Showing posts with label ትምህርት. Show all posts
Showing posts with label ትምህርት. Show all posts

Wednesday, March 6, 2013

የይሖዋ ምስክሮች መሠረት ምንድነው?


ይህንን መረጃ ለማውጣት መነሻ የሆነን አንድ ጠያቂያችን ባቀረበው ጥያቄ ሲሆን ሌሎችም ስለይሖዋ ምስክሮች አነሳስ የበለጠ ግንዛቤ እንዲያገኙ በማለት እንዲያነቡ ወይም ዳውንሎድ እንዲያደርጉ አቅርበነዋል።በቀኝ ጠርዝ ያለውን ምልክት ተጭነው ገጹን ማስፋት ይችላሉ።

Monday, March 4, 2013

«ያዘዝሁህንም ቃል ኪዳኔንና ሥርዓቴን አልጠበቅህምና መንግሥትህን ከአንተ ቀዳድጄ ለባሪያህ እሰጠዋለሁ»

ከኒቆዲሞስ

 የተወደዳችሁ ደጀብርሃኖች እንደስማችሁ ብርሃንናሰላም ሊያመጣ የሚችል ጽሑፍ እያወጣችሁ እያስነበባችሁንና እንድንረዳላችሁ እየሞከራችሁ ነውና እግዚአብሔር ይስጥልን::በተቻለ መጠን በተለይ በተከፋፈልችው ቤ/ክርስቲያናችን ውስጥ ሰላም እንዲሆን የምትጽፉት ጽሑፍና ጥረታችሁ ያስመሰግናችኋል::ግን አንድ ነገር አስተውለን ይሆን?መለያየትና መከፋፈል መልካም ጎን የለውም እንደምንል ሁሉ መለያየት በመጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ራሱ ያደረገበትን የእስራኤል ነገድን ሕዝብ ታሪክ በማን ልናላክክ ነው?በሰይጣን ወይስ በሰው?ታውቃላችሁ በ1ኛ ነገሥት ምዕራፍ 11:9-13 እና 29-40 ድረስ ያለውን ስናነብ የምናየው የማንን ሥራ ነው?ታዲያ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክ ብትከፋፈል ምን ያስደንቃል?እኔ ፈራጅ ባልሆንና ባልናገር እውነቱንና ሐቁን ግን ለማሳየት እሞክራለሁ!!
 ( ቀሪውን ጽሁፍ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ )

ጥንቆላ - በሀገራችን ፣ በቤተ ክርስቲያናቸን እንዲሁም በእያንዳንዳችን ላይ ሊኖረው የሚችለው ተጽዕኖ


ክፍል ሁለት         (www.abaselama.org)


ባለፈው ጽሑፌ ጥንቆላ ምን እንደሆነ ጥቂት ለማሳየት ሞክሬያለሁ፤ በሰፊው ግን አልገለጥሁትም። የሰይጣንን ክፋት በሰፊው ከመግለጥ የእግዚአብሔርን ደግነት አጉልቶ መግለጥ ይሻላል የሚል እምነት ስላለኝ ነው። ነገር ግን ወገኖቼ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ጥንቆላን እንደቀላል ልማድ በማየት በጨለማው ገዢ ሥር ሲወድቁ እያየሁ ስለማዝን እውነታውን ለማሳየት ምክሬያለሁ። ዛሬ ደግሞ አንዳድ መናፍስት ጠሪዎችና ደጋሚዎች የሚያጠምቁበትን ዘዴ ከአንድ ደብተራ ጓደኛዬ ያገኘሁትን ምስጢር በጥቂቱ መግለጥ እሞክራለሁ።


አስማቱ በመስቀል፤ በጣት ቀለበት እና በመቁጠሪያ ሊሠራ ይችላል። በመስቀል ቅርጽ እንዲሁም በመቁጠሪያነት ለድግምቱ የሚያገለግሉ እጸዋት ሁለት ናቸው። አንደኛው አርግፍ የሚባል ሲሆን ሁለተኛው ጠንበለል ይባላል። እጸዋቱ በደጋማ ሥፍራዎች ይገኛሉ። በትክል ድንጋይና በሰከላ በብዛት ይገኛሉ። የአስማቱ ባለሙያዎችም ከላይ በጠቅስሁአቸው ቦታዎች አሉ። በተለይ አርግፍ የሚባለውን እንጨት በአካባቢው ያሉ ገበሬዎች እየጠረቡ ለሕጻናት ከሰይጣን እና ከቡዳ ይጠብቃል እያሉ ባንገታቸው ያደርጉላቸዋል።

 ይህ እንጨት የማይሰራበት አስማት የለም ይባላል፤ ሰዎችን ለክፉዎች አሳልፌ እንዳልሰጥ ሁሉን ከመግለጥ እቆጠባለሁ። ለማጥመቅ ሲጠቀሙበት ግን የሚያደርጉትን መናገር ግድ ሆኖብኛል። እንጨቱን ሲቆርጡት የሚደግሙት አላቸው። ሰባት ቀን ሲደግሙ ቆይተው የዶሮ ወይም የሰው ደም ቀብተው ይቆርጡታል። ቅጠሉን በአዲስ ሸክላ[ውሃ ወይም እህል ያልነካው] ዘፍዝፈው አርባ ቀን ከደገሙበት በኋላ ዋናው ለማጥመቅ የተዋረሰው ግለሰብ ይጠመቅበታል። አጥማቂው አርባ ቀን በተደገመበት ውሃ ሲጠመቅ መናፍስት ያለ ከልካይ በብዛት እንደሚያድሩበት ይነገራል።

Saturday, February 23, 2013

አማኝ እንጂ አክራሪ አትሁን!


አማኝ ያመነውን የሚኖር በፍቅርም የሚማርክ ጀግና ነው። አክራሪ ግን ጥቂት እውቀቱን ከዱላ ጋር ለማስከበር የሚሞክር ነው። የከረረ ነገር መበጠሱ አይቀርም። የከረረ ነገር ሲከርም ሲበጠስም ስጋት ነው። አክራሪነት የአለሙ ልከኛ ሰው እኔ ነኝ። ከኔ በቀር በአለም ላይ ማንም መኖር የለበትም። ከምስራቅ ስገላበጥ ምእራብ እደርሳለሁ። ከሰሜን ስራመድ ባንድ ስንዝር ደቡብን እረግጣለሁ። ስለዚህ ከኔ ውጪ ማንም መኖር የለበትም ብሎ እንደማሰብ ነው። የአክራሪነት ምንጩ አለማወቅ ነው። አክራሪ ሰው በከሳሽነት መንፈስ የተያዘ እንጂ የሚያሳየው ማራኪ ስራ የሌለው ነው። ጥቂት እውቀቱ ከሰፋች የካደ ስለሚመስለው ላለማወቅ ተጠንቅቆ የሚጓዝ ነው። እርሱ ካለበት ገድጓድ ውጪ አለም ያለ የማይመስለው ። የለመድኩት ሰይጣን ይሻላል ብሎ ከመቃብር ጋር በኪዳን የሚኖር ተስፋ የሌለው ሳይሞት መኖር ያቆመ ሳይቀበር እውቀቱን የጨረሰ ሰው ነው። የአክራሪነት ወንድሙ አለማወቅ ነው።

Friday, February 22, 2013

«የቀረውንም ነገር ሳልቆጥር፥ ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው» ፪ኛ ቆሮ ፲፩፤፳፰


 በዘመኑ የግንኙነት መሣሪያ በሆነው መረጃ መረብ ላይ ተቀምጠን ከውድ ጊዜያችን ላይ ቀንሰን የምናካፍለውን መልእክት አንዳንዶች እነሱን ደስ በሚያሰኝ መንገድ እንድናስተላልፍ  ይፈልጋሉ። ገሚሶቹ ደግሞ የሆነ ስውር ዓላማ አንግበን የተሰለፍን  አስመስለው ይስሉናል። አንዳንዶቹም በእግዚአብሔር መንግሥትና አሁን ባለው ምድራዊው የቤተክህነት አስተዳደር መካከል ያለውን ልዩነት በደንብ ያልተረዳን አድርገውም ይገምታሉ። በተለይም የሰሞኑን የፓትርያርክ ምርጫን በተመለከተ የምናወጣቸውን ዘገባዎች የሚያስከፋቸው ሰዎች እንዳሉ ለማወቅ ችለናል። በዚህም ይሁን በዚያ የእግዚአብሔር እቅድና ዓላማ እንዳይሆን የሚከለክል ምንም ኃይል እንደሌለ እያመንን የእኛ ዓላማና ፍላጎትም ምን ጊዜ እግዚአብሔርን የሚያስደስት ሥራና ዘመን  እንዲመጣ ከመፈለግ የመነጨ ትግል ለማድረግ ብቻ እንደተሰለፍን ለሚጠሉንም ሆነ ለሚወዱን ማሳወቅ እንፈልጋለን።
ይህንንም አቋማችን ከሐዋርያው ጳውሎስ ቃል ተውሰን በአጭር ቃል ስናስቀምጠው ««የቀረውንም ነገር ሳልቆጥር፥ ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው» ፪ኛ ቆሮ ፲፩፤፳፰ እንዳለው የቤተ ክርስቲያናችን ነገር ብቻ ያሳስበናል።
አንዳንዶችን ቅር የሚያሰኝ፤ ሌሎችን ደግሞ የሚያሳዝን፤ ለገሚሱም ደስታን የሚሰጥ መረጃ ስናወጣ በእኛ በኩል ያለው ስሌት ግን አንድ ሃሳብ ብቻ ነው፤ እሱም የእግዚአብሔር መንግሥት እንዳይስፋፋ መንገድ ላይ ያሉ ጋሬጣዎችን እየነቀስን በማሳየት ሰው በመረጃና በእውቀት እውነቱን እንዲረዳ ማድረግ ነው።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከዓለም ቀደምት ቤተክርስቲያን ተርታ የምትመደብ ቤተክርስቲያን ናት። በእውቀት የበለጸገች፤ በአስተምህሮ የዳበረች፤ በትውፊትና በታሪክ ከፍተኛ ስፍራ የያዘች መሆኗም ለማንም የሚሰወር አይደለም።  ይሁን እንጂ እንደቀደምትነቷ ወደኋላ እየሄደች፤ በአስተምህሮዋ እየደከመች፤ በአስተዳደሯ እየወደቀች፤ በትውፊቷ እየኮሰመነች፤ በታሪኳ እየተሸፈነች መሄዷ በገሃድ የሚታይ እውነት መሆኑንም መካድ አይቻልም።
በቁጥር 75 የእስልምና ሰዎች መካና መዲናን ለቀው ወደኢትዮጵያ ሲሰደዱ ክርስትና የኢትዮጵያ መንግሥታዊ ሃይማኖት ነበር። መንግሥቱንም፤ ጉልቱንም፤ሕዝቡንም ትቆጣጠር የነበረችው ቤተ ክርስቲያን ከኋላዋ የመጣው እስልምና አንድም የዐረብ ተወላጅ ሳይኖረው የሸሪአ መንግሥት ለማቋቋም የሚያስችል ኃይል አለኝ እስከማለት የደረሰው የቤተ ክርስቲያኒቱ እድገት እንደመሠረቱ ከፍ እያለ መጓዙን ሳይሆን እያቆሽቆለቆለ  የመሄዱ አንዱ ማሳያ ነው ብሎ መጥቀስ ይቻላል። እንደዚሁ ሁሉ ከ16ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ብቅ ጥልቅ ይል የነበረው የአውሮፓውያን የወንጌል ሰዎች እንቅስቃሴ በስውር የነበረው ስርጭት ዛሬ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አባላትን ማፍራት የቻለው ይህችው ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን ቤተ መንግሥቱን፤ ቤተ ክህነቱንና ሕዝቡን እስከጉልተ ርስቱ  የመቆጣጠር አቅም እያላት መሆኑን አይተን ዛሬ ላይ የደረሰችበትን ደረጃ ስንመረምር ሽቅብ ሳይሆን እያቆለቆለች መጓዟን ቢመረንም የሚታየውን እውነታ መቀበል የግድ ይለናል።
በተለይም ቤተ ክርስቲያኗ የነበራትን የክብር ሥፍራና መንፈሳዊ ኃይል ቀስ በቀስ እያጣች በዝናና በስም ብቻ ወደመኖር የደረሰችው ዘርዓ ያእቆብ የተባለውን ሰው ንጉሥ አድርጋ ከተቀበለች ወዲህ ባሉ ዘመናት ውስጥ ስለመሆኑ፤ እውነት በሀሰት ሰርዶ ተሸፍኖ የሌለ ታሪክ እውነት እንዲመስል ከተደረገበት ጊዜ አንስቶ እንደሆነ ታሪክ አፍ አውጥቶ እየተናገረ ይገኛል።  ዛሬ ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ  በአንድ በኩል  ከቅዱሳኖቿ እንደ አንዱ አድርጋ የምትቆጥረው ፤ በሌላ መልኩም በተደለዘው ገድሏ ከሰውነት ተርታ አውጥታ ከውሾች መድባ የምትረግመው ሰማእቱ አባ እስጢፋኖስንና ደቀ መዛሙርቱን እያሳደደች ለ100 ዓመት ባሳረፈችባቸው ሰይፍ የፈሰሰው ደም በዐውደ ምሕረቷ ላይ እየጮኸ እነሆ የሰማይ ክሳት ተለቆባት እየከሳችና እየደከመች በመሄድ ላይ ትገኛለች። የግራኝ ወረራ፤ የድርቡሽ፤ የግብጽ፤ የቱርክ፤ የጣልያን ሰይፍ የወረደው ሳያንስ እርስ በእርስ ስንበላላ ኖረናል።

Thursday, February 7, 2013

ጥቃቅን ሹመኞችና የገደል ቅራፊ ሚያካክሉ መዘዞቻቸው

በዳዊት ወርቁ

pomjos@yahoo.com


ቱኒዚያዊው የሃያ ስድስት ዓመቱ ወጣት ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ ጋሪ እየገፋ ፍራፍሬና አትክልት በመሸጥ ኑሮውን የሚገፋ የጎዳና ላይ ለፍቶ አዳሪ  ነበር፡፡  በሚያገኛት ጥቂት ፈረንካም የራሱንና የስምንት ቤተሰቡን ነፍስ ይቀልብ ነበር፡፡  ፋይዳ ሃምዲ የተባለች ፖሊስ፣ ዘጠኝ ራሱን መደጎሚያ ጋሪውንና ፍራፍሬውን በግፍ እስክትነጥቀው ድረስም፣ ለሰባት ዓመታት ያህል በደቡብ ቱኒዚያ 300 ኪሎሜትር ያህል ከምትርቀውና ሲዲ ቡዚድ ከምትባለው የትውልድ ስፍራው እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጥሮ፣ ማስኗል፣ ተንከራቷል፣ በእሰራለሁ አትሰራም እንካ ሰላንቲያም ከጥቃቅን ሹመኞችጋ እሰጥ አገባ ገብቷል፡፡ በመጨረሻም ውድ ህይወቱን ከፍሏል፡፡

እንዲህ አይነት ተደጋጋሚ ሁኔታ ብዙ ጊዜያት አጋጥሞት የነበረው ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ በቀን ያገኝ የነበረውን 10 ዲናር፣ (በኢትዮጵያ 126 ብር ያህል) ንብረቱን ትመልስለት ዘንድ እንደ እጅ መንሻ አድርጎ የዕለት ጉርሱን ለነጠቀችበት ፖሊስ ፋይዳ ሃምዲ አቅርቦ ነበር፡፡ ነገር ግን፣  የፋይዳ ሃምዲ ምላሽ በህይወት የሌሉትን አባቱን መስደብና የሙሐመድ ቡዓዚዝን ጉንጭ በጥፊ ማጮል ነበረ፡፡ በድርጊቱ ከፍተኛ ውረድት የደረሰበት ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ የደረሰበትን በደል አቤት ለማለት ወደ በላይ አካላት ቢያቀናም፣ የበላይ አካላት ተብዬዎቹ ከእጅ አይሻል ዶማ በመሆናቸው አቤቱታው የውሃ ሽታ ሆነ፡፡

ዘጠኝ ራሱን የሚያኖርበትን ጋሪና አትክልት በግፍ ከተነጠቀ አንድ ሰዓት በኋላም፣ ሙሐመድ ቡዓዚዝ፣ ምን ሊያደርግ እንዳሰበ ለቤተሰቦቹ እንኳ ትንፍሽ ሳይል፣ ልክ ከቀኑ 530 ሲሆን ንብረቱን ወደ ተነጠቀበት አደባባይ በማምራት በገዛ ሰውነቱ ላይ ቤንዝን ካርከፈከፈ በኋላ፣ ከአስተዳደሩ ያጣውን ፍትህ የገዛ ነፍሱን በማጣት ‹‹አግኝቷል››

ለሰላማዊው ለፍቶ አዳሪ ሙሐመድ ቡዓዚዝ ሰላማዊ ጥያቄ፣ ፖሊስ የሰጠው ኢ-ምግባራዊ ምላሽና የባለሥልጣናት ቸልተኝነት ያስከተለው ውጤትም፣ ጅማሬውን በሲኢዲ ቡዚድ ያደረገና በኋላም ቀስበቀስ መላውን ቱኒዚያና ከፊል የዓረብ አገራትን ያካለለ ሕዝባዊ አመጽ ነበር፡፡ አመጹ ሥር ሰዶም፣ በተለይም ፌስቡክና ዩቲዩብን በመሳሰሉ ድረገጾች የሱቅ መስኮቶችን በሰባበሩና መኪኖችን ባወደሙ ወጣቶች ላይ ፖሊስ የወሰደውን ኢሰብአዊ ርምጃዎች የሚያሳዩ ምስሎች እንደሰደድ እሳት ተስፋፉ፡፡


የማታ ማታም፣ የሙሐመድ ቡዓዚዝን ነፍስ ለማዳን  በዋና ከተማዋ ቱኒዝ አቅራቢያ በሚገኝ ሆስፒታል ርብርብ ቢደረግም፣ ክፉኛ በመጎዳቱ፣ ታሪቅ ጣይብ ሙሐመድ ቡዓዚዝ ጃንዋሪ 4 2010 (ታህሳስ 26፣ 2002 ዓ.ም.) በተወለደ 26 ዓመቱ፣ እስከመጨረሻው አንቀላፍቷል፡፡

ከህልፈቱ በኋላም የዓረቡ ዓለም ታሪክ ይለወጥ ዘንድ ታላቅ ድርሻ ላበረከቱ ሌሎች አራት ሰዎችን ጨምሮ፣ የሻክሃሮቭን ሽልማት ተሸልሟል፡፡ የቱኒዚያ መንግሥትም ምስሉን በአገሪቱ ቴምብር ላይ በማስፈር ክብር ሲያጎናጽፈው የእንግሊዙ ታይም መጽሔት 2011 የዓመቱ ምርጥ ሰው ብሎታል፡፡

ከጥቃቅን ሹመኞች ዕይታ ውስጥ ያልገባውም የሙሐመድ ቡዓዚዝ ጉዳይም፣ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ዚን ኢል አቢድን ቤን አሊ በትረ መንግሥታቸውን እስከማጣት ድረስ የከበደ፣ ትልቅ ዋጋ እንዲከፍሉ አድርጓቸዋል፡፡

ዛሬ ለማነሳው ነጥብ ይመቸኝ ዘንድ እንደ አብነት የሙሐመድ ቡዓዚዝን ቅንጭብ ታሪክ አነሳሁ እንጂ፣ በዓለማችን፣ በተለይም በአህጉራችን አፍሪቃ፣ ደግሞም በእኛ ኢትዮጵያ በየዘመናቱ የሚፈጠሩትን፣ ሙሐመድ ቡዓዚዚዎችና ፋይዳ ሃምዲን መሰል ተበዳዮችንና በዳዮችን  ዘመንና ታሪክ ሲቆጥሯቸውና ሲያስታውሷቸው ይኖራሉ፡፡

ታዝባችኋል፣ አንዲት እናት በድንገት ምጥ ይዟት፣ አሊያም የሆነ ላገር የሚጠቅም፣ ገና ሮጦ ያልጠገበ ጎረምሳ፣ አንዳች አደጋ ነገር ደርሶበት ወደ አንድ ክሊኒክ አሊያም ሆስፒታል በህክምና ህይወታቸውን ለማትረፍ ሄደው፣ በጊዜው ተረኛው ሐኪም ባለመኖሩ ምክንያት እናቲቱ ምጡ ጠንቶባት፣ ጎረምሳውም ደሙ ፈሶ ለሞት ከተዳረጉ በኋላ፣ ዜጎች፣ ‹‹ አዬ እኛ አገርማ ምን መንግሥት አለ!!›› እያሉ እንባቸውን ወደላይ ሲረጩ? . . .

ታዝባችኋል፣ ዜጎች ለዘመናት ነጭ ላባቸውን አንጠፍጥፈው የሰሩትን ገንዘብ በማጅራት መቺዎች ከተዘረፉ በኋላ፣ ‹‹በገዛ አገራችንኮ ሠርተን መኖር አልቻልንም፣ ንብረታችን የቀማኞች ሲሳይ እየሆነ ለህይወታችን እንኳ እየሰጋን ነው፣ ታዲያ እንዴት ነው የሚቀርጠን መንግሥት ህይወታችን ከተራ የመንደር ሌቦችና ዘራፊዎች ሊታደገን የሚችለው›› ሲሉ? . . .

ታዝባችኋል፣ የሆነ መንደር መብራት ወይም ውኃ በተደጋጋሚ እየተቋረጠ፣ ዜጎች ‹‹አዬ የኛ መንግሥት፣ በጨለማ ስንዋጥና፣ ውኃ ስንጠማ እንኳ የማያውቅ ከንቱ መንግሥት›› ሲሉ ሲንገፈገፉ፣ ሲማረሩ፣ ሲያለቅሱ? . . . (በነገራችን ላይ የሆነ ቦታ በተደጋጋሚ እንዲህ አይነት ሁኔታ ሲከሰት የሌላ ቀበሌ ሰዎች እንዴት ነው እሱ፣ እናንተ ቀበሌ አንድ የዘመኑ ሰው የለም እንዴ . . . ብለው እርስ በርስ ይጠያየቃሉ፣ ምክንያቱም የዘመኑ ሰው ያለበት መንደር ውሃም ሆነ መብራት ተቋርጦ ስለማይሰነብት )

በሐሰተኛ ሰነድ፣ በተጭበረበረ ማስረጃ፣ በገንዘብና ስጦታ በጉቦኛ የፍትህ አካላት ፍትህ ተጣሞባቸው፣ አቤት የሚሉበት አጥተው በራቸውን ዘግተው ስለሚያነቡ ወገኖችስ ምን ያህል ታዝባችኋል?   . . .

ውበቷን በልባቸው ከቋመጡና ተክለሰውነቷን ባይናቸው ከቀላወጡ በኋላ አልጋ ላይ እንዴት ልትሆን እንደምትችል እያሰላሰሉ፣ ብዙ የውኃ ጋሎን የያዘ የእሳት አደጋ መኪና እንኳ ሊያጠፋው የማይችል የወሲብ እሳት አይኖቻቸው ውስጥ እየተንቀለቀለ፣ ያቀረቡላትን የወሲብ ግብዣ አልቀበልም ስላለቻቸው ብቻ ‹‹ቀልቤ አልወደዳትም›› ወይም ‹‹ለስራው የሚሆን የተሟላ መረጃ አላቀረበችም›› አሊያም ‹‹ቆንጆ ሴት ሥራ አይሆንላትም›› በሚል እንቶፈንቶ ምክንያት ብቻ ለሥራ ያስገባችውን ሲቪ የቅርጫት እራት ስለሚያደርጉ ሹመኘኞችስ? . . .  እኔ ለጊዜው የመጣልኝን አልኩ እንጂ ይኼን ጊዜኮ እናንተ የታዘባችሁት በርካታ ከዚህ የከፉ ጉዳዮች አእምሯችሁን አጣበዋል፡፡

አገራችን በየዘመናቱ በእንደዚህ አይነት ጥቃቅንና አነስተኛ የየዘመኑ ሹመኞች ሰለባ ናት፡፡ ታዲያ ብዙ ጊዜ በነዚህ ሰዎች ምክንያት  ትልቁ መንግሥት በዜጎቹ ይሰደባል፣ ይብጠለጠላል፣ ይታማል፣ ይጠላል፣ ሲያልፍም አመጽ፣ ኩዴታና አብዮት ይነሳበታል፡፡