Wednesday, October 5, 2016

"የጎርፍ ዘመን ላይ ደርሰናል"


ቀን 08/27/2016

ይድረስ
       
ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣
ለኢትዮጵያ የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት በሙሉ ።

   በቅድምያ እናንተ በዚህ በአገራችን በኢትዮጵያ የሥልጣን ወንበር ላይ ለበጎም ይሁን ለክፉ ያስቀመጣችሁ ቸሩ አምላክ እግዚአብሔር እርሱ ባወቀው መንገድ እንደሆነ ስለማምን ለዚህም ኃላፊነትና ሥልጣን የተሰጣችሁ ናችሁና በእየ መዓርጋችሁ የከበረ የአክብሮት ሰላምታዬን አቀርባለሁ።

  ከዚህ በመቀጠል ሌላው
 ፩ኛ ሳሙ ፲፭፥፳ "....ሳሙኤልም እግዚአብሔር የእስራኤልን መንግሥት ዛሬ ከአንተ ቀደዳት፥ ከአንተም ለሚሻል ጎረቤትህ አሳልፎ ሰጣት...."ይላል።

 ይህንን ካልኩ በኋላ በእውነቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ የዛሬ ሃያ አምስት ዓመት የደርግን መንግሥት አስተዳደራዊ ሥርዓትን አስወግዳችሁ እናንተ በትረ መንግሥቱን በጨበጣችሁ ጊዜ ምናልባት ከደርግ የተሻለ ለአንድነት ለእኩልነትና ለነፃነት የሚያስብልን፣የብሔር ብሔረሰቦችና፣ሁሉን ያቀፈ፣በሕገ መንግሥቱ የሚተዳደር መንግሥት ይፈጠራል ብሎ ሲጠብቅ እናንተ ግን የሕገ መንግሥቱን ሥርዓት ባልጠበቀ መልኩ የኢትዮጵያን ሕዝብና የኤርትራን ሕዝብ ፍላጎት ባላካተተ፣ ባልጠበቀና፣ባላገናዘበ መልኩ የኹለቱን ሰላማዊ ሕዝብ አንድነት አጥፍታችሁ፣በአንድነቱ ፈንታ ኹለትነትን ፈጥራችሁ፣ ለያይታችሁ፣በኹለቱ ሕዝብ መካከል ጥቁር ነጥብ ጥላችሁ፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት፣ነፃነትና እኩልነት ያልቆማችሁ ለመሆናችሁ የምልክት ማህተብ በአንገታችሁ ያጠለቃችሁባትን ቀን ሳስብ መቼ ይሆን ይህ ዘመን የሚያልፈው ብዬ አስብ ነበር። የሚመጣውም ዘመን ምን እንደ ሚመስልና እንደሚሆን ስገምት በጣም ያስፈራኛና ያስጨንቀኝ ነበር።ታዲያ ዘመናትም ተቆጥሮ ዕለታትም አልፎ ኢየዋለ ኢያደረ ልዩነቱ፣መከፋፈሉ፣መለያየቱ፣መናናቁ፣መተራረዱ፣መገዳደሉና፣መጠላላቱ...ወዘተ በዝቶ ተባዝቶ እነሆ ዛሬ ያለንበት የደም ጎርፍ ዘመን ላይ ደርሰናል።

  ቅዱስ መጽሐፍ በማቴ ፩፪፥፳፭ ላይ "....ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው።እርስ በእርሷ የምትለያይ መንግሥት ሁሉ ትጠፋለች፤እርስ በእርሱ የሚለያይም ከተማም ወይም ቤት አይቆምም....."ይላልና ይህንን በአንድነት ሊያኖረን የማይችለውን ነገር አስወግደን ለሕዝብ የፈለገውን የመጠየቅ፣የመኖር፣ፍትህ የማግኘት እድል ካልሰጠን የኛም ሕልውና አጠራጣሪ ነው የሚሆነው።ሕዝብን ሁሉ በመግደልና፣በማሰር የምንመራው ከሆነ የሚቀረው ማነው?ሁሉም ከሞተ? ሁሉ ከታሰረ? በመንግሥት ስር የሚተዳደረው ማነው?ሕዝብ አልገዛም፣ አልተዳደርም፣እምቢ ካለ? ካመፀ? ።
ስለዚህ መንግሥት ለሕዝቡ ተማርኮ እጁን ሰጥቶና በቃኝ ብሎ መውረድና ሥልጣኑንም ለሕዝቡ መልቀቅ ላለፈው ላጠፋው ጥፋትና፣ በደል ይቅርታ ጠይቆ መቀመጥ አለበት።
   ምክንያቱም እስከ ዛሬ ድረስ ለተፈጠረው ጥፋት ሁሉ በየሚድያችሁ የመንግሥት የመልካም አስተዳደር ብሉሽነት ነው ኢያላችሁ ትናገራላችሁ።ሕዝቡም ያላችሁ ይህንኑ ነው።ትርፍ ነገርም አልጨመረም።መልካም አስተዳደር ከሌለ ያለው በተቃራኒው ክፉ አስተዳደር ነው ማለት ነው።ክፉ አስተዳደር ደግሞ ለሃያ አምስት ዓመታት ከመምረር አልፎ ይጎመዝዛል።አሁን ዛሬ የናንተን የመንግሥት አስተዳደር ማብቃት የሚፈልግና የሚጠይቅ ሁሉ ዕድሜ ተርፎትና በሚመጣው አዲስ የመንግሥት አስተዳደር ውስጥ ገብቶ ተደስቶና ተንደላቆ ለመኖር ፈልጎ ሳይሆን ለቀሪውና ለተተኪው አዲስ ትውልድ መልካም አስተዳደር ይምጣለት ሲል ብቻ ነው እንጂ፤እርሱማ አስራ ሰባት ዓመታት በደርግ መንግሥት፣ሃያ አምስት ዓመታት በእናንተ/ኢህአዴግ/ በአጠቃላይ ከአርባ ዓመታት በላይ በጥይት ሲቆላና ሲታመስ፣አንጀቱ አሮና ከስሎ፣ተስፋው ተሟጦ፣የሞተው ሞቶ፣የቀረው ያለ ፍትህ በየእስር ቤቱ ታፍኖና፣ታስሮ፣ሌላውም በዘር፣በጎሳ፣ቋንቋና፣ክልል ተከፏፍሎና፣ተበትኖ፣በስደት የአውሬና የውቅያኖስ እራት ኢየሆነ ይገኛል።

      ስለዚህ እናንተ የኢትዮጵያ መንግስት ባለሥልጣን ሆይ፥እስቲ እናንተም አሁን ይብቃችሁና ይህንን ምስኪን ሕዝብ በተራው በቃህ በሉትና ዕረፍት ስጡት፤እናንተም ደግሞ ዕረፉ።ደክሞአችኋል፣ዝላችኋል።አሥራ ሰባት ዓመታት በጫካ ሃያ አምስት ዓመታት በሕዝብ ጫንቃ ላይ ሳትወርዱ ተንጠላጥላችሁ በጣም ብዙ ዓመታትና ዘመናት ነው ይከብዳል።ከዚህ በላይ ብዙ ብትደክሙ መልካም አስተዳደርን ለሕዝቡ ልታመጡ በፍፁም አትችሉም።ምክንያቱም ሃያ አምስት ዓመታትን በሙሉ ተደክሞበት ያልታየ መልካም አስተዳደር በአንድ ሌሊት ስብሰባና ግምገማ በተአምራት ልታመጡ አትችሉም፣አይሆንም።ጊዜያችሁና ዕድላችሁ ሻግቶ ተበላሽቶአል።ስለሆነም እናንተ በሰላማዊ መንገድ እውነተኛ ሰላምን ፈልጋችሁ መልካም አስተዳደራዊ መንግሥት ሊፈጠርበት የሚችለውን የሕዝብ የሆነ የሽግግር መንግሥት ይመሠረት ዘንድና ሥልጣናችሁንም ለአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ወይም ድርጅት ሳይሆን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አስረክባችሁ በሰላም ውረዱና የዘመኑን ታሪክ ሥሩ።ያን ጊዜ የታሪክ ባለቤቶች ትሆናላችሁ።
አለበለዚ ግን ነቢየ እግዚአብሔር ሳሙኤል ለእስራኤል ንጉሥ ለሳዖል እንደ ነገረው ሳዖል በእስራኤል ሕዝብ ላይ መልካም አስተዳደርን አላመጣምና "... እግዚአብሔር መንግሥትህን ዛሬ ከአንተ ላይ ቀደዳት፣ለጎረቤትህም ሰው ሰጣት.." እንዳለው የዚህ ምስኪንና ደግ ሕዝብ እንባ
ወደ አምላኩ ወደ እግዚአብሔር ወደ ፀባዖት ጌታ ደርሶ መንግሥታችሁን ከእናንተ ላይ በቀደደ ጊዜ ያን ሰዓት ወየውላችሁ፣ወዮታ አለባችሁ።ምክንያቱም ያን ወቅት እናንተ በሰፈራችሁበት መስፈሪያ፣በመዘናችሁበት ሚዛንና፣በፈረዳችሁበት ፍርድ መሰፈር፣መመዘንና መፈረድ አለና ነው።
ያን ጊዜ ጩኸት ይሆናል የማይጠቅም ጩኸት ነው፤ያን ጊዜ ልቅሶ ይሆናል የማይጠቅም ልቅሶ ነው።ይህ ሁሉ የብድራታችሁ ክፍያ ውጤት ነው።

    ጊዜያት ሁሉ የአምላክ ናቸው።ሰዎች የጊዜያት ባለቤቶች አይደሉም።ነገር ግን በተሰጣቸውና፣ በተወሰነላቸው ጊዜ ውስጥ ኖረው መልካምም ይሁን ክፉ ሠርተው ያልፋሉ።ያ የሠሩትም መልካምም ይሁን ክፉ ሥራቸው ለዘለዓለም ሲነገርና ሲዘከር ይኖራል።እናም ምናልባት እናንተም ሥልጣናችሁን ተመክታችሁ ያላችሁበትን ወቅትና ሰዓት ሁሉ የእኛ ብቻ ብላችሁ የምታስቡ ከሆነ ተሳስታችኋል።ትላንት ያልነበራችሁብትን፣ዛሬ ደግሞ ያላችሁበትንና ነገ ደግሞ በተራው የማትኖሩበትን ጊዜ እንዳለ ማስተዋል ያስፈልጋችኋል ነው የምለው።ነገር ግን
እናንተ የደነደነ ልባችሁን ሰብራችሁ በይቅርታ ከዚህ ንፁህ፣ቅዱስና፣ደግ ሕዝብ ጋር ባትደራደሩ ነገ የጊዜያት ባለቤት ቸሩ አምላክ በጊዜው ለዚህ የዋህ ሕዝብ እጁን አጥፎና፣አመሳቅሎ፣ኢየታሰረ፣ኢየተደበደ፣ኢየደማና፣ኢየሞተ፣ለነፃነቱ፣ለእኩልነቱ፣ለአንድነቱና፣ለፍትህ ለሚጮኸው እናንተ ጩኸቱን ባትሰሙትና፣ባትፈርዱለት የሰማይ አባታቸው ቸሩ አምላክ ግን እንኳን ወደ እርሱ ጮኸው ለምነውት ቀርቶ ያልለመኑትንና ያልጠየቁትን
ሳይለምኑትና ሳይጠይቁት ይሰማቸዋል፣
ይሰጣቸዋል፣ይፈርድላቸዋል።

ክቡር የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር ኃይለ ማርያም፥
ክቡራን የኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ባለ ሥልጣናትና ኃላፊዎች በሙሉ፥
እስከ ዛሬ ድረስ ለሃያ አምስት ዓመታት እኛ ብቻ ነን የምንናገረው፣እኛ ብቻ ነን የምናውቅላችሁ ብላችሁ ስትናገሩልንና፣ስታውቁልን እውቀታችሁንም፣ንግግራችሁንም ሰምተናል፣ተቀብለናል።ዛሬ ደግሞ የእኛ ተራ ነው።እናንተም ስሙን።ስለ እናንተ እናውቅላችኋለን አድምጡን።
እግዚአብሔርን በማመን የሚሠሩት ሥራ ይባረካል፣ ይቀደሳል።
እግዚአብሔር በማመን የሚጓዙት መንገድ ቀና ነው።
እግዚአብሔርን በማመን ለሚቀርቡት ይቀርባልና እመኑበት።
እግዚአብሔርን በማመን የሚመሩት ሕዝብ
ታዛዥ ይሆናል።
ስለዚህ እስቲ እናንተ ደግሞ ዛሬ ላለፈው ጊዜና ዘመን በሕዝብ ላይ ለሠራችሁት በደልና ግፍ ምህረቱ ይደረግላችሁ ዘንድ ከልባችሁ ቸሩ እግዚአብሔርን በነገሮች ሁሉ ጠይቁት።ንስሐ ጠማማውን ያቀናል፣ኃጥኡን ጻድቅ፣ክፉውን መልካም፣
 መልካም አስተዳደርን፣ቅን ፍርድንና ሰላማዊ ሕይወትን ለሕዝቡና ለአገሩ ያጎናፅፍላችኋል። ለዚህ ሁሉ ጥፋት ጉስቁልና የመሪዎች ከእግዚአብሔር ሕግና መግቦቱ መራቅና ከእርሱ ጋር ያይደለ ድካም ለብቻቸው በክፉ መንፈስ ኃይል ስለሚድክሙ ጭምር ነው።
ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ
መዝ፦፻፳፮፥፩-፫
"እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ
ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ፤
እግዚአብሔር ከተማን ካልጠበቀ
ጠባቂ በከንቱ ይተጋል፤
በማለዳ መግሥገሣችሁም ከንቱ ነው...."
ይላልና እናንተ መሪዎች ቸሩ አምላካችን በነገሮች ሁሉ ተጨምሮ ለአገሪቱና ለሕዝቡ ሥልጣናችሁን በማስረከብ መልካም አስተዳደርን የምታመጡበትን የንስሐ ዘመንን ይሰጣችሁ ዘንድ አምላኬን እለምነዋለሁ።ለዚህም ቅን ልቡናን፣ አስተዋይ አእምሮን፣እግዚአብሔርን የምትፈሩበትን፣ሰውንም የምታከብሩበት ሕሊናን ይስጣችሁ።አሜን።

ቅዱስ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር.
ተፃፈ
በቀሲስ አሸናፊ ዱጋ ዋቄ።

Saturday, September 17, 2016

ለምናምንቴ እረኛ ወየውለት!

ሕዝቅኤል 34
"የሰው ልጅ ሆይ፥ ትንቢት ተናገር፥ በእስራኤል እረኞች ላይ ትንቢት ተናገር፥ እረኞችንም እንዲህ በላቸው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ራሳቸውን ለሚያሰማሩ ለእስራኤል እረኞች ወዮላቸው! እረኞች በጎችን ያሰማሩ ዘንድ አይገባቸውምን? ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።እረኛንም በማጣት ተበተኑ፥ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፥ ተበተኑም። በጎቼ በተራሮች ሁሉና በረዘሙ ኮረብቶች ሁሉ ላይ ተቅበዝብዘዋል፥ በጎቼም በምድር ፊት ሁሉ ላይ ተበትነዋል፤ የሚሻም የሚፈልግም አልነበረም። ስለዚህ፥ እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝና እረኛ ስለሌለ እረኞቼም በጎቼን ስላልፈለጉ እረኞችም ራሳቸውን እንጂ በጎቼን ስላላሰማሩ፥ በጎቼ ንጥቂያ ሆነዋልና፥ በጎቼም ለምድር አራዊት ሁሉ መብል ሆነዋልና"



Monday, September 12, 2016

ኦርቶዶክስ ሆይ ድምፅሽ ወዴት አለ?


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የወቅቱን የሀገሪቱን ቀውስ ከጸሎት ባሻገር በመምከርና በመገሰጽ ወደሰላማዊና የተረጋጋ ሁኔታ በመመለስ ረገድ ልትጫወተው የምትችለው ድርሻ ትልቅ እንደሆነ ይገመታል። ነገር ግን "መጽሐፉም ዝም፣ ቄሱም ዝም" እንዲሉ ሆነና እያየች እንዳላየች፣ እየሰማች እንዳልሰማች መሆንን የመረጠችው ለምን ይሆን?
ከሰማያዊው መንግሥት  ምድራዊውመንግሥት አስፈርቷት ነው? ወይስ ዝም እንድትል ከሰማያዊው መንግሥት መልእክት መጥቶላት ይሆን?
ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ ሆና ቤተ መንግሥቱንም፣ ሕዝቡንም ልትገስጽ፣ ልትመክር ካልቻለች ወደምድራዊ ውግንና ወይም ሥጋዊ ፍርሃት ገብታለች ማለት ነው። የተሰጣትን እውነት የመናገር ብርሃናዊውን መቅረጽ የምትቀማው መናገር ሲገባት ዝምታን ከመረጠችና ዝምታ በሚገባት ሰዓት መናገር ከፈለገች ብቻ ነው። እናም ዝምታዋ ዞሮ ዞሮ የተሰጣትን መንፈሳዊ ሃብት እንድትቀማ ያደርጋታል። ለሌላው አሳልፎ እንዲሰጥ ይሆናል። ለልክ እንደጥንታዊዋ የኤፌሶን ቤተክርስቲያን ማለት ነው። ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ሳይፈጸም አይቀርም። ደግሞም እያየን ያለንበት ወቅት ላይ ነን።
መንግሥት ሆይ፣ ሕዝብህን በሕግና በፍርሃት ግዛ። ሕዝብ ሆይ፣ ለመንግሥትህ በሕግና በፍርሃት ተገዛ ማለት የእርቅ አንደበት እንጂ ለማንም መወገን አይደለም። ምን ጊዜም ብጥብጥና ሁከት ለሕግና ለተአዝዞት ፈቃደኛ ካለመሆን የሚመጣ ስለሆነ የትኛውም አካል ለሕግ ተገዢ ይሁን ብሎ መናገር የሚያስፈራ ጉዳይ አልነበረም። ገዳይም፣ ሟችም፣ ሕግ አፍራሽም፣ ሕግ ደንጋጊም ሁሉንም እንደ ልጆቿ አድርጋ በማየት ለሕግ ተገዙ ልትል ሲገባት የኦርቶዶክስን አንደበት ሌሎች እየተናገሩበት ይገኛል። ልጆቿን ልጆቻቸው አድርገው አንደበቷን ወስደው እየተናገሩበት ይገኛሉ። ይሄ መነሳት የነበረበት ከእርሷ ቢሆንም የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጎዶሎ ወንጌል የሌላት ሆኖ ሳለ የወንጌል ሙሉ ነን የሚሉ ቀድመው የአስታራቂነት ሽምግልናውን ወስደዋል። ለመሆኑ የሀገር ቤቱ ሲኖዶስ በሕይወት አለህ?




Thursday, September 8, 2016

"ሳይቃጠል በቅጠል"




by ኢትዮ - አፖሎጂስት

አክራሪ እስልምና አፋጣኝ መፍትሄ ይሻል

ይህ ጊዜ ዓለማችን በከፍተኛ ሁኔታ እየተናጠችና እየታመሰች ያለችበት ጊዜ ነው፡፡ ሰላሟን እያናጉ የሚገኙ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ቢኖሩም አብይ መንስኤው ግን ለሰው ልጆች ሰላምና ደህንነት እንደቆመ የሚሰብከው የእስልምና ሃይማኖት መሆኑ የሚያከራክር አይደለም፡፡ በሦርያ፣ በኢራቅ፣ በየመን፣ በሊብያ፣ በናይጄሪያ፣ በሶማሊያ፣ በፓኪስታን፣ በአፍጋኒስታንና በሌሎችም ብዙ የዓለም ሃገራት የሚታዩት ሁኔታዎች ይህንኑ የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ በሌላ ወገን ደግሞ እስልምና “የሰላም” ሃይማኖት መሆኑ በተደጋጋሚ ይነገረናል፡፡ እንዲህ ዓይነት ስብከቶች ከሙስሊሞች ዘንድ ብቻ ሳይሆን ሙስሊም ካልሆኑት እና እንዲያውም የሽብር ተግባራቱ ሰለባዎች ከሆኑት ግለሰቦችና ሃገራት ዘንድ መሰማታቸው ጉዳዩን አደናጋሪ ያደርገዋል፡፡ እስልምና የሰላም ሃይማኖት ከሆነ እምነቱን አክርረው የያዙ ሙስሊሞች ስለምን እጅግ ሰላማውያን ከመሆን ይልቅ እጅግ ነውጠኞች ሆኑ? እንዲህ ዓይነት ተግባራትስ ስለምን የእምነቱ መታወቂያዎች ሆኑ? በማለት ተገቢ የሆነውን ጥያቄ የሚሰነዝሩ ወገኖች “እስላሞፎብያ” የሚል “የአዕምሮ ህመም” ስም ይለጠፍላቸዋል፡፡ እስልምና የሰላም ሃይማኖት እንዳልሆነ በድፍረት የሚናገሩ ሰዎች ሕይወታቸውን ለአደጋ ያጋልጣሉ፡፡ ታዋቂ ግለሰቦች እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑን ሲናገሩ ከተደመጡ ፅንፈኛ ሙስሊሞች አደባባይ በመውጣት ንብረት ያወድማሉ፣ የንፁኀንን ደም ያፈስሳሉ፣ በእምነት ተቋማት ላይ ቦምብ ይጥላሉ፣ የሰላም ሃይማኖት መሆኑን ለማሳመን ሰላምን ያደፈርሳሉ፡፡ የሙስሊሞች ተግባርና ስለ እምነቱ የሚሰበከው ስብከት አራምባና ቆቦ ሆኖብን ግራ ተጋብተን ሳናበቃ እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑንና “ካፊሮችን” ማሸበር እስላማዊ መሆኑን የሚናገሩ ሙስሊም ሊቃውንት ይገጥሙናል፡፡ በአንድ ወቅት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊዩ ቡሽ “እስላም ሰላም ነው” በማለት መናገራቸውን ተከትሎ አቡ ቀታዳ የተሰኘ በጂሃድ የሚያምን ሙስሊም አስተማሪ የሚከተለውን ብሎ ነበር፡- “ፕሬዚዳንት ቡሽ በእስልምና ስም የሚደረገውን የጂሃድ ሽብር የሚደግፍ ምንም ዓይነት ነገር በቁርአን ውስጥ አለመኖሩን መናገሩ በእጅጉ አስገርሞኛል፡፡ ለመሆኑ እርሱ የሆነ ዓይነት የእስልምና ሊቅ ነውን? እንደው በእድሜ ዘመኑ ቁርአንን አንብቦ ያውቃልን?”[1]
ሙስሊሞች በሚበዙባቸው ሃገራት ውስጥ የሚገኙት ብዙ ሙስሊም ሊቃውንት እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑን ይናገራሉ፡፡ በምዕራብ ሃገራት እና ሃገራችንን በመሳሰሉ የሙስሊሞች ቁጥር ከአጠቃላዩ የሕዝብ ቁጥር በሚያንስባቸው ሃገራት ውስጥ የሚገኙት ደግሞ እስልምና የሰላም ሃይማኖት መሆኑን ይሰብካሉ፡፡ የፖለቲካ መሪዎቻችንና የሃይማኖት አባቶቻችንም ከእነርሱ ጋር ይስማማሉ፡፡ እውነቱ የቱ ነው? ማንን እንስማ? የቱን እንቀበል? ከዚህ ግራ መጋባት ለመውጣት እስላማዊ የሃይማኖት መጻሕፍትን ማጥናት አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው፡፡
ከፊት ለፊታችን ከባድ አደጋ የተጋረጠ ቢሆንም ብዙዎቻችን የአደጋውን ግዝፈት ማየት አለመቻላችን ወይም ለማየት አለመፈለጋችን የሚያሳዝን ነው፡፡ በአክራሪ ሙስሊሞች በዚህች ሃገር ውስጥ ለደረሱት ጉዳቶች የኛ ቸልተኝነትና ዝምታ አስተዋፅዖ ማበርከቱን መካድ አንችልም፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ነገሮች ከልክ አልፈው ሃገሪቱ ከገደሉ አፋፍ ደርሳ ከመውደቋ በፊት እግዚአብሔር መንግሥትን ባያነቃ ኖሮ መፃዒ እጣ ፋንታችን ምን ሊሆን እንደሚችል ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን የማስታገሻ እርምጃ እንደተወሰደ እንጂ ትክክለኛ መፍትሄ እንደተሰጠ በልበ ሙሉነት መናገር አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የህመሙ ምልክት እንጂ መንስኤው አልታከመምና፤ መንስኤው እስካልታከመ ድረስ ደግሞ ጊዜ ጠብቆ መልሶ ማገርሸቱ የማይቀር ሃቅ ነው፡፡ የአክራሪነት ሥረ መሰረት በቁርአን፣ በሐዲሳትና በሌሎችም እስላማዊ ምንጮች ውስጥ ሰፍረው የሚገኙት ትምህርቶች መሆናቸውን መካድ አያዋጣንም፡፡ ሽብርተኝነት የዛፉ ፍሬ በመሆኑ ሥራ መሰራት ያለበት ከፍሬው ይልቅ በግንዱ ላይ ነው፡፡ ይህንን የተረዱት የግብፁ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ ኧል-ሲሲ የዓለም ግምባር ቀደም እስላማዊ ዩኒቨርሲቲ እንደሆነ በሚነገርለት በአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ ሙስሊም ሊቃውንት ፊት ያደረጉት ዓለምን ያስደመመ ንግግር ጥሩ ምሳሌ ይሆነናል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ያለ ምንም መሸፋፈን ችግሩ የሚገኘው እድሜ ጠገብ በሆኑት እስላማዊ ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ መሆኑን በማስገንዘብ በዓለም ላይ ለሚገኘው የሽብርተኝነት ችግር መፍትሄ እንዲመጣ ከተፈለገ እነዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት መስተካከል እንዳለባቸው ጥብቅ ማሳሰብያ ሲሰጡ ተደምጠዋል፡፡ ሙስሊሞች በዓለም ላይ የሚገኙትን ሕዝቦች ሁሉ በማጥፋት እራሳቸው ብቻ ለመኖር መፈለጋቸው የሚያስከትለውን አደጋ በመጠቆም የማስጠንቀቂያ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ የሚከተለው ከንግግራቸው ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው፡-
“… እዚህ ጋ እየተናገርኩ ያለሁት የእምነት አባቶችን ነው፡፡ እየተጋፈጥን ስላለነው ነገር በአንክሮ ማሰብ ያስፈልገናል – በእርግጥ ይህንን ጉዳይ ከዚህ ቀደም አንድ ሁለት ጊዜ አንስቻለሁ፡፡ በጣም ክቡርና ቅዱስ አድርገን የያዝነው አስተሳሰብ አጠቃላይ ኡማውን [እስላማዊውን ማሕበረሰብ] ለዓለም ማሕበረሰብ የጭንቀት፣ የአደጋ፣ የግድያ እና የጥፋት ምንጭ እንዲሆን ማድረጉ የማይታመን ነው፡፡ ይህ ሊሆን አይችልም!
ያ አስተሳሰብ – “ሃይማኖት” እያልኩ አይደለም ነገር ግን “አስተሳሰቡ” – ከእርሱ ማፈንገጥ የማይቻልበት ደረጃ ላይ እስክንደርስ ድረስ ለክፍለ ዘመናት አክብረን የያዝነው የመጻሕፍትና የአስተሳሰብ ስብስብ መላውን ዓለም እየተፃረረ ይገኛል፡፡ ዓለምን በሞላ እየተፃረረ ነው!
እነዚህን ቃላት እዚህ በአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ፣ በዚህ የሊቃውንትና የኡላማ ጉባኤ ፊት እየተናገርኩ ነው – አሁን እየተናገርኩ ያለሁትን ነገር በተመለከተ ሁሉን ቻይ የሆነው አላህ በፍርዱ ቀን ስለ እውነተኛነታችሁ ምስክር ይሁንባችሁ፡፡
እየነገርኳችሁ ያለሁትን ይህንን ሁሉ ነገር በዚህ አስተሳሰብ ውስጥ ተጠምዳችሁ የምትኖሩ ከሆነ ልትረዱት አትችሉም፡፡ በትክክል መገምገም እንድትችሉና የበለጠ አብርሆት ካለው ፅንፍ ማየት ትችሉ ዘንድ ከራሳችሁ ሁኔታ መውጣት ያስፈልጋችኋል፡፡
ደግሜ ደጋግሜ እላለሁ ሃይማኖታዊ አብዮት ያስፈልገናል፡፡ እናንተ ኢማሞች በአላህ ፊት ተጠያቂዎች ናችሁ፡፡ መላው ዓለም፣ እደግመዋለሁ መላው ዓለም የእናንተን ቀጣይ እርምጃ እየተጠባበቀ ይገኛል… ምክንያቱም ይህ ኡማ እየፈረሰ ነው፣ እየወደመ ነው፣ እየጠፋ ነው – እየጠፋ ያለው ደግሞ በገዛ እጃችን ነው፡፡[2]
በዚህ ንግግር ውስጥ ፕሬዚዳንት ኧል-ሲሲ በእስላማዊ ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ የተሰገሰገው የነውጠኝነት አስተሳሰብ የዓለም ስጋት ምንጭ መሆኑን በግልፅ አስረድተዋል፡፡ በዚህ ገፅ ላይ በተከታታይ ስናወጣ እንደቆየነው የሽብርተኝነት ሥረ መሰረት እስላማዊ መጻሕፍት እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ (አይ ኤስ የተሰኘው የሽብር ቡድን እየፈፀማቸው የሚገኙት የሽብር ተግባራት በእስላማዊ ምንጮች የተደገፉ መሆናቸውን ማስረጃዎችን በመጥቀስ ያሳየንበትን ጽሑፍ ለአብነት ያህል ማየት ይቻላል፡፡) ካለማወቅም ይሁን ከፖለቲካዊ ትክክለኝነት (Political Correctness) በመነጨ አስተሳሰብ እስላማዊ መጻሕፍት ሰላምን እደሚያስተምሩ በመስበክ ለእስልምና ጥብቅና ሲቆሙ የነበሩ ወገኖች ይህንን ማድረጋቸው ምንም አልፈየደም፡፡ አንድን ከሥነ ምግባር የወጣ ሰው ሥነ ምግባሩ ጥሩ እንደሆነ ደጋግሞ በመንገር ፀባዩን እንዲያርም ማድረግ እንደማይቻል ሁሉ ሽብርን የሚሰብክ ሃይማኖት ሰላምን እንደሚሰብክ በመናገር ሰላማዊ ማድረግ አይቻልም፡፡ ይልቁኑ ስህተቱን ነቅሶ በማውጣት እንዲያስተካከል መንገር እንጂ መፍረግረግና መለማመጥ አጥፊው የልብ ልብ እንዲሰማው ማድረግ ነው፡፡ እውነትን ሸሽጎ ውሸትን በመናገር ችግሩን ማፈርጠም መፍትሄ አይሆንም፡፡ የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ንግግሮች ዘላቂ መፍትሄ ሊያመጡ ይቅርና ጊዜያዊ መፍትሄ እንኳ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡ የሃይማኖት አባቶችና የፖለቲካ መሪዎች የእስልምናን ሰላማዊነት አጥብቀው ቢሰብኩንም ነገር ግን ችግሮች እየተባባሱ ሄዱ እንጂ ሲቀንሱ አልታዩም፡፡ እውነትን በመናገር ሊፈጠር የሚችለውን ጊዜያዊ ችግር በመፍራት ዝንተ ዓለም በሽብር እየተናጡ ከመኖር እውነቱን አፍረጥርጦ በመናገር ዘላቂ መፍትሄ መፈለግ ይበጃል፡፡ “ጅቡ እግሬን እየበላው ነውና እንዳይሰማን ዝም በል” እንዳለው ሞኝ ሰው መሆን ይበቃናል፡፡
ማሕበረሰባችንን ከዚህ አስከፊ የጥፋት ማዕበል ለመታደግ የመጀመርያው እርምጃ መሆን የሚገባው የችግሩን ምንጭ ለመረዳት ጥረት ማድረግ ነው፡፡ በአንድ ወቅት የምንጊዜም ምርጥ ሳይንቲስት የሆነው አንስታይን ዓለምን ከጥፋት ለመታደግ አንድ ሰዓት ብቻ ቢሰጠው የተሰጠውን ጊዜ እንዴት እንደሚጠቀም ተጠይቆ ሲመልስ 55 ደቂቃዎችን ችግሩን ለመረዳትና 5 ደቂቃዎችን ብቻ መፍትሄ ለማፈላለግ እንደሚጠቀም ተናግሮ እንደነበር ይነገራል፡፡ የብዙ ችግሮቻችን መፍትሄ ያለማግኘት ምክንያቱ ችግሮቹን ራሳቸውን በትክክል አለማወቃችን መሆኑ እሙን ነው፡፡ ሽብርተኝነት በህዝባችን ላይ አደጋን የደቀነ የዘመናችን ችግር መሆኑን እናውቃለን፡፡ ነገር ግን የሽብርተኝነት ምንጭ ምን እንደሆነ ስለማናውቅ የችግሩ አሳሳቢነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ይገኛል፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ ሃገራችን በዙርያዋ ከሚገኙት ጎረቤቶችዋ ጋር ሊነፃፀር በማይችልበት ሁኔታ ከሽብር አደጋዎች ተጠብቃ ትገኛለች፡፡ ነገር ግን የሽብርተኝነት ምንጭ የሆነውን የእስልምናን ትምህርት በትክክል ተረድተን መፍትሄ ካላፈላለግን በስተቀር ይህ አንፃራዊ ሰላም በዚህ ሁኔታ ለመቀጠሉ ምንም ዋስትና አይኖረንም፡፡ ስለዚህ ዜጎችም ሆንን መሪዎች እስልምና ሽብርተኝነትን በተመለከተ ምን እንደሚያስተምር፣ ምን እንደሚያቅድ፣ የአፈፃፀም ስልቶቹ እንዴት እንደሆኑ፣ ወዘተ. ማጥናት ያስፈልገናል፡፡ እውቀቱ ካላቸው፣ በተለይም ደግሞ በእስልምና ትምህርቶች ከሰለጠኑና እስልምናን ለቀው ከወጡ ሰዎች መማር እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡
አክራሪ እስልምና ለዓለምም ሆነ ለሃገራችን አዲስ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የአክራሪ እስልምናን ተግዳሮቶች ስትጋፈጥ ኖራለች፡፡ አንዳንዶች አክራሪ እስልምና ፖለቲካዊ ችግር በመሆኑ መፍትሄው ፖለቲካዊ ነው ስለዚህ ችግሩ ለመንግሥት ብቻ መተው አለበት ይላሉ፡፡ ነገር ግን፡-
መንግሥት ሥልጣንና ጉልበት ቢኖረውም የትምህርቱን ውጤት እንጂ ትምህርቱን መጋፈጥ አይቻለውም፡፡ የመንግሥት አካላት ብዙ ጊዜ በሃይማኖት ካባ ተሸፍኖ ለክፍለ ዘመናት የኖረውን አይ የእስልምናን ፖለቲካ ለመረዳት ሲቸገሩ ይስተዋላሉ፡፡ ስለዚህ ትክክለኛ መፍትሄ ለመስጠት ይቸገራሉ፡፡
የመንግሥት አካላት የነገሩን ውስጠ ሚስጥር ቢረዱትም እንኳን መንግሥት ሁሉን አቀፍ በመሆኑ ገለልተኛነትን ይመርጣሉ፡፡ ስለዚህ የችግሩ መንስኤ የሆነውን የእስልምናን መሰረት መንካት አይፈልጉም፡፡
አክራሪ እስልምና አይዲዎሎጂ በመሆኑ በጉልበት አይቀለበስም፡፡ ስለዚህ መንግሥት አክራሪ እስልምና የጦር መሳርያ ይዞ አደባባይ ሲወጣ በጦር መሳርያ ማስታገስ ቢችልም ነገር ግን ትምህርቱን የሚጋፈጥበት ሥነ መለኮታዊ መሳርያ የለውም፡፡
ባለፉት ጥቂት ዓመታት እንደታዘብነው አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ይባስ ብለው ከአክራሪ እስልምና ጋር በመተባበር አጀንዳውን ሲያራግቡና ጥብቅና ሲቆሙለት ታይተዋል፡፡ ይህ የሚያመለክተው አንዳንድ ፖለቲከኞች የዛሬ ጥቅማቸውን እንጂ የነገውን አደጋ ማየት አለመፈለጋቸውን ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰዎች ሥልጣን ቢይዙ ችግሩን ከማባባስ ውጪ መፍትሄ መስጠት አይችሉም፡፡
የመገናኛ ብዙኃንን ስንመለከት እንኳንስ መፍትሄ ሊሰጡ ይቅርና ጥያቄውን እንኳ በትክክል የተረዱት አይመስልም፡፡ በትክክል ቢረዱትም እንኳን ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ስለሚጫናቸው የችግሩን ስረ መሰረት በመንካት መፍትሄ ማፈላለግ አይችሉም፡፡
ምሑራን ጥያቄውን የተወሰነ ያህል ይረዱታል ነገር ግን የችግሩን ስረ መሰረት በመጥቀስ የመፍትሄ ሐሳቦችን እንዳይሰነዝሩ በፍርሃትና በፖለቲካዊ ትክክለኝነት ተሸብበዋል፡፡
አንዳንድ ለዘብተኛ አመለካከት ያላቸው ምዕራባውያን የሚከተሉትን “መፍትሄዎች” ያስቀምጣሉ፡-
ለአክራሪ ሙስሊሞች ምንም ትኩረት አለመስጠትና ችላ ማለት፡፡ ነገር ግን ችላ የሚባሉት እምን ድረስ ነው? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ሰይፍ አንገታችን ላይ ተቀምጦ ትኩረት አንሰጠውም ማለት የሞኝ መፍትሄ ነው፡፡
ባሉበት እንዲሆኑ ማገድ (ወደ ክልላችን እንዳይገቡ ማድረግ፡፡) o አሁን ካለው የሕዝቦች እንቅስቃሴና የመረጃ ቴክኖሎጂ ደረጃ አኳያ አያስኬድም፡፡ የውጪዎቹ እንዳይገቡ ማገድ ይቻል ይሆናል፣ ውስጥ የሚገኙትንስ? መግደል? ማሰር? ከሃገር ማባረር? አያዋጣም፡፡
እስልምናን ከፖለቲካዊ ይዘቱ በማፋታት ምዕራባዊ መልክ ያለውን እስልምና መፍጠር [ለምሳሌ ኪልያም (Quilliam) ፕሮጀት]፡፡[3]

Saturday, August 27, 2016

ሴቶች ሁልጊዜ ልብ በሉ!



ሴቶች ከወንድ ጓደኛ ማንን ትወዱ? ማንንስ ትመርጡ? ከማንስ ጋር ጋብቻን ትፈፅሙ? እስኪ ራሳችሁን ጠይቁ።
በራስ መተማመን ያላት ሴት ለችግሮች ራሷን አሳልፋ አትሰጥም። በሁኔታዎች መለዋወጥ አትሸበርም። ራሷን ላጋጠማት ተግዳሮት ታዘጋጃለች እንጂ በሽንፈት ለቅሶን አታስተናግድም። ታዲያ ይህንን ኃይል ከየት ማግኘት ትችላለች?
               ✔ ✔✔
መልካም ክርስቲያናዊ ቤተሰብ ውስጥ ያደገች ሴት ስነምግባርን፣ እውቀትን፣ ችሎታና በራስ መተማመንን የምታዳብረው በቅርቧ ባለው ከቤተሰቧ ነው። በአስተዳደግና በልጅነት ሕይወት ጉድለት የደረሰባት፣ በብዙ ችግሮችና መከራ ውስጥ ያለፈች ሴት በስነልቦናዋ ላይ በሚደርሰው ጉዳት በራስ መተማመኗን በማጣት ችሎታዋን ለማውጣትና ችግሮችን ለመጋፈጥ ያላትን አቅም አውጥታ ለመጠቀም ሊያዳግታት ይችላል።

 በተለይም በአስገድዶ መደፈር፣ በእናት ወይም በአባት ብቻ ወይም ከሁለቱም አሳዳጊ ውጪ ያደገች፣ የኑሮ ጫናና ድህነት፣ አካባቢያዊና ሀገራዊ ችግሮች ( ጦርነት፣ ረሃብ፣ ስደት) በሴቷ ስነልቦና ላይ የሚያደርሱት ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በቃላትም መግለፅ ከሚቻለው በላይ የስነልቡና ተጠቂ ልትሆን ትችላለች።
 በዚህም የተነሳ ሴቶች ለአካለ መጠን ከደረሱ በኋላ ቤተሰባዊ ሕይወትን ለመመስረት በሚያስችላቸው ሁኔታ ላይ ያሳለፉት ቁስል የሚያደርስባቸው የአእምሮ ፈተናና ትግል እጅግ ውስብስብ ነው።
የመጠራጠር፣ ያለማመን፣ አንዳንዴም በቀላሉ የመታለል ወይም የመሸወድ ክስተት ሲያጋጥማቸው ያታያል። ሴቶች በፈገግታና በሳቅ ሸፍነው በማህበራዊ ኑሮው ቶሎ የመቀላቀል ተፈጥሮአዊ ችሮታ አላቸው እንጂ በኋላቸው የተሸከሙት ህመም በጣም ብዙ ነው። ሲስቁና ሲጫወቱ ዘመናቸውን ሁሉ እድለኞች የነበሩ ሊመስለን ይችላል። እውነቱ ግን እሱ አይደሉም። ሴቶች መከራቸውን እንደወንድ እያመነዠኩ ስለማይኖሩ ከሰው ለመቀላቀል ብዙም አይቸገሩም። ያ ደግሞ ሴትን ልዩ ፍጥረትና የተወደደች ያደርጋታል። ሴት ለወንድ ሚስት ብቻ ሳትሆን የጉድለቱ ሙላት የመሆኗም ምስጢር ሁሉን መከራ መሸከም መቻሏ ነው። 6 ልጆቿን ያለአባት አሳድጋ ለቁምነገር ያበቃች እናት አውቃለሁ።
                ✔✔✔
ክርስቲያን ሴቶች ምንም እንኳን ያለፈ ሕይወታቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ባለ አዲስ የእምነት ልምምድ የተለወጠ ቢሆንም ያሳለፉት ስነልቦና በቀላሉ የሚፋቅ ባለመሆኑ አልፎ አልፎ መቸገራቸው አይቀርም። ከጋብቻ በፊት የመንፈሳዊ ጋብቻ ትምህርትና የምክር አገልግሎት ማግኘት የበለጠ ተጠቃሚ ሊያደርጋቸው ስለሚችል በዚሁ መልኩ አስቀድመው ቢገለገሉ የተሻለ ግንዛቤ ይኖራቸዋል።
በኛ በኩል ያሉንን ምክሮች ጥቂት እንበል።
               ✔✔✔
ባለፈ ስህተትሽ አትቆጪ። የዛሬውን ሃሳብሽን እንዲቆጣጠረውም አትፍቀጂ። ያለፈው ላይመለስ አልፏል። ያለፈው ለዛሬው ያለው እድል አስተማሪ መሆኑ ብቻ ነው። ጎበዝ ሰው በሌላ ሰው ስህተት ይማራል፣ ሰነፍ ሰው ደግሞ ከራሱ ስህተት ይማራል። ያለፈው ስህተትሽ ለዛሬው ማንነትሽ ትምህርት ከሆነሽ፣ አንቺ የዛሬዋ ጎበዝ ነሽ። ካለፈችው ሰነፏ አንቺነትሽ በልጠሻል ማለት ነው። ስህተት አንዴ ከበዛ ደግሞ ሁለቴ ቢሆን ነው። ከደጋገመሽ ግን ስህተቱ ከጎዳሽ ነገር ሳይሆን ካንቺ አለመለወጥ የመጣ ነው።
ፈረንጆች እንዲህ የሚል አባባል አላቸው። "ስትሄድ የመታህ የድንጋይ እንቅፋት ስትመለስም ከደገመህ ስህተቱ የእንቅፋቱ ሳይሆን ድንጋዩ አንተው ነህ" ይላሉ።
ፍርሃትን በራስ መተማመን፣ ስህተትሽን በመታረም ማሸነፍ ትችያለሽ።
አብዛኛው ወንድ ሴትን የሚወደው በአይኑ ነው። የውስጧን ማንነት ሳያይ ውጫዊውን አይቶ ማድነቅም፣ መውደድም ይቻላል። ብቻውን ግን ለፍቅር ግንኙነት አያበቃም።
 የደም አይነት ልዩ ልዩ ነው። ሁሉም ደም ለሁሉም ሰው አይሆንም። በአይን የመጣ መውደድም በሁሉም ሴት ላይ ፍቅርን ሊመሰርት አይችልም። ለምርጫ የሚያበቃ ጥናት ያስፈልገዋል። የወደዱን ሁሉ ያፈቅሩናል ማለት አይደለም። ይህን ለማወቅ ጊዜ ወስዶ ማጥናት ተገቢ ነው። ለኛ የተሰጠ ሰው ከሆነ ለማጥናት በምንወስደው ጊዜ ያመልጠናል ብለን መስጋት አይገባም። እንዲያውም ሳናውቀው ዘው ከምንል ቢያመልጠን ይሻላል። ለኛ የተሰጠን እንዳይዘገይ ቶሎ መሄዱ ይሻላል። የከረመ ወይን ሲጠጡት ሆድ አይነፋም።

በአይን የወደደ የአይኑን አምሮት በአካል ባገኘው ጊዜ ቶሎ ይረካል። ከዚያም የማያርፈው አይኑ ወደሌላ ይሄዳል። ሴት ሆይ፣ የሚወድሽን ወንድ አይኑን ብቻ ሳይሆን ልቡን እዪው። ምን ይልሻል? ስሚው። አንቺን አይቶ ለልቡ አምሮት የሚቅበዘበዝ ከሆነ ችግር አለ። በአፉ እወድሻለሁ እያለ ፍቅሩን በተግባር የማያሳይ ከሆነ ችግር አለ። እንጋባ ሳይሆን እስክንጋባ አልጋ ላይ እንውጣ የሚልሽ ከሆነ ችግር አለ። የሚሰጥሽን ጊዜ ቀስ በቀስ የሚቀንስ ከሆነ ችግር አለ።
ታማኝ ወንዶችን ከአስመሳዮች ለመለየት ጊዜ ውሰጂ። አትቸኩዪ። በምላስ ብልጠት አትሸነፊ። ልቡን ለማወቅ አንቺ አምላክ አይደለሽም። ምላሱን በተግባሩ ፈትኚ። ከትዳር በፊት የተደጋገመ ውሸት በትዳር ውስጥም ይቀጥላልና ተጠንቀቂ።
በሰውኛ ሚዛን መልክና ውበት ጥሩ ነው። ነገር ግን ለእግዚአብሔር መንግስት በተመረጠ ትዳር ውስጥ ሁሉም ከንቱ ነው። ቅን እንጂ ቅንቅን አትሁኚ። ገንዘብ፣ ጌጥና ምቾት አያታልሽ። ዝሙት ኃጢአት ነው። ፍፃሜውም ሞት ነው። ስለዚህ በታማኝነት ለእግዚአብሔር መንግስት ራስሽን አስገዢ።

 ጠቢቡ በመጽሐፉ እንዳለው መክብብ 6፣12
"ሰው በከንቱ ወራቱ ቍጥርና እንደ ጥላ በሚያሳልፈው ዘመኑ በሕይወቱ ሳለ ለሰው የሚሻለውን የሚያውቅ ማነው? ወይስ ለሰው ከፀሐይ በታች ከእርሱ በኋላ የሚሆነውን ማን ይነግረዋል?" ነውና ለጊዜው ለእግዚአብሔር ክብር ለሚሆን ሕይወት እንጂ ይህ ቋሚ መኖሪያችን አይደለምና ራስን መግዛት አትርሺ።
             ✔✔✔
"ጌታ ቅርብ ነው። በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ"
ፊልጵ 4:6

Monday, August 22, 2016

ወሀቢዝም በኢትዮጵያ ውስጥ!


by ኢትዮ - አፖሎጂስት

ከ1983 ዓ.ም. የመንግሥት ለውጥ ወዲህ በኢትዮጵያ ውስጥ የሃይማኖት ነፃነት ከቀደሙት ዘመናት ጋር ሊነፃፀር በማይችልበት ሁኔታ መከበሩ የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ ነገር ግን ይህንን ነፃነት የለአግባብ የተጠቀሙና የጥፋት መርዛቸውን በትውልዱ መካከል ለማሰራጨት የተጉ፣ ከዚህም የተነሳ ብዙ ጥፋቶችን ያስከተሉ ቡድኖች መኖራቸው አልቀረም፡፡ በዚህ ረገድ በተለይ የወሃቢዝም (ሰለፊ) ፍልስፍናን የሚከተሉ ወገኖች ይጠቀሳሉ፡፡ ዛሬ በሃገሪቱ ውስጥ በብዛት ተሰራጭቶ በሕዝቦች መካከል ያለውን የመቻቻልና አብሮ የመኖር ባሕል እያደፈረሰ የሚገኘው ወሃቢዝም ይህንን ነፃነት ተጠቅሞ የተስፋፋ ይሁን እንጂ እግሩን  በሃገሪቱ ውስጥ ካሳረፈ ብዙ አስርተ አመታት አልፈዋል፡፡

ፋሺስት ኢጣልያ  በኢትዮጵያ ላይ የነበረውን እኩይ አጀንዳ ለማስፈፀም ሙስሊሞችን መንከባከብ የሚል መርሃ ግብር ስለነበረው ሙስሊሞች የሐጅ ጉዞ እንዲያደርጉ ያበረታታ ነበር፡፡ በገንዘብም በመደጎም ይልክ ነበር፡፡ በ1933 ለሐጅ ወደ መካ የተጓዙት ኢትዮጵያውያን ቁጥር 11 ብቻ ሲሆን ከ1934-1935 የሄዱት 29፣ ከ1935-1936 ደግሞ 7 ሰዎች ብቻ ነበሩ፡፡ ነገር ግን በ1937 ይህ ቁጥር ወደ 1,700 አድጓል፡፡ ሁሉም ደግሞ በኢጣሊያ መንግሥት ድጎማ የሄዱ ነበሩ፡፡[1] ሳዑዲ አረብያ ለሐጅ የሚሄዱትን ኢትዮጵያውያን በወሃቢዝም ፍልስፍና አጥምቃ ወደ ሃገር ውስጥ በማስገባት ፍልስፍናውን የማስፋፋት ሥራዋን የጀመረችው ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ከመውረሯ በፊት ነበር፡፡ በተለይም ደግሞ ሼኽ ዩሱፍ አብደል ረህማን እና ሐጂ ኢብራሂም ሀሰን የተሰኙ ሁለት ሰዎች ለዚህ በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ ሁለቱም ወደ ሳዑዲ የተጓዙት በ1930ዎቹ መጀመርያ አካባቢ ነበር፡፡ ሼኽ ዩሱፍ በ1939 ወደ ኢትዮጵያ በመመለስ በሐረር ከተማ የወሃቢዝም ትምህርታቸውን ማስተማር የጀመሩ ሲሆን የሐረርን ከተማ የቀድሞ ነፃነት ለመመለስ የከተማይቱን ሙስሊም ሊቃውንት አደራጅተው ፊርማ በማሰባሰብ በወቅቱ የብሪቲሽ የአካባቢው አማካሪ ለነበሩት ለኮሎኔል ዳላስ ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡ ነገር ግን ኮሎኔሉ ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርገዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ነበር ሼኽ ዩሱፍ ለረጅም ጊዜ ትግል መሰረት ለመጣል የወሰኑት፡፡ ከዚያም ብሔራዊ እስላማዊ ማሕበር (አል-ጀማኢያ አል-ወኒያ አል-ኢስላሚያ) ወይም አል-ዋታኒ የተሰኘ ማሕበር በማቋቋም መንቀሳቀስ ጀመሩ፡፡ የማሕበሩ አባላት በሙሉ ሐረርን “ከኢትዮጵያ ቅኝ ነፃ በማውጣት” አሕመድ ግራኝባስቀመጠው ምሳሌነት መሰረት እስላማዊ መንግሥት እንደገና ለማቋቋም ቃል ኪዳን ገቡ፡፡ የሐረርን ሕዝብ በሚገባ ሳያስተምሩ መንግሥትን መጋፈጥ እንደማይቻል ስለተገነዘቡም ዋታኒ እስላማዊ ማሕበር ቀደም ሲል የተሰራውን ትምህርት ቤት በመጠቀም እስላማዊውን ትምህርት በማስተማር ላይ እንዲያተኩር ተወሰነ፡፡ ትምህርት ቤቱም ዘመናዊ መልክ ኖሮት አረብኛና በሐጂ ኢብራሂም ሀሰን አማካይነት ደግሞ የወሃቢዝም ትምህርት እንዲሰጥ ተባለ፡፡ ሐጂ ኢብራሂምም በከፍተኛ ትጋት በየምሽቱ በቤታቸውም ጭምር ይህንን ፍልስፍና ማስተማር ተያያዙ፡፡ የግራኝ ታሪክና ወታደራዊ አካሄድ እንደ አንድ ዋና ትምህርት ይሰጥ ነበር፡፡ ዋታኒ እስላማዊ ማሕበር በሚያዘጋጃቸው ክብረ በዓላት ላይ በአሕመድ ግራኝ ዙርያ የሚያጠነጥኑ ግጥሞችና የውዳሴ መዝሙሮችም ተዘጋጅተው በተማሪዎች ይዘመሩ ነበር፡፡ ሼኽ አብደል ረህማን ደግሞ በአዲስ አበባ ውስጥ በነበራቸው የመጻሕፍት መደብር አማካይነት በአረብኛ የተዘጋጁ የወሃቢያ መጻሕፍትን እያስመጡ ያከፋፍሉ ነበር፡፡ ነገር ግን ኋላ ላይ የትምህርት ሚኒስቴር ሆነው የተሾሙት ከበደ ሚካኤል ትምህርት ቤቱን በጎበኙበት ወቅት ለግራኝ የሚዜሙትን መዝሙሮች ትርጉም ከሰሙ በኋላ እንዳይዘመሩ ያገዱ ሲሆን አማርኛም የመማርያ ቋንቋ እንዲሆን አዘዋል፡፡[2]

ነገር ግን ከመንግሥት ይልቅ የዋሃቢዝም ዋና ጠላት የነበሩት ሼኽ አብደላህ ኢብን ሙሐመድ ኢብን ዩሱፍ (አብደላህ አል-ሐረሪ) የተሰኙ ሙስሊም ሊቅ ነበሩ፡፡ እኚህ ሰው የሃገራችን አብዛኛው ሙስሊም የሚከተለው በአንፃራዊነት ሰላማዊ ሊባል የሚችለው የሱፊ እስልምና ተከታይ ሲሆኑ ከፀረ ሰላም ትምህርቱ በተጨማሪ አሁን በዝርዝር የማናያቸውን የወሃቢዝም አስተምህሮዎች ይቃወሙ ነበር፡፡ ሼክ አብደላህ ከሐረር ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ውሏቸውን በመርካቶ አካባቢ በማድረግ ሙስሊሙን ህብረተሰብ በማስተማር ዝነኛ ሆነው ነበር፡፡ ኋላም ወደ ሊባኖስ በማቅናት በመካከለኛው ምስራቅ ትምህርታቸውን በማስፋፋት በዓለም ላይ ዋነኛ ፀረ ወሃቢዝም ለሆነው ዓለም አቀፍ እስላማዊ ማሕበር ሊቀ መንበር ሆነዋል፡፡[3] የኚህን

ኢትዮጵያዊ ትምህርት አረቦች “አሕባሽ” በማለት ይጠሩታል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሐጂ አብደላህ ከሐበሻ ምድር የመጡ መሆናቸው ነው፡፡ ትምህርቱ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ለዘመናት የኖረውና አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝበ ሙስሊም የሚከተለው የሱፊ እስልምና እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ ትምህርቱን የተቀበሉና ከኢትዮጵያዊው የተማሩ ሊቃውንት ስልጠናዎችን ለመስጠት ከሊባኖስ በመጡበት ወቅት ወሃቢዮች “መንግሥት አሕባሽ የሚባል አዲስ ሃይማኖት አመጣብን” በማለት ሁከት መፍጠር ጀመሩ፡፡ እነርሱ ባለ ሃገር ሆነው የሃገሪቱን የሱፊ ሊቃውንት ማሳደድና መግደል ተያያዙ፡፡ መንግሥትም የኢትዮጵያ ሕዝብ ቅሬታ እስኪገባው ድረስ ታገሳቸው፡፡ አሁንም አቅማቸው ቢሟስስም በየስርቻው መሽሎክሎካቸውንና “ድምፃችን ይሰማ” እያሉ በሰላላ ድምፆቻቸው መጮኻቸውን አልተውም፡፡

ሼኽ አብደላህ በአንድ ወቅት በሐረር ውስጥ በነበረው የወሃቢዮች ትምህርት ቤት ላይ ባስነሱት ተቃውሞ ምክንያት ለእስር ተዳርገው ነበር፡፡ አዲስ አበባ በነበሩበት ጊዜ ሐጂ ኢብራሂም ለአንድ የአረብኛ ጋዜጣ በፃፉት መጣጥፍ ክርስቲያናዊት ኢትዮጵያንና ንጉሡን ማጣጣላቸውን ለመንግሥት መረጃ እንደሰጡም ይነገራል፡፡ በዚህም ምክንያት ሐጂ ኢብራሂምና የትምህርት ቤቱ የወሃቢያ መምህራን ታስረው ለፍርድ የቀረቡ ሲሆን ሐጂ ኢብራሂም ከሐረር ከተማ ወደ ሌላ የኢትዮጵያ ክፍል ሄደው እንዲኖሩ ተፈርዶባቸዋል፡፡ እኚህ ሰው አሁን በሕይወት የሉም፡፡ ከዚያም ሼኽ አብደላህ የሐረር ከተማ ሙፍቲ ሆነው በመሾማቸው ምክንያት ወሃቢዮች ድምፃቸውን አጥፍተው ለመኖር የተገደዱበት ሁኔታ ነበር፡፡ የሐረር ወሃብዮች ኋላ ላይ በ1948 የሶማሌ ወጣቶች ክበብ ተብሎ በመንግሥት ፈቃድ በተቋቋመው ቡድን ውስጥ እጃቸውን አስገብተው የነበረ ሲሆን የአሕመድ ግራኝ መንፈስ እንደገና በመምጣት ከተማይቱ ላይ አንዣቦ ነበር፡፡ ነገር ግን ጥር 1948 ጉዳዩ ይፋ በመሆን 200 የሚሆኑ የክበቡ አባላት በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡ ወጣቶቹ ይቅርታ በመጠየቅ የተፈቱ ሲሆን ሰማንያ አንድ የሚሆኑ የወሃቢያን እንቅስቃሴ የሚመሩ የዋታኒ ማሕበር አባላት ከተማይቱን በመልቀቅ እንዲበተኑ ተደርጓል፡፡ በዚሁ ዓመት ኢትዮጵያ የኦጋዴን ግዛቷን በማግኘቷ ምክንያት በሐረርጌ ላይ ያላት ሙሉ ቁጥጥር እውን ስለሆነ በ1936 በሐረር ከተማ የተጀመረውም በወሃቢዝም የተመራው የእስላማዊ ፖለቲካ መነቃቃት ሊከሽፍ ችሏል፡፡[4]ኢትዮጵያዊ ትምህርት አረቦች “አሕባሽ” በማለት ይጠሩታል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሐጂ አብደላህ ከሐበሻ ምድር የመጡ መሆናቸው ነው፡፡ ትምህርቱ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ለዘመናት የኖረውና አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝበ ሙስሊም የሚከተለው የሱፊ እስልምና እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ ትምህርቱን የተቀበሉና ከኢትዮጵያዊው የተማሩ ሊቃውንት ስልጠናዎችን ለመስጠት ከሊባኖስ በመጡበት ወቅት ወሃቢዮች “መንግሥት አሕባሽ የሚባል አዲስ ሃይማኖት አመጣብን” በማለት ሁከት መፍጠር ጀመሩ፡፡ እነርሱ ባለ ሃገር ሆነው የሃገሪቱን የሱፊ ሊቃውንት ማሳደድና መግደል ተያያዙ፡፡ መንግሥትም የኢትዮጵያ ሕዝብ ቅሬታ እስኪገባው ድረስ ታገሳቸው፡፡ አሁንም አቅማቸው ቢሟስስም በየስርቻው መሽሎክሎካቸውንና “ድምፃችን ይሰማ” እያሉ በሰላላ ድምፆቻቸው መጮኻቸውን አልተውም፡፡

የደርግ መንግሥት ባጠቃላይ ሃይማኖትን በተመለከተ ከሚከተለው ፖሊሲ የተነሳ ያን ያህል የጎላ የወሃቢዝም እንቅስቃሴ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ውስጥ ለውስጥ የተሰሩ ሥራዎች እንደነበሩ እሙን ነው፡፡ በ1958 ከየመን በመጣ ስደተኛ የተመሰረተው የአል-አወልያ ትምህርት ቤት በዘመነ ደርግ ጥብቅ በሆነ የመንግሥት ቁጥጥር ስር ነበር፡፡[5] ደርግ ወደ መውደቂያው አካባቢ “የሰርገኛ መጣ…” ዓይነት የፖሊሲ ለውጦችን በማድረጉ ምክንያት ለሳዑዲ እንቅስቃሴዎችም በር ከፍቶ ነበር፡፡ በዚህም መሰረት የዓለም የሙስሊሞች ሊግ ከእርዳታ ማስተባበርያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን (እማማኮ) ጋር በመተባበር ትምህርት ቤቶችን፣ እጓለ ሙታንን እና ክሊኒኮችን ለማቋቋም ስምምነት አደረገ፡፡ መንግሥትና ሊጉ ያላቸው ግንኙነት መጥበቁን ከሚያመለክቱ ተግባራት መካከል አንዱ ሊጉ የሃይማኖትና የአረብኛ ቋንቋ ሥልጠናዎችን እንዲሰጥ መፈቀዱ ነበር፡፡ በ1991 ወደ ኢትዮጵያ ለጉብኝት የመጣው የሊጉ ልዑካን ቡድን በወሎ፣ በሐረር፣ በአዲስ አበባና በደብረ ዘይት ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ሥራ ላይ መሆኑን መግለፁ ኢትዮጵያን የማስለም እንቅስቃሴው በአዲስ መልክ መጀመሩን አመላካች ነበር፡፡[6]

ከ1991 ወዲህ የተደረገውን የመንግሥት ለውጥ ተከትሎ በሃገራችን ውስጥ የተገኘውን የእምነት ነፃነት ሽፋን በማድረግ ብዙ ጥፋቶች ተፈፅመዋል፡፡ በተለይ የወሃቢዝም ፍልስፍና ተከታዮች ነፃነቱ የሰጣቸውን ክፍተት በመጠቀም አክራሪ የሆኑ ትምህርቶችን በማስተማር  ግርምቢጠኛ ባህርያቸውም ከልክ አልፎ በሚያሰራጯቸው ጽሑፎችና የድምፅ እንዲሁም የምስል መልዕክቶች ሌሎች ሃይማኖቶችን በነገር በመጎሽመጥ ሃገሪቱን ሲያምሱ ቆይተዋል፡፡ የተሰጣቸውንም የመንግሥት ሥልጣን ለእምነታቸው ማስፋፍያ በመጠቀም ብዙ በደሎችን ፈፅመዋል፡፡ በአንድ ወቅት ከውጪ ሃገራት በገፍ በመግባት ሃገሪቱን ያጥለቀለቁት የጂሃድ ፊልሞችና አክራሪነትን የሚሰብኩ የህትመት ሥራዎች ያስከተሉትን ውጤት ሁላችንም በግልፅ ያየነው ነው፡፡ በተለይ ከሳዑዲ አረብያ በሚመጣው ፔትሮ ዶላር የተገነቡት መስጊዶችና እስላማዊ ማዕከላት  ሃገሪቱን እንደሙጃ ውጠዋታል፡፡ በበጎ አድራጎት ሥም ወደ ሃገር ውስጥ የገቡ በርካታ እስላማዊ ድርጅቶችም ውስጥ ለውስጥ ጂሃዳውያንን እያሰለጠኑና የገንዘብ ድጋፍ እያደረጉ ሃገሪቱን ቁልቁል ወደ ጥፋት አዘቅት ነድተዋታል፡፡ እቅዳቸው ተሳክቶ ቢሆን ኖሮ ሊከተል የሚችለውን አደጋ ማሰብ በእጅጉ ይከብዳል፡፡ አደጋውን ከማስቀረት አንፃር መንግስት ይበል የሚያሰኙ እርምጃዎችን ወስዷል፡፡ በተለይም የወሃቢዝም ዋነኛ የርቢ ማዕከል የሆነው አል-አወልያ እስላማዊ ትምህርት ቤት ከወሃቢዮች እጅ ወጥቶ ለተገቢው አካል መሰጠቱ ትክክለኛ እርምጃ ነበር፡፡ ይህ ከአንደኛ ደረጃ ተነስቶ በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በምስራቅ አፍሪቃም ጭምር ግምባር ቀደም እስላማዊ ትምህርት ቤት ለመሆን የበቃው የፅንፈኞች ማዕከል በሃገሪቱ ላይ ያሳደረው ተፅዕኖ ቀላል አልነበረም፡፡ የተወሰደው እርምጃ ከረፈደ በኋላ ቢሆንም ነገር ግን ከመሸ በኋላ አለመሆኑ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን በመርዛማ ትምህርቱ ተበክለው የወጡ ወጣቶች ክትትል ሊደረግላቸውና በፅንፈኝነት ቅልበሳ መርሃ ግብር (De-radicalisation Program) ሊታቀፉ ይገባል፡፡

በኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ላይ የደረሱ እስላማዊ ጥቃቶች የቅርብ ዘመን ትዝታዎች

ቀን ቦታ የሞተ የቆሰለ የክስተቱ ዝርዝር
6/2/97 አርሲ – ቆሬ 10 3 2237 ክርስቲያኖች ተፈናቀሉ፡፡ 1 ቤተ ክርስቲያንና 194 የክርስቲያን ቤቶች ሙሉ በሙሉ ተቃጠሉ፡፡ 24 የክርስቲያን ቤቶች በከፊል ተቃጠሉ፡፡ 304 ከብቶች ተዘረፉ፡፡
16/1/99 ጀምሮ ጂማ – በሻሻ 18 38 488 በግድ ሰልመዋል፡፡ ከ2000 በላይ ተፈናቅለዋል፡፡ ከ850 በላይ የክርስቲያን ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ 3 አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፡፡ 4 ተዘርፈዋል፡፡
ከላይ የተቀመጡት መረጃዎች የተወሰዱት “በኢትዮጵያ የሃይማኖት መቻቻል አለን” በሚል ርዕስ በአባ ሳሙኤል ከተዘጋጀው መጽሐፍ ገፅ 28-31 እና “አክራሪ እስልምና በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ በኤፍሬም እሸቴ ከተዘጋጀው መጽሐፍ ገፅ 172-175 ነው፡፡ ዓመታቱ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ናቸው፡፡

ቀን ቦታ የሞተ የቆሰለ የክስተቱ ዝርዝር
3/8/11 ጅማ – አሰንዳቦ 2 – በቁጣ የተሞሉ ሙስሊሞች አብያተ ክርስቲያናትን የማቃጠል ዘመቻ አድርገዋል፡፡
3/1/11 ባሌ – ሆማ ቀበሌ – 17 ወንጌልን ለማስተማር በወጡ የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ክርስቲያን ተማሪዎች ላይ ድብደባ ተፈፅሟል፡፡
9/13/10 አፋር – ዱፍቲ – 1 ከእስልምና የወጣን አንድ ክርስቲያን ወጣት ሙስሊሞች በስለት ወግተዋል፡፡
8/21/10 አዲስ አበባ – 1 ታዋቂ ክርስቲያን መሪ በበትር ተደብድቧል፡፡
7/16/2010 አዲስ አበባ – 1 ከእስልምና የመጣ ክርስቲያን በቁጣ በተሞሉ ሙስሊሞች ተደብድቧል፡፡
9/11/09 ሸዋ – ሰንበቴ – 3 የሙስሊሞች ቡድን ወደ ቤተ ክርስቲያን ግር ብሎ በመግባት በፀሎት ላይ የነበሩትን ክርስቲያኖች ክፉኛ አቁስለዋል፡፡
7/3/09 ደሴ 2 – በቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ በሥራ ላይ የነበሩ 2 ክርስቲያኖች ተኩስ ተከፍቶባቸው ተገድለዋል፡፡
9/20/08 አዲስ አበባ – 1 አንድ ዕድሜው 35 ዓመት የሚሆን ክርስቲያን መሪ ለሞት እስኪቀርብ ድረስ በሙስሊሞች ተደብድቧል፡፡
7/19/08 ጂጂጋ – 2 ሁለት ከእስልምና የመጡ ክርስቲያኖች በድንጋይ ተደብድበዋል፡፡
4/30/07 ጂጂጋ 2 3 ሙስሊሞች በድንኳን ውስጥ በተሰበሰቡ ክርስቲያኖች ላይ ቦምብ በመጣል 2 ክርስቲያኖችን ሲገድሉ 3 አቁስለዋል፡፡
1/5/07 ኮፈሌ 1 – ሙስሊሞች አንድ ክርስቲያን በብረት ቀጥቅጠው ገድለዋል፡፡
10/1/06 ጂማ 10 12 ሁለት አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፡፡
4/16/06 ጂጂጋ 3 23 በሁለት ምግብ ቤቶችና በአንድ ቤተ ክርስቲያን ላይ በሙስሊሞች በተፈፀመ የቦምብ ጥቃት የደረሰ አደጋ
3/22/06 አርሲ ነጌሌ 1 – ሙስሊሞች በአንድ የፕሮቴስታን ቤተ ክርስቲያን በር ፊትለፊት ከእስልምና የመጣን አንድ ክርስቲያን በጥይት ገድለዋል፡፡ ሟች የ 7 ልጆች አባት ነበሩ፡፡
7/19/05 ጂጂጋ 1 – የታጠቁ ሙስሊሞች አውቶብስ በማስቆም በውስጥ የነበሩትን ክርስቲያኖች ሸሃዳ አስብለዋል፤ ወደ መካም በመዞር እንዲሰግዱ አስገድደዋል፡፡ ይህንን ለማድረግ ፍቃደኛ ያልሆነ አንድ ወጣት ተገድሏል፡፡
መረጃዎቹ የተወሰዱት በክርስቲያኖች ላይ የሚደርሱትን እስላማዊ ጥቃቶች በመዘገብ ከሚታወቅ ክርስቲያናዊ ድህረ ገፅ ላይ ነው፡፡ ዓመታቱ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ናቸው፡፡

http://www.thereligionofpeace.com/pages/christianattacks.htm

ከላይ የተጠቀሱት ጥቃቶች ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ሲሆኑ ፍትህን በማዛባት፣ አድማ በማድረግ፣ የክርስቲያን ልጆችን አፍኖ በመውሰድ፣ አስገድዶ በመድፈር፣ አስፈራርቶ አካባቢን በማስለቀቅ፣ የክርስቲያን ይዞታዎችን በልዩ ልዩ ዘዴዎች በመንጠቅ፣ ወዘተ. የተፈፀሙ የግፍ ሥራዎችን ዘርዝሮ መጨረስ አይቻልም፡፡

[1] Haggai Erlich, Saudi Arabia & Ethiopia, 2007, p. 73

[2] Ibd, 80-83

[3] Ibd, 84

[4] Ibd, 85-92

[5] Ibd, 189-190

[6] ኤፍሬም እሸቴ፣ አክራሪ እስልምና በኢትዮጵያ፣ 2000፣ ገፅ 142-143


Thursday, August 18, 2016

ከመንጋ አድር ባይ ጳጳስ፣ ፓስተር፣ ቄስና ሼክ ተብዬ አንድ ሳበኬ ወንጌል ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ያቀረበው ማሳሰቢያ ይሻላል!


ለኢትዮጲያ የኢፌድሪ መንግስት ጠቅላይ ሚንስተር ለአቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እና አመራሩ።

ከፀጋአብ በቀለ(የወንጌል ሰባኪ)

          የየትኛውም የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም አራማጅ አይደለሁም፡፡ ጥሪዬ ስላልሆነ፡፡ ለፖለቲከኞች ግን አክብሮቴ ትልቅ ነው፡፡ በግሌ በዚህ መንግሥት ከቀበሌ እስከ ፌደራል ስላሉት መሪዎች እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡ ቃሉ፡-"ነፍስ ሁሉ በበላይ ላሉት ባለ ሥልጣኖች ይገዛ። ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና፤ ያሉትም ባለ ሥልጣኖች በእግዚአብሔር የተሾሙ ናቸው"(ሮሜ.13፡1) የሚለውን ቃል ስለማምን፡፡ እንዲሁም በእግዚአብሔር መንፈስ የተመራው ሐዋርያ "ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ"(1ጢሞ.2፡1) ስለሚል ሁለም እግዚአብሔር ማስተዋልና ጥበቡን እንድሰጣችሁ እፀልያለሁ፡፡ እግዚአብሔር መንግሥትን ያፈልሳል ደግሞም ሌላ ያስነሣል፡፡ እግዚአብሔር፡- "ጊዜያትንና ዘመናትን ይለውጣል ነገሥታትን ያፈልሳል፣ ነገሥታትንም ያስነሣል ጥበብን ለጠቢባን እውቀትንም ለአስተዋዮች ይሰጣል"(ዳን.2፡21)፡፡
ለመንግሥት ያለኝ አድናቆት

      በዚህ ሥርዓት እውነተኛና ሚዛናዊ ሕሊና ያለው ዜጋ ቀርቶ ዓለም ሁሉ ያደነቀው በትምህርት፣ በጤና፣ በኢኮኖሚ፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የብሔርሰቦች እኩልነት፣ በኢንቪስትመንት፣ በሃይማኖት ነፃነት፣ ...ረገድ የተገኘው ድል ትልቅ በመሆኑ ለዚህ ሁሉ አቅምና ኃይል የሆነን እግዚአብሔርን በማመስገን ለኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ያለኝ ግላዊ አድናቆቴን ከልቤ መግለጥ እፈልጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር የአገሬን ሕዝብና መንግሥት ይባርክ!

ለመንግሥታችን በትህትና የቀረበ ግልጽ መልዕክት                                                                                                                      
    በተቃራኒው ኃላፊነትና ሸክም እንደምሰማው እንደ አንድ የዚህች አገር ዜጋና የወንጌል አገልጋይ ስለዚህች አገር መጻኢ ሕይወት ሳስብና ስጸልይ ብሩህ ገጽታና ያን ለማጥፋት የሚታገል አሉታዊ ሁለት ገጽታዎች ይታዩኛል፡፡ በዚህም ይች አገር በመስቀለኛ መንገድ ላይ መሆኗ ተገነዘብኩ፡፡ እነዚህ ተግዳሮቶች በትክክል ከተጠቀምንባቸው የሚበልጥ ዕድገትና ለውጥ ይዞ የመጣ ሲሆን ካልተጠንቀቅን በዚህች አገር ትልቅ ጥፋትም ሊያመጣ የሚችል አቅም እንዳለሁ ስገነዘብ ባልተለመደ መንገድ ያልተለመደ ድምፅ ግልጽ አሰተያየት በትልቅ ትህትናና አክብሮት በማኅበራዊ ሚዲያ ለማቅረብ ወሰንኩ፡፡

1. የብሔር ብሔረሰቦች እኩልነት በሕግ መደንገጉ፤ ራስን በራስ ማስተዳደሩ፣ የራስን ቋንቋ፣ ባሕልና እሴቶች ማሳደጉ መልካም ሆኖ ሳለ ባለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ስለ ልዩነታችን፣ ስለመንደራችን፣ ስለብሔራችን፣ ስለጎጣችን እንድናስብ የተደረገውን ያህል ስለ አንድነታችንና ስለአገራችን እንድናስብና እንድንነጋገር አልተደረግንም የሚሉ ብዙዎች ናቸው፡፡
 ዓመታዊ የብሔር ብሔረሰቦችን ቀን ለአንድ ሳምንት ከማክበር ያለፈ፡፡ ዛሬ ከደቡብ ወደ ሰሜን፣ ከሰሜን ወደ ምዕራብ፣ ከምዕራብ ወደ ምስራቅ ሄዶ በነፃነት ከመሥራት ኢትዮጵያውያን ወደ ተለያዩ አገራት መሰደድን ይመርጣሉ፡፡ ለመገናኛ ብዙሀን ዜና ግብአት አንድነታችንን የሚያሳዩ ሰሞነኛ ዜናዎችና ትእይንቶች እንጂ ለእርስ በርሳችን ያለን እይታና ልብ እጅግ መጥበቡ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡
 ለምሳሌ፡- በቅርቡ በተነሳው ግጭት አንዳንድ አካባቢዎች ሌላውን ብሔር ለይቶ የማጥቃትና ከአካባቢያችን ውጡ የሚሉ ግልጽ መልዕክቶች ሲተላለፉ አይተናል፡፡ ሌላው ከኦሮምያ ዩንቨርሲቲ የጨረሱ ወጣት ተማሪዎች ወደ ሌሎች ክልሎች ሄደው ሥራ መሥራት እየቻሉ አይደለም፡፡ ምክንያቱም የአገሪቷን ብሔራዊ ቋንቋ አማርኛን ስለማይችሉ፡፡ በአብዛኛው የተማረ ኃይል ተምሮ እየተመለሰ ያለው ወደ መንደሩ ሲሆን ወደ ሌላ ስፍራ ሲሄዱ ተቀባይነት የላቸውም፡፡ ከዚህም የተነሣ በብዙ ወረዳዎች ዩንቪርሲቲ የጨረሱ ወጣቶች ሥራ ፈተው ይቀመጣሉ፡፡ ሥራ የፈታ አዕምሮ ደግሞ አደገኛነቱ የታወቀ ነው፡፡
 ያ ሚዛናዊ ሥራ እንደሚገባው ባለ መሠራቱ አሁን የገባንበት አንዳንድ ተግዳሮቶች ተጨባጭ ማስረጃዎችና ገሃዳዊና ጊዜ የማይሰጣቸው የለውጥ ጥሪ ናቸው፡፡ ለዚህ ትክክለኛ ጥሪ መንግሥት የተቃዋሚዎች ድምፅ አድርጎ ከመደምደም ይልቅ ትክከለኛ ምላሽ ቢሰጥ የሚል የብዙዎች ጩኼት ነው፡፡
 መንግሥታችን ያለፈውን ድልና ስኬት ብቻ ሳይሆን በብዙዎች ልብ በቅሎ ምድሪቷ ወዳልተፈለገው አቅጣጫ ሊወስዳት እየታገለ ያለውን በብሔርና በቋንቋ ላይ ያውጠነጠነ አደገኛ ጽንፈኝነት ላይ በጥንቃቄ መሥራት አለበት፡፡ ተሐድሶ የግድ ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ ጠባብነት ታላቅቷን ሶቪየት ኅብረት፣ ዩጎዝላቪያ ...የሕዝብን ጭፍጨፋ፣ መፈናቅሎችና የአገር መፋራረስና የሩዋንዳውያን መተላለቅ ምክንያት መሆኑን ምሁራን ይጠቅሳሉ፡፡ በብዙ አስቸጋሪ መንገድ ውስጥ ሄዶ ለዚህ የበቃውና ሕዳሴን መለያው ያደረገ መንግሥት ይህን ማድረግ ቀላል ባይሆንም አይችልም የሚል ልብ ግን የለኝም፡፡ ይህን እውን ለማድረግ መንግሥት ብቻውን አይደለም፡፡ ዜጎች ሁላችንም እጅ ለእጅ ተያይዘን መሥራት አለብን፡፡ መንግሥት በዚህ ላይ ለመሥራት ካልፈቀደ ግን መጪው መልካም እንዳልሆነ የማገለግለው የሕያው አምላክ መንፈስ አመልክቶኛል፡፡

ቤንጃሚን ፍራንከሊን የተባሉ ሊቅ ሲናገሩ፡- "የፖሊሲ ማሻሻያ ማድረግ እንደ ሞት ሽረት የሚቆጥሩ መንግሥታት በተፈጠሩበት ቆዳ ተጠቅልለው የሚሞቱ ናቸው፡፡ አንድ አገር ወይም ሕዝብ የሚመራበት ፖሊሲ፣ ስትራቴጂዎችና ርዕዮተ ዓለማዊ ፍልስፍናዎች እንደ ተጨባጭ ዓለማዊ ሁኔታ ወይም ሕዝቡ ከደረሰበት የግንዛቤና የውጤት ደረጃ አንፃር መቃኘት አለባቸው፡፡ ይህን ማድረግ አለመቻል ነው ጉዞን የሚያደናቅፈው፡፡"

2. መንግሥት የደጋፊዎችን ድምፅ ብቻ ሳይሆን የተቃዋሚዎችንም ድምፅ ከዚህ በበለጠ ቢሰማ መልካም ነው፡፡ (በስሜት የሚደገፍ የደጋፊዎች ድምፅ አንዳንዴም መንግስት እውነቱን ሊጋርደው ይችላል) የሚሰራው ፖለቲካ እንጂ የሃይማኖት ህግ አይደለም። ዴዝመንድ ቱቱ እንዳሉት፡" ሰላም ከፈለክ ከወዳጅ ጋር ሳይሆን ከጠላት ጋር መንጋገር ጀምር" እንዳሉት የተለያየ ርዕዮተ ዓለም መከተል ጠላትነት ባይሆንም እኛ ከሚንለው የተለየ ፍልስፍና ላላቸው ሰዎች ትክክለኛ ቦታ ልኖረን ይገባል፡፡ ሁለታችንም ለአንድ አገር ጥቅም እስከቆምን ድረስ፡፡ ይህን የሚንለው ብዙውን ጊዜ የፖለቲካው ምህዳር ከቀን ወደ ቀን እየጠበበ እንደመጣና አሳታፍ አይደለም በማለት አንዳንዶች በተስፋ ቁረጥ ስናገሩ ይሰማልና፡፡ ይህ ደግሞ ለዲሞክራሲያዊ ግንባታ አይበጅም፡፡

3. መንግሥት ቀርቶ መላዕክትም ይሳሳታሉ፤ ስለዚህ መንግሥት አንዳንዴ ገሃዳዊ ስህተት ሲፈጽም ይቅርታን ይጠይቅ፡፡  (እንደሚሳሳት አምኖ ለፈፀመው ስህተት ይቅርታ አለመጠየቅ ግብዝነት ነው)

መደምደሚያ
    መንግሥት ጠባብነት፣ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዳሉ አምኖ ደጋግሞ በመገናኛ ብዙሃን ስናገር ይሰማል፡፡ ይህም ትልቅ ነገር ነው፡፡ ብርቱ አቋም፣ ጠንካራ እርምጃ ከእያንዳንዱ ዜጋ ይጠበቃል፡፡ ከላይ የተዘረዘሩ ሀሳቦች አዲስ ባይሆኑም አዲስ ትኩረት ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ይፈልጋሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ የትላንቱ ታሪክ ታሪክ ነው፡፡ መጥፎም ይሁን ጥሩ፡፡ የእኛ ታሪክ ነው፡፡ ያለፈው ታሪክ አይለወጥም፤ አይከሰስም፡፡ ዛሬ የተሻለ ነገር ከሠራን ግን መልካም ታሪክ ሆኖ ነገ ይጻፋል፡፡ መልካም ታሪክ በሠራን መጠን የትላንቱ አሉታዊና የማንፈልገው ታሪካዊ ገጽታዎች እየተዋጡ ይመጣሉ፡፡ የትላንቱን አሉታዊ የታሪክ ክስተት ለበቀልና ለህቡዕ የጥፋት አጀንዳ እየመዘዝን ከተጠቀምንበት ግን የጥፋት ሠራተኞች እንሆናለን፤ ምድራችንን የደም መሬት እናደረጋታለን፡፡ ከመጥፎ ታሪክ ጋር ሁልጊዜ ስማችን እየተጠራ ይኖራል፡፡ ስለዚህ መልካም ታሪክ ለመሥራት መልካም አመለካከት ይኑረን፡፡

 ትልቁ ችግራችን ችግሮቻችንን ያየንበት ዓይን እንጂ ያለፉም ሆኑ አሁን ያለንበት ችግሮቻችን በራሳቸው ከአሉታዊ አመለካከቶቻችን በላይ አደገኞች አይደሉም፡፡ ችግሮቻችን ከእኛ በላይ ትልቅ አይደሉም፡፡ ችግሮቻችን አደገኛ መሆን የሚጀምሩት እኛ ፈጥረናቸው መፍትሔ በመስጠት ማስወገድ ሲገባን እኛን መፍጠር ወይም መምራት ሲጀምሩ ብቻ ነው፡፡

 
ሰላም፣ ብልጽግና፣ ዕድገት፣ ለውጥ፣ አንድነት፣ ፍቅር በአገራችን ለሚገኙት ብሔር ብሔረሰቦችና መንግሥት ይሁን፡፡


እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!
ፀጋአብ በቀለ/ሐዋሳ/ ነሐሴ 4/12/2008 ዓ.ም

ይህን ፅሁፍ ከጠቅላይ ሚንስተሩ እጅ ይደርስ ዘንድ ሼር በማድረግ የበኩሎን ይወጡ።

Tuesday, August 9, 2016

ተገቢ ትኩረት የሚያሻው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ካህናት አቤቱታ!



በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ያሉ አጠቃላይ ማኅበረ ካህናቱ በአቤቱታ ድምጻቸው  ወቅታዊ፤ ትክክለኛና አፋጣኝ ምላሽ የሚያስፈልገው አቤቱታ አቅርበዋል የሚል እምነት አለን። ይህንን አቤቱታ ዝም ብሎ ማለፍ በቤተክርስቲያኒቱ አጠቃላይ ውድቀት ላይ ከኤጲስቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ ስህተቶች ጋር ተባባሪ መሆን ብለን እናምናለን።
ዘረኝነት፤ ጉቦና የኃጢአት ገመና እንዲህ እንደዘንድሮው ታይቶም፤ ተሰምቶም አይታወቅም። ማኅበረ ቅዱሳን በትክክል ቤተ ክርስቲያኒቱን መቆጣጠሩን ያስመሰከረበት ጊዜ ቢኖር በዚህ የኮሚቴ ምርጫ የታየው የኩነኔና የፍርድ መዝገብ በአደባባይ መነገሩ ነው። ዘረኝነት ቦታውን ተረክቧል። ሙስናው በግልጽ ይታያል። ድሮም ቢሆን በእነጉድ ሙዳይ የሚመራ ኮሚቴ ከዚህ ዓይነቱ ቆሻሻ ተግባር የራቀ ሊሆን እንደማይችል የነበረን ግምት ትክክለኛ ነበር።
የኛም ግምት ስህተት እንዳልነበር የሚያሳየው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ካህናት ድርጊቱን በመመልከት ቀጥተኛ አቤቱታ ማቅረባቸው ሲሆን ለካህናት ጩኸት ጆሮ ሊሰጠው ይገባል እንላለን። ፓትርያርክ ማትያስም ለራሳቸው ክብርና ስም፤ ታላቂቱ ቤተክርስቲያኒም ከተደቀነባት ውርደት ማዳን ካለባቸው ጊዜው አሁን ነው። የካህናቱን አቤቱታ እዚህ ያንበቡ!








Sunday, August 7, 2016

ሕይወት የሆነን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ብቻ ነው!


ቅዱሳንን ማክበር እንደሚገባ ምንም ጥያቄ የለንም። መታሰቢያን በተመለከተም የድርጊቶቻችን አፈፃፀም የሁሉ ነገር ባለቤት የሆነውን እግዚአብሔርን ስምና ክብር እስካልጋረደና  እስካልተካ ድረስ የሚደገፍ ነው። ነገር ግን  «ጥቂት አሻሮ ይዞ፤ ዱቄት ወዳለው መጠጋት» የሚለውን ብሂል ለመተግበር መሞከር ግን አደገኛ ነገር ነው። በተለይም በሃይማኖታዊ አስተምህሮ ወቅት ወንጌል እንደዚህ ስለሚል፤ እኔም እንደዚህ ብል ችግር የለውም የሚለውን ራስን መሸሸጊያ ምክንያት በማቅረብ ለመከለል መሞከር ፀረ ወንጌል ነው። በእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ሥር ኑፋቄና ክህደትን ማስተማር በአምላክ ፊት ያስጠይቃል። እግዚአብሔር ሁሉን ማድረግ ስለሚችል የኛን ተረት ሁሉ ይሰራልናል ማለት አይደለም። ብዙ ጥያቄዎች የሚነሱትና እነዚህ የመሳሰሉ የስህተት ችካሎች አልነቀል ያሉት በምክንያት ስር በመደበቃቸው ነው።
ቅዱሳንን በማክበርና በመውደድ ሽፋን ወደአምልኮና ተገቢ ያልሆነ ሥፍራ ወደማስቀመጥ ያደገው መንፈሳዊ በሚመስል ማሳሳት ተሸፍኖ ነው።
ለክርስቲያኖች ድኅነት ዋናው ቁልፍ የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነው። ከዚህ ውጪ ያለው የማንም ሰው ሞትና ትንሣኤ ለመዳናችን ላይ የሚያመጣው ለውጥ የለም። አይጨምርልንም፣ አይቀንስልንም። ማዳን የእግዚአብሔር ነውና
ኢሳይያስ 43፣11
"እኔ፥ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፥ ከእኔ ሌላም የሚያድን የለም"
ይህ የተሠጠን የቃሉ እውነት እንደተጠበቀ ሆኖ የጌታ እናት የድንግል ማርያም ሞትና ትንሣኤ ለክርስቲያኖች ዘላለማዊ ድኅነት መስጠት ይችላል? ወይ ብለን ብንጠይቅ መልሱ አይችልም ነው። ታዲያ በድንግል ማርያም ሞትና ትንሣኤ ላይ ጥንታዊያን የሚባሉ አብያተ ክርስቲያናት የተለየ ሃይማኖታዊ ትኩረት የሚሰጠው ለምንድነው? ልዩ ልዩ ሃይማኖታዊ ትርጉምና ትረካ የሚገልፁበትስ ምክንያት ለምን ይሆን?

እንኳን እኛ ጠያቂዎቹ ራሳቸው በትክክል ምክንያቱን የሚያውቁ አይመስለንም። የሆኖ ሆኖ ትርክታቸውን ለመዳሰስ እንሞክራለን።

ስለማርያም እረፍት፤ ትንሣኤና እርገት አብያተ ክርስቲያናት አንድ ዓይነት የእምነት አቋም የላቸውም። ካቶሊኮች በጥር ሞቶ በነሐሴ መቀበር የሚለውን ታሪክ አይቀበሉም። በየዓመቱ ነሐሴ 8 ያከብራሉ። በሌላ መልኩ ንዲያውም ስለማርያም ሞትና የእርገት ዕለት በግልጽ የሚታወቅ ማስረጃ እንደሌለ በ5ኛው ክ/ዘመን  የኖረው የሳላሚሱ ኤጴፋንዮስ   ተናግሯል።  ዕረፍቷና እርገቷ በኢየሩሳሌም እንደሆነ  የሚናገሩ ቢኖሩም  ይህንን አባባል የማይቀበሉ አብያተ ክርስቲያናትና የቴኦሎጂ ምሁራን ሞልተዋል። በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚለውን አባባል የማይቀበሉበትን ማስረጃ ሲያቀርቡም ዮሐንስ በወንጌሉ ላይ እንደተናገረው «እናትህ እነኋት አለው። ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት»  ዮሐ19፤27 ባለው መሠረት ማርያም እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ ከዮሐንስ ጋር ስለኖረችና ወንጌላዊው ዮሐንስም ከጌታ ሞት በኋላ በኢየሩሳሌም  ጥቂት ዓመታትን ከቆየ በኋላ በ37 ዓ/ም ገደማ ወደ ቤዛንታይን ከተማ ኤፌሶን ሄዶ ወገኖቹን ወንጌል እያስተማረ መቆየቱንና  ማርያም በሞት እስከተለየችው ድረስ  ከ48-52 ዓ/ም እዚያው እንደነበር ብዙ ተጽፏል። ሌሎቹ ደግሞ ኤፌሶን መኖሯን ይቀበሉና ያረፈችው በኢየሩሳሌም ነው ይላሉ።
 ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን ነበረች ባዮች በቅርብ ርቀት ባለችው ደሴተ ፍጥሞም  በግዞት መኖሩ መኖሩና ከዶሚኒሽን አገዛዝ ቀደም ብሎ የራእይ መጽሐፉን  ከ55-65 ዓም ገደማ ስለፃፈ የማርያምም ቆይታ እስከዚያው ድረስ በኤፌሶን ነበር ይላሉ።
እንደዚህ ከሆነ  ማርያም በኤፌሶን ከዮሐንስ ጋር ኖራለች  ወይስ አልኖረችም ነው ጥያቄው።  በኢየሩሳሌም አርፋለች የሚሉ ሰዎች አንድም ጊዜ ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን ኖራለች ሲሉ አይደመጥም። ለምን?  ዮሐንስ ማርያምን እንደእናት ሊይዛት አደራ ተሰጥቶታል የሚባል ከሆነ ከዮሐንስ ጋር ኤፌሶን ስለመቀመጧ የማይነገረው ለምንድነው?  ዮሐንስ እስከ 96 ዓመቱ ድረስ ከኤፌሶንና ከደሴተ ፍጥሞ ውጪ ስለመኖሩ የተነገረ ነገር የለም። ማርያም ከዮሐንስ ጋር በኤፌሶን አልኖረችም ብሎ በመከራከርና ከኤፌሶን መጥታ ኢየሩሳሌም  ማረፏን በግልጽ በመናገር  መካከል ልዩነት አለ።  «እነኋት እናትህ» ባለው መሰረት አብረው ኤፌሶን ኖረው እዚያው ማረፏን የማይቀበሉና  የለም፣ ኢየሩሳሌም  አርፋለች የሚሉ ሰዎች የታሪክም፣ የጊዜም ልዩነት አላቸው።

 ወይ ደግሞ ኤፌሶን ላይ እድሜውን ሙሉ የኖረው ዮሐንስ ከማርያም ጋር ተለያይተው ነበር ሊሉ ይገባል።
ሮበርት ክሬው የተባለ የነገረ መለኮትና የታሪክ ጸሐፊ ዮሐንስ ወንጌላዊ ዘመኑን ሁሉ በኖረበት ከኤፌሶን ከተማ 8 ኪሎ ሜትር ወጣ ብላ ባለች ኰረብታ ላይ በተሰራ ቤት ውስጥ እንደኖረና ማርያምም እዚያ ማረፏን ጽፏል።  ይህንን በኤፌሶን ያለውን የማርያምን መቃብር የዓለም ክርስቲያኖች እንዲሆም ሙስሊሞች ሳይቀሩ ይጎበኙታል፤ ይሳለሙታል።  በቱርክ ግዛት ያለው ይህ ስፍራ በቱርካውያን ሙስሊሞች ዘንድ «ሜሪዬ ማና» ተብሎ ይጠራል።

ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ ዓለም የተለየችው መቼ ነው? በሚለውም ጥያቄ ላይ ጥንታዊያን አብያተ ክርስቲያናት የሚባሉት የምሥራቁና የምዕራቡ ጎራዎች የተለያየ አመለካከት አላቸው።
 በተወለደች በ58 ዓመቷ ዐርፋለች የሚሉ አሉ። በ72 እና 63 እድሜዋም አርፋለች የሚሉ መረጃዎች አሉ። እንደ ግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ግን የሚታመነው በ64 ዓመት እድሜዋ ማረፏ ነው።  ኖረችበት ተብሎ ከሚገመተውና አርፋለች ከሚባለው ቦታ ያለው ልዩነት እንዳለሆኖ በጥር ወር ከዚህ ዓለም በሞት ተለይታ በ40ኛው ቀን ማረጓን የሚናገሩ አሉ። በነሐሴ ወር አርፋ ከተቀበረች በኋላ ትንሣኤዋን ሳያዩ መቃብሯ ባዶ ሆኖ ስላገኙት ሐዋርያት ሱባዔ ይዘው በሦስተኛው ቀን ተገለጸችላቸው የሚሉም አሉ። እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ደግሞ በጥር ሞታ፤ በነሐሴ ተቀበረች የሚል ትምህርት አለ። በጥር ወር አርፋ፤ በነሐሴ ተቀብራለች የሚሉ ሰዎች ሥጋዋ በገነት ዛፍ ስር ለስምንት ወራት መቀመጡንና በሱባዔ ጸሎት በተደረገው ልመና የተነሳ ለመቀበር መቻሏን አስፋፍተው ይነግሩናል። ከጥር እስከ ነሐሴ ድረስ ለ8 ወራት ማርያም አልተቀበረችም።

 በጥር ወር እንዳረፈች፤ ለመቀበር ያልተቻለውም ታውፋንያ የሚባል ሽፍታ፤ ጎራዴ ሲመዝባቸው ወደ ቀብር ሥጋዋን ተሸክመው ይሄዱ የነበሩት ሐዋርያት በመፍራት ጥለዋት በመሸሻቸውና ዮሐንስ ብቻውን ቀርቶ ወደ  መቃብር ሳትገባ ወደ ገነት ዛፍ ስር በመወሰዷ ይባላል።  ነገር ግን የገነት ዛፍ ማለት ምን ማለት እንደሆነና በገነት ዛፍ ስር የሰው ሬሳ እንዴት ሊቀመጥ እንደሚችል አንድም ጽሑፍ በአስረጂነት ሲቀርብ አላየንም።

 ይህ በጥያቄነቱ ይቆየንና ታሪኩን እንቀጥል። ዮሐንስም ወደቤቱ ማምራቱንና ሸሽተው የነበሩትም ሐዋርያት ሥጋዋስ የታለ? ብለው ቢጠይቁት በገነት ዛፍ ስር መቀመጧን  ስለነገራቸው ዮሐንስ ገነት ዛፍ ሥር ሬሳዋ መቀመጡን አይቶ  እኛስ ለምን ይቀርብናል በማለት ነሐሴ 1 ቀን 49 ዓ/ም የጾም፣ የጸሎት ሱባዔ አውጀው በ15ኛው ቀን ትኩስ ሬሳ ከገነት ዛፍ ስር እንደመጣላቸውና በጌቴሴማኒ እንደቀበሯት ይናገራሉ።  ዮሐንስ በገነት ዛፍ ሥር ስትቀመጥ አያት የሚለውን ተረት እውነት አድርገን ብንቀበለው እንኳን ዮሐንስ ሀገረ ስብከቱ የሆነውንና እስከ መጨረሻው ጊዜውም የኖረበትን ኤፌሶንን ትቶ ወደኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር ወይ? እንድንል ያደርጋል።

ሌላው ጥያቄ የሚያስነሳው ነገር  በጥር ወር አርፋ  ለቀብር ሲሄዱ ሽፍታ በፈጠረው ሁከት ሐዋርያቱ ስለሸሹ ወደገነት ዛፍ ስር ስለመወሰዷ ዮሐንስ ለሐዋርያቱ ከነገራቸው በኋላ ለስምንት ወራት የመቆየታቸው ምክንያትና ዮሐንስ ያየውን ማየት አለብን ያሉበት የጊዜና የሃሳብ አለመገጣጠም ጉዳይ አስገራሚ ይሆንብናል።
ዮሐንስ እንደነገራቸው ማየት አልፈለጉም ነበር? ከስምንት ወራት ቆይታ በኋላስ ማየት የፈለጉት ምንድነው?
ይህ ሁሉ ሲሆን የማርያም ሥጋ በተባለው የገነት ዛፍ ሥር ተቀምጧል። ሐዋርያቱ ሱባዔ ባይገቡ ኖሮ ሥጋዋ ምን ሊሆን ነበር? አይታወቅም። ዘግይቶም ቢሆን የሐዋርያቱ ሱባዔ ችግሩን ለማቃለል ችሏል።

የሚያስገርመውና የሚያስደንቀው ትርክት በጥር ወር አርፋ ሳይቀበር የቀረውን የማርያምን ሥጋ በስምንተኛው ወር ከገነት ወጥቶ ከተሰጣቸውና ከቀበሯትም በኋላ ማርያም ከመቃብር ተነስታ ስታርግ ሐዋርያቱ ለማየት አለመታደላቸው ነው።  ሐዋርያቱ ቀብረዋት ወደ ቤታቸው  ከገቡ በኋላ ከሐዋርያቱ አንዱ የነበረውና በቀብሯ ላይ ያልተገኘው ቶማስ የተባለው ሐዋርያው በደመና ተጭኖ ከህንድ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለስ ማርያምን ሐዋርያት በቀበሯት በሦስተኛው ቀን ወደ ሰማይ ስታርግ የዳመናው ጎዳና ላይ ያገኛታል።  መላእክት አጅበዋት ሲሄዱ ያገኛት ቶማስ ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፣  አሁን ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ልቀር ነው? ብሎ ራሱን ከዳመናው ሠረገላ ላይ ወደመሬት ሊወረውር ሲል ቶማስ አትዘን፣ ትንሣኤዬን ያላንተ ማንም አላየም ካለችው በኋላ ለማየቱ ማስተማመኛ እንዲሆነው የተገነዘችበትን ጨርቅ እራፊ ሰበን ለምልክት ሰጥታው እንዳረገች ሰፊ ታሪክ ይነገራል።

ሰዎቹ ነገሩን ሁሉ ለማጣፈጥ የሚጠቀሙበት ነገር አስገራሚ ነው። የሰው ልጅ ከትንሣኤው በኋላ የዚህን ዓለም ጨርቅና ልብስ እንደተሸከመ ወደ ሰማይ ይገባል? ብለን እንድንጠይቃቸው ይጋብዙናል። እንደዚህ የሚናገር ክርስቲያናዊ አስተምህሮስ አለ ወይ? የሚል ጥያቄን ያስነሳል። ወንጌል ከትንሣኤ በኋላ ክርስቶስን ይመስል ዘንድ  ይለወጣል ይላል እንጂ የመቃብሩን ልብስና ሰበን እየተሸከመ ያርጋል የሚል ትምህርትን አይነግረንም።
« 2ኛ ቆሮ 3፤18
እኛም ሁላችን በመጋረጃ በማይከደን ፊት የጌታን ክብር እንደ መስተዋት እያብለጨለጭን መንፈስ ከሚሆን ጌታ እንደሚደረግ ያን መልክ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንለወጣለን»

ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን በመቃብሩ የተገነዘበትን ጨርቅ ትቶ መነሳቱን እንጂ  ያንኑ ለብሶ መነሳቱን አላነበብንም።
ዮሐ 20፤6-8. «ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት መጣ ወደ መቃብሩም ገባ፤ የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፥ ደግሞም በራሱ የነበረውን ጨርቅ ለብቻው በአንድ ስፍራ ተጠምጥሞ እንደ ነበረ እንጂ ከተልባ እግሩ ልብስ ጋር ተቀምጦ እንዳልነበረ አየ»
የሁላችን አማኞች ትንሣኤ የክርስቶስን ትንሣኤ መምሰል ካለበት በቀብር ወቅት ከዚህ ዓለም ጉድጓድ የገባ ጨርቅ ወደ ሰማይ አብሮን የሚያርግበት ምንም መንገድ የለውም። ስለዚህ ከምድራዊ ማንነት ወደተለየ ሰማያዊ ማንነት እንሻገራለን እንጂ እንደሀገር ጎብኚ ጓዝ ይዘን የምንሄድበት ታሪክ ፀረ ወንጌልና ፈጠራ ላይ የተመረኮዘ ተረት ከመሆንአአያልፍም።
ስለዚህ ተጠራጣሪ እንደሆነ ሁል ጊዜ የሚነገርበት ቶማስን በማርያም ትንሣኤ ላይ ግን የተለየ ተጠቃሚ እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ  ሲባል ማርያም ወደ ሰማይ ስታርግ የመቃብሯን ከፈን ተሸክማ የሄደች በማስመሰልና ለምልክት ይሆን ዘንድ ከፍላ  ሰጠችው የሚለው አባባል በአንዳችም ነገር  ከወንጌል እውነት የተጠጋ አይደለም።
ሌላው ነገር በመንፈስ ቅዱስ በመነጠቅ፤  በሌላ ስፍራ ወዲያውኑ መገኘት ስለመቻል ለሐዋርያው ፊልጶስ  ከተነገረው የወንጌል ቃል  በተለየ በዳመና ላይ ተቀምጦ ስለመሄድ ግልጽ የሆነ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ባይኖርም የቶማስን ጉዞ ከህንድ ወደ ኢየሩሳሌም መመለስ እንደፊልጶስ መነጠቅ አድርገን ብንቆጥረው እንኳን የቶማስ ሰብአዊነትና የማርያም የትንሣኤ እርገት የተለያየና ፈጽሞ የማይገናኝን ነገር ለማቀራረብ መሞከር ነው።  የቶማስን የዳመና ላይ ውይይትን ከረቂቅ  ክርስቶሳዊ አዲስ ፍጥረት ጋር ለማገናኘት መሞከር የጥንቶቹን የግሪክ ወጎች/fable story/ እንድናስታውስ ያደርገናል። በግሪኮች የተረት ታሪክ "ጁፒተርና ሳተርን ተጋብተው ቬነስን ወለዱ" የሚል ታሪክ አለ። ይህ ታሪክ የገሀዱ ዓለም ተቃራኒ መሆኑን ማንም አይስትም። ቶማስና የማርያም ነፍስ የዳመናው ሜዳ ላይ ሰፊ ውይት አደረጉ. የተሸከሟት መላእክትም ጉድ፣ ድንቅ እያሉ ውይይቱን ይከታተሉ ነበር ዓይነት አባባል ከግሪኮች ጥንታዊ የተረት የተቀዳ ይመስላል።
በሞትና በትንሣኤ እንዲሁም በእርገት መካከል እንደዚህ ዓይነት ነገሮችን እግዚአብሔር በሰውኛ ትረካ ይጫወታል ማለት እግዚአብሔር ስለሞትና ትንሣኤ በተናገረው መቀለድ ይሆናል።
ከሁሉ የሚገርመው ደግሞ ማርያምን በጥር ሞታለች ያሉ ሰዎች፤  በመጀመሪያው ሞት ዮሐንስ ብቻ እድለኛ ሆኖ በገነት ዛፍ ስር ለማየት መቻሉ አንዱ ክስተት ሲሆነረ በኋለኛውም ቀብር ቶማስ ብቻ ተጠቃሚ የሆነበትን የእርገት እድል፤  ሌሎቹ ሐዋርያት ለማግኘት ባለመቻላቸው ሐዋርያቱ ሁለተኛ እድል ያመለጣቸው መሆኑ ነው።   ተረቱን የሚያቀናብሩት ሰዎች ለዚህም መላ አስቀምጠዋል።
ሐዋርያቱ ቶማስ በዳመና ላይ ያገኘው እድል ለምን ያምልጠን ብለው በቀጣይ ዓመት ነሐሴ1 ቀን 50 ዓ/ም ጀምረው ሱባዔ ለመያዝ መገደዳቸውንና በ16ኛው ቀን ኢየሱስ ክርስቶስ ማርያምን ከገነት አምጥቶ አሳያቸው።
ሁለተኛ  ትንሣኤና እርገትን ለማየት የመቻላቸው ነገር  አስደናቂ ትርክት ነው።
ቀብር ሳይኖር ትንሣኤዋንና  እርገቷን እንዴት ማየት እንደቻሉ ግልጽ አይደለም። በምሳሌ ይሁን በምትሃት እርግጠኝነቱን ያብራራ ማንም የለም።  ሁለት ጊዜ ትንሣኤና እርገትስ ማለት ምን ማለት ነው?
ዛሬም ድረስ ትንሣኤና እርገቷን የተመለከተውን ሱባዔ በማሰብ በየዓመቱ የሱባዔ ጺም ይደረጋል። የዘንድሮውም ነሐሴ 1/2008 ዓ/ም ተጀምሯል። የድሮውን ለማሰብ ነው ወይስ እንደገና ለማየት?

ሌላው  ደግሞ  ማርያምን መንበር፤ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፤ እስጢፋኖስን ገባሬ ዲያቆን አድርጎ በመቀደስ አቁርቧቸዋል የሚለው  ትረካ እርገቷን ተከትሎ የመጣው አባባል ነው። የማርያም ነፍስ እንዴት መንበር መሆን እንደሚችል? ምን የሚባለው ቅዳሴ እንደተቀደሰ? ለማወቅ አልተቻለም።   ሰራዔ ካህኑ ክርስቶስ የማንን ሥጋ  እንደቆረበ? እንዲነግሩን ግን እንጠይቃቸዋለን። ለየትኛው ድኅነት/መዳን/ እሱ ይቆርባል?  ክርስቶስ ቀደሰ እንጂ አልቆረበም ማለት አንድ ነገር ነው።  ቆርቧል የሚባል ከሆነም ምክንያትና ውጤቱን የሚተነትን ትምህርት አያይዞ ማቅረብ የግድ ይላል። እሱማ የሕይወት ምግብ ሰጪ እንጂ ተቀባይ አይደለም የሚባል ከሆነም  ሰራዔ ካህናት በዚህ ምድር መቅደስ ውስጥ ከመቀደስ ባሻገር መቁረብ አይጠበቅባቸውም በማለት አብነታዊ የክህነት አስተምህሮን አያይዞ ማቅረብ  የተገባ ይሆናል። ቀድሶ አለመቁረብን ከክርስቶስ አብነት መውሰድ ይቻላል እያሉ ነው።
እንግዲህ ማርያምን እንዴት መንበር አደረጋት፤ ክርስቶስ ሰራዔ ካህን ሆኖ  ያልታወቀ ቅዳሴ ቀደሰ ማለትስ ምንድነው?
  ስለማርያም  ትንሣኤና እርገት ማጠናከሪያ በማቅረብ ትዕይንቱን  ተአማኒ ለማድረግ ካልሆነ በስተቀር አንድም እውነትነት የለውም። እንደተለመደው አባባል ቅዳሴ እግዚእ ነው የተቀደሰው የሚል  ካለም ክርስቶስ ራሱን በሁለተኛ መደብ አስቀምጦ « ነአኩተከ አምላክ ቅዱስ፤ ፈጻሜ ነፍስነ፤ ወሀቤ ሕይወትነ ዘኢይማስን»  ሲል አይገኝም።  ራሱ ሕይወት ሰጪ ሆኖ ሳለ ሕይወት ይሰጠው ዘንድ አይለምንምና ነው። እንደዚህ ዓይነቱ አደገኛ ክህደት፤ ሰዎች ለማርያም ባላቸው ፍቅር ውስጥ ተደብቆ ለዘመናት ቆይቷል።

በጉ መስዋእቱን ለሕይወታችን ሰጥቷል። ከዚያ ውጪ እሱ  በመንግሥቱ የፍርድ ሰዓት ዳግመኛ ሊመጣ ካልሆነ በስተቀር ከማእዱ አይካፈልም።«ሰዓቱም በደረሰ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር በማዕድ ተቀመጠ። እርሱም፦ ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር፤ እላችኋለሁና፥ በእግዚአብሔር መንግሥት እስኪፈጸም ድረስ፥ ወደ ፊት ከዚህ አልበላም አላቸው። ጽዋንም ተቀበለ አመስግኖም። ይህን እንካችሁ በመካከላችሁም ተካፈሉት» ሉቃ 22፤14-17

ወደዋናው ሃሳባችን ስንመለስ ለመሆኑ በማርያም ላይ ስንት ቀብር፤ ስንት ትንሣኤና ስንት እርገት ተደረገ? ብለን ብንጠይቅ እንደሚነገረው  ከሆነ ፤
1/ዮሐንስ ያየውና አፈር ያልነካው እርገት በገነት ዛፍ ስር
2/ አፈር የነካው የሐዋርያቱ ቀብር በነሐሴ 14 ቀን /ከስምንት ወር በኋላ/
3/ ቶማስ ያየው የትንሳኤ እርገት፤ ከቀብር በኋላ በሦስተኛው ቀን ነሐሴ 16
4/ ከአንድ ዓመት በኋላ ሐዋርያት ያዩት የነሐሴ 16 ትንሣኤና እርገት ናቸው።
እንግዲህ በማርያም ሞትና እርገት መካከል አራት ትእይንት መከሰቱን ዛሬም ድረስ ከሚሰጡት የቃል አስተምህሮዎችና የተዘጋጁ ጽሁፎች ውስጥ በግልጽ እናገኛለን። ማርያምን መውደድ አንድ ነገር ነው። ማርያምን ግን እየቀበሩና እያነሱ ለማረጋገጥ መሞከር ደግሞ ሌላ አሳዛኝ ክስተት ይሆናል። እንዲያውም  ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻልኩ ሰባት ጊዜም ቢሆን እሞታለሁ ብላ ለልጇ ተናግራለች የሚልም  ተረት ተያይዞ ይነገራል።  የእሷ መሞት የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆን ከቻለ የክርስቶስ ከእሷ መወለድ አስፈላጊ አይደለም የሚል ሃሳብን የሚያንጸባርቀው ይህ አባባል ከአሳሳች ትረካዎች ውስጥ የሚደመር ከመሆን አያልፍም።
እኛ  ማርያምን ብንወዳትና ብጽእት ብንላት «እናትህንና አባትህን አክብር»  ያለውን  የአምላክ ቃል መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ለእርሷ  የተነገረ ቃል ስላለም ጭምር ነው። ነገር ግን የዘላለማዊ አምላክ የክርስቶስ ፤ እናቱ ስለሆነች  በማዳላት ወይም አምላካዊ ባህርይውን በሰውኛ ጠባይ በመለወጥ ከፍርድ ሚዛኑ በማጉደል  የእሷን ሞትና ትንሣኤ የተለየ ያደርጋል ብሎ ማሰብ የዋሕነት ይሆናል። የእሷ ሞትም የመድኃኒትነትን ውክልና ለሰው ልጆች የያዘ እንደሆነ ማሰብ ክህደት ነው። ብቸኛው መድኃኒት አንዱ በግ ኢየሱስ ብቻ ነው። ማርያምም ይህንን ስለምታውቅ « ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ተስፋ ታደርጋለች» ብላ ነግራናለች።የትንሣኤ በኩር የሆነው ሁላችንም በሞቱ እንድንመስለው እንጂ የተለየ አድሎአዊ ጥቅምን/ faver/ ለተለዩ ሰዎች በመስጠት አይደለም።ወንጌል የሚናገረው ይህንን ነውና።
ሮሜ 6፥5
«ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን»
 ስለዚህ ደጋግሞ መሞት፤ መነሳትና ደጋግሞ ማረግ አለ ከተባለ ያ ነገር ከክርስቶስ ትንሣዔ ጋር ያልተባበረ ስለሆነ አንቀበለውም። እንዲያውን ይህ ኑፋቄና ወንጌልን መካድ ነው።  ሐዋርያው ጳውሎስም የተናገረው ስለክርስቶስ ወንጌል በሞቱም ክርስቶስን እንዲመስል ነበር።
ፊልጵ 3፥10-11  «እርሱንና የትንሣኤውን ኃይል እንዳውቅ፥ በመከራውም እንድካፈል፥ ወደ ሙታንም ትንሣኤ ልደርስ ቢሆንልኝ፥ በሞቱ እንድመስለው እመኛለሁ»
ማርያምን እንወዳለን እያሉ በጥር ሞተች፤ ገነት ዛፍ ስር ስምንት ወር በሬሳ ቆየች፤ በስንት ሱባዔ ስጋዋ መጥቶ ነሐሴ ተቀበረች፤ እስከነ ምድራዊ ልብሷ አረገች፤ በዳመናው ጎዳና  ላይ ከቶማስ ጋር ጨርቅ ተለዋወጠች፤ እድል ላመለጣቸው ሐዋርያት ዳግመኛ በስንት ሱባዔ በሌላ ትንሳኤና እርገት ተረጋገጠች፤ መንበር ሆና ተነጠፈች ወዘተ  በማለት እየገደሉና እያነሱ በማርያም ላይ መጫወት ተገቢ ነው ብለን አናምንም። የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤንም ማፋለስና መካድ ይሆናል።

የማርያም ሞትና ትንሣኤ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ካዘጋጀው የትንሣኤው በኩር አንድያ ልጁ የተለየ አያደርገውም።  ሞትም አንድ ነው ትንሣኤ ዘሙታንም አንድ ነው።  በትንሣኤ ዘሙታንና በእርገት መካከል ልዩነት አለ። ባልሆነ ጭንቁር ሃሳብ ተረቱን እያጋነንን ሕይወት የሆነንን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ መጋረድ ተገቢ አይደለም።

Monday, July 25, 2016

የሚፈውስና የሚያሳምም ስም - ኢየሱስ!!


(ከዙፋን ዮሐንስ)
የሆነ ጊዜ ፷፬ ሰው በሚይዝ አገር አቋራጭ አውቶቡስ ተሣፍረን ወደክልል የሁለት ቀን መንገድ ተጓዝን። ቁርስ፣ ምሳ፣ አብሮ ከመብላት፣ አብሮ ከመቀመጥ፣ የተነሳ ሁሉ ዘመድ ቤተሰብ ሆነ። የሆድ የሆዱን ተጫወተ። ስልክ ተቀያየረ፣ እጮኛም ያገኘ አይጠፋም። ያልተነሳ ርእስ አልነበረም። ፖለቲካ፣ የኑሮ ውድነት፣ ስለሳይንስ፣ ሃይማኖት፣ ስለታዋቂ ደራሲያን፣ ዘፋኝ፣ ፈላስፋ፣ ስለሃይማኖት አባት፣ ብዙ ብዙ….ብቻ ያልተወራ አልነበረም። አንዳንዶቹም ወሲብ ቀስቃሽ ቀልዶችን ግጥሞችን አውርተው መኪናው ውስጥ ከጫፍ እስከጫፍ አነቃቅተዋል። የወሲብ ነገር ሲወራ ጆሮውን ቀስሮ ያዳምጣል። የሚያስቅ ከሆነ ይስቃል፣ የሚያሳፍር ከሆነም መስማት ያልፈለገ ይመስል የኮረኮሩት ያህል ግንባሩ ጥርስ በጥርስ ይሆናል። የአለቃ ገ/ሐና ነገር ሲነሳማ የአለቃን ወሲብ ወዳጅነትና ይጠቀሙ የነበረበትን የማማለል ዘዴ እያደነቀ ከልምዳቸው ብዙ የቀሰመው ነገር ያለ ይመስል ተሳፋሪው ይስቃል፣ ያውካካል።

ይህ ሁሉ ሲሆን አንድ ሰው ከዚህ ሁሉ ሳቅና ፍንደቃ ራሱን አግልሎ ከመስኮት ጥግ ተቀምጦ ያነብ ነበር። ድንገት ብድግ ብሎ “ኢየሱስ“ የሚለውን ስም አንስቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ አዳኝነቱን፣ ተስፋነቱን፣ አጽናኝነቱን መናገር ሲጀምር ብዙ ፊቶች ተቀያየሩ። አንዳንድ ፊቶች ቲማቲም መስለው ቀሉ። የባሰባቸው አንዳንዶች ደግሞ እንደበርበሬ ቀልተው የቁጣ ብናኛቸው በሰውየው ላይ በተኑ። ስለዝሙት ቀልድ ቦታ ሳይመርጡ ሲያውካኩ የነበረውን ረስተው ስለኢየሱስ ለመስማት ቦታ አጡና “ሰብከት ቦታ አለው“ አሉና ደነፉ። ጫወታችንን አታበላሽ አሉና አጉረመረሙ። ስለፌዝ፣ እርባና ስለሌለው ቀልድና ስለዝሙት ማውራት እንደጥሩ ጫወታ ተቆጥሮ ስለኢየሱስ መስማት ግን ጫወታን እንደማበላሸት ሆኖ ተቆጠረ።
እርግጥ ነው። የሥጋን ነገር መከተል ከእግዚአብሔር የመለየት ጉዳይ ስለሆነ ማበሳጨቱ የሚጠበቅ ነበር።

ሮሜ 8፣7
 “ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሔር ሕግ አይገዛምና፥ መገዛትም ተስኖታል” እንዳለው ሐዋርያው።

በየትኛውም መመዘኛ “ኢየሱስ” የሚለው ሃይለኛ ስም ሲጠራ ለመቀበል ወይም ላለመቀበል የሰዎች አስተሳሰብ ከሁለት ነገር ውጭ አይሆንም።
አንድም የኢየሱስን ጌትነትና አዳኝነት የሕይወቷ ቤዛ ላደረገችው ነፍስ ሃሴትን ያመጣልና በስሙ መጠራት ይኽች ነፍስ አታፍርም፣ አትቆጣም።
 ሁለትም የኢየሱስ አዳኝነት፣ ጌትነትና አምላክነት ብቸኛ ቤዛዋ ያላደረገችውን ነፍስ ያበሰጫታል፣ ያናድዳታል።

ምክንያቱም ፪ቆሮ ፪፣፲፮ “ለእነዚህ ለሞት የሚሆን የሞት ሽታ፣ ለእነዚያም ለሕይወት የሚሆን የሕይወት ሽታ ነን“ እንደሚል ይኽ ስም ለዘላለማዊ ሕይወት ለተመረጡት የፕሮቴስታንት ይሁኑ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ አማኞች ሕይወት፣ ሕይወት የሚሸት ሰላምና እረፍት የሚያመጣ ሲሆን ለጥፋት ለተመረጡት ግን የሚያስቆጣ፣ የሚያነጫንጭ ጥርስ የሚያፋጭ ይሆናል። ዘፈንና ቀልዱ፣ ቧልትና ፌዙ ሲነገር ሁሉ ያለምንም ልዩነት አንድ ሆነው ሲስቁና ሲፈነድቁ እንዳልነበር “ኢየሱስ” የሚለው ስም ሲጠራ የሚያበሳጭበት ምክንያት ለምንድነው? እነዚህ ጴንጤዎች ቦታ የላቸውም እንዴ ማሰኘቱስ ለምን ይሆን? የራሱ የሆነውን ኢየሱስ ያዘጋጀ ሃይማኖት የለም።

ቢያንስ አዳምጦ ከወንጌል ቃል ውጪ የሆነውንና ያልሆነውን መለየት ሲቻል መቃወም ተገቢ አይደለም። ደደግሞም ፌዝና ሥጋዊ ነገርን ከማውራት ስለኢየሱስ መስማት በብዙ መልኩ ይሻላል። ለሁሉ ስለሞተው ስለኢየሱስ መናገር የተወሰኑ ሰዎች ስጦታ ሆኖ ሲያስወቅስ፣ ስለዝሙት መናገር ግን ለሁሉ የተፈቀደ መልካም ተግባር ሆኖ የሚቆጠርበት ምክንያት መኖር አልነበረበትም። ነገር ግን ይኽ ስም ሲጠራ ያስፈራቸውና ሐዋርያቱን፣ “ጀመሩ ደግሞ እነዚህ የተረገሙ!” ያስብል እንደነበር ወንጌል ያስታውሰናል።

1. ስሙን ሲጠራ ለተቀበሉ የሕይወት ሽታ የሆነላቸው። ሐዋ ፰
 ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ፊልጶስ ስለኢየሱስ ሲሰብክለት ልቡ ደስ ተሰኘ። አጥምቀኝ አለው እንጂ “የእናትና አባት ሃይማኖቴን ተከትዬ ከኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ድረስ ያስመጣኝና ተራራ የወጣሁበትን ታላቅ የበረከት ጉዞ አድርጌ ከመመለስ ባለፈ ያንተን ኢየሱስ ለመስማት አልመጣሁም“…ብሎ አልተቆጣም።
በሉቃ ፳፯-፳ ላይም የኤማሁስ መንገደኞች ስለኢየሱስ በመጽሐፍ የተጻፈውን ሲሰሙ ልባቸው ይቃጠልባቸው ነበር። በዚያ በነበርንበት አውቶቡስ ላይ ግን ለብዙዎች ልባቸው የተቃጠለው ለምን ይኄንን ስም ትጠራላችሁ? ብለው በመናደድ ነበር።
ሐዋ ፲-፳፬ ላይ መቶአለቃ ቆርኔሌዎስም ጭራሽ ዘመዶቹንና ወዳጆቹን ጠርቶ ስለኢየሱስ ስበኩኝ ብሎአል። ስለኢየሱስ መስማት ደስ የሚያሰኝ ሆኖ ሳለ ጆሮ የሚያሳክክበት ምክንያት አይኖርም። ቢያንስ ስለአለቃ ገ/ሐና የዝሙት ጥበብና ሴቶችን እንዴት እንደሚያጠምዱ ከመስማት ይልቅ አምነው ባይቀበሉት እንኳን ስለኢየሱስ የሚነገረውን የወንጌል ቃል ማዳመጥ ለዝሙት ልብን ከማነሳሳት ከንቱ ወሬ ሳይሻል አይቀርም።
  በበዓለ ሃምሳ የተሰበሰቡት አይሁድ ስለኢየሱስ ሲወራ ልባቸው ተነክቶ ሐዋርያትን “ምን እናድርግ ?? “ብለው እርዳታ ጠየቁ እንጂ “በየመንገዱ በየአደባባዩ በየባሱ እየሰበካችሁ፣ አታስቸገሩ “ብለው በተቆርቋሪነት ሰበብ የአጋንንትን ቁጣ አልተቆጡም። እነዚህ ስሙን የሰሙና ያልተቃወሙ ሁሉ መጨረሻቸው ያመረ ክርስቲያኖች ሆነው በሰማይ የዘላለም ሕይወትን በምድርም በረከትን አግኝተው ወደጌታ ሄደዋል።

2. የሞት ሽታ የሆነባቸውና ስሙ ሲጠራ የሚያበሳጫቸው የሚያስቆጣቸው ሰዎች እንዲህ የሚሆኑት እነሱ ሳይሆኑ በውስጣቸው የተቀመጠው ክፉ የክርስቶስ ተቃዋሚ መንፈስ ነው። ይኽ ስም ሰዎችን ከሥጋዊና መንፈሳዊ ደዌ ስለሚፈታ ሰይጣን ይጠላዋል። መድኃኒትን ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ሰውነት መድኃኒት ለሞት እንደሚሆንበት ሁሉ ኢየሱስ የሚለውም ስም ለሞት ይኾንባቸዋል። ሐዋርያው ጳውሎስ ከመለወጡ በፊት የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብን አምላክ እንደሚያመልክ ስለሚያምን “ኢየሱስ” የሚባለው ስም ያበሳጨው ነበር። ይኽንን ስም የሚጠሩትን ያስርና ያስገድል ነበር። ሐዋ ፬:፲፰ “በኢየሱስ ስም ፈጽመው እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዙአቸው” “ በማለት ፈሪሳዊያን ስሙ የሞት ሽታ እንደሆነባቸው ያሳያል። “ገረፉአቸው፥ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው።“ በማለት ስሙ እንዳስገረፈ አንብበናል።

ወንድሞቼና እህቶቼ ዛሬም ይህንን ስም መጥራት ያስደነግጣል/ያስፈራል/ኤሌክትሪክ ያስጨብጣል። በስካር መንፈስ ናውዞ ውሃ መውረጃ ቱቦ ስር የሚያድረው ብረቱ፣ አንበሳው ሲባል ዘማዊውና አለሌው ቀምጫዩ እየተባለ ሲሞካሽ፣ ሌባው ቢዝነሳሙ፣ እሳቱ ሲሉት የኢየሱስ ስብከት ሲነሳ ግን ሃይማኖተኛ ሆኖ ሲያፈጥ ማየት በጣም ያሳዝናል። ጫትና ሲጋራ፣ ሀሺሽና ሺሻ የሚያናውዘው ሱሰኛው ሰው ለጥምቀትና ትንሣኤ በአጭር ታጥቆ መንገድ ከሚጠርግ፣ ቄጠማ ከሚጎዘጉዝ፣ ምንጣፍ ከሚያነጥፍ ውስጡ ተጎዝጎዞ ከተቀመጠው ክፉ መንፈስ ኢየሱስን ንጉሡ አድርጎ ቢያኖር ኖሮ ከዐመጻ ተግባራቱ ነጻ በወጣ ነበር። የሕይወቴ መሪ ነው ያለ ሰው ንሰሃ ገብቶ ኢየሱስ ሰው አደረገኝ ይላል እንጂ “ኢየሱስ” ብሎ የሚሰብክን ሰው “መግደል ነበር“ አይልም። እህቴና ወንድሜ ዛሬ ኢየሱስ አንተና አንች ጋር የሞት ሽታ ወይስ የሕይወት ሽታ ነው? ሁላችን ራሳችንን እንመርምር።
 ክብርና ምስጋና ነፍስ ሥጋና መንፈስን ነጻ ለሚያወጣው ሰው ለሚያደርገው ትልቅ ስም፣ ለኢየሱስ ክብር ይሁን! አሜን

Friday, July 15, 2016

ትወደኛለህን?


(ከነገ ድል አለ)
ምላሽ የሚያሻው የክርስቶስ ጥያቄ - ትወደኛለህን? (ዮሐንስ 21)
ይህን ጥያቄ ስናነብ ወደ አእምሮአችን በቶሎ የሚመጣው ምንድን ነው? ምናልባት ምን ዐይነት ጥያቄ ነው? ብለን እናስብ ይሆናል፤ ወይም ጥያቄው የአፍቃሪ ጥያቄ አንደሚሆን ልንገምት እንችላለን። አሊያ እንደዚህ ተብሎ ይጠየቃል ወይ? ብለን ልንጠይቅም እንችላለን። ጥያቄው ረጅም ጊዜ ዐብሮን ከኖረ ሰው፥ በጣም ከሚያውቀንና ከምናውቀው ሰው፥ ለምሳሌ፥ ከባለቤታችን ወይም ከጓደኛችን ቢመጣስ ምን ይሰማናል? ያለ ጥርጥር ምን አይቶብኝ ይሆን? ወይም ምን አይታብኝ ይሆን? ምን ሰምቶብኝ/ምን ሰምታብኝ ይሆን? የሚሉ ጥያቄዎችን ሊያጭርብን ይችላል።
ጥያቄው “አዎን እወድሃለሁ” የሚል ምላሽን ለማግኘት ወይም መወደድን ለማወቅ የተጠየቀ ጥያቄ አይደለም። ጥያቄው ከፍቅረኛ፥ ከትዳር አጋር ወይም ከጓደኛ የመጣ ሳይሆን ከጌታችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ በተለይም ለጴጥሮስ የቀረበ ጥያቄ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ በወንጌሉ በ21ኛው ምዕራፍ አንደ ዘገበልን፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ያህል “ትወደኛለህን?” ሲል ጠይቆታል።

እወድሃለሁ
“ትወደኛለህን?” የሚለው ጥያቄ ፍቅርን ለማወቅ ወይም ለማረጋገጥ የሚጠየቅ ጥያቄ ቢሆንም፥ ዮሐንስ እንደ ጻፈው ጥያቄው ከዚያ የሚያልፍ መልእክት አለው። በርግጥ ትወደኛለህን? ተብሎ ሲጠየቅ ምላሹ አልወድህም የሚል አይሆንም። በክርስቶስና በጴጥሮስ መካከል የነበረውን ግንኙነት መለስ ብለን ስናስታውስ፥ ጌታ ደቀ መዛሙርቱን በሥጋ ልለያችሁ ነው፤ ልሄድ ነው ብሎ በነገራቸው ጊዜ፥ ጴጥሮስ ‘ተለይተኸን ወዴት ትሄዳለህ? የትም ብትሄድ ዐብሬህ እሄዳለሁ፤ ሞት እንኳ ቢመጣ ከአንተ አልለይም’ ያለው ሰው ነበር (ዮሐ. 13፥36-38)። ጌታ ለጴጥሮስ ንግግር የሰጠው ምላሽ፥ ‘እንኳ ነፍስህን ልትስጠኝ፥ ዶሮ ከመጮኹ በፊት ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ’ የሚል ነበር።

ፍቅር እንዴት ይገለጣል?
እንደሚታወቀው በዓለም ላይ የፍቅር መገለጫ አንድ ዐይነት አይደለም፤ ከማኅበረሰብ ማኅበረሰብ፥ ከባህል ባህል ይለያያል። የፍቅር መግለጫ ቋንቋ፥ የጋለ ጭብጨባ፥ እንባ፥ የቃል ንግግር፥ አበባ ማበርከት፥ መተቃቀፍ፥ መጨባበጥ፥ መሳሳም ሊሆን ይችላል። ከእነዚህ በአንዱ ወይም በሌሎች መንገዶች ፍቅር ይገለጣል። ጌታ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ መላልሶ ሲጠይቀው፥ ጴጥሮስም ሦሰት ጊዜ መላልሶ እወድሃለሁ ብሎታል። እንዲሁም በኋላ ላይ ግራ የገባው በሚመስል መልክ፥ በማዘንም ጭምር እንደምወድህ አንተ ታውቃለህ ብሎታል።

ፍቅርና ተግባር
በአጠቃላይ በወንጌል በተለይም በጌታችን ትምህርትና ሕይወት ውስጥ እንደምንመለከተው፥ የፍቅር ዋና መገለጫ ቃላት ሳይሆኑ ተግባር ነው። ጴጥሮስ “እወድሃለሁ” ቢልም በተግባር ግን ይህን ፍቅር ማሳየት አልቻለም፤ እወድሃለሁ ያለውን ጌታውን ክዶታል። ጌታችን ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል 15፥13 ላይ ነፍሱን ለወዳጆቹ ከመስጠት የበለጠ ፍቅር እንደሌለና ነፍስን መስጠት የፍቅር ጣሪያ መሆኑን እንዳስተማረ፥ በተግባርም ነፍሱን በመስጠት ፍቅሩን አሳይቷል። ከዚህ በኋላ ነው ጌታ ጴጥሮስን “ትወደኛለህን?” ሲል መላልሶ የጠየቀው። ጴጥሮስም እንደ ቀድሞው፥ “ከአንተ ጋር መሞት እንኳ የሚያስፈልገኝ ቢሆን፥ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. 26፥35) አላለም። የራሱን ምላሽ ከመስጠት ይልቅ “እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” ነበር ያለው። ጴጥሮስ ፍቅሩን በተግባር መግለጽ ባይችልም፥ ኢየሱስ ፍቅሩን በተግባር ከገለጠና፥ የካደውን ጴጥሮስን በዚህ ፍቅር እንደ ገና ከመለሰው በኋላ አልከሰሰውም። ይልቁንም ሲመልሰውና ወይም እንደ ገና ሲያድሰው፥ ኀላፊነትንም ሲሰጠው እንመለከታለን።

መልእክቱ

“ትወደኛለህን?” የሚለው የጌታ ጥያቄ “አዎን እወድሃለሁ” ከሚል ምላሽ ያለፈ ቀጥተኛ መልእክት አለው። መልእክቱም የምትወደኝ ከሆነ አደራዬን ተወጣ የሚል ነው። ጌታ ሦስት ጊዜ፥ “ትወደኛለህን?” ሲል ከጠየቀው በኋላ ጴጥሮስ “አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” የሚል ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ፥ ግልግሎቼን አሰማራ፤ ጠቦቶቼን ጠብቅ፤ በጎቼን አሰማራ የሚል ግልጽ አደራ ሰጥቶታል (ዮሐ 21፥15-17)። ይህ ኀላፊነት ወይም አደራ የሕይወት መሥዋዕትነትን የሚጨምር እንደሚሆን ቀጥሎ በተጻፈው ቃል ውስጥ እናነባለን። “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ አንተ ጒልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ ራስህ ታጥቀህ ወደምትወደው ትሄድ ነበር፤ ነገር ግን በሸመገልህ ጊዜ እጆችህን ትዘረጋለህ፥ ሌላውም ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል አለው። በምን ዐይነት ሞት እግዚአብሔርን ያከብር ዘንድ እንዳለው ሲያመለክት ይህን አለ።” የዚህ ክፍል መልእክት በእኛም ሕይወት ሊተገበር የሚገባው ነው። ምክንያቱም ክርስቶስ በዕለታዊ ሕይወታችን ተግባራዊ ምላሽን ይጠብቃል። ትወደኛለህን? ለሚለው ጥያቄ በቃል “እወድሃለሁ!!” የሚለውን ምላሽ ከመስጠት ይልቅ፥ ራሳችንን መልሰን መጠየቅ የተሻለ ሳይሆን አይቀርም። በርግጥ ጌታን እንወደዋለን ወይ?

Monday, July 4, 2016

እሳትና ውሃ አጥፊና ጠፊ ቢሆኑም አስፈላጊዎች ናቸው!

(ከኪሩቤል ሮሪሳ ጽሑፍ ተሻሽሎ የተወሰደ)
ነገሥታቶች በሪፐብሊካዊ መንገድ ሥልጣንን በእጃቸው ካስገቡ መሪዎች የበለጠ ቅቡል ነበሩ። የሥልጣን መሠረታቸው መለኮታዊ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ ሕዝብ በፈቃዱ ይገዛላቸው ነበር። እነርሱም ሕዝባቸውን ይወዳሉ... ሕዝብም ይወዳቸዋል። በንጉሣዊ አገዛዝ ንጉሡ አባወራ.., ንግሥቲቱ እማወራ... ሕዝብ ደግሞ ልጆች ናቸው። አዋጅ ሲነገር "የምንወድህና የምትወደን ህዝብ ሆይ" ብለው ንግግር ይጀምራሉ። ይኼ ጭምብል ያለው ማታለያ አይደለም። እውነት ነው። በእነዚህ አካላት መካከል እውነተኛ ፍቅር ነበር። ምክንያቱም በታዛዥ ልጅና አባት መካከል ፀብ አይኖርም። ፀቡ የሚጀምረው ልጅ እምቢ ሲል ነው።
ሕዝብ ሁሉንም ነገር እሺ ብሎ በሚቀበልባቸውና ንጉሣዊ አስተዳደር ባለባቸው አገሮች የተሻለ ሰላም አለ። ሕዝብ ጠግቦ ሊበላ ይችላል። ባይበላም ከላይ ከሰማይ የተሰጠን የ40 ቀን እድል ነው ስለሚባልና የመብት ጥያቄዎች ስለማይኖሩ የአገርም አንድነት አይናጋም። እዚህም እዚያም የቦምብ ፍንዳታና ግድያ አይኖርም። የትልቅ አገር (በተለየ አተያይ) ባለቤት የመሆን እድልም ሰፊ ነው። በኛም አገር ከነበሩት የንጉሣዊ አስተዳደር ጥቅሞች መካከል ከላይ የተጠቀሱት ይገኙበታል። ስለዚህ እነኚህን የንጉሣዊ አስተዳደር ጥቅሞችን የቀመሰም ሆነ የሰማ ሰው... ዛሬ ላይ የድሮ ሥርዓት ናፋቂ ነኝ ቢል ላይገርም ይችላል።
ሥልጣንን የመጋራትም ሆነ ሌሎች የዴሞክራሲ ጥያቄዎች መነሳት የሚጀምርባቸው አገሮች ላይ ሰላም አይኖርም። ስደትና እንግልቶች ይኖራሉ። የረጋና ጸጥታ የሰፈነበትን ንጉሣዊ አስተዳደር ወደ ሌላ ሥርዓት የሚቀይረው እምቢታ ነው።
እምቢታ የለውጥ መጀመሪያ ነው። የዓለምን ቅርጽ የቀየረው እምቢታ ነው። የእምቢታ መሠረቱ ደግሞ እውቀት ነው። የንጉሣዊ አስተዳደሮች አገዛዝ ማዕበል አልባ ሐይቅ ነው። የማይንቀሳቀስ ውሃ ከሩቅ ሲታይ ፀጥታው ቢያስጎመዥም ውስጡ ላሉ አሣዎች ግን መራር ነው። ማዕበል ሲቆም አሣዎች መሞት ይጀምራሉ። እንቅስቃሴ አልባ የሆነ ነገር መልካም ቢመስልም ቆይቶ ግን ይገማል... ይሞታልም። ስለዚህ ንጉሣዊ አስተዳደሮች ለለውጥ የማይጋብዙ ስለነበሩ በኃይል መቀየራቸው ግድ ነበር። ሕዝብ በፀጥታው ውስጥ ተኝቶ ነበር። ሕይወት በድግግሞሽ የተሞላች አሰልቺ ነበረች።
በንጉሣዊ የአስተዳደር ሕግ ገዢው ግለሰብ እንጂ ሃሳብ አይደለም። ንጉሣዊ ባልሆነው ዓለም ደግሞ ገዢ የሚሆነው ሃሳብ ነው። የግለሰብ መኖር አስፈላጊ ላይሆንም ይችላል። ፓርቲዎች ሃሳቦችን ሲያመነጩ ሕዝቦች ደግሞ "ገዢ" ለሆነው ሃሳብ ድምፅ ይሰጣሉ። በዚህ የሥርዓት ሂደት... ሕይወት በምርጫ ውሳኔ ውስጥ ትወድቃለች። ለመምረጥ ሁለቱም መኖር አለባቸው። ሁለቱ ነገሮች ተነፃፃሪ እንጂ ተጻራሪ አይደሉም። መጻረር የሚባል ነገር የለም። ሁለቱም ትክክል ናቸው። የተሳሳተ የሚባል ነገርም የለም። አንዱ ከሌለ ምርጫ የሚባል ነገር ይጠፋል። አንዱ ፓርቲ ወንበር ይዞ ይቀርባል። አንዱ ደግሞ ሶፋ። ሕዝብ የፈለገውን መርጦ ያስቀመጥበታል። በዚህ መሃል ፓርቲዎች "ሶፋ ለእንቅልፍ ይጋብዛል" ወይም "ደረቅ ወንበር ለኪንታሮት ሕመም ይዳርጋል" ተባብለው ልዩነቱን ማጦዝ ይችላሉ። ነገር ግን ወንበር፣ ወንበር መሆኑ ሶፋም፣ ሶፋ መሆኑ እሙን ነው። ሁለቱም ይጠቅማሉ። ይህ ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት ፈጠራን አበረታቶ ለለውጥ ይጋብዛል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ባለ የፖለቲካ አረዳድ ሶፋ ካለ ወንበር አያስፈልግም። ወንበርና ሶፋ ተጻራሪ እንጂ ተነጻጻሪ አይደሉም። ሁለቱም ጎራዎች ውስጥ በውስጣቸው የተቀበረ ንጉሳዊ መለዮ አለ። እኔ ብቻ ነኝ፣ የሥልጣን ምንጭ የሚል። ልዩነትን እንደጠላት የማየትና የእኔ ብቻ ትክክል የማለት አባዜ አገራችንን ጠፍንጎ ይዟታል። ከንጉሣዊ አስተዳደር ተላቀን ከለውጡ ልናገኝ የነበረውን ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እነዚህ ሁለት ጎራዎች መና አስቀርተውታል። የለውጡ ችቦ ከተለኮሰ ከ40 በላይ ዓመታት ቢቆጠሩም ዛሬም ፖለቲካችን አዙሪት ውስጥ ነው። የአዙሪቱ ምክንያት አንድ ነው። የመቀያየር ሳይሆን የመጠፋፋት አባዜ። ገዢው የተቃዋሚው.... ተቃዋሚው ደግሞ የገዢው ጠላቶች ናቸው። አንዱ በአንዱ መቃብር ላይ መንገሥ ይፈልጋል።
ይህ በሽታ ወደ አዲሱ ትውልድም እየተዛመተ ነው። ወጣቱ ልዩነትን ባየ ቁጥር፣ ስም መለጠፍ ሥራዬ ብሎ ተያይዞታል። ፍላጎቱ አይታወቅም።
የንጉሣዊ አስተዳደርን ባሕርያት በጥልቀት በማጥናት ለውጡ አስፈላጊ እንደነበረ መረዳትና ወደኋላ ተመልሰን እሱን የምንናፍቅበት መሠረት እንደሌለ ማመን ላይ ገና ብዙ ክፍተት አለ። በዚህ ዘመን ወደኋላ ተመልሶ ንጉሥ መናፈቅ ምን ይባላል?
መነሻው ባለው ላይ በትንሽ ነገር ተስፋ መቁረጥ... እልህና አጉል ጀብደኝነት ነው። የታሰረ ሁላ ጀግና.... ተቃዋሚ ሁላ ሽብርተኛ በማለት ፈርጆ ለመጠፋፋት ምሏል። ለዚህ ሁላ ምስቅልቅል የፖለቲካ ባህል ተጠያቂው ስንፍናና ድንቁርና ነው። በየጊዜው ዓላማችን ሥርዓት ለመቀየር እንጂ እኛ ለመቀየር ፍላጎት የለንም። ያልተቀየረ አስተሳሰብ ደግሞ የተቀየረ ሕብረተሰብ ሊፈጥር አይችልም። መለወጥ ያለበት አተያያችን ነው። እሳትና ውሃን አለቦታው ለመጠቀም መፈለግ የፈጣሪ ስህተት ሳይሆን የኛ ጉድለት ነው።
ውሃን እሳት ውስጥ ብንጨምር ወይም እሳትን ውሃ ውስጥ ብናስገባ ለመጠፋፋታቸው ስህተቱ የማነው? የበረደው ሰው እሳትን በብብቱ ይይዝ ዘንድ አይጠበቅም።
ነገር ግን ውሃንና እሳትን መጥነን በመደጋገፍ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እንችላለን። ይህ የአስተሳብ ብስለት ነው። ፖለቲካችንን ግን ለምንኖርባት ቤታችን እንደሚመጥን አድርገን አስማምተን መጠቀም አልቻልንም። አጥፊና ጠፊ መሆኑ እስካላከተመ ድረስ አዙሪቱ ደግሞ አይለቀንም። ስለዚህ መለወጥ ያለበት ወንበሩ ሳይሆን ወንበሩን የሚፈልጉ ጭንቅላቶች ናቸው።
መጽሐፍ ቅዱሳችን እንደሚነግረን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ከቀረቡ ክሶች መካከል አንዱ "ንጉሥ ነኝ ይላል" የሚል ነበር። ይኽ ንግግር ደግሞ በወቅቱ በሕዝቡ ላይ ተሹሞ ለነበረው ሰው ትልቅ ራስ ምታት ነው። ምክንያቱም ሥልጣን የሚቀናቀን ሰው ቶሎ መጥፋት አለበት። ከሳሾቹም ይኽንን ያውቃሉ። በአደባባይም የተጠየቀው "አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህን?" የሚለው መቅደሙ መልሱን ለማወቅ ነው። የሚቀናቀን ከሆነ ቶሎ የማጥፋት አስተሳሰብ እስካልተቀየረ ድረስ መጠፋፋት አያቆምም። እርግጥ ነው፣ እንደሥርዓት ዛሬ አፄ የለም። በወንበር ላይ ግን መንግሥትም፣ ተቃዋሚም ሁሉም የአስተሳሰብ አፄ ነው። ትውልድ ከዚህ አስተሳሰብ መውጣት አለበት። እሳትና ውሃ አጥፊና ጠፊ ቢሆኑም በወሰን፣ በክልል፣ በመጠንና በልክ ከተጠቀምንባቸው ሁለቱም የግድ አስፈላጊዎቻችን ናቸው።

Wednesday, June 22, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጌልን ማቆም ያልቻለው ለምንድነው?


ከዙፋን (ተስተካክሎ የቀረበ)
ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሰረተ 25 አመት ሞላው። ድርጅቱ ከተመሰረተ ጀምሮ የፕሮቴስታንት፣ የካቶሊክና ሌሎች የክርስትና ክፍሎች የወንጌል ስብከት በፊት ከነበራቸው ውስንነት በበለጠ ሲሰፉ እንጂ ሲጠፉ አልታየም።
 በተለይም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች የሆኑና ቤተክርስቲያኒቱ ከወንጌል ጋር አንዳንዴም ከወንጌል በላይ ስፍራ የምትሰጣቸው ትውፊቶች፣ ድርሳናት፣ ገድላት ከዚያም ባለፈ ልዩ ልዩ አስማትና ተረቶች የእግዚአብሔርን የክብር ስፍራ ወስደውና ጋርደው መገኘታቸውን ያስተዋሉና ከውስጥ የተነሱ የተሃድሶ እንቅስቃሴዎች ከነበሩበት ሁኔታ እየሰፉና እያደጉ መጥተዋል። ግንዛቤያቸውን በሁሉም ዘንድ በማዳረስ ረገድ ሰፊ ተቀባይነት በማግኘታቸው ከነበሩበት የተወሰነ ሁኔታ ወጥተው ዛሬ ከማኅበሩ የ25 ዓመታት ቁጥጥር ውጪ ናቸው። ማኅበሩ የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመጨፍለቅ ያልቆፈረው ጉድጓድ፣ ያልፈነቀለው ድንጋይ አልነበረም። ከንግድ ድርጅቶቹ የሚያገኘውን ግዙፍ ገንዘብ፣ የሰው ኃይልና ማቴሪያልም ጭምር ለዚህ ስራ ያውላል። በተሐድሶ ላይ ግንዛቤ ማስጨበጫ፣ ዐውደ ርእይ፣ ስብሰባ፣ ወርክሾኘ፣ በንግሥ በዓላት፣ በዐውደ ምሕረት፣ በፅሑፍ፣ በምስል ወዘተ ልዩ ልዩ መንገዶች ህዝቡን ያስተምራል፣ ያስጠነቅቃል ቪዲዮ ይበትናል፣ ካሴት ይለቃል፣ በራሪ ወረቀቶችን ያሰራጫል። በዩኒቨርሲቲዎች፣ በኮሌጆች፣ በሕጻናት፣ በወጣቶች፣ በጎልማሶች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ባሉ ሰንበት ት/ ቤት ተማሪዎች ላይ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ሰርቷል። ተጽእኖውና መልእክቱ ያልገባበት ቤት የለም። ተሐድሶ፣ ሃራጥቃ፣ መናፍቃን፣ የአውሬው ተከታዮች፣ ፀረ ማርያሞች፣ ጠላቶች፣ ነካሾች፣ ቡችሎች…ወዘተ ብዙ ስም አውጥቶ ለማስጠላት ሞክሯል። በስለላ፣ በክትትል፣ በጥርጠራና በድጋፍ አብሮት ያልቆመውን ሁሉ ስም እየለጠፈ በማባረርና በማስፈራራት ብዙ ቢጓዝም ትምህርተ ተሐድሶ ግን ሊቀንስ አልቻለም። ከዚህ ሁሉ ልፋት በኋላ በውጤቱም በ25 አመት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማታወቅ መልኩ 15 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ከኦርቶዶክስ አካውንት ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ጎርፏል።
ብዙ ሚሊዮን ኦርቶዶክሳዊያን ምእመናን፣ መምህራን፣ ሊቃውንት፣ ቀሳውስት፣ መነኮሳት፣ ጳጳሳት ሳይቀሩ ባሉበት ቤታቸው ሆነው የተሐድሶ እንቅስቃሴን ደጋፊና አራማጅ ሆነዋል። የተሐድሶ እንቅስቃሴ መጀመር ወደሌላ የእምነት ድርጅት የሚኮበልለውን ምዕመን ቁጥር መቀነስ ችሏል። ችግሩ ያለው ከኦርቶዶክስ መሠረታዊ አስተምህሮ ሳይሆን በጊዜ ብዛት በገቡ የስህተት ትምህርቶችና የፈጣሪን ሥፍራ የተረከቡ የክህደቶች አምልኰዎች የተነሳ መሆኑን ተሐድሶዎች ማሳወቅ በመቻላቸውና ይህንን ለማስወገድ ደግሞ እዚያው ሆኖ በማስተማርና በመለወጥ እንጂ በመኮብለል አለመሆኑን ብዙ በመሥራታቸው የተነሳ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ የሱን የኑፋቄ ጽዋ ለመጨለጥ ያልፈለጉት እዚያው ከሚቆዩ ይልቅ ኮብልለው የትም ገደል ቢገቡለት ይመርጣል። በጀትና ኃይል መድቦ ተሐድሶዎችን ከመከታተል ይልቅ ከበረት አስወጥቶ፣ በረቱ ውስጥ የቆዩለትን በጎች የራሱ የግል ንብረት አድርጎ ለመቆጣጠር ያመቸዋል። ያስቸገረውና ብዙ ድካሙን መና ያስቀረው ነገር የተሐድሶ ኃይል በእውቀት፣ በጥበብና በተዋሕዶ ቀደምት እውነት ሁሉን ማዳረስ መቻሉ ነው።
የማኅበረ ቅዱሳን ትልቁ ችግር ራሱን የእውነትና የእምነት ጫፍ አድርጎ መመልከቱ አንዱ ጉዳይ ሲሆን ሌላው ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተምህሮ ጥግ ላይ ከማኅበረ ቅዱሳን ውጪ ያለው ለማስተማር መሞከር ማለት አፍን ማሞጥሞጥ እንደሆነ አድርጎ ማሰቡ ነው። እውነታው ግን በተሐድሶ ምሁራንና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለው የእውቀት ልዩነት የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ተሐድሶ አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ይቀመጥ ሲል ማኅበሩ ደግሞ በአሮጌው አቁማዳ አዲሱን የወይን ጠጅ ማስቀመጥ ይቻላል በሚለው የእምነት አስተሳሰብ ልዩነት የተነሳ በተደራጀ አቅምና ሥልጣን በሚያደርገው ሩጫ ተሐድሶን ማስቆም አልቻለም። ተሐድሶ የግለሰቦች አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔር አሰራር መገለጫ በመሆኑ ማንም ድርጅት በትግል ሊያቆመው አይችልም።
“ወልበስዎ ለሐዲስ ብእሲ ዘሐደሶ እግዚአብሔር በጽድቅ፣ ወበርትዕ፣ ወበንጽሕ” ኤፌ 4:24
“ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ” የሚለን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ነው። በተረታ--ተረትና በእንቶ ፈንቶ ጩኸት በመባከን ፈንታ የወንጌልን እውነት መጨበጥ፣ ባዶ ተስፋ ከሚያስጨብጡ ዝናብ አልቦ ደመናዎች ዝናብ ከመጠበቅ ይልቅ ባለቤቱ ራሱ የሕይወት ውሃ ምንጭ እኔ ነኝ ካለው እውነት ቃሉ በመጠጣት መርካት መቻል ማለት መታደስ፣ መለወጥ፣ አዲስ ሰው መሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ሁሉም ሰው እንዲታደስለት ይፈልጋል። የተሰራነው አንድ ጊዜ ተሞልቶ ፈፅሞ ከማይደክም የባትሪ ኃይል አይደለም።
“ወዘንተ ውስጥነሰ ይትሔደስ ኩሎ አሚረ”
“... የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” 2ኛ ቆሮ 4:16 እንዳለው መታደስ በመንፈሳዊነት ኃይል እግዚአብሔር እንደሚወደው ሆኖ መሰራት ማለት ነው።
በዚህም የተነሳ ማኅበረ ቅዱሳን የሚታገለው የእግዚአብሔርን ሃሳብ ለማስቆም ነው። ነገር ግን እስካሁንም አልቻለም፣ ወደፊትም አይችልም። ምክንያቱም ተሐድሶ፣

1. የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው።

 በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ወንጌል በምድር ሁሉ ሊሰበክ ግድ ነው። ሉቃ 12:49 “በምድር ላይ እሳት ልጥል መጣሁ “ እንደሚለው ጌታ የጣለው እሳት ይነዳል እንጂ አይጠፋም። ሐዋ 5-38
  “ይህ አሳብ ከሰው እንደ ሆነ ይጠፋልና፤ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ግን ታጠፉአቸው ዘንድ አይቻላችሁም፣ ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ” እንዳለው ከእግዚአብሔር ስለሆነ ሊጠፉ አልቻሉም፣ አይጠፉምም ።

2. የአብርሖት (enlightenment) ዘመን በመሆኑ፣

ይህ ዘመን ትምህርት የተስፋፋበት ብዙዎች ከመሃይምነት ነጻ የወጡበት መረጃ የበዛበት ነው። የሰዎች መንፈሳዊ ረሃብ በማይረዱት ግእዝ የማያውቁትን ነገር ተቀብለው ወደቤት ከመሄድ ባለፈ መጽሐፍ ቅዱስና መንፈሳዊ ፅሑፎችን በማንበብ ማብራሪያና መልስ የሚፈልግበት ዘመን ነው። ትውልዱ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ልምምድን በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ይፈትሻል። ለእምነቱ በቂ ማብራሪያ ይሻል። ያነጻጽራል። መጽሐፍ ቅዱስን በሞባይሉ አስጭኖ የትም ቦታ ያነባል። እንደ መጨረሻ ባለሥልጣን ቃልም ያየዋል። ከዚህ ቃል ጋር የሚጋጭ ወይም ለማስታረቅ የሚሞክርን ማንኛውንም ውሸት ለመቀበል አይፈልግም። ይህንን ዘመነ አብርሖት ከእውነት ጋር በመስማማት እንጂ በመሸፋፈን ወይም ትቀሰፋለህ፣ በሰይፍ ትቆረጣለህ በሚል ማስፈራራት ማስቆም አይቻልም።

3. ዛሬም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መዳንና ፈውስ ስላለ፣

 እግዚአብሔር በአንድ ቃልና በጸሎት በአንዴ መፈወስ ያቃተው ይመስል ለሥጋዊ ፈውስ ሸንኮራ፣ ጻድቃኔ፣ግሼን፣ሚጣቅ፣ ሺፈጅ፣ ኩክየለሽ፣ ግንድአንሳ፣ ከድንጋይ አጣብቅ፣ መሿለኪያ፣ መንከባለያ፣ ገልብጥ፣ ሰንጥቅ ወዘተ አዳዲስ የፈውስ መደብር እየፈጠሩ የአንዱ ወረት ሲያልቅ ሌላ እየፈለሰፉ ገንዘብ ጉልበት ጊዜ ጨርሶ መፍትሄ በማሳጣት ተራራ ለተራራ መንከራተት ስለሰለቸው ሰው ከዚህ እንግልት ማረፍ ፈልጓል። ከ 5 ትውልድ ወደ10 ትውልድ፣ ወደ 30 የማይጨበጥ ቃል ኪዳን ለመጨበጥ ሲያበላልጥ በክርስቶስ ላይ ብቻ አንዴ ታምኖ በመኖር ዕረፍትን ፈልጓል።

4. ትውልዱ ከሱስ መፈታትን ስለሚፈልግ

የጫት፣ የሲጋራ፣ የሺሻ፣ የሃሺሽና የመጠጥ ሱስ በየመንደሩ ብዙ ወጣቶችን ተብትቧል። ሴተኛ አዳሪነት፣ ስርቆትና ዝሙት አንገቱ ላይ ያሰረው ክር ወይም መስቀል ነፃ ሊያወጡት አልቻሉም። የጠለንጅ ወይም የጊዜዋ ቅጠል ማጫጫስ መፍትሄ አልሆኑትም።
 44 ታቦት ባነገሠ ማግሥት ከነበረበት ሕይወት ሊፈታ ባለመቻሉ ከተስፋ መቁረጥ የሚያድነውን ይፈልጋል። ይኼውም ያልተቀላቀለበት የእውነት ወንጌል መስማት መቻሉ ነው።
2 ቆሮንቶስ 4፣2
“ነገር ግን የሚያሳፍረውን ስውር ነገር ጥለናልና በተንኮል አንመላለስም፣ የእግዚአብሔርንም ቃል በውሸት አንቀላቅልም፤ እውነትን በመግለጥ ግን በእግዚአብሔር ፊት ለሰው ሕሊና ሁሉ ራሳችንን እናመሰግናለን”

5. ለሥራ ስለሚያነሳሳ፣

 እምነቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያስተካከለ ሁሉ ለበጎ ሥራ የተነሳሳ ሰው ነው። ከወንጌል ሥራን እንጂ ስንፍናን አይማርም። ዐባይን ብቻዋን እንድትጠቀም ግብጽ በሕዝባችን ላይ የጫነችው የስንክሳር የበዐላት ሸክሟን ከራሱ ላይ አራግፎ በመሥራት ራሱንና ወገኖቹን የሚጠቅም ትውልድ እንጂ ስለአባ እገሌ እያለ የሚለምን ዜጋ ሊኖር አይችልም። ትንሽ ሠርቶ ያገኛትን ደግሞ በፍትሃት ድግስ እያራገፈ፣ ብዙውን ጊዜ ደግሞ ዛሬ መልአከ እገሌ፣ ነገ አባ እገሌ፣ በዓታ፣ ጸአታ፣ ፍልሰታ፣ ልደታ፣ ግንቦታ፣ እያለ አበሻ ሥራ ቢሰራ የተለየ ቀሳፊ የተመደበበት ይመስል ዐዛሬ ቅጠል አልበጥስም” እያለ ይኖርበት ከነበረው ዘመን ተፈትቶ በዘመነ ተሐድሶ ነፃ እየወጣ የዕለት እንጀራውን ለማግኘት ሌሊትና ቀን እየሰራ ነው። በዐል ሳያከብር ፈረንጅ ያመረተውን ስንዴና ዘይት በእርዳታ የሚለምን በዐል አክባሪ እንደአበሻ ግብዝ የት ይገኛል?

ስለዚህ የዘመነ ተሐድሶ የክርስቶስን ወንጌል የሚቋቋም ማንም አይኖርም። የክርስቶስን ወንጌል የሚያቆም ከሰማይ በታች ምንም ዓይነት ኃይል ወይም ማኅበር የለም። ይሁን እንጂ ወርክሾፕ፣ ስልጠና ፣ አቅም ግንባታ፣ ሕንጻ ግንባታ፣ ኤግዚብሽን ግንባታ፣ ዐውደ ርእይ ወዘተ መደረጉ አይቀርም፣ ይኽ መደረጉ የእግዚአብሔርን የተሐድሶ ሐሳብ አያቆመውም። ማኅበረ ቅዱሳን የብር ኢዮቤልዩውን እንዲህ ካሳለፈ ዕድሜው ከሰጠው የወርቁን ደግሞ አመራሩ ራሱ ከኑፋቄ ወጥቶ ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ በማምለክ ያከብረው ዘንድ የእግዚአብሔር የተሐድሶ እቅድ መሆኑን አንጠራጠርም።

Wednesday, June 15, 2016

በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው!!


የቁልቁለት መንገድ ተጀምሯል!

ይህ ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2004 በመካነ ጦማራችን ላይ የወጣ ነው። ደግመን ማውጣት ያስፈለገን፤ ሞት የሁሉም ሰው ጽዋ ቢሆንም ማኅበረ ቅዱሳን ፓትርያርክ ጳውሎስን በደጋፊ ጳጳሳቱ በኩል እስከሞት እያዋከበ መቆሚያና መቀመጫ እንዳያሳያቸው እነሆ ፓትርያርክ ማትያስን በተራቸው እስከሞት እየተዋጋ ለመቆየት መቁረጡ በዳበረ ልምዱ ሲሰራበት መቆየቱን ለማሳየት ነው። እንዲህ ብለናቸው ነበር። አንዳች ነገር ሳያደርጉ ሞት ወሰዳቸው፤ ማኅበሩም ሰፋለት። (አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው) ዛሬም ፓትርያርክ ማትያስን ለተመሳሳይ ጽዋ  በወከባና በአድማ እያንደረደረ ይገኛል። ማኅበሩ የሚተዳደርበት አዲስ ሕግ ሳይጸድቅ፤ በዐቃቤ መንበርና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የሥልጣን ነጠቃውን ጀምሯል። ወደፊትስ?

በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ማኅበረ ቅዱሳን ከተራ ማኅበርነት ወደ ሀገረ ስብከትነት  አደገ። በዚህም የተነሳ ሲኖዶሱ ሙሉ በሙሉ በማኅበረ ቅዱሳን እጁን ተጠምዝዞ እንደሚሰራ አስመሰከረ። የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ  የየሀገረ ስብከቶቹ  ጠቅላይ ጽ/ቤት ሆኖ ያገለግላል። ይህ ጽ/ቤት ደግሞ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ በየ3 ዓመቱ በሚያደርገው ምርጫ በሚመድበው ሊቀጳጳስ ነው። እንግዲህ ማኅበረ ቅዱሳን ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና አሥኪያጅ ሆነ ማለት ራሱን የቻለ ሀ/ስብከት  ሆነ ማለት ነው። የጠቅላይ ቤተክህነቱ መምሪያዎች ሊያዙት አይችሉም። ከዚያም በላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ ሊያዙት፤ ሊናገሩትና ሊቆጡት አይችሉም ማለት ነው። በቀጥታ በቅዱስ ሲኖዶስ በሚመደበው ሊቀጳጳስ በኩል ግንኙነቱ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋር ብቻ ይሆናል ማለት ነው። እንዲህ ነው እንጂ ሹመት፤ መሾም ካልቀረ!! አንድ ማኅበር ባንድ ጊዜ እመር ብሎ አናት ላይ ፊጢጥ ብሎ ከመቀመጥ ወዲያ ሹመት ከወደየት ይገኛል? ከእንግዲህ  ከተቀመጠበት ደረጃ አንጻር ማኅበር መባሉ ዝቅ የሚያደርገው ስም ስለሆነ የቅዱሳን መምሪያ ወይም የወጣቶች ሀ/ስብከት እንዲባል ሲኖዶሱ በነካካው እጁ ስሙንም ማሻሻል ይገባዋል። ከዚያም አያይዞ ለዚሁ አዲስ ሀ/ስብከት አንድ ሊቀጳጳስ እንዲመድቡለትም ጥቆማውን እናቀርባለን። አንድ ነገር ታዘብን። ቤተክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ የሚባል አካል እንደሌላት ተረዳን። በአንድ ተራ ማኅበር እየተመሩ የእሱን ጉዳይ ብቻ ሲያነሱና ሲጥሉ ሦስትና አራት ቀናት ስብሰባ መወዘፍን ምን ይሉታል? ስንት ስራ መስራት እየቻሉ ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ማውረድ እስኪያቅታቸው ድረስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አጀንዳ ይዞ መከራከርን እውነት ሰዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ነው የሚመሩት እንድንል ያደርገናል። ይህ ማኅበር ባይኖር ኖሮ ስለምን ጉዳይ ሊሰበሰቡ ነበር፤፤
ይህ ማኅበር እስካሁን እየታዘዘ እንዳልቆየ የተጻፉለት ደብዳቤዎች አረጋጋጮች ናቸው። እሱ ራሱ አልቀበልም ብሎ በደብዳቤ አረጋግጧል። አንዴ ከኢህአዴግ፤ አንዴ ደግሞ ከተቃዋሚ ነኝ እያለ፤ ሌላ ጊዜ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለልተኛ እየመሰለ የተጓዘበትን ሁላችንም እናውቃለን። የወንድሞች ከሳሽና አሳዳጅ ስለመሆኑም ግፉን የቀመሱ ሁሉ ይመሰክራሉ። የተጓዘባቸውን ስልቶች ሁሉ ያጠናው መንግሥት ከሽብር አቀንቃኝ  ከሰለፊያ ጋር በአንድ ረድፍ አንዳስቀመጠው ነግሮናል። ስለሆነም አቡነ ጳውሎስ ይህንን የአድማና በጥቅም የተሳሰረ ውሳኔ አልፈርምም በማለት ውድቅ ሊያደርጉት ይገባል። ማኅበሩ አስቀድሞ ከሰለፊያ ተግባር ነጻ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ማምጣት ይጠበቅበታል። ደጋፊዎቹ ጳጳሳትን በማስረጃና በሰው ምስክር ተጠንተው ብቁ ሆነው ያልተገኙ ካሉ ከማዕርጋቸው መሰናበት አለባቸው።  ቄስ የነበሩ፤ ልጆች የወለዱ፤ ቅምጥ ያላቸው እንዳሉ ይወራል፤ የአንዳንዶቹም ይታወቃል።  እየተሸፋፈነ መቀመጡ ለቤተክርስቲያን ጠንቅ የሆነ ውሳኔ ለማስወሰን ያልተመለሱ ሰዎች ስብስብ መሆኑ ከታየ ውሎ አድሯል።  ነውራቸውን ለመሸፈን እንኳን ከድመት አንሰዋል።
በአንድ ወቅት አባ ገብርኤል፤ አቶ ኢያሱ ተብለው ከማዕርጋቸው ተገፈው እንደነበረው፤ ማንነታቸው እንደገና ተመርምሮ  አስቸጋሪ በሆኑት ላይ ዛሬም ተመሳሳይ ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል። ጨከን ያለ የሥርዓት ማስከበር አካሄድ መውሰድ ካልተቻለ ሲኖዶሱን በነሱ በኩል እያወከ ነገ ፓትርያርክነቱን አስቀድሞ ከዚያም ቤተመንግሥቱን እንደሚረከብ የሚጠራጠር ካለ የማኅበሩን አካሄድ የማያውቅ ብቻ ነው። አመኑንም አላመኑም ፓትርያርክ ጳውሎስ፤ አንድ ነገር አስረግጠን እንነግርዎታለን። በማኅበረ ቅዱሳንና በደጋፊዎቹ ጳጳሳት ግብዓተ መሬትዎ ሊፈጸም የቀረው ጥቂት ነው። ከሆነለት ፓትርያርክነቱን ለሚታዘዝ  ሰው  ሰጥቶ ወደ ቤተመንግሥት ሰተት ብሎ ለመግባት ከጽዋ ማኅበርነት ወደ መምሪያ ተገዳዳሪነት፤ አሁን ደግሞ ወደ ሀገረ ስብከትነት ማደጉ ከምንም በላይ ማሳያ ነው።  ታዲያ ከእንግዲህ የቀረው ምንድነው? ይህ ሁሉ ለጽድቅ ነው እንዳይትሉንና እንዳንስቅ ጥቂት እዘኑልን። ነጋዴና  ሸቃጭ የሆነ  ቅዱስ ማኅበር  አራት ኪሎ የለም ። እያየነው በትንሽ በትንሹ የወጣው ይህ ሐረግ ቤተ ክህነቱን አንቆ ወዳሰበበት በመጓዝ ላይ ነው። እግዚአብሔር ለዚህ ክፉ ማኅበር አሳልፎ ከሰጠ በእውነትም ቤተክርስቲያኒቱ ለፈተናና ለውድቀት ተመርጣለች ማለት ነው። ተወደደም፤ ተጠላ ሲኖዶስ በየዓመቱ ያለህውከት ማለፍ አይችልም።
ሰውዬው «ሁሉን ለማየት መቆየት»እንዳለው የሚሆነውን ለማየት ከዕድሜው አይንፈገን!

Monday, June 13, 2016

"ፓ" ይላል ምዕመኑ!!!



«በዘውድአለም ታደሰ»
ነብይ ነኝ ባዩ የቤተክርስቲያን ደላላ!

ይሄ ሰውዬ "ጎሳ" ይባላል። በተለያየ ጊዜ የተለያዩ ቸርቾች ሲሰብክ አይቼዋለሁ። (ጎፋ መድሃኒአለም ፣ ዘፀአት ፣ FBI ፣ ወዘተ... ) የሚደክም አይነት ሰው አይደለም። ውሃ ሳይጎነጭ በተከታታይ ለሶስት ሰአታት የማውራት አቅም አለው! የምእመኑን ሳይኮ በልቶታል። ህዝቤን ምን እንደሚያስጮሀት ስለሚያውቅ አዳራሹን በጩኸት መናጥ ለነብይ ጎሣ ቀላል ነው!
ብዙ ግዜ ቸርቾች ይህን ሰውዬ ሚጋብዙት ገንዘብ ክፉኛ ሲያስፈልጋቸው ነው። ወይ መሬት ሊገዙ ሲያስቡ ... አሊያም የተሻለ አዳራሽ ሊከራዩ ሲፈልጉ ... ብቻ የሆነ የፈንድ ሬይዚንግ ጉዳይ ሲኖር ጎስሻን ይጠሩትና በዚያች ጮሌ ምላሱ የራሱንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ታሪክ እያጋነነ በመስበክ የዚህን ምስኪን ምእመን ኪስ ያራቁትላቸዋል!
«ነኝ ያልኩ ኮንትራክተር ነበርኩ፣ ነፍፍ መኪኖችና ብዙ ሰራተኞች ነበሩኝ፣ ጌታ ሲገባኝ ግን ንብረቶቼን ሸጬ ለቸርች ሰጠሁ» ብሎ ይጀምራል ተረት ተረቱን።
«ፓ» ይላል ምእመኑ!
«ከዛ ክፉኛ ተቸገርኩና፣ ምልስ ምቀምሰውን አጣሁ፣» ብሎ ለፅድቅ ሲል የከፈለውን መከራ እያጋነነ ያወራል!
«በከተማዋ ስሜ የተጠራ ኮንትራክተር እንዳልነበርኩ ምልስ ምቀምሰውን አጥቼ ተቸገርኩ» ሲል ረሃብን የሚያውቀው የዚህ ህዝብ አንጀት በሀዘኔታ ይላወሳል።
የሰዉን አቴንሽን ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ታዲያ ... እንዴት ተአምራዊ በሆነ ሁኔታ እግዜር ሀብታም እንዳደረገው፣ እንዴት እንዳበለፀገው ትረካ በሚመስል ሁኔታ ያወራ ያወራና የህዝቡን አእምሮና ስሜት በሚገባ እንደተቆጣጠረ ሲረዳ እንዲህ ይላል ..
«ጌታ እንዲህ ሲል ተናግሮኛል» ብሎ ይጀምራል ነብይ ጎሳ። (ማን ነብይ እንዳረገው እንጃለቱ)
«ጌታ ዛሬ በዚህ አዳራሽ ውስጥ ያላችሁትን ሁላችሁን እባርካለሁ ብሎኛል» ሲል እቺ በረከቷን ከአርያም ሳይሆን መድረክ ላይ ከቆመው አረም የምትጠብቅ ምእመን አዳራሹን በጩኸት ታቀልጠዋለች! በጭብጨባው የሚሟሟቀው ጎሲሻም «አንዳንዶቻችሁ ከዚህ አዳራሽ ስትወጡ ከበረከታችሁ ጋር ትገናኛላችሁ» ሲል አዳራሹ በአንድ ድምፅ «አሜን» ይላል።
«አንዳንዶቻችሁ ደግሞ ቤታችሁ ስትገቡ በረከታችሁ ቁጭ ብሎ ይጠብቃችኋል»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ ስራ ቦታችሁ ላይ»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ሳምንት»
«አሜን»
«አንዳንዶቻችሁ የዛሬ ወር»
«አሜን»
«እግዜር በተራራው ላይ ሙሴን ሲያገኘው በእጅህ ላይ ምን አለ? ብሎ ነው የጠየቀው ወገኖቼ። እግዜር እጃችን ላይ ባለ ነገር ነው ሚሰራው። ዛሬ በእጃችሁ ላይ ምን አለ?» ይላል ብልጣብልጡ ጎሳ!
ይሄ የዋህ ሁን ሲባል ሞኝ የሆነ ህዝብም እውነት መስሎት እጅና ኪሱን ያያል! ከዛማ በቃ አዋራው ይጨሳል .... ፒፕሉ በረከቱን በስጦታው ለመግዛት ይጋፋል! አዳሜ ወርቋን ከአንገቷ ላይ እየበጠሰች፣ ገንዘቧን ከቦርሳዋ እያራቆተች፣ ምንም የሌላት ደግሞ የእጅ ስልኳን ሳይቀር መባ እቃ ውስጥ እየጨመረች የማይፈፀም ትንቢት ታቅፋ እርቃኗን ከአዳራሹ ትወጣለች ... ልትባረክ ነዋ ሃሃሃሃ
ከላይ እንዳልኩት ነብይ ጎሳ ነብይነቱን ከየት እንዳገኘው ማንም አያውቅም። የሚያወራው ታሪክም እውነት ስለመሆኑ ምንም ማረጋገጫ የለም። ይህን ሰውዬ የሚጋብዙት ስግብግብ የቤተክርስቲያን አገልጋዮችም የሰውየው ምስክርነት እውነት የተፈፀመ ይሁን አይሁን ለማረጋገጥ ምንም አይነት ጥረት አያደርጉም! እነሱ ሚፈልጉት በሱ ጅንጀና የሚዘንበውን የገንዘብ ዶፍ ነው። የስብከቱ መለኪያ በሱ ስብከት አማካኝነት የገባው የገንዘብ መጠን ነው እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም!
አሁን ቤተክርስቲያን በጎሳና ጎሳን በሚመስሉ መንፈሳዊ ደላሎች እየታመሰች የምትገኝበት ሰአት ላይ ትገኛለች። መፅሀፉ ጎሳንና መሰል አገልጋዮችን «ለመንጋው የማይራሩ» ይላቸዋል!
እንዲጠብቁት የተሰጣቸውን ምእመንና እረኛ የሆኑለትን መንጋ ስጋ እየበሉ ሰብተው ቆዳውን ገፍፈው ይለብሳሉ! በአስራትና በበኩራት፣ በመባና በፍቅር ስጦታ ስም፣ ገንዘቡ ወደካዝናቸው ይጋዝ እንጂ የገንዘቡ አመጣጥ እነሱን አያስጨንቃቸውም። በምእመኑ ፍራንክ ትልልቅ እቅዶች ያቅዳሉ፣ የህዝቡን መሶብ አራቁተው ሰማይ ጠቀስ ፎቆችን ይገነባሉ፣ በሊትር ሶስት ኪሎሜትር የሚሄዱ ላግዥሪ መኪኖችን ይነዳሉ። ይሄ ተስፈኛ ምእመን ግን ከሰማይ መና እየጠበቀ በደረቅ ምድረ በዳ ደረቅ ትንቢታቸው ታቅፎ ከቃዴስ ቃዴስ ሲንከራተት ይኖራል።
በአብዛኞቹ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያኖች ዘንድ ምድር ምድር የሚሸት ስብከት በዝቷል። ሰባኪው ሁሉ የ prosperity Gospel (የብልፅግና ወንጌል) አቀንቃኝ ሆኗል፣ ምእመኑም በረከቱን የሚለካው በምድራዊና ቁሳዊ ሀብት ብቻ ነው! «ሀገሬ በሰማይ ነው» አይነት ንግግሮች ከምእመኑ አንደበት መደመጥ አቁመዋል። ኢየሱስ የሞተው ለቼቭሮሌት መኪናና ለግራውንድ ፕላስ ስሪ ፎቅ ይመስል ወሬው ሁሉ ቤት ስለመስራትና ቤት ስለማፍረስ ሆኗል ... እንደ ዊነርስ ቻፕል አይነት ቸርቾችማ ወሬው ሁሉ ሱሪ ስለመቀየርና መኪና ስለመንዳት ከሆነ ቆየ። «በመንፈስ መኪና የመንዳት» ፕሮግራም ሁሉ ያካሂዳሉ አሉ! ሃሃሃ
ነብያቶች በዝተዋል። ነብይነት ግን ከሞተ ቆየ! ሰባኪዎችም አሸን ናቸው። ስብከት ግን ስልሳዎቹ ላይ ቆሟል! በየመድረኩ ተኳኩለው እንጣጥ እንጣጥ የሚሉ (ባለብዙ ሚስት ዘማሪዎች እልፍ ናቸው) መንፈሳዊ ማንነትን የሚያንፅ መዝሙር ግን ከመድረኩ ነጥፏል!
በፅድቅና በቅድስና የሚያገለግሉ አንዳንድ አገልጋዮች እንዳሉ አይጠፋኝም። ግን እነዚህ አገልጋዮች ከጎሳውያኑ ጋር ሲተያዩ በገምቦ ውስጥ እንዳሉ ጥቂት ጠብታዎች ናቸው! ስለዚህ ባህር ውስጥ እንዳሉ አይቆጠሩም። እኔ ማወራው ባህሩን ስለሞሉት የተበከሉ አሳዎች ነው!
 ቸርቾች በየመቶ ሜትሩ ከተማ ውስጥ ፈልተዋል። ደቀመዝሙር ማፍራት የማይችሉ ውሀ አልባ ምንጮች ናቸው እንጂ! ክርስቲያን ያልሆኑ የክርስቶስ ሰባኪዎችና ክርስቶስን የማያውቁ አገልጋዮች ይሄን ምስኪን ምእመን እንደአሻንጉሊት እየተጫወቱበት ነው! አገልግሎታቸው ያከበራቸውን ህዝብ በመናቅና በማስፈራራት ላይ የተመሰረተ ነው! «ለምን?» ብሎ ጥያቄ የሚያነሳ ሲመጣ «ጌታ በቀባው ላይ እጅህን አታንሳ» በማለት በጥቅስ ያስፈራሩታል። በፅድቅ ለማገልገል ከላይ እታች እያሉ የጅብ ድግሳቸው ላይ የማይሳተፉትን ንፁሀን ደግሞ የተለያየ ስም ጀርባቸው ላይ በመለጠፍ ከአገልግሎት ያግዷቸውና የሚከተላቸውን ምእመን ኑሮ እየቀሙ ይኖራሉ! ሳቁን መንትፈው ይስቃሉ! ደስታውን አራቁተው ይደሰታሉ! እውነትም ለመንጋው የማይራሩ ሆዳሞች!
ዘመኑ የባቢሎናውያኑን ዘመን ይመስላል። ትርምስ እንጂ መረጋጋት የለም! ጩኸት እንጂ መግባባት ጠፍቷል። ግራ የተጋቡ ባለራእዮችና ያልተማሩ አስተማሪዎች መሬት ባልረገጠ የትምህርት ወጀብ ህዝቡን እየናጡት ነው። በተቀየጠ ዶክትሪንና በስህተት አስተምህሮ ምእመኑን ከወንጌል አርቀው አይኑን በማሰር ወደቁልቁለት እየነዱት ነው! ነብያት ነን ባዮቹ ወንዝ በማያሻግር ትንቢት ሲወራጩ መድረኮቻችን ላይ ውለው ያድራሉ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች በተራ ፉከራና ሽለላ የተሞሉ ፍሬ አልባ ደረቅ መሬቶች ናቸው!
በተለያዩ ቤተክርስቲያኖች እየተጋበዘ ህዝቡን የሚያራቁተው ደላላው ነብይ .... «ነብይ ጎሳም» ከላይ ለጠቀስኳቸው ሆዳም አገልጋዮች እውነተኛ ምልክት ሊሆን ይችላል ባይ ነኝ!

እቀጥላለሁ!‎

Saturday, June 4, 2016

ማኅበረ ቅዱሳን አሁን የቤተ ክርስቲያን፤ ቆይቶ የመንግሥት መጥበሻ ምድጃ ነው!


በታሪክ አጋጣሚ የደርግን መውደቅና ግርግርን ተተግኖ የተፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን የመጥበሻ ምድጃ ከሆነ እነሆ 23 ዓመታት አለፉት። ብዙዎችን በትኗን፤ አሳዷል። ዳግም እንዳይመለሱ በማድረግ እንደተዋጊ በሬ እየበጠበጠ ከበረት አስወጥቷል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አፋፍተው ያሳደጉትን አቡነ ጳውሎስን ሳይቀር በአድማ የመጥበሻ እሳት እየለበለበ እስከመቃብር ሸኝቷል። የአሁኑን ፓትርያርክ የአቡነ ማትያስን ወንበር በተሾሙ ሰሞን ለመረከብ ተፍ ተፍ ብሎ ሳይሳካለት ቢቀር በተለመደ የመጥበሻ ምድጃው ላይ አስቀምጦ ላለፉት 3 ዓመታት  በአድማው ግሪል / GRILL/ እየጠበሰ ይገኛል።

ፓትርያርክ ማትያስ ብቻቸውን ሆነው ይህንን መጥበሻ ምድጃ ሊያስወግዱ ብዙ ታግለዋል። ነውራም ጳጳሳቱ እዳ በደላቸው በዚህ ማኅበር የኃጢአት መዝገብ ላይ ስለሰፈረ ከፓትርያርኩ በተጻራሪ ቆመው ውግንናቸው ለማኅበሩ ሆኖ ታይቷል። የማኅበሩ ሥፍራ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የት ነው? በሚለው ነጥብ ላይ ጥያቄ ያላቸው ፓትርያርክ ማትያስ ድርሻውን፤ አቅሙንና ተጠሪነቱን የሚወስን አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲወጣለት ያደረጉት ተጋድሎ ላይ ውሃ በመቸለስ የሲኖዶስ ጉባዔ በመጣ ቁጥር የሚያጨቃጭቅ አጀንዳ እያስገባ ሲሾልክ ቆይቷል። ዘንድሮም ይህን የቤት ሥራ ሰጥቶ በአንድ አጀንዳ ላይ ለ4 ቀናት ካጨቃጨቀ በኋላ የሲኖዶስ አባል የሆነው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር መፍትሄ አስምጦ ሊገላግላቸው ችሏል። ይህ ሁሉ የሆነው በማኅበሩና በጉዳይ ፈጻሚ ጳጳሳቱ የተነሳ ነው።

የእንደራሴ መኖር አለመኖር ለማኅበረ ቅዱሳን አሳሳቢው አይደለም። ነገር ግን በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ማንሳት ያስፈለገው የራሱ ስሌት ስላለው እንጂ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ድክመት ከሱ መኖር በላይ አስቸጋሪ ፍጡር ስለመጣ አይደለም። በዚህም የተነሳ በአቅም ማነስ ሰበብ ፓትርያርኩን አሸመድምዶ በማስቀመጥ ለ3 ዓመታት ያህል እሳት ካነደዱበት ሥጋት ነጻ ለመውጣት የተያዘ መላ ከመሆን አይዘልም። ከዚህም በፊት እንዳልነው ጳጳሳቱ በሀገረ ስብከታቸው መሥራት ያልቻሉትን የመንፈሳዊና ሥጋዊ የልማት ሥራዎች  እንደራሴው እየዞረ የሚሰራላቸው አለመሆኑንም በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን እስካለ ድረስ ታዛዥ ያልሆነ የትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለሥልጣን  ማኅበሩ ባዘጋጀው መጥበሻ ላይ ይጣዳል። ምርጫቸው ከማኅበሩ ጋር መቆም አለያም በተጻራሪ ሆነው ለመጥበሻው ራሳቸውን ከማዘጋጀት የግድ ነው። አባ ሳዊሮስ ከአዲስ አበባ ማኅበረ ካህናት ጋር ቆመው ማኅበሩን ሲያጋልጡ ምድጃውን አዘጋጅቶ መጥበስ ሲጀምር እጃቸውን አንስተው ለማኅበሩ ለማስረከብ መገደዳቸውን አይተናል። አባ ፋኑኤል ማኅበሩ የሌለበት ቦታ የት ሄጄ ልሥራ? እንዳላሉ ሁሉ ምርኮኝነታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን ከማኅበሩ መጥበሻ ግሪል ላይ ወርደው እረፍት ሊያገኙ ችለዋል። ሌሎቹ ግን የሚደርስባቸውን እሳት አስቀድመው ስለሚያውቁ ቃላቸውን አክብረው የጫናቸውን በማራገፍ ግንቦትና ጥቅምት በመጣ ቁጥር በማኅበሩ አጀንዳ አስፈጻሚነታቸው ቀጥለዋል።

 ማኅበረ ቅዱሳን በስመ ተሐድሶና ሙሰኛ ነጠላ ዜማው የፈጃቸውና ያቃጠላቸው ካህናት ቁጥራቸው ብዙ ነው። ስለቅድስናና መንፈሳዊ ንጽህና በዋለበት ያልዋለ የዋልጌዎች ስብስብ ይህ ማኅበር ስም እያጠፋ ያሳደዳቸው፤ ስለኃጢአታቸው ንስሐ የሚገቡበትን በር እየዘጋ ተስፋ በማስቆረጥ ያስወጣቸው የትየለሌ ናቸው። የሚገርመው ግን ነውራም ጳጳሳቱን በቅድስና ካባ ሸፍኖ ለአገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው የከባቴ አበሳ ተፈጥሮ ስላለው ሳይሆን እስካለገለገሉት ድረስ ብቻ ነው። እያንዳንዱ የማኅበሩ አባል በተለይም አመራሩ እነአቡነ እገሌ እስከምን ድረስ የጉስቁልና ባሕር ውስጥ እንደሰጠሙ እያወቀ በስምምነት አብሮ ይሰራል። ነገር ግን ከማኅበሩ አቋም ካፈነገጡ ከዚህ በፊት እንዳደረገው የእዳ ደብዳቤአቸውን ከማንበብ አይመለስም። ይህ በተግባር የተረጋገጠ እውነት ነው።

አንዳንዶች ማኅበሩን የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ብቻ አድርገው ያያሉ። ነገር ግን ማኅበሩ  እንደግብጹ የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር በፖለቲካው መድረክም የረቀቀ ተልእኮ ያለው ማኅበር ነው። በአባልነት ያቀፋቸው ሚኒስትሮች፤ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች፤ ሥራ አስኪያጆች፤ ፖሊሶች፤ ዳኞች፤ የሕዝብ አገልግሎት ሠራተኞች፤ መምህራንና ተማሪዎች፤ የሙያ ማኅበራት፤ በ44 አኅጉረ ስብከት ውስጥ ያሉ ሚሊዮኖች የሰንበት ት/ቤት አባላት፤ የጥምቀት ተመላሽ ተጠባባቂ ጦር የመሳሰሉትን በአባልነት እየመለመለ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የራሱን ዶክትሪን በመጋት ማኅበረ ቅዱሳን፤ ማኅበረ ቅዱሳን ካሰኛቸው ውሎ አድሯል። ዛሬ ከሲኖዶስ ወይም ከፓትርያርኩ በላይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪና ጠባቂ ከማኅበሩ በላይ የለም የሚለው አስተሳሰብ በእያንዳንዱ ሰው አእምሮ ውስጥ እንዲሰርጽ በሰፊው ተሰርቷል። ዘመናዊ የክርስቲያን ብራዘር ሁድ ማለት ማኅበረ ቅዱሳን ነው።

ሌላው የማኅበሩ ተንኮል አሁን ካሉት ታማኝና ታዛዥ ጳጳሳት በተጨማሪ ከእንግዲህ የሚሾሙ ኤጲስ ቆጶሳት በራሱ መስፈርት የተመለመሉና ወደፊት ችግር እንደማይፈጥሩ የተረጋገጠላቸው ብቻ እንዲሆኑ ይፈልጋል። እነዚህ የማኅበሩ እጩ ኤጲስቆጶሳት ያለፈ ታሪካቸው የቱንም ቢመስል አሳሳቢ አይደለም። ተቀባይነታቸው አርአያነት ባለው ሁኔታ ቢሆንም፤ ባይሆንም ለማኅበሩ አስጊ እስካልሆኑ ድረስ እንዲመረጡ አጥብቆ ይሰራል። ነገር ግን በተቃራኒ ማኅበሩን የሚፋለሙ ከሆነ እንደአባ ሠረቀብርሃን ወ/ሳሙኤልን የመሳሰሉት በልዩ ልዩ ስምና ወንጀል በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ እጃቸውን ካልሰጡ በስተቀር ለእጩነት ሊቀርቡ አይችሉም።

በአጠቃላይ ማኅበሩ በታሪክ አጋጣሚ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የተገኘ መጥበሻ ምድጃ ነው። በዚህ ምድጃ ዲያቆናት፤ ቀሳውስት፤ መነኮሳት ተጠብሰዋል። ሰባኪያነ ወንጌልና አስተዳዳሪዎች ተጠብሰዋል። ጳጳሳትና ፓትርያርኮች ተጠብሰዋል። እውነቱን እያወቁ ከመናገር ብዙዎች የተቆጠቡት ማኅበሩ መጥበሻው ላይ ከጣዳቸው የሚያወርዳቸው ስለሌለ ነው። ልክ እንደ መንግሥታዊ የስለላ መዋቅር የማኅበሩን ስም በተቃውሞ በአውቶቡስ፤ በታክሲ፤ በሬስቶራንት፤ በየካፌውና በሕዝብ መሰብሰበቢያ ቦታዎች መጥራት ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። መንግሥት ላይ ምን ዓይነት የአንኮበር መድኃኒት እንደተረጨበት ባናውቅም እሱም በፍርሃት ይሁን በድንዛዜ ፈዞ ቀርቷል።  እውነታው ግን ማኅበሩ ለየትኛውም ወገን መጥበሻ ምድጃ መሆኑ በተግባር የተረጋገጠ ነው።

Wednesday, June 1, 2016

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?




አበው ዘይቤያዊ ምሳሌ ሲሰጡ፤ ፍሬ ነገሩን  ሊገልጥ የሚችል ጥሩ ኃይለ ቃል ይጠቀማሉ። በአንድ ዐረፍተ ነገር ብዙ ሐተታ ሊወጣው በሚችል መልኩ የጉዳዩን ብስለትና ጠጣርነት በደንብ ያሳዩበታል። ለዚህም ነው «ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» በማለት መሆን የማይገባው ነገር ሆኖ ቢገኝ መፍትሄው ግራ የሚያጋባ እንደሆነ ለማስረዳት ይፈለጉት። አዎ፤ በዘመነ አበው ምላጭ፤  እባጭ እንዲፈነዳ፤ የተቋጠረው መግል እንዲፈርጥ ይበጡበት ነበር። በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ዛሬም አልፎ፤ አልፎ ይሰራበታል።  ነገር ግን ምላጭ ራሱ ቢያብጥ በምን ይቆረጣል? ውሃስ ቢያንቅ በምን ማወራረድ ይቻላል? ግራ የሚያገባ ነገር ነው። መሆን የሌለበት ሆኖ ሲገኝ ያስገርማል፤ ያስደነግጣል፤ መፍትሄውም ሩቅ ይሆናል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየታየ ያለው ድርጊት የዚሁ ምሳሌ ተመሳሳይ ነገር ነው። በቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ የቅዱስ ሲኖዶስ መንበር ከተመሠረተ ከ50 ዓመታት እጅግም ያልዘለለ ጊዜን ያስቆጠረ ቢሆንም በዚህ አጭር እድሜው 50 ጉድ አሳልፏል። ፓትርያርኳን አሳልፋ በመስጠት ለደርግ ጭዳ ማቅረቧም በማስረጃ የተረጋገጠ እውነት ነው። ፓትርያርክ አውርዳ ፓትርያርክ ሾማለች። ለሁለት የተከፈለ ሲኖዶስም የያዘችው በዚሁ አጭር እድሜዋ ነው። የሐዋርያትን መንበር ተረክቤአለሁ የምትለዋ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያት እንዳደረጉትና የራሱን ሥፍራ በለቀቀው በይሁዳ ምትክ እንደሾመችው ሐዋርያ በመንፈስ ቅዱስ ምርጫ እጣ ማጣጣል ሲገባት እንደፖለቲካ የካድሬ ምርጫ በሰውኛ አሳብና እንደተሰጣቸው ተልእኮ በሚመለመሉ ሰዎች ምርጫ መሾሟም የዚሁ የአጭር ዘመን ታሪኳ አንዱ ክፍል ነው። 

ነውርና ነቀፋ የሌለበት፤ ራሱንና ቤተሰቡን በአግባቡ ስለመምራቱ በምእመናንና ምእመናት የተመሰከረለት አገልጋይ ሰው ኤጲስ ቆጶስ እንዲሾም ቃለ ወንጌሉ ቢናገርም ከንባብና ከአንድምታው በዘለለ ተግባር ዳገቷ ቤተ ክርስቲያን ሆና ለሰሚ የሚቀፍ፤ ለሚያውቁት የሚያሳፍር ሹመት እየፈጸመች በመገኘቷ እነሆ ጥቅምትና ግንቦት በመጣ ቁጥር የዘራችውን እያጨደች ትገኛለች።
   «መልካም ዘር መልካም ፍሬ ያፈራል» እንዲል ወንጌል የዚህ ተቃራኒ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለመዘራቱ ደግሞ ፍሬውን ሲኖዶስ በመጣ ቁጥር ጭቅጭቅ፤ ንትርክ፤ ሁከትና አድማ ሲያስተናግድ ማየት የተለመደ ሆኗል። ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ለትውልድ የፈውስና የምሕረት መልእክተኛ መሆን የሚገባው አካል ለራሱ ከፈውስም ሆነ ከምሕረት ስለራቀ መሆን በማይገባው ሁኔታ ውስጥ ይገኛል። 

«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡታል፤ ውሃስ ቢያንቅ በምን ይውጡታል?» ማለት ይኼ ነው። ሰው በልቡ መታደስ ካልተለወጠና የማይሞተውን የሞት አሸናፊ ካልለበሰ አዲስ ፍጥረት እንደማይሆን ሐዋርያው በመልእክቱ ነግሮናል።  ካልተለወጠና የቀድሞ ግብሩን ካልተወ አሮጌነት ደግሞ አብሮት ያለው ማንነት በክፋትና በተንኮል ተግባር እየተገለጠ በዘመኑ ሁሉ ይቀጥላል። ዛሬም በሲኖዶስ ጉባዔ ላይ የሚታየው ችግር ሁሉ የውስጥ ማንነቱ ማሳያ መስታወት ነው። ሰው የሌለውን ውበት ከየትም ሊበደር አይችልም።
ሰሞኑን እየተካሄደ ባለው ሲኖዶስ (ቅዱስ ለማለት ይከብደኛል) ምክንያቱም ካልተወሻሸንና ሞራል እንጠብቅ ካልተባለ በስተቀር መንፈስ ቅዱስ የሁከትና የንትርክ አምላክ ስላይደለ ቅዱስ ለማለት ይከብዳል። በስብሰባው ላይ እየታየ ያለው ኢ-መንፈሳዊና ኢ-ሥነምግባራዊ ድርጊት ከስምና ከማዕርግ እድገት በስተቀር ያልተለወጠ ማንነት የተንጸባረቀበት እጅግ አሳፋሪና አሳዛኝ ክስተት የታየበት ስለሆነ ነው። 

 «ከእናንተ አንዱ ከባልንጀራው ጋር ሙግት ቢኖረው በቅዱሳን ፊት በመፋረድ ፋንታ በዓመፀኞች ፊት ሊፋረድ ይደፍራልን? ቅዱሳን በዓለም ላይ እንዲፈርዱ አታውቁምን? በዓለምስ ላይ ብትፈርዱ ከሁሉ ይልቅ ትንሽ ስለሚሆን ነገር ልትፈርዱ አትበቁምን?» 1ኛ ቆሮ 6፤1-2

በቅዱስ ስም ተሰብስቦ፤ በዓለማውያን ምናልባትም እግዚአብሔርን በማያውቁ ዐመጸኞች ፊት የጉባዔ ዳኝነት ከመጠየቅ ወዲያ ለሲኖዶስ ምን ሞት አለ? አሁን እውነት ሕይወት ያለው ሲኖዶስ የሚባል አካል አለ ማለት ነው? ይህ ሁሉ የሆነውና እየሆነ ያለው በሞተ አካል ውስጥ ያለው የሙት መንፈስ ፍሬውን እያፈራ በመገኘቱ የተነሳ ነው።  ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ፤

 «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ» በማለት የተናገረው። የሐዋ 20፤28-30

መንጋው ተበትኗል፤ ለሚጠፋው በግ የሚራራ እረኛ የለም፤ ቤተመቅደሱ በርግብ ሻጮችና በለዋጮች ተሞልቷል፤ እርስ በእርሳቸው የሚነካከሱና የሚበላሉ ሆነዋል፤ ነገር ግን በሕይወት አለን ይላሉ። ለሥልጣን ሽሚያ፤ ለመፈንቅል፤ ለቡድን አሸናፊነት፤ ለማኅበር የበላይነት ይጋደላሉ።
 በየተመደቡበት ሀገረ ስብከት እንደነገሥታት የሚሰጣቸው ስግደት ሳይጎድል፤ እንደሰማያዊ ሹም ሆነው መታየታቸው ሳይጠፋ ምንም የሰሩትና ያለሙት በሌለበት ሁኔታ ዓይናቸው ሁል ጊዜ የሚያየው እዚያ ጣሪያ ላይ ነው። ጣሪያው ደካማ ይሁን ሰነፍ የሚያስቀምጠው አንድ ሰው ነው። ጣሪያው ላይ ሰው ሲቀመጥ ያልታገሉ ፈራህያን ዛሬ የሚያደቡት ምን ለማግኘት ነው? ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስበው? ተጨንቀው? በጭራሽ አይደለም።
 ጳጳሳቱ ሰው ከመቅጠርና ከማባረር ባለፈ ሚሊዮን ተከታዮቻቸውን አሰልፈው ትምህርት ቤት፤ ጤና ጣቢያ፤ የንጹህ መጠጥ ውሃ፤ የብሎኬት ማምረቻ፤ የእንጨት መሰንጠቂያ፤ የመስኖ ልማት፤ የልብስ ስፌት፤ የጧፍና ሻማ ማምረቻ፤ የአልባሳትና ቅርሳ ቅርስ ተቋም፤ የዶሮና የከብት እርባታ፤ የዳቦ መጋገሪያ፤ የካህናት ማሰልጠኛ፤ ኮሌጆች፤ ዩኒቨርሲቲዎች፤ የህጻናት ማሳደጊያ፤ የአረጋውያን መጦሪያ ለምን አያቋቁሙም? ለምን አይሰሩም? ማን ከለከላቸው?
ከ15 ሚሊዮን ያልበለጠ ተከታዮች ያሏት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት በረሃውን ገነት ያደረጉት፤ ምርትና ሃብታቸው የተትረፈረፈው እንደእኛ ጳጳሳት በፎጣ በመሸፋፈን ሳይሆን በአጭር ታጥቀው ከእስላም ሰይፈኞች ጋር በመታገልና ተግተው በመስራታቸውና በማሰራታቸው ነው። ከላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ያልሰራችው የልማት ስራ የለም።  በጀት ተመድቦላቸው፤ ባለሙያ ተቀጥሮላቸው ሳይሆን መነኮሳቱን፤ ካህናቱን፤ ምእመናኑን በማስተማርና በማሰልጠን በራስ አገዝ የልማት ተሳትፎ የተመሰረተ ነው።
 የኛዎቹ ለግንቦቱ ጉባዔ ከጥቅምት ጀምሮ ከመዶለትና ለጥቅምቱ ጉባዔ ደግሞ ከግንቦት ጀምሮ ሴራ ከመጎንጎን በስተቀር በሀገረ ስብከታቸው የልማት ርእይ፤ እቅድና ግብ በጭራሽ የላቸውም። ከሐውልት ምርቃት፤ ከቀብር ክፍያ፤ ከክርስትና፤ ከጋብቻ፤ ከፍትሃት፤ ከጸበል፤ ከሰበካ ጉባዔ አባልነት ወዘተ የሚሰበስቡትን ሚሊዮኖች ብር ለደመወዝና ለስራ ማስኬጂያ ከማዋል ባለፈ ተመልሶ ለሕዝቡ ልማት የዋለው ምን ያህሉ ነው? በደቡብ ክልል አካባቢ ያሉ የኦርቶዶክስ ምእመናን «እናንተ አምጡ እንጂ እንደሌሎቹ እንኩ አታውቁም» ማለታቸውን ስንሰማ የኛዎቹ መስጠትን ሳይማሩ አምጡን ከየት ለመዱት ያሰኛል።

    በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውድቀትና ማሽቆልቆል ተጠያቂዎቹ ጳጳሳቱ ናቸው። ለመንጋው መበተን፤ ለስርቆትና ሥነ ምግባር ጉድለት ኃላፊነቱን መውሰድ አለባቸው። የታጣው መሪ እንጂ  ለመመራት ፈቃደኛ፤ ለመስጠት እጁን የማይዘረጋ  ምእመን የለም። ደግሞስ እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ምእመን እጁን የሚዘረጋ አለ እንዴ?
 በሀገረ ስብከታቸው ልማት ሳያሳዩ ወደላይ መንጠራራት ስንፍናቸውን እንጂ አዋቂነታቸውን አያመለክትም። ጳጳሳቱ ለድክመታቸው ምክንያት ፓትርያርኩ ላይ አመልካች ጣታቸውን ከመቀሰራቸው በፊት እኔ በሀገረ ስብከቴ ምን ሰራሁ? ብለው ራሳቸውን ይጠይቁ። ብዙዎቹን ጳጳሳት ከምንኩስና ጀምሮ ስለምናውቃቸው ስለማንነታቸው ነጋሪ አያሻንም። ከታች ጀምሮ ያልተገነባ ስብእናና ችሎታ ደረጃቸው ስላደገ ባንዴ አብሮ አይመነደግም። ቁም ነገሩ እንደእኛው ችሎታ የሚያጥራቸው ሰዎች መሆናቸው ሲሆን አሁን አለቃቸውን ማስቸገር ቀደም ሲል በአለቅነታቸው ካዳበሩት ችግር የተማሩት ብቸኛ እውቀት ይመስለኛል።  ከዚያ ባሻገር በልማታቸው ለሕዝቡ የመኖር ተስፋ ወይም በጸሎታቸው ለሀገር የሚተርፉ ሆነው 15 ሚሊዮን ሕዝባችንን ከድርቅ ሲታደጉ አላየንም። ከመንጋ ጳጳስ እንዴት አንድ ኤልያስ ይጥፋ? ተግባር እንጂ ስም አላልኩም።

በግንቦቱ ሲኖዶስ ተሰብስበው በፓትርያርክ ማትያስ የችሎታ ማነስ ላይ ከመሳለቅ አስቀድመው በራሳቸው የአቅም ማነስ ላይ ቢወያዩ የተሻለ ነበር። ምሳሌ እንስጥ፤  ከ1985 ዓ/ም ጀምሮ 23 ዓመት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ሆነው የቆዩት የአሁኑ አባ ጎርጎርዮስ፤ ሟቹ አቡነ ጎርጎርዮስ ከመሰረቱት የዝዋይ ካህናት ማሰልጠኛና የአትክልት ልማት ወዲህ ስንት ማሰልጠኛ አቋቋሙ? ስንት የልማት አውታር ተከሉ? እውነታው ምንም ነው። አባ ቄርሎስስ በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት ስንት የካህናት ማሰልጠኛ፤ ስንትስ የእደ ጥበብ ተቋም ተከሉ? ስንት የከብት ማድለቢና የዶሮ እርባታ አቋቋሙ? ማን እንዳያደርጉ ከለከላቸው? ሟቹ አባ ጳውሎስ ወይስ ሕያው አባ ማትያስ?

 በምሥራቅ ጎጃምና በምዕራብ ጎጃምስ ምን ተሰራ፤ በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ሀ/ስብከትስ ምን ልማት ተቋቋመ? በአጭር ጊዜና በረጅም ጊዜ እቅዳችሁ ምን አሳካችሁ?  በደን ልማት ላይ ሕዝቡን በማስተባበር በዚህ ዓመት ስንት ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል ተዘጋጅታችኋል?
እርግጥ ነው ጳጳሳቱ በሌላ የሥራ መስክ ላይ አልቦዘኑም። የግል ቤታቸውን ገንብተዋል፤ ዘመናዊ መኪና አስገዝተዋል። በባንክ ገንዘባቸውን አጭቀዋል። ዘመድ አዝማዳቸውን በየቤተ ክርስቲያናቱ ቀጥረዋል።  
በአንድ ወቅት መንግሥቱ ኃ/ማርያም ሚኒስትሮቹን ሰብስቦ « የምትነዱትን የመኪና ዓይነትና ብዛት፤ ያላችሁን ቤት፤ የምትውሉበትን፤ የምታድሩበትን ቦታና ጭምር ይኽ ሕዝብ ብታምኑም ፤ ባታምኑም አሳምሮ ያውቃል» ብሏቸው ነበር።  ሕዝብ ምን የማያውቀው አለ? ተከድኖ ይብሰል ብለነው እንጂ የኛዎቹን ስንቱን ጉድ እናውቃለን።
 አሁን እነሱ ምን ስለሆኑ ነው፤ እንደራሴ ይሾም የሚሉት?  እንደራሴ ምን ያድርግላቸው? መፈንቅለ ፓትርያርክ መሆኑ ነው ወይስ እንደራሴው በየሀገረ ስብከታቸው እየሄደ ት/ቤት ሊሰራላቸው ነው? ጉዳዩ ፓትርያርኩን ወደጎን አስቀምጦ ለጳጳሳቱና ለማኅበረ ቅዱሳን ያደረ ሰው ለማስቀመጥ እንደሆነ ሳይታለም የተፈታ ነው። እቅዱም የኃጢአታቸው ዐቃቤ ኃጢአት ከሆነው ከማኅበረ ቅዱሳን ሴራነት የዘለለ አይደለም።  የሚያሳዝነውና የሚያስገርመው ነገር የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር እንደራሴ ለመሾም ይችሉ ዘንድ እንዲያግዛቸው መለመናቸው ነው።
 የፖለቲካ ሰው ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ቅዱስ በሚባለው ጉባዔያችሁ ተቀምጦ ሲነገራችሁ ከመስማት ሞት ይሻላችሁ ነበር። ዳሩ ግን የሞታችሁት ቀድሞ ነውና ይኼ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ውርደት ለእናንተ ግን ክብር ነው። ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር በጠሩት ጉባዔ ላይ አንድ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተወካይ የተናገረውን ጠቅሼ ልቋጭ። «ፖለቲከኛው እጣን፤ እጣን ሲሸት፤ የሃይማኖት አባት ፖለቲካ፤ ፖለቲካ ሲሸት አስቸጋሪ ነው» ማለቱን አስታውሳለሁ።
አዎ፤«ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡት፤ ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡት?» እንዲሉ።




Monday, May 23, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



(Part two) www.chorra.net
ትምህርተ ተዋሕዶ ምን ይላል?[3]
“ክርስቶስ አሁን መካከለኛ አይደለም” የሚለው ኑፋቄ ምንጩ የአውጣኪ ትምህርት መሆኑ ይታወቃል። አውጣኪ በአንዱ በክርስቶስ የቃልና ሥጋ መደባለቅ (ቱስሕት)፣ የሰውነት ወደ አምላክነት መለወጥ (ውላጤ) ወይም መለዋወጥ (ሚጠት) ተከናውኗል ብሎ የተነሣ መናፍቅ ሲሆን፣ እርሱም ትምህርቱም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተወግዘው ከተለዩ ብዙ ምእት ዓመታት ተቈጥረዋል። በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት አንጻር ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ትምህርተ ተዋሕዶን አምልተውና አስፍተው አስተምረዋል።
የተዋሕዶ ትምህርት “አንቀጸ ተዋሕዶ” እንደሚባል ሊቃውንቱ ያስረዳሉ። ተዋሕዶ ሊገኝ የቻለውም አንቀጸ ተከፍሎን መነሻ በማድረግ ነው ሲሉ ያክላሉ። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ የአንቀጸ ተከፍሎ ትምህርት የሚያመለክተው ከተዋሕዶ በፊት የነበረውን የሥግው ቃልን ባሕርያውያን ምንጮችን ነው። ይኸውም ከሁለት ባሕርያተ ልደታት፣ ማለትም ቃል እም ቅድመ ዓለም ከአብ መገኘቱን፣ ትስብእትም ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም አብራክ መገኘቱን (መከፈሉን) ነው። በጥቅሉ የሁለቱም ምንጭና ተረክቦ (መገኘት) የሚታሰበብትን ጊዜ ያሳያል። አንቀጸ ተከፍሎን ፊልክስ ሰማዕት እንደሚከተለው አብራርቷል፤ “ወካዕበ ይቤ ንጠይቅ ክፍላተ ፪ቱ ህላዌያት ወስመ ፪ቱሂ ክፉል በኵሉ ጊዜ በምግባር ወበነገር ዘውእቶሙ መለኮት ወትስብእት። ወሶበ ንቤ ከመዝ ኢይምሰልክሙ ዘንከፍሎ እም ድኅረ ፩ዱ ከዊን ወዳእሙ ናጤይቅ ህላዌ መለኮት ወህላዌ ትስብእት ወዓዲ ነአምር እስመ ቃል አኮ ዘተመይጠ እም ህላዌ መለኮቱ ለከዊነ ትስብእት ሶበ ኀደረ ላዕሌነ። - ዳግመኛ [ቅድመ ተዋሕዶ የነበረ] የሁለቱን ባሕርያት (የመለኮትንና የትስብእትን) ልዩነት፣ የሁለቱም ስም በጊዜው ሁሉ በሥራ በአነጋገር ልዩ እንደ ነበረ እንወቅ፤ እነዚህም መለኮትና ትስብእት ናቸው። እንደዚህም ባልን ጊዜ ከተዋሕዶ በኋላ የምንለየው አይምሰላችሁ፤ የመለኮትን ባሕርይ የትስብእትን ባሕርይ እናስረዳለን እንጂ፤ ዳግመኛም ቃል ባሕርያችንን በተዋሐደ ጊዜ ከመለኮቱ ባሕርይ ሥጋ ወደ መሆን እንዳልተለወጠ እናውቃለን።” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 131)።
“በዚህ መሠረት የአንቀጸ ተዋሕዶ ትምህርት በአንቀጸ ተከፍሎ መሠረት ከጥንት ተለያይተው ከኖሩ ከሁለቱ … የአንዱን የዐማኑኤልን ህላዌ ቅውም አድርጎ የሚያሳይ የምስጢረ ተሠግዎ ወይም የምስጢረ ተዋሕዶ ትምህርት ነው።”[4] ስለዚህ በተከፍሎ የነበሩት ከተወሐዱ በኋላ አንዱን ከሌላው መለየትና እየብቻቸው ማድረግ አይቻልም። ቄርሎስ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ኢትፍልጥ ሊተ እም ድኅረ ትድምርት እስመ ዘፈለጠ እንተ ባሕቲቶ ብእሴ ወእንተ ባሕቲቶ አምላከ ቃለ ክልኤተ ይሬስዮ ለዐማኑኤል። - ከተዋሕዶ በኋላ አትለይብኝ፤ ከተዋሕዶ በኋላ ብቻውን ሰው፥ ብቻውን አምላክ ቃል የሚል ሰው ቢኖር ዐማኑኤልን ሁለት ያደርገዋል።”[5]
የአንጾኪያው ባስልዮስም፣ “አይትከፈል ኀበ ክልኤቱ ህላዌያት እም ድኅረ ተዋሕዶ እስመ ለምንታዌ አእተታ ተዋሕዶ፤ ወተዋሕዶኒ ያግሕሥ ኵነኔሁ ለምንታዌ እስመ ውእቱ ተዋሕዶ አካላዊ ዘኢይትከፈል። - ከተዋሕዶ በኋላ ወደ ሁለት ህላዌያት አይከፈልም፤ ተዋሕዶ መንታነትን አስወግዷልና፤ የመንታነትንም ፍርድ አርቋል። እርሱ የማይከፈል አካላዊ ተዋሕዶ ሆኖአል” ብሏል (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 422)።  
ከእነዚህ ምስክርነቶች ስለ ወልድ ከትስብእትና ከተዋሕዶ በፊት ስለ ነበረው አቋም በአንቀጸ ተከፍሎ ሊነገር እንደሚገባና ከተዋሕዶ ወዲህ ስላለው አቋሙ ደግሞ በአንቀጸ ተዋሕዶ ሊነገር እንደሚገባ እንረዳለን። ምስጢረ ተዋሕዶ የተከናወነው በተለመደውና በሚታወቀው የውሕደት ሕግ ሳይሆን በሕገ ተዐቅቦ ነው። “ተዐቅቦ ማለት በቀላል አገላለጽ መጠበቂያ ማለት ነው። ለምሳሌ መጠበቂያ ያለው ነገር ከተፈለገ፣ ለጊዜው የጠመንጃ ሁኔታ ሊታወስ ይቻላል። ጠመንጃው ጥይት ጐርሶአል እንበል። ነገር ግን በአስፈላጊው ሁኔታና ጊዜ ምላጩ ተስቦ እስኪተኰስበት ድረስ መጠበቂያ ይደረግበታል። መጠበቂያም ስላለው፣ ምላጩን ወይም ቃታውን ሲስቡ፣ ጥይቱ አይተኰስም፤ አይባርቅም። ለዚያውም (ለተኳሹም) ለሌላውም ሰው ጕዳት አያስከትልበትም። መጠበቂያው እንዳይተኰስ ጠብቆታልና። እንግዲህ የመጠበቂያው መኖር በአስፈላጊነቱ መጠን ጠቀመ ማለት ነው።”[6] በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ ሕገ ተዐቅቦ ያስፈለገውም ቃልና ሥጋ እንዲጠባበቁ ለማድረግ ነው። “ተዐቅቦ ተራርቀው ይኖሩ የነበሩትን ባዕል፣ ምሉእና ፍጹም የሆነ አካለ ቃልን እና ድኻ፣ ውሱንና ትሑት የሆነ አዳማዊ ትስብእትን አገናዝቦ የሚገኝ” የምስጢረ ተዋሕዶ መጠበቂያ ነው።
ምስጢረ ተዋሕዶ የተመሠረተው “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ ዐደረ” በሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ላይ ነው (ዮሐ. 1፥14)። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ በጥቅሱ ውስጥ የምናገኛቸው “ኮነ” እና “ኀደረ” (ሆነ እና ዐደረ) የሚሉት ቃላት ተዋሕዶንና ተዐቅቦን በኅብረት ይዘዋቸዋል። አንዱ ለብቻው ተነጥሎ ማለትም “ኮነ” ለብቻው “ኀደረ”ም ለብቻው የተዋሕዶን ምስጢር ለመጠበቅ አያስችሉም። ስለዚህ ኮነ እና ኀደረ በአንድነት ምስጢረ ተዋሕዶን የሚጠብቁ ቍልፍ ቃላት ናቸው ማለት ነው። ቃላቱ ለተዐቅቦ ሕግ የተወሰኑት ሁለቱን ነጣጥለው በመጠቀም የተዋሕዶን ምስጢር ያፋለሱትን የንስጥሮስንና የአውጣኪን የተሳሳተ ትምህርት ለማረም መሆኑን ከሊቃውንቱ ማብራሪያ እንገነዘባለን።
ንስጥሮስ ምስጢረ ተዋሕዶን ለመግለጽ ኮነን ትቶ ኀደረን ነው የወሰደው። ስለዚህ “ ‘በአንዱ ክርስቶስ ሁለት ህላዌያት አሉ’ እስከ ማለት ደረሰና ውስጣዊ መለያየትን (ቡዓዴን) እና መከፋፈልን (ፍልጠትን) በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ አመጣ። ለዚህም የኮነን እውነተኛ ትርጕም ወይም ፍቺ የያዘና ከኀደረ ጋር የሚያገናኝ መጠበቂያ እንዲኖር አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቡዓዴ (ያለመለያየት)፣ ዘእንበለ ፍልጠት (ያለመፈራረቅ/ያለመከፈል)፣ በኢተላፅቆ (ያለመነባበር)’ የሚሉ መጠበቂያዎች፣ የኮነን ምስጢር ይዘው “ኀደረ” ያለውን እንዲጠብቁ ተደረገና የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ። ለዚህ ለንስጥሮስ ንጥል ሐሳብ ተዐቅቦ ባይደረግበት ለተዋሕዶ ትምህርት አደገኛ ይሆናል። የመጻሕፍት አተረጓጐምም ይጥበረበርበታል።”[7]    
ከንስጥሮስ በተቃራኒ አውጣኪም እንዲሁ ምስጢረ ተዋሕዶን የሚያጠፋ ትምህርት አስተማረ። “በአንዱ ክርስቶስ ቱስሕት (መደበላለቅ)፣ ውላጤ (የሰውነት መለወጥ)፣ ሚጠት (መለዋወጥ) እንዳለበት፣ ሰውነቱ ወደ አምላክነቱ እንደ ተለወጠ ተናገረ። አውጣኪ ኀደረን በመተው የኮነን ፍቺ በተሳሳተ አተረጓጐም ተመለከተና ኮነን ‘ተለወጠ’ በሚል ቃል ተርጕሞ ተሳሳተበት። እንደርሱ ዐሳብ ቢሆን የተዋሕዶን ምስጢር ተዋሕዶንም ደመሰሰበት። ለዚህም መጠበቂያ ልጓም አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቱስሕት (ያለመደበላለቅ)፣ ዘእንበለ ውላጤ (ያለመለወጥ)፣ ዘእንበለ ሚጠት ያለመለዋወጥ/ያለመመላለስ)’ የሚሉ ቃላት የኀደረን ምስጢር ይዘው የኮነን ፍቺ ወደ ሌላ እንዳይሄድ፣ ይኸውም በመለወጥ እንዳይተረጐም ይጠብቁ ዘንድ ተደረገ። በዚህም ተዐቅቦ የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ፤ ታወቀ። ይህ ተዐቅቦ ባይኖር የአውጣኪን ግንጥል ዐሳብ ለተከተለ ሰው የተዋሕዶ እምነቱንና በቅዱሳት መጻሕፍት ያለው የአተረጓጐሙን መንገድ ያቃውስበታል።”[8]
በአጠቃላይ ምስጢረ ተዋሕዶን “የምንጠብቀው በእነዚህ ሕጋውያን የውሳኔ ቃላት መጠበቂያዎች /ሕገ ተዐቅቦ/ ነው። ተዋሕዶ ባለበት ሁሉ ተዐቅቦም ዐብሮት ይገኛል።” ስለዚህ በተዐቅቦ በሆነው ተዋሕዶ አንዱ ክርስቶስ ያለመለያየት፣ ያለመፈራረቅ/ ያለመከፈል፣ ያለመነባበር፣ ያለመደበላለቅ፣ ያለመለወጥ፣ ያለመለዋወጥ ወይም ያለመመላለስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑ ከትምህርተ ንስጥሮስና ከትምህርተ አውጣኪ የተለየ የተዋሕዶ ትምህርት ነው።
ምስጢረ ተዐቅቦን በተመለከተ ቄርሎስ፣ “ኢይደልወነ ንፍልጦ ለ፩ዱ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመ ውእቱ ብእሲ በዐቅሙ ወለእመኒ ነአምሮሙ ለ፪ቱ ህላዌያት በዘዘዚኣሆሙ ወነዐቅቦሙ ዘእንበለ ቱስሕት በበይናቲሆሙ ንብል እንከ ፩ዱ ውእቱ ክመ ኢየሱስ ክርስቶስ። - በዐቅሙ እንደ ዕሩቅ ብእሲ አድርገን አንዱን ኢየሱስ ክርስቶስ ልንለየው አይገባንም፤ ሁለቱን ባሕርያት በየገንዘባቸው ብናውቃቸውም ያለመቀላቀል በየራሳቸው ብንጠብቃቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መቸም መች አንድ ነው እንላለን” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 338)።