Thursday, October 30, 2014

«የሚያስፈራሩን ከሆነ ወደየገዳማችን እንሄድልዎታለን!» አባ አብርሃም፤ «ወደየትኛው ገዳምዎ? ለመሆኑ ገዳም ያውቃሉ?» ፓትርያርክ ማትያስ


ቅዱስ ፓትርያርኩ ስለማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውን የፈረጠመ ጡንቻ ሲገልጹ «የፈርዖን አገዛዝ» ነበር ያሉት። ማኅበረ ቅዱሳን የደርግ መንግሥት መውደቅ የወለደውና በዓለት ስንጥቅ መካከል የበቀለ ዛፍ ነው። ዓለቱን አንቆ ይዞ በላዩ ላይ የለመለመ ነገር ግን ከአለቱ መካከል ከወጣ ኅልውና የሌለው ሥር አልባ መሆኑም እርግጥ ነው።  ይህን ሽብልቅ ገብቶ የፈረጠመውን ዛፍ ከማነቃነቅ ባለፈ ከሥሩ ነግሎ ለመጣል ጊዜና ሰው የተገናኙት ዘንድሮ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ዘመነ ፕትርክና ነው። ዋና ዓላማውም ከመሠሪና ስውር የቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወረራ ብቸኛዋን ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያንን መታደግ መሆኑን ቅዱስ ፓትርያርኩ በግልጽ ደጋግመው ተናግረዋል።

 «ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር» እንዲል መጽሐፉ ዘንድሮ ቀኑ ደርሶ ማኅበረ ቅዱሳንም ሆነ በማኅበረ ቅዱሳን እስትንፋስ የሚንቀሳቀሱ ተላላኪ ጳጳሳቱ የቤተ ክርስቲያኒቱን እጅ ጠምዝዘው ለማስረከብ ደፋ ቀና የሚሉበት ዘመን ግብዓተ መሬቱ እየተፈጸመ ይገኛል። ከትናንት በስቲያ በነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ የጉድ ሙዳይ የሚባለው ሊቀጳጳስ አባ አብርሃም በአቡነ ጳውሎስ ላይ የለመደ አፉን በአቡነ ማትያስ ላይ በመክፈት «የመንግሥትን ኃይል ተማምነው አያስፈራሩን፤ የሚያስፈራሩን ከሆነ ሲኖዶሱን ለቀንልዎ ወደየገዳማችን እንሄድልዎታለን» ብሎ እስከመናገር የደረሰ ሲሆን ቅዱስ ፓትርያርኩም ለሱም ይሁን ለቢጤ ወንድሞቹ ራስ ምታት የሆነ ምላሽ በመስጠት ዝም ጭጭ እንዲል አድርገውታል።

«ኧረ ለመሆኑ የእርስዎ ገዳም የት ነው? እስኪ ንገሩኝ የትኛው ገዳም ነው ያገለገሉት?  ደግሞስ እኔ አባ ማትያስ ለእርስዎ አንሼ ነው የመንግሥትን እርዳታ የምጠይቀው? ምነው! ቤተ ክርስቲያን እንደተሸከመችዎ አውቀው አርፈው ቢቀመጡ?!» በማለት የጳጳሱን ጉድ ጫፍ ጫፉን በመናገር አፉን እንዳስያዙት የውስጥ ምንጮች ገልጸዋል።

ተመሳሳይ በሽታ የነበረባቸው የማኅበሩ ጳጳሳት የጓደኛቸው ጉድ ፊታቸው ሲነገር በመስማታቸው የተሸማቀቁ ሲሆን አንዳንዶቹ በብስጭት ጉባዔውን ለመረበሽና ለምን ተነካን? የማለት ያህል ሲቁነጠነጡ ታይተዋል። ይሁን እንጂ ከቅዱስ ፓትርያርኩ የተሰጣቸው ምላሽ «ምን አለፋችሁ? ዘንድሮ ማኅበረ ቅዱሳንን በሕግና በሥርዓት ሳላስገባው አልተወውም!» በማለት ቁርጡን እንደነገሯቸው ተያይዞ የደረሰው ዜና ያስረዳል።
ቀደም ሲል የማኅበሩ ደጋፊ የነበሩ አንዳንድ ጳጳሳት ግን የፓትርያርኩን የጠነከረ አቋም ያጤኑ በሚመስል መልኩ ተዐቅቦን መርጠዋል። እነአባ ኤልያስ፤አባ ሉቃስ፤ አባ ቀውስጦስና በእድሜ ገፋ ያሉት ጳጳሳት ጥቂት የታገሉ ቢሆንም ከአባ ገብርኤል በስተቀር ወሎዬዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ግን ዝምታን መምረጣቸው ተዘግቧል። ምናልባትም «እነዚህ እኮ መንግሥትን ከአንድ ክፍለ ሀገር፤ ወደ ሌላ ክ/ሀገር ማዛወር የቻሉ ናቸው፤ ዛሬ አቤሲዲ ቆጥረውማ ማን ይችላቸዋል?» የተባለው ኃይለ ቃል ሳይከነክናቸው የቀረ አይመስልም።

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የተደረሰበት ውሳኔ እንደሚያሳየው ማኅበረ ቅዱሳን አፈንግጦ ከወጣበት የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ተመልሶ በሥሩ እንዲተዳደር፤ በቤተ ክህነቱ ሞዴላ ሞዴሎች እንዲጠቀም፤ እስከዛሬ የፈጸመው የገቢና ወጪው አጠቃላይ ሂሳብ በቤተ ክህነት ባለሙያዎች እንዲመረመር፤ አዲስ በሚረቀቀውና ፀድቆ በሚሰጠው የመተዳደሪያ ደንብ በቤተ ክህነቱ ቁጥጥር እንዲንቀሳቀስ፤ ማንኛውንም ሥራ ቤተ ክህነቱን እያስፈቀደ እንዲፈጽም የሚያስገድደው ውሳኔ የተላለፈበት መሆኑም ተዘግቧል። ድንቅ ውሳኔና ተገቢነቱም ትክክለኛ እንደሆነ አስምረንበታል።

 ድሮም በዚህ ዓይነቱ ልክና ገደብ ባለው አካሄድ ይስራ ከመባሉ ውጪ ይፍረስ፤ ይውደም ያለው  ማንም አልነበረም። ነገር ግን ማኅበሩ ያለውን ዓላማ ከግብ ለማድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግና ሥርዓት ዘለለ መልኩ በአባላት ጳጳሶቹ በኩል እንደሚመቸው አጣሞ በማስቀረጽ መንቀሳቀሱ እንዲገደብ ካለመፈለጉ የተነሳ ወደመላተም አድርሶታል።

የሚደርስበትን ጥላቻና ተቃውሞ ለመሸፈንና በቅዱስ ሲኖዶስ ሥር ለመሸሸግ በመፈለግ «ሲኖዶሱ ቀርጾ ከሰጠኝ መተዳደሪያ ደንብ ውጪ አልንቀሳቀስም» እያለ መደዴ አካሄዱን ሕጋዊ ለማስመሰል ይፈልጋል። እንደነአባ የጉድ ሙዳይ አባላቱ የሰጡትን ገደብ አልባ መተዳደሪያ ደንብ በማሞካሸት በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ የተጻፈ ለማስመሰል መሞከሩ ራሱን ከሚያታልልበት በስተቀር ማንንም ማሞኘት አይችልም። «የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው» በሚል ስልት የሚያጨበጭቡለት ጥቂቶች ባይታጡም አብዛኛው የቤተ ክህነት ሰው ዓይንህን ላፈር ካለው ውሎ አድሯል።
ጳጳሳቱ በማኅበረ ቅዱሳን አዚም ነፍዘው ቤተ ክርስቲያኒቱን አጨብጭበው ለማስረከብ በደረሱበት ሰዓት ፓትርያርክ አባ ማትያስ ደርሰው ልጓም አልባ ሩጫውን ገደብ ሰጥተውታል። ምናልባትም በማኅበሩ ግፍና መከራ የወረደባቸው ማኅበረ ካህናት፤ በኃጢአት ገመናቸውን እየገለበ የሚያሳድዳቸው ማኅበረ መነኮሳትና በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ያለቀሱት ልቅሶና ያፈሰሱት እንባ ከመንበረ ጸባዖት ደርሶ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ የመጣ ፍርድ ይሆን ይሆናል።
ወደፊትም ማኅበሩ ጊዜ በመግዛት የራሱን ሌላ አማራጭ ለመፍጠር እስትንፋሱን ያሰባስብ ይሆናል እንጂ አሁን በሚሰጠው ሕግና ሥርዓት ይተዳደራል ተብሎ አይጠበቅም። ለሁሉም አሁን የተያዘው የፓትርያርኩ እርምጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ዘንድ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት ያለው ነው።
 ሁላችንም ይበል ብለናል!