Saturday, April 27, 2013

በአካፋ የሚዛቀውን ሳይጨምር የ71 ሺህ ብር የወር ደመወዝተኛ ሐዋርያ/ፓስተር/ በኢትዮጵያ? ይቺ ናት ጫወታ!!


በእንግሊዝኛ የአማርኛው ስም «ቸርች» ተብለው ከሚጠሩት ባንዱ የተፈጸመ ድርጊትና እሮሮ ነው።  ምሬት የበዛበት ይህ ሰው «ሐዋርያዬ» በሚለው የዘመኑ ሰው የደረሰበትን ሰቆቃ ሲያሰማ አገኘነውና ራሳቸውን የክርስቶስ ባለሟል አድርገው እውቀት የጎደለውን ሰብስበው እንዴት እንደሚያጃጅሉ ከማሳየቱም በላይ በግራም በቀኝም በክርስቶስ ስም የሚፈጸመውን ዐመጻ ልናካፍላችሁ ወደድን። በወዲህ ሰባኬ ወንጌልና ማኅበር፤ በወዲያ ደግሞ ሐዋርያና ፓስተር ገንዘብ አምላካቸውን ይነግዳሉ።  ከረጅሙ ትርክት ውስጥ ቆንጥረን አቀረብን።
የጽሁፉ ባለቤት ኢዮብ ደምሴ ነው።
ይሄን ጽሑፍ ለምታነቡ ወገኖች ልጠይቅ የምፈልገው ነገር፣
1ኛ. “መልሱኝ” ብዬ ያልጠየቅሁና በብዙ ውትወታና ንግግር ቤተ ክርስቲያን ጥሪ ያደረገችልኝ ሆኖ ሳለ፣
2ኛ. በቤተ ክርስቲያኒቱን ባገለገልኩበት ጊዜ ሁሉ በትጋት በማገልገሌ ውጤታማና ፍሬያማ መሆኔ በራሱ በሐዋርያው እጅ በምስጋና የተጻፈ ያማረ የመሸኛ ደብዳቤ ተሰጥቶኝ እያለ፣
3ኛ. የእረኞች አለቃ የሆነው ጌታ “ጠብቁልኝ” ያለውን መንጋ “ምስጢሩን አያውቅም” በሚል እሳቤ ብቻ፣ በሐሰት ንግግር በማሳሳት ለተሳሳተ ዓላማ እንዲሰለፉ እንዳደረገው ሳይሆን፣ መንጋው እንዳያዝንና እንዳይበተን፣ በመጠንቀቅ ከቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ካቆምኩበት ጊዜ ጀምሮ ራሱን በአደባባይ እስከገለጠበት ጊዜ ድረስ የማውቀውን የሐዋርያውን ችግር በአመራር ክፍሉ ብቻ እንዲያልቅ በምስጢር ይዤ የቆየሁ መሆኔ እየታወቀ፣
4ኛ. እግዚአብሔር ሰፊ የአገልግሎት በር ከፍቶልኝ ከጌታ ምሕረት የተነሳ ተቀባይነትም ባገኘሁበት ጊዜ የተበላሸውንና የፈረሰውን ነገር መልሶ ለመገንባቱ ሥራ ራሴን መስጠቴ ስሕተቱ ምንድን ነው?

Friday, April 26, 2013

ማኅበረ ቅዱሳን እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተሐድሶ ያስፈልጋታል የሚሉ ተሐድሶዎች!


ጽሁፍ፤ በተስፋ አዲስ (ይህ ጽሁፍ ከዚህ በፊት የቀረበ ነው)1
ክፍል አንድ
ተሐድሶዎች እነማን ናቸው?

ብዙ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ስሄድ የስብከት ካሴት ሳዳምጥ፤ የተለያዩ ሥነ ጽሑፎችን ሳነብ ፡ተሃድሶዎች ተሐድሶዎች፡ የሚል ጩኸት እሰማለሁ። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሥር የተቋቋመው ማህበረ ቅዱሳን የሚባለው ድርጅት አባላቱም ሆኑ አመራሮቹ ስለተሃድሶዎች በስብከታቸው እና በጽሑፋቸው ሁሉ በቀጥታም ሆነ በተዛዋዋሪ ሳያነሱ አያልፉም።
እኔም ተሐድሶዎችን ለማወቅ ብዙ ጥረት አድርጌአለሁ። ምን ዓይነት አቋም እንዳልቸውና የት እንደሚገኙ፤ አላማቸው ምን እንደሆነ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማሳወቅ ፈለግሁ። እነርሱ ግን ተሃድሶ የሚለውን  ስም አይቀበሉትም።  እኔ ተሃድሶዎች ስል አንባቢ በሚገባው ቋንቋ ለመጠቀም እንዳሰብሁ ይረዳልኝ። ማህበረ ቅዱሳን የሚባለው ማህበርም ከተሐድሶዎች ጋር ያለውን ቅራኔ ለማቅረብ እሞክራለሁ። አንባቢ የራሱን ተቃውሞም ሆነ ድጋፍ እንዲሠጥ አንዳችም ሳልቀንስ እና ሳልጨምር ትክክለኛውን መረጃ ለማቅረብ እሞክራለሁ። መነሻየ ግን ከማህበረ ቅዱሳን እና ከተሐድሶዎች ሥነ ጽሑፎች ነው። የሁለቱንም ቡድን እንቅሥቃሴ በተከታታይ አቀርባለሁ መልካም ንባብ።
ተሀድሶ ማለት ይላሉ ቤተ ክርስቲያን መታደስ አለባት የሚሉ ወገኖች ማደስ፣ መጠገን፣ ማጽዳት፣ ማለት ነው ይላሉ።ለምሳሌ ቤት ከተሠራ በኋላ ሳይታደስ ብዙ ከቆየ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሊፈርስ ይችላል ስለዚህ ከመፍረሱ በፊት የሚደርግለት እንክብካቤ ቤቱን ያጸናዋል። እንደሸረሪት ድር፤ የጢስ ጠቀርሻ ያሉ ነገሮችም ከቤቱ ላይ ሊጠረጉ ይገባል። ማደስ ማለት ማፍረስ አይደለም በቤቱ ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፤ ማስወገድ እና በፈረሰው በኩል መጠገን ነው በሌላ አነጋገር መሠረቱን ሳይነኩ እና ሳያናውጡ ጥንታዊነቱን እንደያዘ ቤቱን ማሳመር ማለት ነው።የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም ብዙ ዘመን ከመኖሯ የተነሣ ብዙ ስሕተቶች ይገኙባታልና መጽዳት አላባት፤ ባህሉን ከሃይማኖቱ፤ ውሸቱን ከእውነቱ፤ ክፉውን ከደጉ መለየት አለባት የሚል ራእይ ያላቸውና ለዚህ ሌት ተቀን ያለ እረፍት የሚሠሩ ናቸው።
የሚገኙት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው ጳጳሳት፤ ቀሳውስት፤ ዲያቆናት፤ መምህራን፤ የድጓ፤ የቅኔ የቅዳሴ መምህራን የሰንበት ተማሪዎች፤ እንዲሁም ምእመናን ሁሉ ያሉበት የአስተሳሰብ ኃይል ነው። የታወቀ ማህበር ግን የላቸውም። አንዳንዶች ማህበር መሥርተዋል ። ኑራቸው እና ሥራቸው በዚያው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሲሆን በተለያየ ቦታ ጽ/ቤት እና በርካታ ማሰልጠኛዎች አሏቸው። በርካታ መነኮሳት እና ሰባኪዎች በነዚህ ቦታዎች ይሰለጥናሉ። ይህን ሁሉ እንቅሥቃሴ የሚያደርጉት ግን ቤተ ክህነቱ ሳይውቅ ነው። ቀሳውስቱ ስልጠናውን ከወሰዱ በኋላ በየቤተክርስቲያናቸው ሌሎች ቀሳውስት በመመልመል ያሰልጥናሉ። ከጳጳሳትም ውስጥ ለዚሁ ሥራ የሚውል በግላቸው ከፍተኛ እርዳታ ያደርጋሉ። ተሐድሶዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ቁልፍ ቦታና ስልጣን አላቸው። በተለይ በአሁኑ ሰዓት በየአብያተ ክርስቲያናቱ  ሚሊዮኖች በብዛት ይገኛሉ። በገጠር አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እና በገዳማት ሁሉ አሉ። ደሞዛቸውን የሚያገኙት ከዚያው ከቤተ ክርስቲያኒቱ ነው። ግን ከሌሎች የእምነት ድርጅቶችም እርዳታ ያገኛሉ ተብለው ይታማሉ። ተሐድሶዎች  እንደቀደምት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ አማኞች እንጂ እራሳቸውን ተሃድሶ ብለው አይጠሩም።  ስማቸው በሥራቸው ምክንያት ከሚጠሏቸው ወገኖች የተሰጣቸው ነው። በቤተ ክርስቲያን ባሕላዊ ትምህርት ጥልቅ የሆነ ዕውቀት ያላቸው ስለሆኑ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለንተና ደካማ ጎንም ሆነ ጠንካራ ጎን ለይተው የሚያውቁ ሊቃውንት ናቸው። የተሃድሶዎች እንቅሥቃሴ ከባድ እንቅሥቃሴ ነው ምክንያቱም እስከሞት ድረስ የቆረጡ ሲሆኑ ታላቅ ራዕይ ያላቸው ናቸው። በማኅበር መደራጀት ሳይሆን  በግል እያንዳንዱ አውቆ መስራት አለበት ስለሚሉ እዚህ ጋ ወይም እዚያ ጋር ናቸው ያሉት አይባልም። በአጭሩ የሌሉበት ቦታ የለም።
የማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊ ነን የሚሉ ጳጳሳት ሳይቀሩ የዚህ ተሐድሶ የሚባለውን እንቅስቃሴ በስውር ይደግፋሉ። አሁን ባለው ሁኔታ ተሐድሶ የሚባሉት ክፍሎችን ከቤተክርስቲያኒቱ ማስወገድ በፍጹም አይቻልም። ከላይ እስከታች በተያያዘ ሰንሰለት የሚሰሩ ናቸው።

Wednesday, April 24, 2013

ንስሐ ለማን፤ ለምንና እንዴት?


 (ከዚህ በፊት የቀረበ ጽሁፍ ነው)

«ነስሑ እስመ ቀርበት መንግሥተ ሰማያት» (መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ማቴ ፫፤፩-፪)

«ነስሐ»  ስርወ ቃሉ እብራይስጥ ሲሆን ትርጉሙም አዘነ፤ ተጸጸተ፤ ተመለሰ፤ ክፉ ዐመሉን ተወ፤ መጥፎ ጠባዩን ለወጠ ማለት ነው። የግእዙም ግስ ይህንኑ ቃል እንዳለ ወርሶ ይጠቀምበታል።
«ነስሑ እምፍኖቶሙ እኩይ፤ ወእግዚአብሔርኒ ነስሐ እምዘነበበ» ይላል በዮናስ ፫፤፲ ላይ። ከክፉ መንገዳቸው ተመለሱ፤ እግዚአብሔርም በተናገረው ተጸጸተ»  እንደማለት ነው። ሰብአ ነነዌ ከኃጢአታቸው በንስሐ በተመለሱ ጊዜ እግዚአብሔርም ሊቀጣቸው በነበረው ፍርድ አዘነና ምህረትን ሰጣቸው። የእግዚአብሔር ሀዘን ከምህረቱ ሲሆን የሕዝቡ ሀዘን ደግሞ ከበደሉ ነው።       «ነስሐ» የሚለው ቃል በሁሉም ሥፍራ ማዘንን፤ መመለስን፤ መፀፀትን፤ መተውን ያመለክታል። «እግዚአብሔር ተፀፀተ» ስንል አምላካዊ ምሕረቱን ለመቀበል በማይፈልግ የሰው እልክኛ ልብ ወይም በሌላ መልኩ ምሕረቱን በሚጠይቅ ተነሳሒ ላይ ባለው አባታዊ ፍቅር እንጂ የሚጎድለው ወይም የሚጨመርለት ስላለ ያንን ከማጣትና ከማግኘት ጋር በተያያዘ አይደለም። ሰብአ ነነዌ ከተዘጋጀው ጥፋት ለመመለስ ንስሐ ሲገቡ እግዚአብሔርም በአምላካዊ ምህረቱ አዝኖላቸው ጥፋቱን መልሶላቸዋል። በሌላ ቦታም እንዲህ የሚል አለ።
በዘመነ ኖኅ የሰው ልጅ ዐመጻ በዝቶ የጥፋት ውሃ በታዘዘ ጊዜ «እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ፥ በልቡም አዘነ» ዘፍ ፮፤፮ ይላል።
«ተጸጸተ» የሚለው ቃል «ነስሐ» የሚለው ቃል ትርጉም ነው። «እግዚአብሔር ተጸጸተ፤ አዘነ» ሲል ቀድሞ ያላወቀው ነገር በመድረሱ ወይም የማያውቀው ነገር እንደተከሰተ በማየቱ የተሰማው ስሜት ሳይሆን የሰው ልጅ ቀድሞ ከገነት ሕጉን አፍርሶ በመውደቁና ዳግመኛም በዚህ ምድር ላይ ኃጢአቱን እያበዛ በመሄዱ የተነሳ ሰው በራሱ በደል የሚመጣበት የፍርድ ቁጣ ስለሚያሳዝነው ብቻ ነው። ፻፳ የንስሐ ዘመንን ለመጠቀም ያልፈለገ ሕዝብ በውሃ ሰጥሞ ሲጠፋ ቢመለከት እግዚአብሔር መጸጸቱ አምላካዊ ባሕሪው ነው። እግዚአብሔር አባት በመሆኑ ሰዎች ይጠፉ ዘንድ ሳይፈልግ ዐመጻቸው ከሚያመጣባቸው ፍርድ የተነሳ ግን ያዝናል፤ ይጸጸታል።