Sunday, April 24, 2016

ትንሣኤ አንድ ነው፣ ሕይወትም እሱ ነው!



ቀልጣፋ ሬስቶራንቶች በቀላሉ የሚስቡን የፈለግነውን ምግብ በምንወደው መንገድ እንድናዝ መንገድ ስለሚከፍቱልን ነው። ጥቂት ካፌዎች ደግሞ ከመቶ በላይ የተለያዩ የቡና ጣዕም እንደሚያቀርቡ በጉራ ይናገራሉ። መኖሪያ ቤቶችና መኪናዎችን ስንገዛ እንኳ የምንፈልገው ምርጫ እንዲያሟላ እንሻለን። በቼኮላት፣ በቫኒላና በእንጆሪ ዓለም ታጥረን መኖር አንፈልግም። ፍላጎት ንጉሥ ነው! እንደግላዊ ፍላጎትህና ምርጫህ የምታገኝበት ሁሉ የተሟላበት ዘመን ነው። የዓይን አምሮትና ፍላጎትን የሚያሟላው ዓለም የእምነት መንገድንም ለዘላለማዊ ሕይወት ይበጃል ያለውን በአማራጭ አቅርቧል።

ታዲያ ለአንተ /ለአንቺ/ ትክክለኛ እምነት የማግኘቱ ሁኔታስ ምን ይመስላል?

ወቀሳ አልባ፣ ብዙ ጫና የሌለውና ይህንን አድርግ አታድርግ እያለ የማያስቸግር ሐይማኖት ብታገኝስ? ቀደም ብዬ እንደገለፅኩት ያውና እዚያ አለ እንደሚሉት ነገር፣ ሃይማኖት እንደሚወዱት አይስክሬም የሚመረጥ ነው እንዴ?
እድሜው፣ ሥርዓቱና ደንቡ ስለሚስብህ ይሆን? ወይስ በባለብዙ መንገድ የሕይወትህ ቤዛ ቃል ስለተገባልህ በአንዱ ላይ ተስፋህን ለማኖር?

ትኩረታችንን ለመሳብ የሚሻሙ በርካታ ድምፆች ስላሉ ለምን? ብሎ ነው አንድ ሰው ኢየሱስን ከሌሎች ማለትም ከመሐመድ ወይም ከኮንፊሸየስ፣ ከቡድሐ ወይም ቻርለስ ቴዝ ራስል ወይም ከጆሴፍ እስሚዝ አስበልጦ የሚመርጠው? ዞሮ ዞሮ ሁሉም መንገዶች የሚያደርሱት ወደ መንግስተ ሰማይ አይደለም እንዴ?

 “በኢየሱስ እናምናለን” የሚሉቱ ራሳቸው የማዳኑን ተስፋ የሚገልጡበት መንገድ የተለያየ ስለሆነ እንደገበያ ላይ ሸቀጥ ገብተን ድነትን የምንሸምትባቸው አይደሉም።
 በመሰረቱ ሁሉም ሃይማኖቶች አንድ አይደሉምና። እንደ እውነቱ ከሆነ ሁሉም ሃይማኖቶች ወደ መንግስተ ሰማይ አያመሩም። ሁሉም መንገዶች ወደ ኢንዲያና መቼም አያደርሱም። የእምነት ድርጅቶች ሳይሆኑ ወደመንግሥቱ የሚያስገባው ላመኑበት ሁሉ “ኢየሱስ ብቻ ነው” የምንለው ማለት ስለፈለግን ሳይሆን እንድንል የሚያስገድደን እውነት ያለው በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ስለተፈፀመ ነው።

ኢየሱስ ብቻውን በእግዚአብሔር ሥልጣን ይናገራል።

1/ ምክንያቱም ኢየሱስ ብቻ ነው ሞትን ያሸነፈው። እስካሁን ድረስ መሐመድ፣ ኮንፊሸየስና ሌሎች በመቃብር በስብሰው ይገኛሉ። ነገር ግን ኢየሱስ በራሱ ስልጣን በጨካኙ የሮማውያን መስቀል ከሞተና ከተቀበረ ከሦስት ቀን በኋለ መቃብሩን ፈንቅሎ ተነስቶአል። በሞት ላይ ስልጣን ያለው ማንኛውም ሰው ትኩረታችን ሊስብ ግድ ይላል። ማንም በሞት ላይ ስልጣን ያለው ግለሰብ ሲናገር ልናደምጠው አስፈላጊ ነው። ሞትን ማሸነፍ የቻለ ከፍጥረታት መካከል ማንም የለም። ከሰማይ የመጣው ብቻ ሞትን አሸንፎ ወደሰማይ ወጥቷል።ስለዚህ እንዲህ ያለው አሸናፊ የተናገረው የእምነት መሠረት መሆን አለበት። ሰው ሟች መሆኑን ያውቃል። ሟች ደግሞ ከሞት ለማምለጥ የሚችለው በሞት ላይ ባለሙሉ ሥልጣን በሆነ ክንድ ላይ ሲያርፍ ነውና ኢየሱስን ማመን የግድ ይለዋል። በሞት ላይ ሥልጣን ያለው፣ ለሞታችን ብቸኛ ዋስትና የመሆን ብቃት አለው። ሌላ መንገድ፣ ሌላ ቃል ኪዳን፣ ሌላ አዳኝ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ማንም የለም። ይህንን እውነት ያለምንም ድርድር ማወጅ ያልቻለ እምነት፣ ምድራዊ የሃይማኖት ድርጅት እንጂ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ምስክር አይደለም።

2/ የኢየሱስ ሕይወትና ትንሣዔ ምስክር ያለውና እውነት ነው።
የኢየሱስን ትንሣዔ የሚደግፈው መረጃ የሚያጥለቀልቅ ነው። ሮማውያንና ሰቃልያኑ ካህናት የኢየሱስን መቃብር ማስጠበቅ ያስፈለጋቸው «በሦስተኛው ቀን እነሳለሁ» ያለውን ቃሉን ይዘው እንጂ የሞተ ሰው መቃብር ስለሚጠበቅ አልነበረም። አዎ ትንሣኤውን ለመከላከል ወታደሮች ከመቃብሩ ማንም እንዳይወጣ፤ ወደመቃብሩም ማንም እንዳይደርስ አድርገው አስጠብቀው ነበር። ነገር ግን የመቃብሩ ቦታ ባዶ ሆኗል! እንደተናገረው አልተነሳም እንዳይሉ የኢየሱስ ጠላቶች ያን ሁሉ ስለትንሣኤው የተነዛውን ወሬ ለማክሸፍ የበሰበሰውን አካሉን በማቅረብ በቀላሉ ያስታግሱት ነበር። ግን አልቻሉም፤ መላው ሲጠፋባቸው ደቀመዛሙርቱ ሬሳውን ሰርቀውት ይሆን? አሉ። ከሐዋርያቱ መካከል ከዮሐንስ በስተቀር ሌሎቹ የሸሹት በጊዜ ነው። የሸሹ ሰዎች ተመልሰው ከሮማ ወታደሮች ጋር ተዋግተው ሰረቁት ማለት የማይመስል ነገር ነው። የመቃብሩ ባዶ መሆን ሳያንስ ሞቶ የተቀበረ ሰው ዳግም ተነስቶ በሰዎች ፊት ራሱን በመግለጥ ያረጋገጠ በታሪክ ማንም የለም። ኢየሱስ ብቻ ይህን ማድረግ ችሏል።
ትንሣዔውን ያለምስክር ያልተወ ኢየሱስ ግን በአንድና በሁለት ሰዎች ፊት ብቻ ሳይሆን በአምስት መቶ ሰዎች ፊት ትንሣዔውን አስመስክሯል።

«መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ፥ለኬፋም ታየ በኋላም ለአሥራ ሁለቱ፤ ከዚያም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታየ፤ ከእነርሱም የሚበዙቱ እስከ አሁን አሉ አንዳንዶች ግን አንቀላፍተዋል፤ከዚያም በኋላ ለያዕቆብ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ ታየ፤ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ» 1ኛ ቆሮ 15፤4-8

ስለዚህ ሰዎች ኢየሱስን ለማመን የሚያስችላቸው በቂ የእምነት ማስረጃ ስላላቸው ነው። በዚህ ምድር ላይ ካሉ ሃይማኖቶች ውስጥ እንደኢየሱስ ሞትን ያሸነፈ፤ ትንሣኤውን በምስክር ያረጋገጠ ማንም የለም። ስለዚህ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው ማንም ሰው ሊደመጥ ይገባል። ኢየሱስ በሞት ላይ ያለውን ሥልጣን አረጋግጧል። ስለዚህ የሚናገረውን መስማት ይገባናል። ለድነት ብቸኛው መንገድ ኢየሱስ መሆኑን ራሱ ይናገራል።(ዮሐንስ 14፡ 6)። ኢየሱስ ክርስቶስ ካሉትም ብዙ መንገዶች አንዱ አይደለም። ኢየሱስ ብቸኛ የድነት መንገድ ነው። ሌላ መንገድ ሁሉ በትንሣኤና በሕይወት ላይ ሥልጣን የሌለው የሞት መንገድ ነው። በሞትና በትንሣኤ ላይ ሥልጣን በሌለው ማንኛውም የመዳን ተስፋ ቃል ላይ አትታመኑ። እውነት የምትመስል ነገር ግን የጥፋት መንገድ ናት። “በዚህና በዚያም ትድናላችሁ” የሚሉ ድምጾች መጨረሻቸው ሞት ነው። ሟች ለሟች የተስፋ መንገድ መሆን አይችልም።

3/ ኢየሱስ ከሸክም ያሳርፋል።

በዚህ ምድር ላይ ከሸክም አሳርፋችኋለሁ ብሎ ቃል የገባ አንድም ሥጋ ለባሽ የለም። ይህ ብቸኛ ኢየሱስ እንዲህ ይላል “እናንተ ደካሞች፤ ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፣ ወደእኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” (ማቴዎስ 11፡ 28)። ሕይወትም አስቸጋሪ ነው። ብዙዎቻችን ደምተናል፣ ቆስለናል፣ ጦርነትንም እንፈራለን። ዓለምም አስጨናቂ እየሆነች ነው። ስለዚህ የሚያሳርፈንን ብንፈልግ ተገቢ ነው። ነገር ግን ከኢየሱስ በቀር ሸክም የከበዳችሁ ወደእኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ ያለ ማንም ሌላ የለም። በትንሣኤውና በሕይወቱ የታመነ ኢየሱስ ይህንን የማለት ብቃት ስላለው በእርሱ ላይ ማረፍ ከአስጨናቂው ዓለም ለመዳናችን ዋስትናችን ነው። ከድካማችሁ በማያሳርፉ በማንም ላይ አትታመኑ። ትድኑበት ዘንድ ብቸኛው ቃል ኪዳን ኢየሱስ ለመሆኑ “ወደእኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ” የሚል ቃል ነግሮናልና ነው። በዚህ ተራራ ወይም በዚያ ሸለቆ የሚያሳርፍ ቃል የለም። ቃል፣ ቀራንዮ ላይ ስለእኛ አንድ ጊዜ ተሰጥቷል። በሞቱ ሞታችንን ሽሮ፣ በትንሣኤው ሕይወት በሰጠን በክርስቶስ ኢየሱስ ላይ ብቻ እንድንታመን የሚያስፈልገን የሚያስተማምን ምስክርነት ስለተወልን ነው።
ስለዚህ ምን ትፈልጋላችሁ? ከኃጢአት፤ ከድካም፤ ከተስፋ መቁረጥ በንስሐ መታደስ ወይስ የአንዱ ሃይማኖት አባል በመሆን ብቻ መኖር? ሕያው የሆነ አዳኝ ወይስ “ከሞቱት በርካታ ነቢያት ወይም ጻድቅ” አንዱን ተስፋ ማድረግ? ትርጉም ያለው ግንኙነት ወይስ ተራ የአምልኮ ሥነ-ሥርዓት መከተል?

4/ ኢየሱስ አማራጭ ሳይሆን ምርጫ ነው!

ሃይማኖት ማለት አንድ መንፈሳዊ ድርጅት ወይም የአንዱ ተቋም ስያሜና የዚያ አባል ሆኖ መኖር ማለት አይደለም። ከእግዚአብሔር አብ ጋር ትርጉም ያለው ግንኙነት ትፈልግ እንደሆን ሃይማኖትህ ኢየሱስን ማመን ነው። «በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው» ይላል መጽሐፍ። (ዮሐንስ 3፡ 36) አንዳንዶች ይህንንማ እናምናለን ነገር ግን ትክክለኛው እምነት ያለው በኛ ሃይማኖት ውስጥ ስለሆነ አባል ሁነን ይላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ፣ በማኅበር ስለመጸለይ ይነግረናል እንጂ ኢየሱስን ለማመን የዚህ ወይም የዚያ ሃይማኖት ተቋም አባል የመሆን ትዕዛዝ የለውም። ኢየሱስ በሱ የሚያምኑ ሁሉ እንዲድኑ እንጂ የሃይማኖት ድርጅት ሊመሠረት አልመጣም። ለጸሎት በኅብረት መሆን ቢያስፈልግ መጀመሪያውም መጨረሻውም የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ብቻ የሚከብርበት እንጂ ሰው፣ ሰው የሚሸትበት፣ ብቃትና የሰዎች ማንነት የሚደሰኮርበት ከሆነ ድርጅትን ማምለክ ይሆናል። በዚህ ዘመን ብዙዎች ተሰነካክለዋል።
 በራሱ ሥልጣን ከሙታን የተነሳ ማን አለ? ወይም በዓለም ላይ ካሉ የተለያዩ የሃይማኖት ድርጅቶች መካከል ለሰው ልጆች ዘላለማዊ የሕይወት ተስፋ ለመስጠት አስተማማኝ ማን አለ? መሐመድ፣ ኮንፊሽየስ፣ ራስል፣ ስሚዝ፣ ሉተር፣ ካቶሊክ፣ ኦርቶዶክስ፣ ፕሮቴስታንት ወዘተ ማንም ቢሆን ይህን ማድረግ አይችሉም።
እምነት ከሞት በላይ በሆነ በትንሣኤው ምስክርነት ላይ ይታመናል። ሕይወት ከድርጅት ሥልጣንም ባለፈ ብቸኛ የድነት መንገድ በሆነው ኢየሱስ ላይ ይጸናል።

“እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው” ዮሐ 6:47 ያለን ኢየሱስ ብቻ ነው።

Friday, April 22, 2016

በዲሲ ቅ/ማርያም ቤተክርስቲያን የሥልጣንና የገንዘብ ጦርነቱ ተባብሶ ቀጥሏል!


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየተለመደ የመጣ ችግር አለ። በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በሁለትና ሦስት ጎራ ተከፋፍሎ የመጣላት፤ የመደባደብና ፍርድ ቤት ድረስ የመካሰስ አደጋ ከመቼውም ጊዜ በላይ እየሰፋ መጥቷል። መሠረታዊው የግጭቱ ምክንያት ሲገመገም በሁለት ነጥቦች ላይ ያጠነጥናል።


                       የሴራው መነሻ፤
1/ በተለያየ መንገድ ገንዘብ ለመዝረፍ እና

2/ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የማይነቃነቅ ባለሥልጣን  ለመሆን ነው።


                      የሴራው ተሳታፊዎች፤
የተወሰኑ ምዕመናንና ምዕመናት ግን በሴራው ተዋናዮች ዓላማ ተጠልፈው በቅንነት ቤተ ክርስቲያናቸውን ከአደጋ ለመከላከል ሲሉ ወደጦርነቱ ይገባሉ። የፖለቲካ ክፍፍሉም የራሱ ሚና ይኖረዋል። የሁለት ጎራ ሴረኞች ሕዝቡን የሚቀሰቅሱት ለቤተክርስቲያን ያለነሱ የተሻለ አሳቢ የሌለ በማስመሰል እንጂ ሁለቱም ጎራዎች ድብቅ ዓላማቸው አንዱ አንዱን በመንቀል በቦታው ላይ ራሳቸውን ለመትከል ነው። ይህ ሲባል በቅን አስተሳሰብ የተነሱ የለም ማለት አይደለም። ነገር ግን ቅኖቹ «ከነገሩ ጦም እደሩ» ብለው ራሳቸውን ስለሚያገሉ በመፍትሄው ላይ ተሳታፊ አይደሉም። ሁከቱና ብጥብጡ በውጪው ዓለም ባሉ አብያተክርስቲያናት ማለትም በለንደን፤ በሮም፤ በደቡብ አፍሪካ፤ በሰሜን አሜሪካ እየከፋ ሄዷል።


                            የሴራው ተዋናዮች
የሴራው ተዋናዮች ዓይነት ደግሞ የተለያዩ ናቸው። በአብዛኛው በየአኅጉረ ስብከቱ የሴራው ባለቤቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሲሆኑ በየአድባራቱ ደግሞ አስተዳዳሪዎች፤ ቦርዶች፤ የሰበካ ጉባዔ አባላትና ማኅበረ ቅዱሳን  ናቸው።  ከታች የተመለከተው ቪዲዮ ጦርነቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲካሄድ ያሳያል።
«ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ» ገላ 5፤15




Thursday, April 14, 2016

ውስጤ መኖር ያለበት ቃና ቲቪ ሳይሆን መንፈስ ቅዱስ ነው!!

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከወዳጅ ጓደኞቼ ጋር በተገናኘን ቁጥር የመወያያ አጀንዳችን የሆነው ጉዳይ የዛሬውን ፅሁፍ እንድፅፍ አስገደደኝ፡፡ ዋና መቀመጫውን በዱባይ አድርጎ በቅርብ ጊዜ በሀገራቸን ስርጭቱን የጀመረው ቃና ቴሌቪዥን በአማረኛ እየተረጎመ (dubbing) በሚያቀርባቸው የቱርክ፣ የጣሊያን፣ የህንድ፣ የጃፓን እና የመሳሰሉት ሀገሮች ተከታታይ ፊልሞቹ የበርካታ ሰወችን ቀልብ እንደገዛ ሁላችንም እናውቃለን፡፡ በእጅጉ የሚገርመው ደግሞ በዙሪያየ ያሉና የማውቃቸው በርካታ ክርስቲያኖች ጭምር ለእነዚህ የባህር ማዶ ፊልሞች እጅ ሰጥተው በጉጉትና በከፍተኛ ናፍቆት ሲጠብቁ ማየት ነው፡፡ የቃና ቲቪ ፊልሞች የሚታዩበት ሰዓት ደግሞ ወላጆች ከስራ፣ ልጆች ከትምምርት ቤት፣ ወጣቶችም ከሚውሉበት ስፍራ በቤት በሚሰበሰቡበት፣ የእግዚአብሔርን ቃል በሚያጠኑበት፣ በጋራ በሚፀልዩበት ሰዓት ነው፡፡ እውነትም በስጋ አይን ለተመለከታቸው ፊልሞቹ በከፍተኛ ሁኔታ የሰውን ቀልብ የመግዛት አቅም እንዲኖራቸው ሆነው ተሰርተዋል፡፡ አንደኛው ፊልም ሲያልቅ በቅፅበት ሌላው ይቀጥላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ከምሽት 12፡00 ሰዓት የተቀመጠ ሰው እስከ ምሽት 4፡00 ሰዓት ሌላ ስራ ሳይሰራ ያለምንም እንቅስቃሴ ይቀመጥ ዘንድ ግድ ይለዋል ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ልብ እንበል የተቀማነው ወትሮ ለፀሎትና ለእግዚአብሔር ቃል ጥናት በእጅጉ ይመቸን የነበረውን ሰዓት ነው፡፡ ከዛም ደክሞን እንተኛለን፡፡ እዚህ ጋር ግን እንደመንፈሳዊ ሰው ልንነቃ የሚገባን ይመስለኛል፡፡ ሰባት በየቀኑ ለየአንድ አንድ አዓት የሚታዩ መሳጭ የባህር ማዶ ፊልሞች እቤታችን ድረስ መጥተው በራሳችን ቋንቋ እየተመለከትናቸው ነው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ቀድሞ ለጌታ የምንሰጠውን ሰዓት እየተውን፣ በፀሎት የምናሳልፈውን ጊዜ እየሸረሸርን ከክርስትና በእጅጉ የራቁ ሐገሮች ሰርተው በሚልኩልን ነገር ስንጠመድ የእነሱን ባዕድ፣ አምልኮ ኢ-ክርስትናዊ ነገሮች በሙሉ ወደ ውስጣችን እየሰገሰግን ነው፡፡ ልጆቻችንም ከክርስትና በእጅጉ ያፈነገጠ ነገር በየቀኑ እየተመለከቱ እንዲያድጉ እየተፈረደባቸው ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችን በቆላስይስ 2፥8 ላይ ‹‹ እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን፥ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ›› ብሎ በዓለማዊ ነገር እንዳንጠመድ ያስጠነቅቀናል፡፡ ኢየሱስም በማርቆስ ወንጌል 4፥24 ‹‹ምን እንድትሰሙ ተጠበቁ›› ብሎ ከምንሰማውና ከምናየው እንድንጠበቅ ያዘናል፡፡ ዓለማችን ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ኢየሱስ በማቴዎስ ወንጌል ስለመጨረሻው ዘመን የተናገራቸውን የዘመን መጨረሻ ምልክቶች አንድ በአንድ አስተናግዳ ወደ ማገባደደዱ ትገኛለች፡፡ ብዙ ነገሮች ሆነዋል ብዙ ነገሮች ተፈፅመዋል፡፡ ባጠቃላይ ሰይጣን ዲያብሎስ ጥቂት ጊዜ እንደቀረው አውቆ ከመቸውም ጊዜ በላይ በኃይለኛ ቁጣ እየተጋ ያለበት ዘመን ነው፡፡ ዲያብሎስ በዚህ ዘመን በተለይም ወጣቱን ክፍል ከቤተክርስቲያን ለማራቅ ወደ እግዚአብሔር ቃል ትኩረት እንዳያደርግ ከሚጠቀምባቸው ዋና ነገሮች መሀል የፊልምና የሙዚቃው ኢንደስትሪ እጅግ ወሳኙን ድርሻ ይዟል፡፡በዘመናችን የሚሰሩ ፊልሞች በአብዛኞቹ ሰወችን ለዓለማዊ ምኞትና ለርኩሰት አብዝተው የሚጋብዙ ናቸው፡፡ ስለዚህም እኛ ክርስቲያኖች እንንቃ። ሰይጣን በረቀቀ መንገድ በእኛ ላይ እንዲሰለጥን እድል አንስጠው፤ የቱርክና የህንድ ፊልሞችን እያሳየ ከእግዚአብሔር መንግስት የሚለየን ጣቢያ ውስጣችን "ቃና ውስጤ ነው" እያልን ውስጣችን ሊሆንብን አይገባም፡፡ ምክንያቱም እኛ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ነን፡፡ ውስጣችን እሱ ብቻ ነው መኖር ያለበት። ብናምንም ባናምንም ዘመኑ የመጨረሻ ነው፡፡ ያኛው መንግስት እኛን በመዝናኛ ነገር ጠምዶ ከጌታ መንግስት ሊለየን እየተጋ ነው። እኛ ታዲያ ነቅተን ብዙ ምርኮ ልንበዘበዝ ሲገባን በወጥመዱ ከገባንለት እጅግ ከባድ ይሆናል፡፡ ስለዚህም እንንቃ በኢንተርቴመንት ስም ውድ ጊዜያችንን እንዳናስበላ፤ ይልቀንስ የእግዚአብሔርን ዓለምን በልጁ የመጠቅለል አላማ ለማሳካት አብሮ ሰራተኞች እንሁን!ስለወንጌል ግድ ይበለን፡፡
እኛ "መንፈስ ቅዱስ ውስጣችን ነው!"