለእነዘነበ ግርማ፣ በላይ ሸፈራውና አማን ሻሎም የክርክር ጉዳይ እንግባ።
ነብይ ዘነበ ግርማ ስለድነት በተናገረበት አንቀጽ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ በነጻ የተሰጠንን ዋጋ መጠበቅ አለብን፣ ከኃጢአት ካልጠበቅነው የዘላለም ሞት ያገኘናል፣ የተሰጠንን ድነት ልናጣ እንችላለን የሚል ይዘት የነበረው አስተምህሮ አቅርቦ ነበር። በላይ ሽፈራውና አማን ሻሎም የተባሉት ሰዎች ደግሞ በተቃውሞ የሰጡት መልስ የተሰጠንን ድነት እኛ መጠበቅ አይጠበቅብንም። አንዴ ድነናል፣ ይሄንን ድነት የትኛውም ኃጢአት አያጠፋብንም፣ የሚጠፋ ከሆነ ለዘላለም አልዳንም ማለት ነው ሲሉ የሚያግዛቸውን ጥቅስ በማቅረብ እውነቱ በነሱ ዘንድ ብቻ እንዳለ ለማስረዳት ታግለዋል።
እዚህ ላይ እኛ ጥያቄ እናንሳ! ከላይ በመግቢያችን ለማብራራት የሞከርነው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እዚህ ላይ ይነሳል። የመጀመሪያው ሰው፣ አዳም ገነት የገባው ለጊዜው ነበር እንዴ? አይደለም! እግዚአብሔር ሰውኛ ድራማ ስለማይጫወት አዳም የተፈጠረው ከእርሱ ጋር ለዘላለም እንዲኖር እንጂ አዳም የበለሲቱን ፍሬ እስኪበላ ድረስ ለጊዜያዊ ማቆያነት አልነበረም። አዳም የተፈጠረበትን ዘላለማዊ ሕይወት የተሰጠውንና ከእግዚአብሔር ጋር ከመኖር ይልቅ የጠላቱን ድምፅ ሰምቶ ሞትን በራሱ ላይ ስላመጣ እግዚአብሔር ጻድቅ ሆኖ ሳለ ዐመጸኛ እንዴት ከእርሱ ጋር ኅብረት ሊያደርግ ስለማይችል በፍርድ ቀንበር ስር ወደቀ። ዐመጸኛ ከእግዚአብሔር ፍርድ ሊያመልጥ አይችልም። የመጀመሪያው አዳም እምቢተኛ ሲሆን ሁለተኛው አዳም የመጣው ደግሞ የአባቱን ትዕዛዝ ለመፈጸም ነው።
“ፈቃዴን ለማድረግ አይደለም እንጂ የላከኝን ፈቃድ ለማድረግ ከሰማይ ወርጃለሁና።”
— ዮሐንስ 6፥38
በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ የዘላለም ሕይወት በማመን ያገኘ ሰው፣ ዐመጸኛ ሆኖ የዲያብሎስን ድምፅ ቢሰማ ሊሆን ይችላል? አትጠራጠር፣ የዘላለም ሞት ይፈረድበታል! ኢየሱስ ሞት ዋጋ ያለው በሁለት መንገድ ነው። አንደኛው ዋጋ ኢየሱስ የተወደደ የእግዚአብሔር መስዋእት ሆኖ ከአዳም ኃጢአት መዳንህን ባመንክበት ቅጽበት ስርየት ሆኖልህ የእግዚአብሔር ልጅ ትሆናለህ።
“አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና።”
— ሮሜ 8፥15
ልጅ በቅዱሱ በአባቱ ፊት ምን መሆን ይጠበቅበታል? ይሄ ሁለተኛው የኢየሱስ የሞት ዋጋ በእግዚአብሔር ፊት ልጆቹ ሆነን የምንመላለስበት ጉልበታችን ነው። ጸጋ ይባላል።
“ነገር ግን እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን።” ኤፌሶን 4፥7
ይህ ጸጋ በእምነት የዳንነውና የእግዚአብሔር ልጆች የሆንነው እኛን ምን ያደርግልናል?
“ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤”
— ቲቶ 2፥12-13
በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ አምኖ የዳነ ሰው በጽድቅ መኖር ግዴታው ነው። የተሰጠው ድነት በነጻ ነው ማለት ዋጋ አልተከፈለበትም ማለት አይደለም።
“በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።”
— ማቴዎስ 7፥21
አዎ፣ በሥራችን አልዳንም። ይህ ማለት ግን ሥራ የለብንም ማለት አይደለም።
በላይ ሽፈራውና አማን ሻሎም ይሄንን ቃል አይወዱትም። በእምነት አገኘነው ያሉትን ድነት ለሥጋ ፈቃዳቸው የሚከለክል ቃል ስለሆነ አይጠቅሱትም። አንዴ የተሰጠን ድነት በእኛ ስራ አይጠበቅም ይላሉ። ባንሰራም ያገኘነው ድነት አይጠፋብንም ብለው ይጮሃሉ። የሚጠፋ ከሆነ ቀድሞውኑ አልተሰጠንም ነበር እያሉ ስጦታቸውን ለፈለጉት የዐመጽ ተግባር እንደማስረጃ እንዲቆጠርላቸው ይታገላሉ። የተሰጠህን ነጻ ውድ ስጦታ ካልጠበከው ስጦታው ቀድሞውኑ አልነበረም ማለት ነው እንዴ?
ስጦታው የማይጠፋ ነው። የማይጠፋው የሰማይ ስጦታ ስለሆነ ነው። ነገር ግን የሰው ልጅ አጥፊ ልምምድ ስላለው ሊያጠፋው ይችላል። ምሳሌው የገነቱን አዳም አስብ።
“እንደዚሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው።” ያዕቆብ 2፥17 ዐመፀኞች ለተሰጣቸው ድነት ሥራ ስለሌላቸው ዐመጽነታቸውን የሚደግፍ ጥቅስ ይደረድራሉ። አዳም በሄዋን፣ ሄዋንም በእባብ እባብም በዐመጽ ምክንታቸው ስር ቢደበቁም ከፍርድ አላመለጡም።
የዚህ ዘመን ወንጌላውያን የተባሉት አብዛኛዎቹ መንፈሳዊ መረዳት የላቸውም። ብዙ አንብበው፣ ብዙ የቲዎሎጂ ትምህርት ቢኖራቸውም ብዙ አነበቡ እንጂ ከመንፈሳዊ እውቀት የተለዩ ዝናብ የሌለባቸው ዳመናዎች ናቸው። ዳዊት ፋሲል የሚባልም ግብዝ ሰው በተሳልቆና እውቀት በሚመስል የፌዝ ንግግር የገነት በር ቁልፍ በእጄ ነውና፣ በኔ በኩል ግቡ በሚመስል መልኩ ብዙ ያወራል።
አማን ሻሎም የተባለው ሌላኛው ግብዝ ሰው ራሱን ብዙ ባነበበው መጽሐፎች ውስጥ ደብቆ አዋቂ መስሎ ለመታየት ብዙ ጊዜውን ይጨርሳል። ይጋጋጣል። የተከራካሪዎቹን አፍ ዝም ስላሰኘ በእውቀት የበለጣቸው ይመስለዋል። ከነዚህ ደካማ እውቀቶቹ መካከል አንዱ ኢየሱስ የሞተው ለኛ ለጥቂቶች ነው የሚለውን የጆን ካልቪንን Limited Atonement ወይም Particular Redemption መዳን የሆነው ለተወሰኑት ብቻ ወይም የተመረጡ ብቻ ነው የሚል አስተምህሮ አስፋፊ ነው። ይህ ትምህርት የመጨረሻው የክህደት ጫፍ ነው። እግዚአብሔርን ጨካኝ፣ ፈራጅ አድርጎ የሚከስ ነው። እግዚአብሔር ኢየሱስን የላከው የተወሰኑ ሰዎች ብቻ ለማዳን ከሆነ ከመዳን ውጪ ያሉት ሰዎች ለሲኦል ማገዶነት እግዚአብሔር ያዘጋጃቸው ናቸው ማለቱ ነው። እንዳይድኑ ተደርገው የተፈጠሩ ሰዎችን እግዚአብሔር በእሳት እያቃጠለ ለመደሰት ያዘጋጃቸው ናቸው ማለት እግዚአብሔር ፍቅር አይደለም ማለቱ ነው።። እነዚህ ሰዎች ከዘላለም እሳት ውጪ ለመዳን ምርጫም፣ እድልም የሌላቸው ናቸው ማለት ነው። ይህ ትምህርት ደግሞ ይሄንን የእግዚአብሔር ቃል በቀጥታ ይቃወማል።
“በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።”
— ዮሐንስ 3፥16
እግዚአብሔር አብ አንድያ ልጁን ወደዓለም የላከው የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ለማዳን ብቻ ነው የሚለው አማን ሻሎም Mouthpiece of Satan የሰይጣን አፍ አገልጋይ ነው።
በዚህ ቃል ውስጥ ጥቂቶች፣ የተመረጡ፣ የተወሰኑ፣ የተለዩ...የሚል ቃል ይታያችኋል?
“ሁሉ በእርሱ በኩል እንዲያምኑ ይህ ስለ ብርሃን ይመሰክር ዘንድ ለምስክር መጣ።”
— ዮሐንስ 1፥7
"ሁሉ" ማለት በግሪክኛ πάντες ፓንቴስ ማለት ሁሉ፣ all, everyone እያንዳንዱ ማለት እንጂ የተወሰኑ፣ የተለዩ ማለት አይደለም። በላይ ሽፈራው አግብቶ የፈታ፣ ዳግመኛ ያገባና ሌላም፣ ሌላም የሚወራበት፣ በሪል ስቴት ገንዘብ ብዙዎች ያለቀሱበት፣ አማን ሻሎም በሱስ የተጠመደ፣ ቀለበት አስሮ የከዳ፣ ሌላም፣ ሌላም ሆነው ሳለ በእግዚአብሔር ፊት በጽድቅ መመላለስ ሲያቅታቸውና ለምኞታቸው ልጓም ማስገባት ሲሳናቸው፣ ለኃጢአታቸው አርነት የሚሰጥ ጥቅስ በማቅረብ የስህተት ደጋፊዎቻቸውን ለማሰባሰብ ይሯሯጣሉ።
ማጠቃለያ፣
የዳንነው በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ በነጻ ነው። በነጻ የተሰጠን ሕይወት ዋጋ ተከፍሎበታል። የከፈለልንን ስለምንወደው ትእዛዛቱን እንጠብቃለን። ትእዛዛቱን የምንጠብቀው ስለምንወደው እንጂ ለመዳን አይደለም።
“ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል፤”
— ዮሐንስ 14፥15-16
ያ አጽናኝ ከኃጢአት ይጠብቀናል። ተሳስተን ኃጢአት ብናደርግ ስንኳን የንስሐ እድል አለን።
“በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው።”
— 1ኛ ዮሐንስ 1፥9
ድነናል፣ ድነታችንን እንጠብቃለን። እንደዴማስ ኢየሱስን ትተን ለዓለም ኃጢአት ባሪያ አንሆንም።
Tuesday, April 22, 2025
“እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” ቆላስ 1፥13-14
"ለእኔ ኃጢአት ሥርየት ከሞተልኝ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ ቤዛ የለኝም" “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።”
— ቆላስይስ 1፥13-14
ቤዛ የሚለውን ቃል አባ ገብርኤል የተባሉ ሊቀጳጳስ ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ብለው ለምን ተናገሩ? የሚል ንትርክ ተነስቶ በኦርቶዶክሶች መንደር ጩኸቱ በርክቷል። ይሄ ቤዛ በእንግሊዝኛው/ransom,redemption,deliverer/ በማለት ሲተረጉመው ግሪኩ ደግሞ (λύτρον)ሉትሮን ማለት የተከፈለ ዋጋ፣ (λύτρωσις) ሉትሮሲስ ነፃ መውጣት፣ ከእስራት፣ ከባርነት ለመፈታት የተሰጠ ክፍያ፣ ነጻነት ማለት ነው። የጌታችን፣ የመድኃኒታችንና የአምላካችን ቤዛነት ከየትኛው ምትክነት፣ ነጻ አውጪነት፣ አዳኝነትና ከሞት ታዳጊነት ጋር ለንጽጽር የሚቀርብ አይደለም። በዘመነ ኦሪት በባርነት የተሸጠ ሰው ለባርነቱ ዋጋ የሚከፍል ከተገኘ ነጻ ሊወጣ ይችላል። ለሰው ነፍስ ቤዛው ሀብቱ ነው። ምሳሌ13፣8 የመሳሰሉ ስለቤዛ የተነገሩ የቤዛ ቃል ንግግሮች በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ ተፅፈው እናገኛለን። እነዚህ ሁሉ የቤዛነት ትርጉሞች ኢየሱስ ክርስቶስ ካደረገልን ቤዛነት ጋር ለክርክርም፣ ለንጽጽርም፣ ለትርጉም አቻነት የሚቀርቡ አይደለም። የኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ከዘላለማዊ ድኅነት፣ ከአብ ጋር እርቅ የተደረገበት፣ መርገመ አዳም የተወገደበት፣ የገነት በር የተከፈበት ስለሆነ ከሰማይ በታች የተነገሩ፣ የተጻፉ፣ የተወሩ ስለቤዛ የተተረጎሙ ቃላት፣ ሃሳቦች ለንጽጽር ሊቀርቡ አይችሉም።
በእውቀት ለመገራትና ለመመራት እምቢተኛ አእዱገ ገዳም የሆኑ የኦርቶዶክሶች ምእመናን፣ በተረት ተረት ትምህርት ሊቅ የሆኑት ዘበነ ለማ፣ አዋቂ መስሎ ለመታየት ብዙ የሚደክመው ኄኖክ ኃይሌ፣ ክንድ ከስንዘር መስቀል ጨብጠውና አንጠልጥለው ብዙ የሚያጓሩ፣ የተለሰኑ መቃብር መምህራን፣ ቀሳውስትና መነኮሳት ነን ባዮች የጌታችን፣ የመድኃኒታችንና የአምላካችንን ቤዛነትን ከሌሎች ቤዛነት ጋር ለማነጻጸር ወይም ስለቤዛነት የተነገረው ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ አይደለም ለማለት ከሰሜን ዋልታ እስከ አንታርክቲካ ሮጠው ያልቆፈሩት ጥቅስ፣ ያልዘበዘቡት ፅሑፍ፣ ያልተረተሩት ትርጉም፣ በእልህና ብስጭት መንጋጋቸው በመንጋ ያላፋጩት ጥርስ የለም። በየፌስቡኩ፣ ቲክቶኩና በየድረገጾቹ ላይ የታየው ጩኸት ተአምር የሚያስብል ነው። እነዚህ ስብስቦች ከኛ ወዲያ እውቀት ላሳር ነው ብለው የአእምሮአቸውን በር የዘጉት ድሮ ነው። ከእነዚህ ሰዎች ጋር ተነጋግሮ መተማመን ላይ መድረስ አይቻልም። አንዳንዴማ ከእኛ በስተቀር የሚጸድቅ የለም ብለው በድፍረት ሲናገሩ መንግሥተ ሰማያት በር ላይ ቆመው አንተ ተመለስ፣ አንተ ግባ ብለው የማዘዝ ስልጣን ያላቸው ያህል ያስባሉ። መንግሥተ ሰማያት የፍትሐት ድግስ የሚበሉበት የደጀሰላም በር ይመስላቸዋል። ለነገሩ አይሁድ ፈሪሳውያን መምህራንና ጻፎችም እንደዚሁ ያደርጋቸው ነበር።
እነዚህን መሰል ሰዎች ጌታ በአንድ ወቅት እንዲህ ሲላቸው እናገኛለን። (ማቴ23፣27-32) እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ፥ ወዮላችሁ።
እንዲሁ እናንተ ደግሞ በውጭ ለሰው እንደ ጻድቃን ትታያላችሁ፥ በውስጣችሁ ግን ግብዝነትና ዓመፀኝነት ሞልቶባችኋል። ብሏቸው ነበር። እነዚህኞቹ ወደመንግሥተ ሰማይ ወይ እነሱ አይገቡ፣ ወይ ተከታዮቻቸውን አያስገቡ መንገዱን በተረትና እንቆቅልሽ ስብከት ዘግተውታል። በዚያ ላይ እውቀት አለርጂክ የሆነበት ተከታያቸው ምዕመን በጩኸት ስለሚያጅባቸውና አዋቂ ነን ብለው ስለደመደሙ ከእነሱ የተለየውን ቃል እውነት ቢሆን እንኳን አይቀበሉም። ምእመኖቻቸውም ከመምህራኖቻቸው የባሱ ስለሆኑ ያንኑ የአለቆቻቸውን ትምህርት መልሰው ይጓራሉ። ይጮሃሉ። ማርያም ቤዛ ናት፣ ገብርኤል ቤዛ ነው። ገንዘብ ቤዛ ነው። ወንድምህ ቤዛ ነው፣ ጓደኛህ ቤዛ ነው የሚሉ ቃላትን ለቃቅመው በማምጣት ከኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ጋር ለንጽጽር፣ ለትርጉምና ለማብራሪያ በማቅረብ ይንጫጫሉ። አንዳንዴ ስትመለከታቸው ክርስቲያን የሚለውን መጠሪያ አምኖ ለመቀበል እስኪከብድህ ድረስ አንደበታቸውና ጽሑፋቸው ልቅ ነው። እነዚህ ተጯጯኺዎች በዘመቻ የተነሱት የቤተክርስቲያኒቱ ጳጳስ አባ ገብርኤል የተባሉት ሰው "ተቀዳሚ፣ ተከታይ የሌለው፣ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻውን የዘላለም ቤዛ ነው" ብለው ስላስተማሩና ማርያምም የዘላለም ቤዛችን አይደለችም ስላሉ ነበር። የዚህን ትምህርት ቃል ለማፍረስና ሌሎችም ቤዛ አሉን ለማለት ያልቆፈሩት የሙግት ትርጉምና ጥቅስ የለም። ዘቤ የተረት አባት በአንድ ወቅት "ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም" ብሎ ሲያስተምር ነበር። ማርያም ማዳን ከቻለች የኢየሱስ ሰው ሆኖ መምጣት ሳያስፈልግ በማርያም ይፈጸም አልነበረም ወይ? ተብሎ ሲጠየቅ እነዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ያለማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም ማለት ስህተት ነው ብለው ለማረም ቢሞክሩም ዘቤ የተረት አባት ስህተቱን ሳያምን ዛሬም በተመሳሳይ ስህተት ላይ ይገኛል። ዘበነ ለማን ያክል ቤተክርስቲያኒቱን በአስተምህሮ ስህተት የገደለ ማንም የለም። እነኄኖክ ኃይሌ ላይገባቸው የማሉ ያህል የሚከራከሩት ስለቤዛነት የተሰጠው ትርጉም ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ሳይሆን ማርያምን ይጨምራል፣ ሌሎችን ብዙዎችንም በተጨማሪነት ያጠቃልላል ብለው ለመከራከር ሲንደፋደፉ አይተናል።
እዚህ ላይ አስረግጠን የሊቀጳጳሱን ትምህርት የተቀበልነውና ስለኢየሱስ ክርስቶስ ብቸኛ አዳኝነትና ቤዛነት ያስተማሩት ትክክል ነው ያልነው ጳጳሱን በተለየ ስለወደድን ሳይሆን ያስተማሩት እውነት ስለሆነ ነው።
ለእውቀት አእዱገ ገዳም ለሆኑት ሰዎች የምንነግራቸው ነገር ስለቤዛ የተጻፈና የተነገረ አንድ መቶ ሺህ ጥቅስና ትርጉም ቢኖራችሁ ለንጽጽር የማይቀርብበት የኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ብቸኛው ነው። የወደቀውን የሰው ልጅ ወደቀደመ ክብሩ ለመመለስ፣ ለበደለው ኃጢአት የተሰጠ ሥርየት፣ የተከፈለ የሞት ዋጋ ምትክ የሆነው ቤዛነት የኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ይሄንን የሚተካ፣ የሚያክል፣ የሚወዳደር፣ የሚቤዥ ሌላ ቤዛ ከሰማይ በታች የለም። ይሄ ቤዛነት ትልቅነቱ ዘላለማዊ፣ መድኃኒትነቱ ሕያው፣ አዳኝነቱ ሞት ያላሸነፈው ነው። ስለቤዛ በትርጉምም፣ በፍቺም በንፅፅርም ከኢየሱስ ቤዛነት ጋር ሊቀርብ የሚችል ሌላ የለም። ስለቤዛ የተነገረ ሌላ ቃል አለ ብለህ ጭንቁር የቃል ክርክር ታቀርብ ይሆናል። ያንን እያነሳህ እንደዚህ ማለት ነው፣ እንደዚያ ማለት ነው እያልክ ውሃ ወቀጣ ክርክር የማንሳት መብት ይኖርሃል። የጻፎችና የፈሪሳውያን ክርክር የወንጌል እውነት ሊቀይረው እንደማይችለው ሁሉ የትኛውም ስለቤዛ የሚሰጥ፣ የተሰጠ ትርጉምና ንጽጽር ጌታችን ካደረግልን ቤዛነት ጋር አይነጻጸርም፣ ለትርጉም ክርክር ሊቀርብ አይችልም። ለነዚህ የተለሰኑ መቃብሮች የምነግራቸው በኔ በኃጢአተኛው ምትክ ቤዛ ሆኖ የሞተ ከኢየሱስ ክርስቶስ በስተቀር ሌላ ቤዛ ማንም የለም ነው የምንላቸው። ቅድስት ማርያም ቤዛ ናት የሚሉ ሰዎችን ታድናለች ወይ? ተብለው ሲጠየቁ አታድንም፣ ግን መድኃኒትን ወልዳልናለች፣ ስለዚህ ቤዛ እንላታለን ይሉናል። በምትክነትና ለኃጢአት ሥርየት እንዳልሞተችልን ከታወቀ በመጽሐፍ እንደተፃፈ "የጌታ እናት" ማለታችን በቂ አይደለም ወይ፣ ባልተፃፈ የቤዛነቷ ትርጉም ላይ ጉንጭ አልፋ ክርክር ለምን ያስፈልጋል? ሲባሉ ጴንጤ፣ ከሀዲ፣ ጸረ ማርያም የሚሉ ስድቦቻቸውን በእውቶማቲክ ይተኩሳሉ። እነዚህ ለእውቀት አእዱገ ገዳም የሆኑ ሊቀ ሊቃውንትና መተርጉመ መጻሕፍት ነን ባዮች በማርያምም፣ በኢየሱስም ሁለት አዳኝ እንዳላቸው ለጎጋ ምዕመኖቻቸው ያለከልካይ እየጮሁ መገኘታቸው ስናይ በነሱ ዘንድ ኢየሱስ ሌላ ብዙ ቤዛ እንዳላቸው እንረዳለን። አሁንም ደግመን እንላለን፣ ለአዳም ልጆች ቤዛ ሆኖ የሞተና ያዳነን ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ ቤዛ የለንም። ስለቤዛ ሚሊየን ትርጉም ቢኖርህ እሱን እያመነዠክ መኖርህ የኢየሱስን ብቸኛ ቤዛነት አይቀይረውም። የኢየሱስን ቤዛነት አምናለሁ ያለ ሰው በኢየሱስ ብቸኛ የቤዛነት ሥራ ላይ ሌላ ትርጉምና ንጽጽር ለምን ይዞ ሊመጣ አይችልም። የሚመስለው፣ የሚተካከለው፣ የዘላለም የሆነ ቤዛነት ከኢየሱስ ውጪ አለ? የለም!!! አዎ! እናውቃለን፣ የኢየሱስን ዘላለማዊ የቤዛነቱን ሥራ በፍጡራንና በምድራዊያን የትርጉም ቃላት ሸፍኖ ለማሳነስና ሰው ሁሉ ወደአንድያ ቤዛው ዓይኑን እንዳያነሳ ለመጋረድ ጠላት በስንዴው መካከል የዘራው እንክርዳድ ነው። እኛ ግን በየትኛውም የቤዛ ትርጉም ሳንወጣ፣ ሳንወርድ፣ ሳንደክም "እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” እንላለን። ቆላስይስ 1፥13-14
ሊቀጳጳሱ ስለኢየሱስ ብቸኛና ዘላለማዊ ቤዛነት የተናገሩት ትክክል ነው። ከፍጡራን መካከል ሌላ የዘላለም ቤዛ የሆነልን፣ መሆን የሚችልም የለም። ከሰማይ በታች ቤዛ መሆን የሚችል ስለሌለ ነው አብ አንድያ ልጁን የላከልን። ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
Subscribe to:
Posts (Atom)