ከዲ/ን አሸናፊ መኰንን «የኑሮ መድኅን» መጽሐፍ ገጽ
32 ላይ ተቀንጭቦ የተወሰደ
ዲዮጋን የተባለ የግሪክ ፈላስፋ ኑሮው ጎርፍ በሸረሸረው
ፈፋ ውስጥ ነበር። ንብረቱም አንዲት መንቀል
/የውሃ መጠጫ ቅል/ ስትሆን አንዲት ውሻም ጓደኛው ነበረች። ታላቁ እስክንድር ዓለምን አስገብሮ
ሲመለስ ዲዮጋን የተባለውን
ፈላስፋ ማየት አለብህ ስላሉት ሊያየው መጣ። ዲዮጋን ግን ከቤቱ አጠገብ በጀርባው ተኝቶ ፀሐይ ይሞቅ ነበር። ታላቁ እስክንድር አጠገቡ መጥቶ ቢቆም ስንኳ ዲዮጋን ማነው? ብሎ ዓይኑን አልገለጠም። እስክንድርም፤ ዲዮጋን ሆይ፦ ተነስ! እኔ ታላቁ እስክንድር
ነኝ። ዓለሙን ሁሉ አስገብሬ ተመልሻለሁ፤ የምትሻውን
ለምነኝ፤ የመንግሥቴንም እኩሌታ ቢሆን እሰጥሃለሁ» አለው። ዲዮጋን ግን ዓይኑን እንደከደነ «ይልቅስ አንተ ልትሰጠኝ የማትችለውን ፀሐይ እንዳልሞቅ አትከልክለኝ» አለው ይባላል። ንጉሥ እንኳን የማይሰጠውን ብዙ ስጦታ ስለተቀበልን እግዚአብሔር ይመስገን!
ሰውዬው «እግር የሌለውን ሰው እስካይ ድረስ ጫማ ስላልነበረኝ አዝን ነበር» ብሏል። ሰውዬው መለስ ብሎ ራሱን ሲመለከት
የሚበልጥ ነገር አገኘ። ጫማን ገንዘብ ይገዛዋል፤ እግርን ግን ገንዘብ አይገዛውም። ጫማም ያማረው እግር ስለነበረው ነው። ለማማረርም
የበቃነው ስላለን ነው። ለማማረር እንኳን እድሜ ስላገኘን ልናመሰግን ይገባል።
በሣጥናቸው ብዙ ልብስ አጭቀው
ከአልጋዬ ተነሥቼ አንድ ቀን እንኳን በለበስኩት
እያሉ የሞቱ ሰዎችን አውቃለሁ። የሚበላው እያለው የሚሞት፤
እንዲሁም የሚበላውን አጥቶ የሚኖር ብዙ ሰው አለ። ባለጠጎች በገንዘባቸው አንድ ቀን እድሜአቸውን ማስረዘም አይችሉም። እናት ለምትወደው ልጇ ቀንሳ የማትሰጠው እድሜ ስላለንና
ሰው የማይሰጠውን ስለተቀበልን እግዚአብሔርን ልናመሰግን ይገባል።