Showing posts with label ትምህርት. Show all posts
Showing posts with label ትምህርት. Show all posts

Saturday, April 20, 2024

ጸጋ ምንድነው? (What is grace?)

ጸጋ ምንድነው? (What is grace?) ክፍል ዐራት በባለፉት ክፍሎች የተመለከትነው በኢየሱስ አምነን ለዳንን ሰዎች ሁሉ የጸጋ ኃይል የሚያስፈልገን ለምንድነው? ለሚለው ጥያቄ ሦስት የኃጢአት በሮችን ለመዝጋት ነው በሚለው ሃሳብ ዙሪያ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማብራሪያ ስንሰጥ መቆየታችን ይታወሳል። በዚሁ መሠረት ከሦስቱ የኃጢአት በሮች መካከል 1/ሥጋ 2/ ዓለም እንዴት ሊፈትኑን እንደሚችሉና ከሁለቱም የሚመጡ ፈተናዎች እንዴት መዋጋት እንደሚገባን ተመልክተናል። ሥጋ ማለት የተሸከምነውና የራሱ መሻት ያለው በነፍስ ሕያውነት የሚንቀሳቀስ አካላችን ሲሆን ይህም የሚኖረው በዚህች ምድር ላይ እንደመሆኑ መጠን ዓለም ሥጋን በባርነት እንዳትገዛ በሚዛን ለመኖር የሚያስችለን ጸጋ የሚባል ጉልበት እንደሚያስፈልገን አይተናል። ዛሬ ደግሞ ሦስተኛው ክፍል የሆነውንና የክፋት ሁሉ የኃጢአት ሹም ስለሆነው ስለወደቀው መልአክ እንመለከታለን። ይህ ፍጥረት በትዕቢት፣ በተንኮልና በክፋት የተካነ ነው። ረጅም እድሜና ብዙ ልምድ ያለው የሰው ልጆች ሁሉ ጠላት ነው። የዚህ ዓለም ገዢ የተባለውም ዓለሙን ሁሉ በዐመፃና በኃጢአት ስለያዘው ነው። “ከእግዚአብሔር እንደ ሆንን ዓለምም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን።”1ኛ ዮሐ 5፥19 ይህ ጥንተ ጠላታችን ወደጥልቁ ወርዶ ለዘለዓለም እስኪታሰር ድረስ ለሰው ልጆች ምንም ዓይነት ርኅራኄ የለውም። ራእይ 20:10 የወደቀው መልአክ እብሪትና ትዕቢትን ሞሪስ የተባለ የነገረ መጻሕፍት ተርጓሚ “ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፥ በልዑልም እመሰላለሁ አልህ።” ኢሳ 14፥14 ያለውን ቃል ሲተረጉም የወደቀው መልአክ ምኞቱ የመላእክት ሁሉ አለቃ መሆን ብቻ ሳይሆን አምላካዊ ሥፍራንም መፈለጉን ያሳያል ሲል ይፈታዋል። የትኛውም ምኞትና አደገኛ የአምልኮ መሻት ሁሉ ምንጩ የዚህ የወደቀው መልአክ ውጤት ነው። የናቡከደነጾር የዱራ ሜዳ ሐውልት (ዳን3:1) የምናሴ የማመለኪያ አፀድ (2ኛ መዋዕል 33)፣ ዳጎን (መሣ16:23)፣ ቤል (ኤር 50:2) ወዘተ ሁሉም የወደቀው መልአክ ሥራዎች ናቸው። ይህንንም መዝሙረኛው እንዲህ ይላል። “የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸውና፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።” መዝ 96፥5 ይህ የወደቀው መልአክ ለራሱ ብቻውን ወድቆ አልቀረም፣ የመጀመሪያዎቹንም የሰው ልጆች ጣለ እንጂ። የሚገርመው ነገር ሰዎቹ ሳይጠይቁት ራሱ ሰላማዊ ጠያቂ ሆኖ ነው የቀረበው። ከጠያቂነቱ ባሻገር እንዳይበሉ የተከለከሉት ተክል ስለመኖሩ እያወቀ፣ እንደማያውቅ ፍጥረት ሆኖ ነበር የቀረባቸው። "...ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት።”ዘፍ 3፥1 ስለመከልከላቸው እውቀቱ ከሌለው ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? ብሎ ባልጠየቀም ነበር። በሚመልሱት መልስ ለማጥመድ ነው። ይህንን በቃል የማጥመድ ተንኮል በኢየሱስ ላይም ሞክሮት ነበር። “በሕዝቡም ፊት በቃሉ ሊያጠምዱት አልቻሉም በመልሱም እየተደነቁ ዝም አሉ።”ሉቃ 20፥26 ሔዋን እንዳትበሉ አዝዞአልን? ብሎ ለጠየቃት የማጥመጃ ቃል የሰጠችው መልስ እንዲህ የሚል ነበር። (ዘፍጥረት 3:2—3) ሴቲቱም ለእባቡ አለችው፦ በገነት ካለው ከዛፍ ፍሬ እንበላለን፤ ነገር ግን በገነት መካከል ካለው ከዛፉ ፍሬ፥ እግዚአብሔር አለ፦ እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም። ሔዋን ሞትን ሞታ ስለማታውቅ ይሄ ጠላት በገዛ ቃሏ ምን እንደሚመስል ሊያሳያት ነው። (ዘፍጥረት 3፣3—4) እባብም ለሴቲቱ አላት፦ ሞትን አትሞቱም፤ ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ። ይህ ጠላት ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ይልቅ የሱ ድምፅ የተሻለ ፍቺና ምስጢር እንዳለው እየተናገረ ሰዎቹን ወደቤተ ሙከራ እየወሰዳቸው እንዳለ እናያለን። በሚያምረውና በሚያስጎመጀው የጠላት ቤተ ሙከራ የገቡት እንግዶች አብሯቸው የነበረው ፍሬ የተለየ ውበት እንዳለው ያንጊዜ እንደአዲስ የተገለፀላቸው ይመስል ነበር። “ሴቲቱም ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደ ሆነ፥ ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ፥ ለጥበብም መልካም እንደ ሆነ አየች፤ ከፍሬውም ወሰደችና በላች፤ ለባልዋም ደግሞ ሰጠችው እርሱም ከእርስዋ ጋር በላ።” ዘፍ 3፥6 የወደቀው ጠላት አዲሶቹንም ፍጥረቶች ይዞ ወደምድር ተፈጠፈጠ። ይሄንን ሀተታ እዚህ ላይ ማንሳት ያስፈለገው ለመጽሐፍ ቅዱስ አንባቢያን ያልተነበበ ታሪክ ለመንገር ሳይሆን ይሄ ረጅም እድሜ፣ ልምድና ሁሉንም ክፋት የያዘ ፍጡር ዛሬም እየሰራ ያለ መሆኑን ለማስገንዘብ ነው። ዛሬም ያማልላል፣ ያስጎመጃል፣ ያስመኛል፣ ያስፈፅማል፣ ያጋድላል፣ ያፋጃል፣ ሁሉንም ክፋት በሰው ልጆች መሀል ያስፈፅማል። ስለዚህ ይሄንን ባለብዙ ልምድ ጠላት ለመዋጋት "ጸጋ" የተባለ መመከቻ የእምነት ጋሻ የግድ ልንታጠቅ ይገባል። ያለበለዚያ የመጫወቻው ሜዳ ከመሆን ልታመልጥ አትችልም። ይህ ጸጋ እንዴት እንደሚሰራ የጳውሎስ ተማሪ የነበረው ቲቶ በመልእክቱ እንዲህ እያለ ይነግረናል። “ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤” ቲቶ 2፥12-13 ጸጋ በክርስቶስ ኢየሱስ አምነው የዳኑ ሰዎች የክርስቶስን መገለጥ እየጠበቁ፣ ራሳቸውን እየገዙ፣ በጽድቅና በቅድስና እየኖሩ ዘመኑን የሚሻገሩበት ሰማያዊ መሣሪያ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ በጻፋቸው መልእክታት በሙሉ የመዝጊያ ቃል አድርጎ ከሚጠቅሳቸው የጸሎት መደምዲያው ክፍል "ጸጋ" ከእናንተ ጋር ይሁን እያለ ይለምን የነበረው አለምክንያት አልነበረም። ሦስቱን የኃጢአት በሮች መዝጋት የሚቻለው ከእግዚአብሔር በሚሰጠን ጸጋ ብቻ ነው። ይህ ጸጋ እንዴት እንደሚገለጥና እንደሚሰራ እግዚአብሔር ቢፈቅድና ብንኖር በቀጣይ ፅሑፋችን ለማየት እንሞክራለን።

Saturday, September 17, 2016

ለምናምንቴ እረኛ ወየውለት!

ሕዝቅኤል 34
"የሰው ልጅ ሆይ፥ ትንቢት ተናገር፥ በእስራኤል እረኞች ላይ ትንቢት ተናገር፥ እረኞችንም እንዲህ በላቸው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ራሳቸውን ለሚያሰማሩ ለእስራኤል እረኞች ወዮላቸው! እረኞች በጎችን ያሰማሩ ዘንድ አይገባቸውምን? ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።እረኛንም በማጣት ተበተኑ፥ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፥ ተበተኑም። በጎቼ በተራሮች ሁሉና በረዘሙ ኮረብቶች ሁሉ ላይ ተቅበዝብዘዋል፥ በጎቼም በምድር ፊት ሁሉ ላይ ተበትነዋል፤ የሚሻም የሚፈልግም አልነበረም። ስለዚህ፥ እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝና እረኛ ስለሌለ እረኞቼም በጎቼን ስላልፈለጉ እረኞችም ራሳቸውን እንጂ በጎቼን ስላላሰማሩ፥ በጎቼ ንጥቂያ ሆነዋልና፥ በጎቼም ለምድር አራዊት ሁሉ መብል ሆነዋልና"



Saturday, August 27, 2016

ሴቶች ሁልጊዜ ልብ በሉ!



ሴቶች ከወንድ ጓደኛ ማንን ትወዱ? ማንንስ ትመርጡ? ከማንስ ጋር ጋብቻን ትፈፅሙ? እስኪ ራሳችሁን ጠይቁ።
በራስ መተማመን ያላት ሴት ለችግሮች ራሷን አሳልፋ አትሰጥም። በሁኔታዎች መለዋወጥ አትሸበርም። ራሷን ላጋጠማት ተግዳሮት ታዘጋጃለች እንጂ በሽንፈት ለቅሶን አታስተናግድም። ታዲያ ይህንን ኃይል ከየት ማግኘት ትችላለች?
               ✔ ✔✔
መልካም ክርስቲያናዊ ቤተሰብ ውስጥ ያደገች ሴት ስነምግባርን፣ እውቀትን፣ ችሎታና በራስ መተማመንን የምታዳብረው በቅርቧ ባለው ከቤተሰቧ ነው። በአስተዳደግና በልጅነት ሕይወት ጉድለት የደረሰባት፣ በብዙ ችግሮችና መከራ ውስጥ ያለፈች ሴት በስነልቦናዋ ላይ በሚደርሰው ጉዳት በራስ መተማመኗን በማጣት ችሎታዋን ለማውጣትና ችግሮችን ለመጋፈጥ ያላትን አቅም አውጥታ ለመጠቀም ሊያዳግታት ይችላል።

 በተለይም በአስገድዶ መደፈር፣ በእናት ወይም በአባት ብቻ ወይም ከሁለቱም አሳዳጊ ውጪ ያደገች፣ የኑሮ ጫናና ድህነት፣ አካባቢያዊና ሀገራዊ ችግሮች ( ጦርነት፣ ረሃብ፣ ስደት) በሴቷ ስነልቦና ላይ የሚያደርሱት ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በቃላትም መግለፅ ከሚቻለው በላይ የስነልቡና ተጠቂ ልትሆን ትችላለች።
 በዚህም የተነሳ ሴቶች ለአካለ መጠን ከደረሱ በኋላ ቤተሰባዊ ሕይወትን ለመመስረት በሚያስችላቸው ሁኔታ ላይ ያሳለፉት ቁስል የሚያደርስባቸው የአእምሮ ፈተናና ትግል እጅግ ውስብስብ ነው።
የመጠራጠር፣ ያለማመን፣ አንዳንዴም በቀላሉ የመታለል ወይም የመሸወድ ክስተት ሲያጋጥማቸው ያታያል። ሴቶች በፈገግታና በሳቅ ሸፍነው በማህበራዊ ኑሮው ቶሎ የመቀላቀል ተፈጥሮአዊ ችሮታ አላቸው እንጂ በኋላቸው የተሸከሙት ህመም በጣም ብዙ ነው። ሲስቁና ሲጫወቱ ዘመናቸውን ሁሉ እድለኞች የነበሩ ሊመስለን ይችላል። እውነቱ ግን እሱ አይደሉም። ሴቶች መከራቸውን እንደወንድ እያመነዠኩ ስለማይኖሩ ከሰው ለመቀላቀል ብዙም አይቸገሩም። ያ ደግሞ ሴትን ልዩ ፍጥረትና የተወደደች ያደርጋታል። ሴት ለወንድ ሚስት ብቻ ሳትሆን የጉድለቱ ሙላት የመሆኗም ምስጢር ሁሉን መከራ መሸከም መቻሏ ነው። 6 ልጆቿን ያለአባት አሳድጋ ለቁምነገር ያበቃች እናት አውቃለሁ።
                ✔✔✔
ክርስቲያን ሴቶች ምንም እንኳን ያለፈ ሕይወታቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ባለ አዲስ የእምነት ልምምድ የተለወጠ ቢሆንም ያሳለፉት ስነልቦና በቀላሉ የሚፋቅ ባለመሆኑ አልፎ አልፎ መቸገራቸው አይቀርም። ከጋብቻ በፊት የመንፈሳዊ ጋብቻ ትምህርትና የምክር አገልግሎት ማግኘት የበለጠ ተጠቃሚ ሊያደርጋቸው ስለሚችል በዚሁ መልኩ አስቀድመው ቢገለገሉ የተሻለ ግንዛቤ ይኖራቸዋል።
በኛ በኩል ያሉንን ምክሮች ጥቂት እንበል።
               ✔✔✔
ባለፈ ስህተትሽ አትቆጪ። የዛሬውን ሃሳብሽን እንዲቆጣጠረውም አትፍቀጂ። ያለፈው ላይመለስ አልፏል። ያለፈው ለዛሬው ያለው እድል አስተማሪ መሆኑ ብቻ ነው። ጎበዝ ሰው በሌላ ሰው ስህተት ይማራል፣ ሰነፍ ሰው ደግሞ ከራሱ ስህተት ይማራል። ያለፈው ስህተትሽ ለዛሬው ማንነትሽ ትምህርት ከሆነሽ፣ አንቺ የዛሬዋ ጎበዝ ነሽ። ካለፈችው ሰነፏ አንቺነትሽ በልጠሻል ማለት ነው። ስህተት አንዴ ከበዛ ደግሞ ሁለቴ ቢሆን ነው። ከደጋገመሽ ግን ስህተቱ ከጎዳሽ ነገር ሳይሆን ካንቺ አለመለወጥ የመጣ ነው።
ፈረንጆች እንዲህ የሚል አባባል አላቸው። "ስትሄድ የመታህ የድንጋይ እንቅፋት ስትመለስም ከደገመህ ስህተቱ የእንቅፋቱ ሳይሆን ድንጋዩ አንተው ነህ" ይላሉ።
ፍርሃትን በራስ መተማመን፣ ስህተትሽን በመታረም ማሸነፍ ትችያለሽ።
አብዛኛው ወንድ ሴትን የሚወደው በአይኑ ነው። የውስጧን ማንነት ሳያይ ውጫዊውን አይቶ ማድነቅም፣ መውደድም ይቻላል። ብቻውን ግን ለፍቅር ግንኙነት አያበቃም።
 የደም አይነት ልዩ ልዩ ነው። ሁሉም ደም ለሁሉም ሰው አይሆንም። በአይን የመጣ መውደድም በሁሉም ሴት ላይ ፍቅርን ሊመሰርት አይችልም። ለምርጫ የሚያበቃ ጥናት ያስፈልገዋል። የወደዱን ሁሉ ያፈቅሩናል ማለት አይደለም። ይህን ለማወቅ ጊዜ ወስዶ ማጥናት ተገቢ ነው። ለኛ የተሰጠ ሰው ከሆነ ለማጥናት በምንወስደው ጊዜ ያመልጠናል ብለን መስጋት አይገባም። እንዲያውም ሳናውቀው ዘው ከምንል ቢያመልጠን ይሻላል። ለኛ የተሰጠን እንዳይዘገይ ቶሎ መሄዱ ይሻላል። የከረመ ወይን ሲጠጡት ሆድ አይነፋም።

በአይን የወደደ የአይኑን አምሮት በአካል ባገኘው ጊዜ ቶሎ ይረካል። ከዚያም የማያርፈው አይኑ ወደሌላ ይሄዳል። ሴት ሆይ፣ የሚወድሽን ወንድ አይኑን ብቻ ሳይሆን ልቡን እዪው። ምን ይልሻል? ስሚው። አንቺን አይቶ ለልቡ አምሮት የሚቅበዘበዝ ከሆነ ችግር አለ። በአፉ እወድሻለሁ እያለ ፍቅሩን በተግባር የማያሳይ ከሆነ ችግር አለ። እንጋባ ሳይሆን እስክንጋባ አልጋ ላይ እንውጣ የሚልሽ ከሆነ ችግር አለ። የሚሰጥሽን ጊዜ ቀስ በቀስ የሚቀንስ ከሆነ ችግር አለ።
ታማኝ ወንዶችን ከአስመሳዮች ለመለየት ጊዜ ውሰጂ። አትቸኩዪ። በምላስ ብልጠት አትሸነፊ። ልቡን ለማወቅ አንቺ አምላክ አይደለሽም። ምላሱን በተግባሩ ፈትኚ። ከትዳር በፊት የተደጋገመ ውሸት በትዳር ውስጥም ይቀጥላልና ተጠንቀቂ።
በሰውኛ ሚዛን መልክና ውበት ጥሩ ነው። ነገር ግን ለእግዚአብሔር መንግስት በተመረጠ ትዳር ውስጥ ሁሉም ከንቱ ነው። ቅን እንጂ ቅንቅን አትሁኚ። ገንዘብ፣ ጌጥና ምቾት አያታልሽ። ዝሙት ኃጢአት ነው። ፍፃሜውም ሞት ነው። ስለዚህ በታማኝነት ለእግዚአብሔር መንግስት ራስሽን አስገዢ።

 ጠቢቡ በመጽሐፉ እንዳለው መክብብ 6፣12
"ሰው በከንቱ ወራቱ ቍጥርና እንደ ጥላ በሚያሳልፈው ዘመኑ በሕይወቱ ሳለ ለሰው የሚሻለውን የሚያውቅ ማነው? ወይስ ለሰው ከፀሐይ በታች ከእርሱ በኋላ የሚሆነውን ማን ይነግረዋል?" ነውና ለጊዜው ለእግዚአብሔር ክብር ለሚሆን ሕይወት እንጂ ይህ ቋሚ መኖሪያችን አይደለምና ራስን መግዛት አትርሺ።
             ✔✔✔
"ጌታ ቅርብ ነው። በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ"
ፊልጵ 4:6

Monday, July 25, 2016

የሚፈውስና የሚያሳምም ስም - ኢየሱስ!!


(ከዙፋን ዮሐንስ)
የሆነ ጊዜ ፷፬ ሰው በሚይዝ አገር አቋራጭ አውቶቡስ ተሣፍረን ወደክልል የሁለት ቀን መንገድ ተጓዝን። ቁርስ፣ ምሳ፣ አብሮ ከመብላት፣ አብሮ ከመቀመጥ፣ የተነሳ ሁሉ ዘመድ ቤተሰብ ሆነ። የሆድ የሆዱን ተጫወተ። ስልክ ተቀያየረ፣ እጮኛም ያገኘ አይጠፋም። ያልተነሳ ርእስ አልነበረም። ፖለቲካ፣ የኑሮ ውድነት፣ ስለሳይንስ፣ ሃይማኖት፣ ስለታዋቂ ደራሲያን፣ ዘፋኝ፣ ፈላስፋ፣ ስለሃይማኖት አባት፣ ብዙ ብዙ….ብቻ ያልተወራ አልነበረም። አንዳንዶቹም ወሲብ ቀስቃሽ ቀልዶችን ግጥሞችን አውርተው መኪናው ውስጥ ከጫፍ እስከጫፍ አነቃቅተዋል። የወሲብ ነገር ሲወራ ጆሮውን ቀስሮ ያዳምጣል። የሚያስቅ ከሆነ ይስቃል፣ የሚያሳፍር ከሆነም መስማት ያልፈለገ ይመስል የኮረኮሩት ያህል ግንባሩ ጥርስ በጥርስ ይሆናል። የአለቃ ገ/ሐና ነገር ሲነሳማ የአለቃን ወሲብ ወዳጅነትና ይጠቀሙ የነበረበትን የማማለል ዘዴ እያደነቀ ከልምዳቸው ብዙ የቀሰመው ነገር ያለ ይመስል ተሳፋሪው ይስቃል፣ ያውካካል።

ይህ ሁሉ ሲሆን አንድ ሰው ከዚህ ሁሉ ሳቅና ፍንደቃ ራሱን አግልሎ ከመስኮት ጥግ ተቀምጦ ያነብ ነበር። ድንገት ብድግ ብሎ “ኢየሱስ“ የሚለውን ስም አንስቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ አዳኝነቱን፣ ተስፋነቱን፣ አጽናኝነቱን መናገር ሲጀምር ብዙ ፊቶች ተቀያየሩ። አንዳንድ ፊቶች ቲማቲም መስለው ቀሉ። የባሰባቸው አንዳንዶች ደግሞ እንደበርበሬ ቀልተው የቁጣ ብናኛቸው በሰውየው ላይ በተኑ። ስለዝሙት ቀልድ ቦታ ሳይመርጡ ሲያውካኩ የነበረውን ረስተው ስለኢየሱስ ለመስማት ቦታ አጡና “ሰብከት ቦታ አለው“ አሉና ደነፉ። ጫወታችንን አታበላሽ አሉና አጉረመረሙ። ስለፌዝ፣ እርባና ስለሌለው ቀልድና ስለዝሙት ማውራት እንደጥሩ ጫወታ ተቆጥሮ ስለኢየሱስ መስማት ግን ጫወታን እንደማበላሸት ሆኖ ተቆጠረ።
እርግጥ ነው። የሥጋን ነገር መከተል ከእግዚአብሔር የመለየት ጉዳይ ስለሆነ ማበሳጨቱ የሚጠበቅ ነበር።

ሮሜ 8፣7
 “ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሔር ሕግ አይገዛምና፥ መገዛትም ተስኖታል” እንዳለው ሐዋርያው።

በየትኛውም መመዘኛ “ኢየሱስ” የሚለው ሃይለኛ ስም ሲጠራ ለመቀበል ወይም ላለመቀበል የሰዎች አስተሳሰብ ከሁለት ነገር ውጭ አይሆንም።
አንድም የኢየሱስን ጌትነትና አዳኝነት የሕይወቷ ቤዛ ላደረገችው ነፍስ ሃሴትን ያመጣልና በስሙ መጠራት ይኽች ነፍስ አታፍርም፣ አትቆጣም።
 ሁለትም የኢየሱስ አዳኝነት፣ ጌትነትና አምላክነት ብቸኛ ቤዛዋ ያላደረገችውን ነፍስ ያበሰጫታል፣ ያናድዳታል።

ምክንያቱም ፪ቆሮ ፪፣፲፮ “ለእነዚህ ለሞት የሚሆን የሞት ሽታ፣ ለእነዚያም ለሕይወት የሚሆን የሕይወት ሽታ ነን“ እንደሚል ይኽ ስም ለዘላለማዊ ሕይወት ለተመረጡት የፕሮቴስታንት ይሁኑ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ አማኞች ሕይወት፣ ሕይወት የሚሸት ሰላምና እረፍት የሚያመጣ ሲሆን ለጥፋት ለተመረጡት ግን የሚያስቆጣ፣ የሚያነጫንጭ ጥርስ የሚያፋጭ ይሆናል። ዘፈንና ቀልዱ፣ ቧልትና ፌዙ ሲነገር ሁሉ ያለምንም ልዩነት አንድ ሆነው ሲስቁና ሲፈነድቁ እንዳልነበር “ኢየሱስ” የሚለው ስም ሲጠራ የሚያበሳጭበት ምክንያት ለምንድነው? እነዚህ ጴንጤዎች ቦታ የላቸውም እንዴ ማሰኘቱስ ለምን ይሆን? የራሱ የሆነውን ኢየሱስ ያዘጋጀ ሃይማኖት የለም።

ቢያንስ አዳምጦ ከወንጌል ቃል ውጪ የሆነውንና ያልሆነውን መለየት ሲቻል መቃወም ተገቢ አይደለም። ደደግሞም ፌዝና ሥጋዊ ነገርን ከማውራት ስለኢየሱስ መስማት በብዙ መልኩ ይሻላል። ለሁሉ ስለሞተው ስለኢየሱስ መናገር የተወሰኑ ሰዎች ስጦታ ሆኖ ሲያስወቅስ፣ ስለዝሙት መናገር ግን ለሁሉ የተፈቀደ መልካም ተግባር ሆኖ የሚቆጠርበት ምክንያት መኖር አልነበረበትም። ነገር ግን ይኽ ስም ሲጠራ ያስፈራቸውና ሐዋርያቱን፣ “ጀመሩ ደግሞ እነዚህ የተረገሙ!” ያስብል እንደነበር ወንጌል ያስታውሰናል።

1. ስሙን ሲጠራ ለተቀበሉ የሕይወት ሽታ የሆነላቸው። ሐዋ ፰
 ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ፊልጶስ ስለኢየሱስ ሲሰብክለት ልቡ ደስ ተሰኘ። አጥምቀኝ አለው እንጂ “የእናትና አባት ሃይማኖቴን ተከትዬ ከኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ድረስ ያስመጣኝና ተራራ የወጣሁበትን ታላቅ የበረከት ጉዞ አድርጌ ከመመለስ ባለፈ ያንተን ኢየሱስ ለመስማት አልመጣሁም“…ብሎ አልተቆጣም።
በሉቃ ፳፯-፳ ላይም የኤማሁስ መንገደኞች ስለኢየሱስ በመጽሐፍ የተጻፈውን ሲሰሙ ልባቸው ይቃጠልባቸው ነበር። በዚያ በነበርንበት አውቶቡስ ላይ ግን ለብዙዎች ልባቸው የተቃጠለው ለምን ይኄንን ስም ትጠራላችሁ? ብለው በመናደድ ነበር።
ሐዋ ፲-፳፬ ላይ መቶአለቃ ቆርኔሌዎስም ጭራሽ ዘመዶቹንና ወዳጆቹን ጠርቶ ስለኢየሱስ ስበኩኝ ብሎአል። ስለኢየሱስ መስማት ደስ የሚያሰኝ ሆኖ ሳለ ጆሮ የሚያሳክክበት ምክንያት አይኖርም። ቢያንስ ስለአለቃ ገ/ሐና የዝሙት ጥበብና ሴቶችን እንዴት እንደሚያጠምዱ ከመስማት ይልቅ አምነው ባይቀበሉት እንኳን ስለኢየሱስ የሚነገረውን የወንጌል ቃል ማዳመጥ ለዝሙት ልብን ከማነሳሳት ከንቱ ወሬ ሳይሻል አይቀርም።
  በበዓለ ሃምሳ የተሰበሰቡት አይሁድ ስለኢየሱስ ሲወራ ልባቸው ተነክቶ ሐዋርያትን “ምን እናድርግ ?? “ብለው እርዳታ ጠየቁ እንጂ “በየመንገዱ በየአደባባዩ በየባሱ እየሰበካችሁ፣ አታስቸገሩ “ብለው በተቆርቋሪነት ሰበብ የአጋንንትን ቁጣ አልተቆጡም። እነዚህ ስሙን የሰሙና ያልተቃወሙ ሁሉ መጨረሻቸው ያመረ ክርስቲያኖች ሆነው በሰማይ የዘላለም ሕይወትን በምድርም በረከትን አግኝተው ወደጌታ ሄደዋል።

2. የሞት ሽታ የሆነባቸውና ስሙ ሲጠራ የሚያበሳጫቸው የሚያስቆጣቸው ሰዎች እንዲህ የሚሆኑት እነሱ ሳይሆኑ በውስጣቸው የተቀመጠው ክፉ የክርስቶስ ተቃዋሚ መንፈስ ነው። ይኽ ስም ሰዎችን ከሥጋዊና መንፈሳዊ ደዌ ስለሚፈታ ሰይጣን ይጠላዋል። መድኃኒትን ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ሰውነት መድኃኒት ለሞት እንደሚሆንበት ሁሉ ኢየሱስ የሚለውም ስም ለሞት ይኾንባቸዋል። ሐዋርያው ጳውሎስ ከመለወጡ በፊት የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብን አምላክ እንደሚያመልክ ስለሚያምን “ኢየሱስ” የሚባለው ስም ያበሳጨው ነበር። ይኽንን ስም የሚጠሩትን ያስርና ያስገድል ነበር። ሐዋ ፬:፲፰ “በኢየሱስ ስም ፈጽመው እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዙአቸው” “ በማለት ፈሪሳዊያን ስሙ የሞት ሽታ እንደሆነባቸው ያሳያል። “ገረፉአቸው፥ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው።“ በማለት ስሙ እንዳስገረፈ አንብበናል።

ወንድሞቼና እህቶቼ ዛሬም ይህንን ስም መጥራት ያስደነግጣል/ያስፈራል/ኤሌክትሪክ ያስጨብጣል። በስካር መንፈስ ናውዞ ውሃ መውረጃ ቱቦ ስር የሚያድረው ብረቱ፣ አንበሳው ሲባል ዘማዊውና አለሌው ቀምጫዩ እየተባለ ሲሞካሽ፣ ሌባው ቢዝነሳሙ፣ እሳቱ ሲሉት የኢየሱስ ስብከት ሲነሳ ግን ሃይማኖተኛ ሆኖ ሲያፈጥ ማየት በጣም ያሳዝናል። ጫትና ሲጋራ፣ ሀሺሽና ሺሻ የሚያናውዘው ሱሰኛው ሰው ለጥምቀትና ትንሣኤ በአጭር ታጥቆ መንገድ ከሚጠርግ፣ ቄጠማ ከሚጎዘጉዝ፣ ምንጣፍ ከሚያነጥፍ ውስጡ ተጎዝጎዞ ከተቀመጠው ክፉ መንፈስ ኢየሱስን ንጉሡ አድርጎ ቢያኖር ኖሮ ከዐመጻ ተግባራቱ ነጻ በወጣ ነበር። የሕይወቴ መሪ ነው ያለ ሰው ንሰሃ ገብቶ ኢየሱስ ሰው አደረገኝ ይላል እንጂ “ኢየሱስ” ብሎ የሚሰብክን ሰው “መግደል ነበር“ አይልም። እህቴና ወንድሜ ዛሬ ኢየሱስ አንተና አንች ጋር የሞት ሽታ ወይስ የሕይወት ሽታ ነው? ሁላችን ራሳችንን እንመርምር።
 ክብርና ምስጋና ነፍስ ሥጋና መንፈስን ነጻ ለሚያወጣው ሰው ለሚያደርገው ትልቅ ስም፣ ለኢየሱስ ክብር ይሁን! አሜን

Monday, May 23, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



(Part two) www.chorra.net
ትምህርተ ተዋሕዶ ምን ይላል?[3]
“ክርስቶስ አሁን መካከለኛ አይደለም” የሚለው ኑፋቄ ምንጩ የአውጣኪ ትምህርት መሆኑ ይታወቃል። አውጣኪ በአንዱ በክርስቶስ የቃልና ሥጋ መደባለቅ (ቱስሕት)፣ የሰውነት ወደ አምላክነት መለወጥ (ውላጤ) ወይም መለዋወጥ (ሚጠት) ተከናውኗል ብሎ የተነሣ መናፍቅ ሲሆን፣ እርሱም ትምህርቱም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተወግዘው ከተለዩ ብዙ ምእት ዓመታት ተቈጥረዋል። በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት አንጻር ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ትምህርተ ተዋሕዶን አምልተውና አስፍተው አስተምረዋል።
የተዋሕዶ ትምህርት “አንቀጸ ተዋሕዶ” እንደሚባል ሊቃውንቱ ያስረዳሉ። ተዋሕዶ ሊገኝ የቻለውም አንቀጸ ተከፍሎን መነሻ በማድረግ ነው ሲሉ ያክላሉ። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ የአንቀጸ ተከፍሎ ትምህርት የሚያመለክተው ከተዋሕዶ በፊት የነበረውን የሥግው ቃልን ባሕርያውያን ምንጮችን ነው። ይኸውም ከሁለት ባሕርያተ ልደታት፣ ማለትም ቃል እም ቅድመ ዓለም ከአብ መገኘቱን፣ ትስብእትም ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም አብራክ መገኘቱን (መከፈሉን) ነው። በጥቅሉ የሁለቱም ምንጭና ተረክቦ (መገኘት) የሚታሰበብትን ጊዜ ያሳያል። አንቀጸ ተከፍሎን ፊልክስ ሰማዕት እንደሚከተለው አብራርቷል፤ “ወካዕበ ይቤ ንጠይቅ ክፍላተ ፪ቱ ህላዌያት ወስመ ፪ቱሂ ክፉል በኵሉ ጊዜ በምግባር ወበነገር ዘውእቶሙ መለኮት ወትስብእት። ወሶበ ንቤ ከመዝ ኢይምሰልክሙ ዘንከፍሎ እም ድኅረ ፩ዱ ከዊን ወዳእሙ ናጤይቅ ህላዌ መለኮት ወህላዌ ትስብእት ወዓዲ ነአምር እስመ ቃል አኮ ዘተመይጠ እም ህላዌ መለኮቱ ለከዊነ ትስብእት ሶበ ኀደረ ላዕሌነ። - ዳግመኛ [ቅድመ ተዋሕዶ የነበረ] የሁለቱን ባሕርያት (የመለኮትንና የትስብእትን) ልዩነት፣ የሁለቱም ስም በጊዜው ሁሉ በሥራ በአነጋገር ልዩ እንደ ነበረ እንወቅ፤ እነዚህም መለኮትና ትስብእት ናቸው። እንደዚህም ባልን ጊዜ ከተዋሕዶ በኋላ የምንለየው አይምሰላችሁ፤ የመለኮትን ባሕርይ የትስብእትን ባሕርይ እናስረዳለን እንጂ፤ ዳግመኛም ቃል ባሕርያችንን በተዋሐደ ጊዜ ከመለኮቱ ባሕርይ ሥጋ ወደ መሆን እንዳልተለወጠ እናውቃለን።” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 131)።
“በዚህ መሠረት የአንቀጸ ተዋሕዶ ትምህርት በአንቀጸ ተከፍሎ መሠረት ከጥንት ተለያይተው ከኖሩ ከሁለቱ … የአንዱን የዐማኑኤልን ህላዌ ቅውም አድርጎ የሚያሳይ የምስጢረ ተሠግዎ ወይም የምስጢረ ተዋሕዶ ትምህርት ነው።”[4] ስለዚህ በተከፍሎ የነበሩት ከተወሐዱ በኋላ አንዱን ከሌላው መለየትና እየብቻቸው ማድረግ አይቻልም። ቄርሎስ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ኢትፍልጥ ሊተ እም ድኅረ ትድምርት እስመ ዘፈለጠ እንተ ባሕቲቶ ብእሴ ወእንተ ባሕቲቶ አምላከ ቃለ ክልኤተ ይሬስዮ ለዐማኑኤል። - ከተዋሕዶ በኋላ አትለይብኝ፤ ከተዋሕዶ በኋላ ብቻውን ሰው፥ ብቻውን አምላክ ቃል የሚል ሰው ቢኖር ዐማኑኤልን ሁለት ያደርገዋል።”[5]
የአንጾኪያው ባስልዮስም፣ “አይትከፈል ኀበ ክልኤቱ ህላዌያት እም ድኅረ ተዋሕዶ እስመ ለምንታዌ አእተታ ተዋሕዶ፤ ወተዋሕዶኒ ያግሕሥ ኵነኔሁ ለምንታዌ እስመ ውእቱ ተዋሕዶ አካላዊ ዘኢይትከፈል። - ከተዋሕዶ በኋላ ወደ ሁለት ህላዌያት አይከፈልም፤ ተዋሕዶ መንታነትን አስወግዷልና፤ የመንታነትንም ፍርድ አርቋል። እርሱ የማይከፈል አካላዊ ተዋሕዶ ሆኖአል” ብሏል (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 422)።  
ከእነዚህ ምስክርነቶች ስለ ወልድ ከትስብእትና ከተዋሕዶ በፊት ስለ ነበረው አቋም በአንቀጸ ተከፍሎ ሊነገር እንደሚገባና ከተዋሕዶ ወዲህ ስላለው አቋሙ ደግሞ በአንቀጸ ተዋሕዶ ሊነገር እንደሚገባ እንረዳለን። ምስጢረ ተዋሕዶ የተከናወነው በተለመደውና በሚታወቀው የውሕደት ሕግ ሳይሆን በሕገ ተዐቅቦ ነው። “ተዐቅቦ ማለት በቀላል አገላለጽ መጠበቂያ ማለት ነው። ለምሳሌ መጠበቂያ ያለው ነገር ከተፈለገ፣ ለጊዜው የጠመንጃ ሁኔታ ሊታወስ ይቻላል። ጠመንጃው ጥይት ጐርሶአል እንበል። ነገር ግን በአስፈላጊው ሁኔታና ጊዜ ምላጩ ተስቦ እስኪተኰስበት ድረስ መጠበቂያ ይደረግበታል። መጠበቂያም ስላለው፣ ምላጩን ወይም ቃታውን ሲስቡ፣ ጥይቱ አይተኰስም፤ አይባርቅም። ለዚያውም (ለተኳሹም) ለሌላውም ሰው ጕዳት አያስከትልበትም። መጠበቂያው እንዳይተኰስ ጠብቆታልና። እንግዲህ የመጠበቂያው መኖር በአስፈላጊነቱ መጠን ጠቀመ ማለት ነው።”[6] በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ ሕገ ተዐቅቦ ያስፈለገውም ቃልና ሥጋ እንዲጠባበቁ ለማድረግ ነው። “ተዐቅቦ ተራርቀው ይኖሩ የነበሩትን ባዕል፣ ምሉእና ፍጹም የሆነ አካለ ቃልን እና ድኻ፣ ውሱንና ትሑት የሆነ አዳማዊ ትስብእትን አገናዝቦ የሚገኝ” የምስጢረ ተዋሕዶ መጠበቂያ ነው።
ምስጢረ ተዋሕዶ የተመሠረተው “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ ዐደረ” በሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ላይ ነው (ዮሐ. 1፥14)። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ በጥቅሱ ውስጥ የምናገኛቸው “ኮነ” እና “ኀደረ” (ሆነ እና ዐደረ) የሚሉት ቃላት ተዋሕዶንና ተዐቅቦን በኅብረት ይዘዋቸዋል። አንዱ ለብቻው ተነጥሎ ማለትም “ኮነ” ለብቻው “ኀደረ”ም ለብቻው የተዋሕዶን ምስጢር ለመጠበቅ አያስችሉም። ስለዚህ ኮነ እና ኀደረ በአንድነት ምስጢረ ተዋሕዶን የሚጠብቁ ቍልፍ ቃላት ናቸው ማለት ነው። ቃላቱ ለተዐቅቦ ሕግ የተወሰኑት ሁለቱን ነጣጥለው በመጠቀም የተዋሕዶን ምስጢር ያፋለሱትን የንስጥሮስንና የአውጣኪን የተሳሳተ ትምህርት ለማረም መሆኑን ከሊቃውንቱ ማብራሪያ እንገነዘባለን።
ንስጥሮስ ምስጢረ ተዋሕዶን ለመግለጽ ኮነን ትቶ ኀደረን ነው የወሰደው። ስለዚህ “ ‘በአንዱ ክርስቶስ ሁለት ህላዌያት አሉ’ እስከ ማለት ደረሰና ውስጣዊ መለያየትን (ቡዓዴን) እና መከፋፈልን (ፍልጠትን) በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ አመጣ። ለዚህም የኮነን እውነተኛ ትርጕም ወይም ፍቺ የያዘና ከኀደረ ጋር የሚያገናኝ መጠበቂያ እንዲኖር አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቡዓዴ (ያለመለያየት)፣ ዘእንበለ ፍልጠት (ያለመፈራረቅ/ያለመከፈል)፣ በኢተላፅቆ (ያለመነባበር)’ የሚሉ መጠበቂያዎች፣ የኮነን ምስጢር ይዘው “ኀደረ” ያለውን እንዲጠብቁ ተደረገና የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ። ለዚህ ለንስጥሮስ ንጥል ሐሳብ ተዐቅቦ ባይደረግበት ለተዋሕዶ ትምህርት አደገኛ ይሆናል። የመጻሕፍት አተረጓጐምም ይጥበረበርበታል።”[7]    
ከንስጥሮስ በተቃራኒ አውጣኪም እንዲሁ ምስጢረ ተዋሕዶን የሚያጠፋ ትምህርት አስተማረ። “በአንዱ ክርስቶስ ቱስሕት (መደበላለቅ)፣ ውላጤ (የሰውነት መለወጥ)፣ ሚጠት (መለዋወጥ) እንዳለበት፣ ሰውነቱ ወደ አምላክነቱ እንደ ተለወጠ ተናገረ። አውጣኪ ኀደረን በመተው የኮነን ፍቺ በተሳሳተ አተረጓጐም ተመለከተና ኮነን ‘ተለወጠ’ በሚል ቃል ተርጕሞ ተሳሳተበት። እንደርሱ ዐሳብ ቢሆን የተዋሕዶን ምስጢር ተዋሕዶንም ደመሰሰበት። ለዚህም መጠበቂያ ልጓም አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቱስሕት (ያለመደበላለቅ)፣ ዘእንበለ ውላጤ (ያለመለወጥ)፣ ዘእንበለ ሚጠት ያለመለዋወጥ/ያለመመላለስ)’ የሚሉ ቃላት የኀደረን ምስጢር ይዘው የኮነን ፍቺ ወደ ሌላ እንዳይሄድ፣ ይኸውም በመለወጥ እንዳይተረጐም ይጠብቁ ዘንድ ተደረገ። በዚህም ተዐቅቦ የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ፤ ታወቀ። ይህ ተዐቅቦ ባይኖር የአውጣኪን ግንጥል ዐሳብ ለተከተለ ሰው የተዋሕዶ እምነቱንና በቅዱሳት መጻሕፍት ያለው የአተረጓጐሙን መንገድ ያቃውስበታል።”[8]
በአጠቃላይ ምስጢረ ተዋሕዶን “የምንጠብቀው በእነዚህ ሕጋውያን የውሳኔ ቃላት መጠበቂያዎች /ሕገ ተዐቅቦ/ ነው። ተዋሕዶ ባለበት ሁሉ ተዐቅቦም ዐብሮት ይገኛል።” ስለዚህ በተዐቅቦ በሆነው ተዋሕዶ አንዱ ክርስቶስ ያለመለያየት፣ ያለመፈራረቅ/ ያለመከፈል፣ ያለመነባበር፣ ያለመደበላለቅ፣ ያለመለወጥ፣ ያለመለዋወጥ ወይም ያለመመላለስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑ ከትምህርተ ንስጥሮስና ከትምህርተ አውጣኪ የተለየ የተዋሕዶ ትምህርት ነው።
ምስጢረ ተዐቅቦን በተመለከተ ቄርሎስ፣ “ኢይደልወነ ንፍልጦ ለ፩ዱ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመ ውእቱ ብእሲ በዐቅሙ ወለእመኒ ነአምሮሙ ለ፪ቱ ህላዌያት በዘዘዚኣሆሙ ወነዐቅቦሙ ዘእንበለ ቱስሕት በበይናቲሆሙ ንብል እንከ ፩ዱ ውእቱ ክመ ኢየሱስ ክርስቶስ። - በዐቅሙ እንደ ዕሩቅ ብእሲ አድርገን አንዱን ኢየሱስ ክርስቶስ ልንለየው አይገባንም፤ ሁለቱን ባሕርያት በየገንዘባቸው ብናውቃቸውም ያለመቀላቀል በየራሳቸው ብንጠብቃቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መቸም መች አንድ ነው እንላለን” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 338)።