Thursday, March 7, 2013

ግብጽ በአንበጣ መንጋ ተመታች!




በዘመነ ፈርዖን ግብጽን ከመቷት መቅሰፍቶች አንዱ የአንበጣ መንጋ ነበር። የአሁኑ የአንበጣ መንጋ በምን መቅሰፍትነት እንደተላከ ባናውቅም መንጋው ግን በግብጽ ምድር በዓባይ ውሃ የበቀለውን ብዙ ጋሻ መሬት አትክልትና ሰብል ጋጥ አድርጎታል። በየከተማው ውስጥ የተረፈረፈውን የአንበጣ መንጋ ሰብስቦ በማቃጠል ቅርናቱ አያድርስ ሆኗል።
 የግብጽ ፖለቲካ እየተናጠና ሥልጣኑ የእስልምናውን ጽንፍ በሚያራምዱ ክፍሎች የመውደቁ ነገር ተጋግሞ ረብሻና ሁከት ባስከተለው መዘዝ ዓመታዊ የቱሪስት ገቢዋ መጠን ከ12 ቢሊዮን ብር ወደ 4 ቢሊዮን ገደማ የመውረዱ ችግር ሳይለቃት ሰሞኑን አዝመራዋን እምሽክ ያደረገ በአንበጣ መንጋ መቷታል።

 ከታሪክ እንደምንማረው ግብጾች ኢትዮጵያን እንደስትራቴጂክ ጠላት ማየታቸው ያልተጠቀምንበት ዓባይ ወንዛችን ያመጣብን መዘዝ እንጂ በድንበር ይሁን በጉርብትና የምንዛመዳቸው ሆነን አይደለም። ለኢትዮጵያ የሚደግሱት ስውር  የሁከትና የብጥብጥ እጃቸው ሳይሰበሰብ ምንም ሳንነካቸው እዳቸውን እየከፈሉ መገኘታቸው ያስገርማል። ምንም እንኳን የማንንም ጥፋትና ውድቀት ባንመኝም፤ ሳንደርስባቸው እየደረሱብን በሚመጣባቸው መርገም እኛ ተጠያቂዎች አይደለንም።  
ይህ ግብጽን እየበላና እየበረረ በማቋረጥ ላይ ያለው የሰማይ ላይ ነፍሳት መንጋ ወደእስራኤልም እንዳይዛመት የእስራኤል መንግሥት በድንበሮቹ ዙሪያ የተባይ ማጥፊያ መርዝ እየረጨ ይገኛል። 

ግብጾችም ሳያስቡት የደረሰባቸውን ውርጅብኝ ለመከላከል እየታገሉ ይገኛሉ። አንዳንድ ሚዲያዎች በዓለም ክርስቲያኖች ዘንድ የሚታወቀው «የጌታ ጾም» የተባለው በደረሰበት ሰዓት ይህ መቅሰፍት በግብጽ ላይ መምጣቱ ለምን ይሆን? ሲሉ ይጠይቃሉ።  በእርግጥ እንደመጽሐፉ ቃል የምጥ ጣር የመጀመሪያ ምልክቶች አንዱ ይሆን? የሁላችንም ጥያቄ ነው።

«ጉዞው»


መንፈሳዊ ልቦለድ

የሀገርህን እወቅ ጉዞ ደስ ይለኛል። ባለኝ ትርፍ ጊዜ ወይም ዓመታዊ የሥራ ፈቃድ ያላየኋቸውን ታሪካዊም ይሁን ከባቢያዊ መልክዓ ምድሮች፤ የኅብረተሰብ አኗኗርና ባህል መጎብኘት በጣም ስለሚያስደስተኝ እነሆ ተሰናዳሁ። አዲስ አበባ አምስት ኪሎ ባለችው ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን መግቢያ በር አካባቢ በተለጠፈ አንድ ማስታወቂያ ላይ ባገኘሁት አድራሻ መሠረት በዓመታዊው የመርጦ ለማርያም የንግሥ በዓል ላይ ለመታደም ከተጓዦች ጋር እነሆ ታድሜአለሁ።
 
አውቶቡሱ በተቀጠረለት ቦታና ሰዓት ቆሟል። እኔም ሰዓቱን አክብሬ ከቦታው ተገኝቻለሁ። ተጓዦችም ተሰብስበዋል። ግማሹ ሀገሩን ለቆ የሚሄድ እስኪመስል ድረስ የሚያመላልሰው ጓዝ የት የለሌ ነው። ጧፉ፤ ሻማው፤ጥላው ይጫናል። ግማሹ ለስለት፤ ግማሹም ለሽያጭ ነው። ነጋዴው የሚሸቅጠውን እቃ ይጭናል፤ ያስጭናል። ከየአድባራቱ በተንሸዋረረ ጨረታ የሚገዙ ነጋዴዎች በዓላትን እየቆጠሩ ይሸቅጣሉ። የሥራ ፈጠራ ይሁን በተፈጠረው ሥራ የማትረፍ ክህሎት፤ ገንዘብ ለዋጩና ሻማ ሻጩ ብዙ ነው። ግርግሩ ለብቻው ነው። ዓለማየሁ፤ ዓለሚቱ፤ መንግሥቱ.........ከዚህም፤ ከዚያም የሰዉ ስም ይጠራል።  «ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ» የሚል መዝሙር በትልቁ የከፈተ አንድ ተጓዥም ሲንቅ ሲጭን አይቻለሁ። ጆሮው ላይ ማዳመጫውን የወተፈና በመዝሙር ምርቃና ውስጥ የሰጠመ ሌላው ተጓዥም ምናልባት መንግሥቱ፤ ሀብታሙ....... እየተባለ ሲጠራ ያልሰማው በምናቡ መንግሥተ ሰማይ የገባ መስሎት ይሆናል። ቢሆንስ? ማን ያውቃል።

የንጋት ብርድ አጥንት ሰርስሮ ስለሚገባ የለብስኩትን ጋቢ እጥፋት ዘርግቼ ወደአንድ ጥግ ቆምኩኝ። ከእጄ የቪዲዮ ካሜራ በስተቀር የያዝኩት ምንም ጓዝ ስለሌለ ራሴን ከዚህ ግርግር የሰወርኩ እድለኛ አድርጌ ቆጠርኩት።  ሲፈጥረኝ ግርግር አልወድም። በሰርግና በበዓላት ድግስ ላይ ሰዎች ሲዋከቡ ሳይ ይገርመኛል። ግርግሩ ካለፈ ወደነበረ ማንነት መመለስ ስላለ ያንን መዘንጋት መስሎ ስለሚሰማኝ ምንም አይመስለኝም።  ትንሹን ነገር አዋክበው የተዋጣለት ግርግር መፍጠር የሚችሉ ሰዎችን ሳይ ይገርመኛል። መርጦ ለማርያም ለዓመታዊ ክብረ በዓል ለመሄድ መንፈሳዊነቱ ማድላት ሲገባው ይሄ ሁሉ ግርግርና አታሞ ይገርማል።