Thursday, February 7, 2013

ጥቃቅን ሹመኞችና የገደል ቅራፊ ሚያካክሉ መዘዞቻቸው

በዳዊት ወርቁ

pomjos@yahoo.com


ቱኒዚያዊው የሃያ ስድስት ዓመቱ ወጣት ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ ጋሪ እየገፋ ፍራፍሬና አትክልት በመሸጥ ኑሮውን የሚገፋ የጎዳና ላይ ለፍቶ አዳሪ  ነበር፡፡  በሚያገኛት ጥቂት ፈረንካም የራሱንና የስምንት ቤተሰቡን ነፍስ ይቀልብ ነበር፡፡  ፋይዳ ሃምዲ የተባለች ፖሊስ፣ ዘጠኝ ራሱን መደጎሚያ ጋሪውንና ፍራፍሬውን በግፍ እስክትነጥቀው ድረስም፣ ለሰባት ዓመታት ያህል በደቡብ ቱኒዚያ 300 ኪሎሜትር ያህል ከምትርቀውና ሲዲ ቡዚድ ከምትባለው የትውልድ ስፍራው እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጥሮ፣ ማስኗል፣ ተንከራቷል፣ በእሰራለሁ አትሰራም እንካ ሰላንቲያም ከጥቃቅን ሹመኞችጋ እሰጥ አገባ ገብቷል፡፡ በመጨረሻም ውድ ህይወቱን ከፍሏል፡፡

እንዲህ አይነት ተደጋጋሚ ሁኔታ ብዙ ጊዜያት አጋጥሞት የነበረው ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ በቀን ያገኝ የነበረውን 10 ዲናር፣ (በኢትዮጵያ 126 ብር ያህል) ንብረቱን ትመልስለት ዘንድ እንደ እጅ መንሻ አድርጎ የዕለት ጉርሱን ለነጠቀችበት ፖሊስ ፋይዳ ሃምዲ አቅርቦ ነበር፡፡ ነገር ግን፣  የፋይዳ ሃምዲ ምላሽ በህይወት የሌሉትን አባቱን መስደብና የሙሐመድ ቡዓዚዝን ጉንጭ በጥፊ ማጮል ነበረ፡፡ በድርጊቱ ከፍተኛ ውረድት የደረሰበት ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ የደረሰበትን በደል አቤት ለማለት ወደ በላይ አካላት ቢያቀናም፣ የበላይ አካላት ተብዬዎቹ ከእጅ አይሻል ዶማ በመሆናቸው አቤቱታው የውሃ ሽታ ሆነ፡፡

ዘጠኝ ራሱን የሚያኖርበትን ጋሪና አትክልት በግፍ ከተነጠቀ አንድ ሰዓት በኋላም፣ ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ ምን ሊያደርግ እንዳሰበ ለቤተሰቦቹ እንኳ ትንፍሽ ሳይል፣ ልክ ከቀኑ 530 ሲሆን ንብረቱን ወደ ተነጠቀበት አደባባይ በማምራት በገዛ ሰውነቱ ላይ ቤንዝን ካርከፈከፈ በኋላ፣ ከአስተዳደሩ ያጣውን ፍትህ የገዛ ነፍሱን በማጣት ‹‹አግኝቷል››

ለሰላማዊው ለፍቶ አዳሪ ሙሐመድ ቡዓዚዝ ሰላማዊ ጥያቄ፣ ፖሊስ የሰጠው ኢ-ምግባራዊ ምላሽና የባለሥልጣናት ቸልተኝነት ያስከተለው ውጤትም፣ ጅማሬውን በሲኢዲ ቡዚድ ያደረገና በኋላም ቀስበቀስ መላውን ቱኒዚያና ከፊል የዓረብ አገራትን ያካለለ ሕዝባዊ አመጽ ነበር፡፡ አመጹ ሥር ሰዶም፣ በተለይም ፌስቡክና ዩቲዩብን በመሳሰሉ ድረገጾች የሱቅ መስኮቶችን በሰባበሩና መኪኖችን ባወደሙ ወጣቶች ላይ ፖሊስ የወሰደውን ኢሰብአዊ ርምጃዎች የሚያሳዩ ምስሎች እንደሰደድ እሳት ተስፋፉ፡፡


የማታ ማታም፣ የሙሐመድ ቡዓዚዝን ነፍስ ለማዳን  በዋና ከተማዋ ቱኒዝ አቅራቢያ በሚገኝ ሆስፒታል ርብርብ ቢደረግም፣ ክፉኛ በመጎዳቱ፣ ታሪቅ ጣይብ ሙሐመድ ቡዓዚዝ ጃንዋሪ 4 2010 (ታህሳስ 26፣ 2002 ዓ.ም.) በተወለደ 26 ዓመቱ፣ እስከመጨረሻው አንቀላፍቷል፡፡

ከህልፈቱ በኋላም የዓረቡ ዓለም ታሪክ ይለወጥ ዘንድ ታላቅ ድርሻ ላበረከቱ ሌሎች አራት ሰዎችን ጨምሮ፣ የሻክሃሮቭን ሽልማት ተሸልሟል፡፡ የቱኒዚያ መንግሥትም ምስሉን በአገሪቱ ቴምብር ላይ በማስፈር ክብር ሲያጎናጽፈው የእንግሊዙ ታይም መጽሔት 2011 የዓመቱ ምርጥ ሰው ብሎታል፡፡

ከጥቃቅን ሹመኞች ዕይታ ውስጥ ያልገባውም የሙሐመድ ቡዓዚዝ ጉዳይም፣ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ዚን ኢል አቢድን ቤን አሊ በትረ መንግሥታቸውን እስከማጣት ድረስ የከበደ፣ ትልቅ ዋጋ እንዲከፍሉ አድርጓቸዋል፡፡

ዛሬ ለማነሳው ነጥብ ይመቸኝ ዘንድ እንደ አብነት የሙሐመድ ቡዓዚዝን ቅንጭብ ታሪክ አነሳሁ እንጂ፣ በዓለማችን፣ በተለይም በአህጉራችን አፍሪቃ፣ ደግሞም በእኛ ኢትዮጵያ በየዘመናቱ የሚፈጠሩትን፣ ሙሐመድ ቡዓዚዚዎችና ፋይዳ ሃምዲን መሰል ተበዳዮችንና በዳዮችን  ዘመንና ታሪክ ሲቆጥሯቸውና ሲያስታውሷቸው ይኖራሉ፡፡

ታዝባችኋል፣ አንዲት እናት በድንገት ምጥ ይዟት፣ አሊያም የሆነ ላገር የሚጠቅም፣ ገና ሮጦ ያልጠገበ ጎረምሳ፣ አንዳች አደጋ ነገር ደርሶበት ወደ አንድ ክሊኒክ አሊያም ሆስፒታል በህክምና ህይወታቸውን ለማትረፍ ሄደው፣ በጊዜው ተረኛው ሐኪም ባለመኖሩ ምክንያት እናቲቱ ምጡ ጠንቶባት፣ ጎረምሳውም ደሙ ፈሶ ለሞት ከተዳረጉ በኋላ፣ ዜጎች፣ ‹‹ አዬ እኛ አገርማ ምን መንግሥት አለ!!›› እያሉ እንባቸውን ወደላይ ሲረጩ? . . .

ታዝባችኋል፣ ዜጎች ለዘመናት ነጭ ላባቸውን አንጠፍጥፈው የሰሩትን ገንዘብ በማጅራት መቺዎች ከተዘረፉ በኋላ፣ ‹‹በገዛ አገራችንኮ ሠርተን መኖር አልቻልንም፣ ንብረታችን የቀማኞች ሲሳይ እየሆነ ለህይወታችን እንኳ እየሰጋን ነው፣ ታዲያ እንዴት ነው የሚቀርጠን መንግሥት ህይወታችን ከተራ የመንደር ሌቦችና ዘራፊዎች ሊታደገን የሚችለው›› ሲሉ? . . .

ታዝባችኋል፣ የሆነ መንደር መብራት ወይም ውኃ በተደጋጋሚ እየተቋረጠ፣ ዜጎች ‹‹አዬ የኛ መንግሥት፣ በጨለማ ስንዋጥና፣ ውኃ ስንጠማ እንኳ የማያውቅ ከንቱ መንግሥት›› ሲሉ ሲንገፈገፉ፣ ሲማረሩ፣ ሲያለቅሱ? . . . (በነገራችን ላይ የሆነ ቦታ በተደጋጋሚ እንዲህ አይነት ሁኔታ ሲከሰት የሌላ ቀበሌ ሰዎች እንዴት ነው እሱ፣ እናንተ ቀበሌ አንድ የዘመኑ ሰው የለም እንዴ . . . ብለው እርስ በርስ ይጠያየቃሉ፣ ምክንያቱም የዘመኑ ሰው ያለበት መንደር ውሃም ሆነ መብራት ተቋርጦ ስለማይሰነብት )

በሐሰተኛ ሰነድ፣ በተጭበረበረ ማስረጃ፣ በገንዘብና ስጦታ በጉቦኛ የፍትህ አካላት ፍትህ ተጣሞባቸው፣ አቤት የሚሉበት አጥተው በራቸውን ዘግተው ስለሚያነቡ ወገኖችስ ምን ያህል ታዝባችኋል?   . . .

ውበቷን በልባቸው ከቋመጡና ተክለሰውነቷን ባይናቸው ከቀላወጡ በኋላ አልጋ ላይ እንዴት ልትሆን እንደምትችል እያሰላሰሉ፣ ብዙ የውኃ ጋሎን የያዘ የእሳት አደጋ መኪና እንኳ ሊያጠፋው የማይችል የወሲብ እሳት አይኖቻቸው ውስጥ እየተንቀለቀለ፣ ያቀረቡላትን የወሲብ ግብዣ አልቀበልም ስላለቻቸው ብቻ ‹‹ቀልቤ አልወደዳትም›› ወይም ‹‹ለስራው የሚሆን የተሟላ መረጃ አላቀረበችም›› አሊያም ‹‹ቆንጆ ሴት ሥራ አይሆንላትም›› በሚል እንቶፈንቶ ምክንያት ብቻ ለሥራ ያስገባችውን ሲቪ የቅርጫት እራት ስለሚያደርጉ ሹመኘኞችስ? . . .  እኔ ለጊዜው የመጣልኝን አልኩ እንጂ ይኼን ጊዜኮ እናንተ የታዘባችሁት በርካታ ከዚህ የከፉ ጉዳዮች አእምሯችሁን አጣበዋል፡፡

አገራችን በየዘመናቱ በእንደዚህ አይነት ጥቃቅንና አነስተኛ የየዘመኑ ሹመኞች ሰለባ ናት፡፡ ታዲያ ብዙ ጊዜ በነዚህ ሰዎች ምክንያት  ትልቁ መንግሥት በዜጎቹ ይሰደባል፣ ይብጠለጠላል፣ ይታማል፣ ይጠላል፣ ሲያልፍም አመጽ፣ ኩዴታና አብዮት ይነሳበታል፡፡

Monday, February 4, 2013

የሚበልጠውን ይዘናል!!

 ከዲ/ን አሸናፊ መኰንን «የኑሮ መድኅን» መጽሐፍ ገጽ 32 ላይ ተቀንጭቦ የተወሰደ

ዲዮጋን የተባለ የግሪክ ፈላስፋ ኑሮው ጎርፍ በሸረሸረው ፈፋ ውስጥ ነበር። ንብረቱም አንዲት መንቀል /የውሃ መጠጫ ቅል/ ስትሆን አንዲት ውሻም ጓደኛው ነበረች። ታላቁ እስክንድር ዓለምን አስገብሮ ሲመለስ ዲዮጋን የተባለውን ፈላስፋ ማየት አለብህ ስላሉት ሊያየው መጣ። ዲዮጋን ግን ከቤቱ አጠገብ በጀርባው ተኝቶ ፀሐይ ይሞቅ ነበር። ታላቁ እስክንድር አጠገቡ መጥቶ ቢቆም ስንኳ ዲዮጋን ማነው? ብሎ ዓይኑን አልገለጠም። እስክንድርም፤ ዲዮጋን ሆይ፦ ተነስ! እኔ ታላቁ እስክንድር ነኝ። ዓለሙን ሁሉ አስገብሬ ተመልሻለሁ፤ የምትሻውን ለምነኝ፤ የመንግሥቴንም እኩሌታ ቢሆን እሰጥሃለሁ» አለው። ዲዮጋን ግን ዓይኑን እንደከደነ «ይልቅስ አንተ ልትሰጠኝ የማትችለውን ፀሐይ እንዳልሞቅ አትከልክለኝ» አለው ይባላል። ንጉሥ እንኳን የማይሰጠውን ብዙ ስጦታ ስለተቀበልን እግዚአብሔር ይመስገን!
  ሰውዬው  «እግር የሌለውን ሰው እስካይ ድረስ ጫማ ስላልነበረኝ አዝን ነበር» ብሏል። ሰውዬው መለስ ብሎ ራሱን ሲመለከት የሚበልጥ ነገር አገኘ ጫማን ገንዘብ ይገዛዋል፤ እግርን ግን ገንዘብ አይገዛውም።  ጫማም ያማረው እግር ስለነበረው ነው። ለማማረርም የበቃነው ስላለን ነው። ለማማረር እንኳን እድሜ ስላገኘን ልናመሰግን ይገባል። በሣጥናቸው ብዙ ልብስ አጭቀው  ከአልጋዬ ተነሥቼ አንድ ቀን እንኳን በለበስኩት እያሉ የሞቱ ሰዎችን አውቃለሁ። የሚበላው እያለው የሚሞት፤  እንዲሁም የሚበላውን አጥቶ የሚኖር ብዙ ሰው አለ። ባለጠጎች በገንዘባቸው አንድ ቀን እድሜአቸውን ማስረዘም አይችሉም። እናት ለምትወደው ልጇ ቀንሳ የማትሰጠው እድሜ ስላለንና ሰው የማይሰጠውን ስለተቀበልን እግዚአብሔርን ልናመሰግን ይገባል።

Friday, February 1, 2013

«የበላ ዳኛ…………………………..እንዲሉ!!»



ከጥቁሩ የአፍሪካው ዓለም በምድረ እስራኤል ይዞታ ያላት ብቸኛ ሀገር ኢትዮጵያ ናት። መረጃዎች እንደሚያሳዩን ኢትዮጵያ በምድረ እስራኤል 7 ያህል ገዳማት ያሏት ሲሆን በዐረቦችና በእስራኤል መካከል በተደረገው የ6ቱ ቀን ጦርነት ምክንያት የተዘጋው የዮርዳኖስ ዳርቻውና በሃሽማታዊው የንጉሥ ሁሴን ግዛት ያለና ምንም ያልተሰራበት ይዞታ ብቻ ሲቀሩ ሌሎቹ 5ቱ ይዞታዎች ክፍት ሆነው አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ።
ከእነዚህ ይዞታዎች ውስጥ በእስራኤል አሮጌው ከተማ የሚገኘው የኢትዮጵያ ይዞታ የሆነውና በአረብኛው «ዴር ኤል ሡልጣን» ተብሎ እስካሁን የሚጠራውና በአማርኛው ትርጉም «የመንግሥት ገዳም» የሚባለው በጎልጎታ መካነ መቃብር አጠገብ ያለው ይዞታ ዋነኛው ነው። 
ይህ ይዞታ ለ1600 ዓመታት ያህል በጳጳሶቻቸው ሲመሩን ከነበሩት ከግብጾች ጋር በይገባኛል ጥያቄ እያጨቃጨቀ ሲቆይ  ከ230 ዓመት በላይ አስቆጥሯል። ጉዳዩም እስካሁን ማብቂያ ሳይበጅለት ተወዝፎ ይገኛል። የገዳሙ ባለቤት ማን እንደሆነ እስራኤል ብታውቅም በግብጽ መንግሥት ከፍተኛ የፖለቲካ ድጋፍ ካለው ከኮፕቶች ገዳም ኃላፊዎች ጋር ለመጋጨት ስለማትፈልግ ጉዳዩን ያዝ ለቀቅ እያደረገች መያዙን እንደስልት አድርጋ ትጠቀምበታለች።
ኢትዮጵያውያን መነኮሳት በቦታው ላይ እየኖሩ ያለው አኗኗር እጅግ አሳዛኝና አስከፊ ከመሆኑ ጋር ገዳሙን በማሻሻል ለኑሮና ለሰው እይታ እንዲመች አድርገው ለመስራት ፈጽሞ የማይችሉ ሲሆን  ግብጾቹ  እያንዳንዷን እንቅስቃሴ  እየተከታተሉ በእስራኤል ፖሊስ እየገዛ  እንዲቆም ያስደርጋሉ።  ካገኘነው መረጃ እንደተረዳነው ከሆነ ማንኛውንም ልማትና እድሳት ለማከናወን እንዳይቻል የሚቀርበው ብቸኛ ምክንያት በጎልጎታ ዙሪያ ያሉ ቅዱሳን መካናት ሁሉ ቅርጽና ይዘታቸውን ሳይለውጡ ባሉበት ሁኔታ እንዲረጉ የሚያስገድድ ስታተስ-ኮ /Status-quo/ የሚባል ሕግ አለ በማለት ኢትዮጵያውያንን ያግዷቸዋል።