Showing posts with label ትምህርት. Show all posts
Showing posts with label ትምህርት. Show all posts

Saturday, September 17, 2016

ለምናምንቴ እረኛ ወየውለት!

ሕዝቅኤል 34
"የሰው ልጅ ሆይ፥ ትንቢት ተናገር፥ በእስራኤል እረኞች ላይ ትንቢት ተናገር፥ እረኞችንም እንዲህ በላቸው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ራሳቸውን ለሚያሰማሩ ለእስራኤል እረኞች ወዮላቸው! እረኞች በጎችን ያሰማሩ ዘንድ አይገባቸውምን? ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።እረኛንም በማጣት ተበተኑ፥ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፥ ተበተኑም። በጎቼ በተራሮች ሁሉና በረዘሙ ኮረብቶች ሁሉ ላይ ተቅበዝብዘዋል፥ በጎቼም በምድር ፊት ሁሉ ላይ ተበትነዋል፤ የሚሻም የሚፈልግም አልነበረም። ስለዚህ፥ እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝና እረኛ ስለሌለ እረኞቼም በጎቼን ስላልፈለጉ እረኞችም ራሳቸውን እንጂ በጎቼን ስላላሰማሩ፥ በጎቼ ንጥቂያ ሆነዋልና፥ በጎቼም ለምድር አራዊት ሁሉ መብል ሆነዋልና"



Saturday, August 27, 2016

ሴቶች ሁልጊዜ ልብ በሉ!



ሴቶች ከወንድ ጓደኛ ማንን ትወዱ? ማንንስ ትመርጡ? ከማንስ ጋር ጋብቻን ትፈፅሙ? እስኪ ራሳችሁን ጠይቁ።
በራስ መተማመን ያላት ሴት ለችግሮች ራሷን አሳልፋ አትሰጥም። በሁኔታዎች መለዋወጥ አትሸበርም። ራሷን ላጋጠማት ተግዳሮት ታዘጋጃለች እንጂ በሽንፈት ለቅሶን አታስተናግድም። ታዲያ ይህንን ኃይል ከየት ማግኘት ትችላለች?
               ✔ ✔✔
መልካም ክርስቲያናዊ ቤተሰብ ውስጥ ያደገች ሴት ስነምግባርን፣ እውቀትን፣ ችሎታና በራስ መተማመንን የምታዳብረው በቅርቧ ባለው ከቤተሰቧ ነው። በአስተዳደግና በልጅነት ሕይወት ጉድለት የደረሰባት፣ በብዙ ችግሮችና መከራ ውስጥ ያለፈች ሴት በስነልቦናዋ ላይ በሚደርሰው ጉዳት በራስ መተማመኗን በማጣት ችሎታዋን ለማውጣትና ችግሮችን ለመጋፈጥ ያላትን አቅም አውጥታ ለመጠቀም ሊያዳግታት ይችላል።

 በተለይም በአስገድዶ መደፈር፣ በእናት ወይም በአባት ብቻ ወይም ከሁለቱም አሳዳጊ ውጪ ያደገች፣ የኑሮ ጫናና ድህነት፣ አካባቢያዊና ሀገራዊ ችግሮች ( ጦርነት፣ ረሃብ፣ ስደት) በሴቷ ስነልቦና ላይ የሚያደርሱት ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በቃላትም መግለፅ ከሚቻለው በላይ የስነልቡና ተጠቂ ልትሆን ትችላለች።
 በዚህም የተነሳ ሴቶች ለአካለ መጠን ከደረሱ በኋላ ቤተሰባዊ ሕይወትን ለመመስረት በሚያስችላቸው ሁኔታ ላይ ያሳለፉት ቁስል የሚያደርስባቸው የአእምሮ ፈተናና ትግል እጅግ ውስብስብ ነው።
የመጠራጠር፣ ያለማመን፣ አንዳንዴም በቀላሉ የመታለል ወይም የመሸወድ ክስተት ሲያጋጥማቸው ያታያል። ሴቶች በፈገግታና በሳቅ ሸፍነው በማህበራዊ ኑሮው ቶሎ የመቀላቀል ተፈጥሮአዊ ችሮታ አላቸው እንጂ በኋላቸው የተሸከሙት ህመም በጣም ብዙ ነው። ሲስቁና ሲጫወቱ ዘመናቸውን ሁሉ እድለኞች የነበሩ ሊመስለን ይችላል። እውነቱ ግን እሱ አይደሉም። ሴቶች መከራቸውን እንደወንድ እያመነዠኩ ስለማይኖሩ ከሰው ለመቀላቀል ብዙም አይቸገሩም። ያ ደግሞ ሴትን ልዩ ፍጥረትና የተወደደች ያደርጋታል። ሴት ለወንድ ሚስት ብቻ ሳትሆን የጉድለቱ ሙላት የመሆኗም ምስጢር ሁሉን መከራ መሸከም መቻሏ ነው። 6 ልጆቿን ያለአባት አሳድጋ ለቁምነገር ያበቃች እናት አውቃለሁ።
                ✔✔✔
ክርስቲያን ሴቶች ምንም እንኳን ያለፈ ሕይወታቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ባለ አዲስ የእምነት ልምምድ የተለወጠ ቢሆንም ያሳለፉት ስነልቦና በቀላሉ የሚፋቅ ባለመሆኑ አልፎ አልፎ መቸገራቸው አይቀርም። ከጋብቻ በፊት የመንፈሳዊ ጋብቻ ትምህርትና የምክር አገልግሎት ማግኘት የበለጠ ተጠቃሚ ሊያደርጋቸው ስለሚችል በዚሁ መልኩ አስቀድመው ቢገለገሉ የተሻለ ግንዛቤ ይኖራቸዋል።
በኛ በኩል ያሉንን ምክሮች ጥቂት እንበል።
               ✔✔✔
ባለፈ ስህተትሽ አትቆጪ። የዛሬውን ሃሳብሽን እንዲቆጣጠረውም አትፍቀጂ። ያለፈው ላይመለስ አልፏል። ያለፈው ለዛሬው ያለው እድል አስተማሪ መሆኑ ብቻ ነው። ጎበዝ ሰው በሌላ ሰው ስህተት ይማራል፣ ሰነፍ ሰው ደግሞ ከራሱ ስህተት ይማራል። ያለፈው ስህተትሽ ለዛሬው ማንነትሽ ትምህርት ከሆነሽ፣ አንቺ የዛሬዋ ጎበዝ ነሽ። ካለፈችው ሰነፏ አንቺነትሽ በልጠሻል ማለት ነው። ስህተት አንዴ ከበዛ ደግሞ ሁለቴ ቢሆን ነው። ከደጋገመሽ ግን ስህተቱ ከጎዳሽ ነገር ሳይሆን ካንቺ አለመለወጥ የመጣ ነው።
ፈረንጆች እንዲህ የሚል አባባል አላቸው። "ስትሄድ የመታህ የድንጋይ እንቅፋት ስትመለስም ከደገመህ ስህተቱ የእንቅፋቱ ሳይሆን ድንጋዩ አንተው ነህ" ይላሉ።
ፍርሃትን በራስ መተማመን፣ ስህተትሽን በመታረም ማሸነፍ ትችያለሽ።
አብዛኛው ወንድ ሴትን የሚወደው በአይኑ ነው። የውስጧን ማንነት ሳያይ ውጫዊውን አይቶ ማድነቅም፣ መውደድም ይቻላል። ብቻውን ግን ለፍቅር ግንኙነት አያበቃም።
 የደም አይነት ልዩ ልዩ ነው። ሁሉም ደም ለሁሉም ሰው አይሆንም። በአይን የመጣ መውደድም በሁሉም ሴት ላይ ፍቅርን ሊመሰርት አይችልም። ለምርጫ የሚያበቃ ጥናት ያስፈልገዋል። የወደዱን ሁሉ ያፈቅሩናል ማለት አይደለም። ይህን ለማወቅ ጊዜ ወስዶ ማጥናት ተገቢ ነው። ለኛ የተሰጠ ሰው ከሆነ ለማጥናት በምንወስደው ጊዜ ያመልጠናል ብለን መስጋት አይገባም። እንዲያውም ሳናውቀው ዘው ከምንል ቢያመልጠን ይሻላል። ለኛ የተሰጠን እንዳይዘገይ ቶሎ መሄዱ ይሻላል። የከረመ ወይን ሲጠጡት ሆድ አይነፋም።

በአይን የወደደ የአይኑን አምሮት በአካል ባገኘው ጊዜ ቶሎ ይረካል። ከዚያም የማያርፈው አይኑ ወደሌላ ይሄዳል። ሴት ሆይ፣ የሚወድሽን ወንድ አይኑን ብቻ ሳይሆን ልቡን እዪው። ምን ይልሻል? ስሚው። አንቺን አይቶ ለልቡ አምሮት የሚቅበዘበዝ ከሆነ ችግር አለ። በአፉ እወድሻለሁ እያለ ፍቅሩን በተግባር የማያሳይ ከሆነ ችግር አለ። እንጋባ ሳይሆን እስክንጋባ አልጋ ላይ እንውጣ የሚልሽ ከሆነ ችግር አለ። የሚሰጥሽን ጊዜ ቀስ በቀስ የሚቀንስ ከሆነ ችግር አለ።
ታማኝ ወንዶችን ከአስመሳዮች ለመለየት ጊዜ ውሰጂ። አትቸኩዪ። በምላስ ብልጠት አትሸነፊ። ልቡን ለማወቅ አንቺ አምላክ አይደለሽም። ምላሱን በተግባሩ ፈትኚ። ከትዳር በፊት የተደጋገመ ውሸት በትዳር ውስጥም ይቀጥላልና ተጠንቀቂ።
በሰውኛ ሚዛን መልክና ውበት ጥሩ ነው። ነገር ግን ለእግዚአብሔር መንግስት በተመረጠ ትዳር ውስጥ ሁሉም ከንቱ ነው። ቅን እንጂ ቅንቅን አትሁኚ። ገንዘብ፣ ጌጥና ምቾት አያታልሽ። ዝሙት ኃጢአት ነው። ፍፃሜውም ሞት ነው። ስለዚህ በታማኝነት ለእግዚአብሔር መንግስት ራስሽን አስገዢ።

 ጠቢቡ በመጽሐፉ እንዳለው መክብብ 6፣12
"ሰው በከንቱ ወራቱ ቍጥርና እንደ ጥላ በሚያሳልፈው ዘመኑ በሕይወቱ ሳለ ለሰው የሚሻለውን የሚያውቅ ማነው? ወይስ ለሰው ከፀሐይ በታች ከእርሱ በኋላ የሚሆነውን ማን ይነግረዋል?" ነውና ለጊዜው ለእግዚአብሔር ክብር ለሚሆን ሕይወት እንጂ ይህ ቋሚ መኖሪያችን አይደለምና ራስን መግዛት አትርሺ።
             ✔✔✔
"ጌታ ቅርብ ነው። በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ"
ፊልጵ 4:6

Monday, July 25, 2016

የሚፈውስና የሚያሳምም ስም - ኢየሱስ!!


(ከዙፋን ዮሐንስ)
የሆነ ጊዜ ፷፬ ሰው በሚይዝ አገር አቋራጭ አውቶቡስ ተሣፍረን ወደክልል የሁለት ቀን መንገድ ተጓዝን። ቁርስ፣ ምሳ፣ አብሮ ከመብላት፣ አብሮ ከመቀመጥ፣ የተነሳ ሁሉ ዘመድ ቤተሰብ ሆነ። የሆድ የሆዱን ተጫወተ። ስልክ ተቀያየረ፣ እጮኛም ያገኘ አይጠፋም። ያልተነሳ ርእስ አልነበረም። ፖለቲካ፣ የኑሮ ውድነት፣ ስለሳይንስ፣ ሃይማኖት፣ ስለታዋቂ ደራሲያን፣ ዘፋኝ፣ ፈላስፋ፣ ስለሃይማኖት አባት፣ ብዙ ብዙ….ብቻ ያልተወራ አልነበረም። አንዳንዶቹም ወሲብ ቀስቃሽ ቀልዶችን ግጥሞችን አውርተው መኪናው ውስጥ ከጫፍ እስከጫፍ አነቃቅተዋል። የወሲብ ነገር ሲወራ ጆሮውን ቀስሮ ያዳምጣል። የሚያስቅ ከሆነ ይስቃል፣ የሚያሳፍር ከሆነም መስማት ያልፈለገ ይመስል የኮረኮሩት ያህል ግንባሩ ጥርስ በጥርስ ይሆናል። የአለቃ ገ/ሐና ነገር ሲነሳማ የአለቃን ወሲብ ወዳጅነትና ይጠቀሙ የነበረበትን የማማለል ዘዴ እያደነቀ ከልምዳቸው ብዙ የቀሰመው ነገር ያለ ይመስል ተሳፋሪው ይስቃል፣ ያውካካል።

ይህ ሁሉ ሲሆን አንድ ሰው ከዚህ ሁሉ ሳቅና ፍንደቃ ራሱን አግልሎ ከመስኮት ጥግ ተቀምጦ ያነብ ነበር። ድንገት ብድግ ብሎ “ኢየሱስ“ የሚለውን ስም አንስቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ አዳኝነቱን፣ ተስፋነቱን፣ አጽናኝነቱን መናገር ሲጀምር ብዙ ፊቶች ተቀያየሩ። አንዳንድ ፊቶች ቲማቲም መስለው ቀሉ። የባሰባቸው አንዳንዶች ደግሞ እንደበርበሬ ቀልተው የቁጣ ብናኛቸው በሰውየው ላይ በተኑ። ስለዝሙት ቀልድ ቦታ ሳይመርጡ ሲያውካኩ የነበረውን ረስተው ስለኢየሱስ ለመስማት ቦታ አጡና “ሰብከት ቦታ አለው“ አሉና ደነፉ። ጫወታችንን አታበላሽ አሉና አጉረመረሙ። ስለፌዝ፣ እርባና ስለሌለው ቀልድና ስለዝሙት ማውራት እንደጥሩ ጫወታ ተቆጥሮ ስለኢየሱስ መስማት ግን ጫወታን እንደማበላሸት ሆኖ ተቆጠረ።
እርግጥ ነው። የሥጋን ነገር መከተል ከእግዚአብሔር የመለየት ጉዳይ ስለሆነ ማበሳጨቱ የሚጠበቅ ነበር።

ሮሜ 8፣7
 “ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሔር ሕግ አይገዛምና፥ መገዛትም ተስኖታል” እንዳለው ሐዋርያው።

በየትኛውም መመዘኛ “ኢየሱስ” የሚለው ሃይለኛ ስም ሲጠራ ለመቀበል ወይም ላለመቀበል የሰዎች አስተሳሰብ ከሁለት ነገር ውጭ አይሆንም።
አንድም የኢየሱስን ጌትነትና አዳኝነት የሕይወቷ ቤዛ ላደረገችው ነፍስ ሃሴትን ያመጣልና በስሙ መጠራት ይኽች ነፍስ አታፍርም፣ አትቆጣም።
 ሁለትም የኢየሱስ አዳኝነት፣ ጌትነትና አምላክነት ብቸኛ ቤዛዋ ያላደረገችውን ነፍስ ያበሰጫታል፣ ያናድዳታል።

ምክንያቱም ፪ቆሮ ፪፣፲፮ “ለእነዚህ ለሞት የሚሆን የሞት ሽታ፣ ለእነዚያም ለሕይወት የሚሆን የሕይወት ሽታ ነን“ እንደሚል ይኽ ስም ለዘላለማዊ ሕይወት ለተመረጡት የፕሮቴስታንት ይሁኑ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ አማኞች ሕይወት፣ ሕይወት የሚሸት ሰላምና እረፍት የሚያመጣ ሲሆን ለጥፋት ለተመረጡት ግን የሚያስቆጣ፣ የሚያነጫንጭ ጥርስ የሚያፋጭ ይሆናል። ዘፈንና ቀልዱ፣ ቧልትና ፌዙ ሲነገር ሁሉ ያለምንም ልዩነት አንድ ሆነው ሲስቁና ሲፈነድቁ እንዳልነበር “ኢየሱስ” የሚለው ስም ሲጠራ የሚያበሳጭበት ምክንያት ለምንድነው? እነዚህ ጴንጤዎች ቦታ የላቸውም እንዴ ማሰኘቱስ ለምን ይሆን? የራሱ የሆነውን ኢየሱስ ያዘጋጀ ሃይማኖት የለም።

ቢያንስ አዳምጦ ከወንጌል ቃል ውጪ የሆነውንና ያልሆነውን መለየት ሲቻል መቃወም ተገቢ አይደለም። ደደግሞም ፌዝና ሥጋዊ ነገርን ከማውራት ስለኢየሱስ መስማት በብዙ መልኩ ይሻላል። ለሁሉ ስለሞተው ስለኢየሱስ መናገር የተወሰኑ ሰዎች ስጦታ ሆኖ ሲያስወቅስ፣ ስለዝሙት መናገር ግን ለሁሉ የተፈቀደ መልካም ተግባር ሆኖ የሚቆጠርበት ምክንያት መኖር አልነበረበትም። ነገር ግን ይኽ ስም ሲጠራ ያስፈራቸውና ሐዋርያቱን፣ “ጀመሩ ደግሞ እነዚህ የተረገሙ!” ያስብል እንደነበር ወንጌል ያስታውሰናል።

1. ስሙን ሲጠራ ለተቀበሉ የሕይወት ሽታ የሆነላቸው። ሐዋ ፰
 ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ፊልጶስ ስለኢየሱስ ሲሰብክለት ልቡ ደስ ተሰኘ። አጥምቀኝ አለው እንጂ “የእናትና አባት ሃይማኖቴን ተከትዬ ከኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ድረስ ያስመጣኝና ተራራ የወጣሁበትን ታላቅ የበረከት ጉዞ አድርጌ ከመመለስ ባለፈ ያንተን ኢየሱስ ለመስማት አልመጣሁም“…ብሎ አልተቆጣም።
በሉቃ ፳፯-፳ ላይም የኤማሁስ መንገደኞች ስለኢየሱስ በመጽሐፍ የተጻፈውን ሲሰሙ ልባቸው ይቃጠልባቸው ነበር። በዚያ በነበርንበት አውቶቡስ ላይ ግን ለብዙዎች ልባቸው የተቃጠለው ለምን ይኄንን ስም ትጠራላችሁ? ብለው በመናደድ ነበር።
ሐዋ ፲-፳፬ ላይ መቶአለቃ ቆርኔሌዎስም ጭራሽ ዘመዶቹንና ወዳጆቹን ጠርቶ ስለኢየሱስ ስበኩኝ ብሎአል። ስለኢየሱስ መስማት ደስ የሚያሰኝ ሆኖ ሳለ ጆሮ የሚያሳክክበት ምክንያት አይኖርም። ቢያንስ ስለአለቃ ገ/ሐና የዝሙት ጥበብና ሴቶችን እንዴት እንደሚያጠምዱ ከመስማት ይልቅ አምነው ባይቀበሉት እንኳን ስለኢየሱስ የሚነገረውን የወንጌል ቃል ማዳመጥ ለዝሙት ልብን ከማነሳሳት ከንቱ ወሬ ሳይሻል አይቀርም።
  በበዓለ ሃምሳ የተሰበሰቡት አይሁድ ስለኢየሱስ ሲወራ ልባቸው ተነክቶ ሐዋርያትን “ምን እናድርግ ?? “ብለው እርዳታ ጠየቁ እንጂ “በየመንገዱ በየአደባባዩ በየባሱ እየሰበካችሁ፣ አታስቸገሩ “ብለው በተቆርቋሪነት ሰበብ የአጋንንትን ቁጣ አልተቆጡም። እነዚህ ስሙን የሰሙና ያልተቃወሙ ሁሉ መጨረሻቸው ያመረ ክርስቲያኖች ሆነው በሰማይ የዘላለም ሕይወትን በምድርም በረከትን አግኝተው ወደጌታ ሄደዋል።

2. የሞት ሽታ የሆነባቸውና ስሙ ሲጠራ የሚያበሳጫቸው የሚያስቆጣቸው ሰዎች እንዲህ የሚሆኑት እነሱ ሳይሆኑ በውስጣቸው የተቀመጠው ክፉ የክርስቶስ ተቃዋሚ መንፈስ ነው። ይኽ ስም ሰዎችን ከሥጋዊና መንፈሳዊ ደዌ ስለሚፈታ ሰይጣን ይጠላዋል። መድኃኒትን ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ሰውነት መድኃኒት ለሞት እንደሚሆንበት ሁሉ ኢየሱስ የሚለውም ስም ለሞት ይኾንባቸዋል። ሐዋርያው ጳውሎስ ከመለወጡ በፊት የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብን አምላክ እንደሚያመልክ ስለሚያምን “ኢየሱስ” የሚባለው ስም ያበሳጨው ነበር። ይኽንን ስም የሚጠሩትን ያስርና ያስገድል ነበር። ሐዋ ፬:፲፰ “በኢየሱስ ስም ፈጽመው እንዳይናገሩና እንዳያስተምሩ አዘዙአቸው” “ በማለት ፈሪሳዊያን ስሙ የሞት ሽታ እንደሆነባቸው ያሳያል። “ገረፉአቸው፥ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው።“ በማለት ስሙ እንዳስገረፈ አንብበናል።

ወንድሞቼና እህቶቼ ዛሬም ይህንን ስም መጥራት ያስደነግጣል/ያስፈራል/ኤሌክትሪክ ያስጨብጣል። በስካር መንፈስ ናውዞ ውሃ መውረጃ ቱቦ ስር የሚያድረው ብረቱ፣ አንበሳው ሲባል ዘማዊውና አለሌው ቀምጫዩ እየተባለ ሲሞካሽ፣ ሌባው ቢዝነሳሙ፣ እሳቱ ሲሉት የኢየሱስ ስብከት ሲነሳ ግን ሃይማኖተኛ ሆኖ ሲያፈጥ ማየት በጣም ያሳዝናል። ጫትና ሲጋራ፣ ሀሺሽና ሺሻ የሚያናውዘው ሱሰኛው ሰው ለጥምቀትና ትንሣኤ በአጭር ታጥቆ መንገድ ከሚጠርግ፣ ቄጠማ ከሚጎዘጉዝ፣ ምንጣፍ ከሚያነጥፍ ውስጡ ተጎዝጎዞ ከተቀመጠው ክፉ መንፈስ ኢየሱስን ንጉሡ አድርጎ ቢያኖር ኖሮ ከዐመጻ ተግባራቱ ነጻ በወጣ ነበር። የሕይወቴ መሪ ነው ያለ ሰው ንሰሃ ገብቶ ኢየሱስ ሰው አደረገኝ ይላል እንጂ “ኢየሱስ” ብሎ የሚሰብክን ሰው “መግደል ነበር“ አይልም። እህቴና ወንድሜ ዛሬ ኢየሱስ አንተና አንች ጋር የሞት ሽታ ወይስ የሕይወት ሽታ ነው? ሁላችን ራሳችንን እንመርምር።
 ክብርና ምስጋና ነፍስ ሥጋና መንፈስን ነጻ ለሚያወጣው ሰው ለሚያደርገው ትልቅ ስም፣ ለኢየሱስ ክብር ይሁን! አሜን

Monday, May 23, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



(Part two) www.chorra.net
ትምህርተ ተዋሕዶ ምን ይላል?[3]
“ክርስቶስ አሁን መካከለኛ አይደለም” የሚለው ኑፋቄ ምንጩ የአውጣኪ ትምህርት መሆኑ ይታወቃል። አውጣኪ በአንዱ በክርስቶስ የቃልና ሥጋ መደባለቅ (ቱስሕት)፣ የሰውነት ወደ አምላክነት መለወጥ (ውላጤ) ወይም መለዋወጥ (ሚጠት) ተከናውኗል ብሎ የተነሣ መናፍቅ ሲሆን፣ እርሱም ትምህርቱም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተወግዘው ከተለዩ ብዙ ምእት ዓመታት ተቈጥረዋል። በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት አንጻር ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ትምህርተ ተዋሕዶን አምልተውና አስፍተው አስተምረዋል።
የተዋሕዶ ትምህርት “አንቀጸ ተዋሕዶ” እንደሚባል ሊቃውንቱ ያስረዳሉ። ተዋሕዶ ሊገኝ የቻለውም አንቀጸ ተከፍሎን መነሻ በማድረግ ነው ሲሉ ያክላሉ። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ የአንቀጸ ተከፍሎ ትምህርት የሚያመለክተው ከተዋሕዶ በፊት የነበረውን የሥግው ቃልን ባሕርያውያን ምንጮችን ነው። ይኸውም ከሁለት ባሕርያተ ልደታት፣ ማለትም ቃል እም ቅድመ ዓለም ከአብ መገኘቱን፣ ትስብእትም ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም አብራክ መገኘቱን (መከፈሉን) ነው። በጥቅሉ የሁለቱም ምንጭና ተረክቦ (መገኘት) የሚታሰበብትን ጊዜ ያሳያል። አንቀጸ ተከፍሎን ፊልክስ ሰማዕት እንደሚከተለው አብራርቷል፤ “ወካዕበ ይቤ ንጠይቅ ክፍላተ ፪ቱ ህላዌያት ወስመ ፪ቱሂ ክፉል በኵሉ ጊዜ በምግባር ወበነገር ዘውእቶሙ መለኮት ወትስብእት። ወሶበ ንቤ ከመዝ ኢይምሰልክሙ ዘንከፍሎ እም ድኅረ ፩ዱ ከዊን ወዳእሙ ናጤይቅ ህላዌ መለኮት ወህላዌ ትስብእት ወዓዲ ነአምር እስመ ቃል አኮ ዘተመይጠ እም ህላዌ መለኮቱ ለከዊነ ትስብእት ሶበ ኀደረ ላዕሌነ። - ዳግመኛ [ቅድመ ተዋሕዶ የነበረ] የሁለቱን ባሕርያት (የመለኮትንና የትስብእትን) ልዩነት፣ የሁለቱም ስም በጊዜው ሁሉ በሥራ በአነጋገር ልዩ እንደ ነበረ እንወቅ፤ እነዚህም መለኮትና ትስብእት ናቸው። እንደዚህም ባልን ጊዜ ከተዋሕዶ በኋላ የምንለየው አይምሰላችሁ፤ የመለኮትን ባሕርይ የትስብእትን ባሕርይ እናስረዳለን እንጂ፤ ዳግመኛም ቃል ባሕርያችንን በተዋሐደ ጊዜ ከመለኮቱ ባሕርይ ሥጋ ወደ መሆን እንዳልተለወጠ እናውቃለን።” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 131)።
“በዚህ መሠረት የአንቀጸ ተዋሕዶ ትምህርት በአንቀጸ ተከፍሎ መሠረት ከጥንት ተለያይተው ከኖሩ ከሁለቱ … የአንዱን የዐማኑኤልን ህላዌ ቅውም አድርጎ የሚያሳይ የምስጢረ ተሠግዎ ወይም የምስጢረ ተዋሕዶ ትምህርት ነው።”[4] ስለዚህ በተከፍሎ የነበሩት ከተወሐዱ በኋላ አንዱን ከሌላው መለየትና እየብቻቸው ማድረግ አይቻልም። ቄርሎስ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ኢትፍልጥ ሊተ እም ድኅረ ትድምርት እስመ ዘፈለጠ እንተ ባሕቲቶ ብእሴ ወእንተ ባሕቲቶ አምላከ ቃለ ክልኤተ ይሬስዮ ለዐማኑኤል። - ከተዋሕዶ በኋላ አትለይብኝ፤ ከተዋሕዶ በኋላ ብቻውን ሰው፥ ብቻውን አምላክ ቃል የሚል ሰው ቢኖር ዐማኑኤልን ሁለት ያደርገዋል።”[5]
የአንጾኪያው ባስልዮስም፣ “አይትከፈል ኀበ ክልኤቱ ህላዌያት እም ድኅረ ተዋሕዶ እስመ ለምንታዌ አእተታ ተዋሕዶ፤ ወተዋሕዶኒ ያግሕሥ ኵነኔሁ ለምንታዌ እስመ ውእቱ ተዋሕዶ አካላዊ ዘኢይትከፈል። - ከተዋሕዶ በኋላ ወደ ሁለት ህላዌያት አይከፈልም፤ ተዋሕዶ መንታነትን አስወግዷልና፤ የመንታነትንም ፍርድ አርቋል። እርሱ የማይከፈል አካላዊ ተዋሕዶ ሆኖአል” ብሏል (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 422)።  
ከእነዚህ ምስክርነቶች ስለ ወልድ ከትስብእትና ከተዋሕዶ በፊት ስለ ነበረው አቋም በአንቀጸ ተከፍሎ ሊነገር እንደሚገባና ከተዋሕዶ ወዲህ ስላለው አቋሙ ደግሞ በአንቀጸ ተዋሕዶ ሊነገር እንደሚገባ እንረዳለን። ምስጢረ ተዋሕዶ የተከናወነው በተለመደውና በሚታወቀው የውሕደት ሕግ ሳይሆን በሕገ ተዐቅቦ ነው። “ተዐቅቦ ማለት በቀላል አገላለጽ መጠበቂያ ማለት ነው። ለምሳሌ መጠበቂያ ያለው ነገር ከተፈለገ፣ ለጊዜው የጠመንጃ ሁኔታ ሊታወስ ይቻላል። ጠመንጃው ጥይት ጐርሶአል እንበል። ነገር ግን በአስፈላጊው ሁኔታና ጊዜ ምላጩ ተስቦ እስኪተኰስበት ድረስ መጠበቂያ ይደረግበታል። መጠበቂያም ስላለው፣ ምላጩን ወይም ቃታውን ሲስቡ፣ ጥይቱ አይተኰስም፤ አይባርቅም። ለዚያውም (ለተኳሹም) ለሌላውም ሰው ጕዳት አያስከትልበትም። መጠበቂያው እንዳይተኰስ ጠብቆታልና። እንግዲህ የመጠበቂያው መኖር በአስፈላጊነቱ መጠን ጠቀመ ማለት ነው።”[6] በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ ሕገ ተዐቅቦ ያስፈለገውም ቃልና ሥጋ እንዲጠባበቁ ለማድረግ ነው። “ተዐቅቦ ተራርቀው ይኖሩ የነበሩትን ባዕል፣ ምሉእና ፍጹም የሆነ አካለ ቃልን እና ድኻ፣ ውሱንና ትሑት የሆነ አዳማዊ ትስብእትን አገናዝቦ የሚገኝ” የምስጢረ ተዋሕዶ መጠበቂያ ነው።
ምስጢረ ተዋሕዶ የተመሠረተው “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ ዐደረ” በሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ላይ ነው (ዮሐ. 1፥14)። እንደ ሊቃውንቱ ማብራሪያ በጥቅሱ ውስጥ የምናገኛቸው “ኮነ” እና “ኀደረ” (ሆነ እና ዐደረ) የሚሉት ቃላት ተዋሕዶንና ተዐቅቦን በኅብረት ይዘዋቸዋል። አንዱ ለብቻው ተነጥሎ ማለትም “ኮነ” ለብቻው “ኀደረ”ም ለብቻው የተዋሕዶን ምስጢር ለመጠበቅ አያስችሉም። ስለዚህ ኮነ እና ኀደረ በአንድነት ምስጢረ ተዋሕዶን የሚጠብቁ ቍልፍ ቃላት ናቸው ማለት ነው። ቃላቱ ለተዐቅቦ ሕግ የተወሰኑት ሁለቱን ነጣጥለው በመጠቀም የተዋሕዶን ምስጢር ያፋለሱትን የንስጥሮስንና የአውጣኪን የተሳሳተ ትምህርት ለማረም መሆኑን ከሊቃውንቱ ማብራሪያ እንገነዘባለን።
ንስጥሮስ ምስጢረ ተዋሕዶን ለመግለጽ ኮነን ትቶ ኀደረን ነው የወሰደው። ስለዚህ “ ‘በአንዱ ክርስቶስ ሁለት ህላዌያት አሉ’ እስከ ማለት ደረሰና ውስጣዊ መለያየትን (ቡዓዴን) እና መከፋፈልን (ፍልጠትን) በምስጢረ ተዋሕዶ ላይ አመጣ። ለዚህም የኮነን እውነተኛ ትርጕም ወይም ፍቺ የያዘና ከኀደረ ጋር የሚያገናኝ መጠበቂያ እንዲኖር አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቡዓዴ (ያለመለያየት)፣ ዘእንበለ ፍልጠት (ያለመፈራረቅ/ያለመከፈል)፣ በኢተላፅቆ (ያለመነባበር)’ የሚሉ መጠበቂያዎች፣ የኮነን ምስጢር ይዘው “ኀደረ” ያለውን እንዲጠብቁ ተደረገና የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ። ለዚህ ለንስጥሮስ ንጥል ሐሳብ ተዐቅቦ ባይደረግበት ለተዋሕዶ ትምህርት አደገኛ ይሆናል። የመጻሕፍት አተረጓጐምም ይጥበረበርበታል።”[7]    
ከንስጥሮስ በተቃራኒ አውጣኪም እንዲሁ ምስጢረ ተዋሕዶን የሚያጠፋ ትምህርት አስተማረ። “በአንዱ ክርስቶስ ቱስሕት (መደበላለቅ)፣ ውላጤ (የሰውነት መለወጥ)፣ ሚጠት (መለዋወጥ) እንዳለበት፣ ሰውነቱ ወደ አምላክነቱ እንደ ተለወጠ ተናገረ። አውጣኪ ኀደረን በመተው የኮነን ፍቺ በተሳሳተ አተረጓጐም ተመለከተና ኮነን ‘ተለወጠ’ በሚል ቃል ተርጕሞ ተሳሳተበት። እንደርሱ ዐሳብ ቢሆን የተዋሕዶን ምስጢር ተዋሕዶንም ደመሰሰበት። ለዚህም መጠበቂያ ልጓም አስፈለገ። እነሆም ‘ዘእንበለ ቱስሕት (ያለመደበላለቅ)፣ ዘእንበለ ውላጤ (ያለመለወጥ)፣ ዘእንበለ ሚጠት ያለመለዋወጥ/ያለመመላለስ)’ የሚሉ ቃላት የኀደረን ምስጢር ይዘው የኮነን ፍቺ ወደ ሌላ እንዳይሄድ፣ ይኸውም በመለወጥ እንዳይተረጐም ይጠብቁ ዘንድ ተደረገ። በዚህም ተዐቅቦ የሥግው ቃል ተዋሕዶ ተጠነቀቀ፤ ታወቀ። ይህ ተዐቅቦ ባይኖር የአውጣኪን ግንጥል ዐሳብ ለተከተለ ሰው የተዋሕዶ እምነቱንና በቅዱሳት መጻሕፍት ያለው የአተረጓጐሙን መንገድ ያቃውስበታል።”[8]
በአጠቃላይ ምስጢረ ተዋሕዶን “የምንጠብቀው በእነዚህ ሕጋውያን የውሳኔ ቃላት መጠበቂያዎች /ሕገ ተዐቅቦ/ ነው። ተዋሕዶ ባለበት ሁሉ ተዐቅቦም ዐብሮት ይገኛል።” ስለዚህ በተዐቅቦ በሆነው ተዋሕዶ አንዱ ክርስቶስ ያለመለያየት፣ ያለመፈራረቅ/ ያለመከፈል፣ ያለመነባበር፣ ያለመደበላለቅ፣ ያለመለወጥ፣ ያለመለዋወጥ ወይም ያለመመላለስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑ ከትምህርተ ንስጥሮስና ከትምህርተ አውጣኪ የተለየ የተዋሕዶ ትምህርት ነው።
ምስጢረ ተዐቅቦን በተመለከተ ቄርሎስ፣ “ኢይደልወነ ንፍልጦ ለ፩ዱ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመ ውእቱ ብእሲ በዐቅሙ ወለእመኒ ነአምሮሙ ለ፪ቱ ህላዌያት በዘዘዚኣሆሙ ወነዐቅቦሙ ዘእንበለ ቱስሕት በበይናቲሆሙ ንብል እንከ ፩ዱ ውእቱ ክመ ኢየሱስ ክርስቶስ። - በዐቅሙ እንደ ዕሩቅ ብእሲ አድርገን አንዱን ኢየሱስ ክርስቶስ ልንለየው አይገባንም፤ ሁለቱን ባሕርያት በየገንዘባቸው ብናውቃቸውም ያለመቀላቀል በየራሳቸው ብንጠብቃቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መቸም መች አንድ ነው እንላለን” (ሃይማኖተ አበው 1986፣ ገጽ 338)።

Tuesday, May 17, 2016

"ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ"



Part One (www.chorra.net)

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ላይ በዚህ ዐምድ በተከታታይ የወጡትን ጽሑፎች አስመልክተው፣ የተለያዩ አንባብያን የስልክ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ለዝግጅት ክፍሉ አቅርበዋል። ከአንባብያኑ መካከል አንዳንዶቹ የክርስቶስን መካከለኛነት ላለመቀበልና ለሌሎች ቅዱሳን ለመስጠት አለን ያሉትን ማስረጃ በማቅረብ ጭምር ለመከራከር ሞክረዋል። ለክርክራቸው እንዲረዳቸውም፣ “ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም” (2ቆሮ. 5፥16) የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል የጠቀሱ ሲሆን፣ በመጨረሻም፣ “አሁን እርሱ መካከለኛ መሆኑ ቀርቷል፤ አሁን አምላክ ነው” ሲሉ ደምድመዋል። ክርስቶስን ከመካከለኛነቱ ስፍራ አንሥተውም፣ “አሁን መካከለኛው ሥጋ ወደሙ ነው” ሲሉም አክለዋል። ስለ ሥጋ ወደሙ የተባለውን ለቀጣዩ ዕትም እናቈየውና በጥቅሱ ላይ የተላለፈውንና ክርስቶስ አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም የሚለውን አውጣኪያዊ ትምህርት በመመርመር የክርስቶስን መካከለኛነት መጽሐፍ ቅዱስንና የአበውን ምስክርነት በመጥቀስ ወደ ማሳየት እንለፍ።
‘ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ብቻ ነበረ እንጂ አሁን ወደ ክብሩ ከገባ በኋላ መካከለኛ አይደለም’ የሚሉት በትምህርተ ሥጋዌ ላይ በቂ ዕውቀት የሌላቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ተምረዋል የሚባሉትም ጭምር እንደ ሆኑ ይታወቃል። በተለይም የተማሩት ክፍሎች እንዳልተማሩቱ አፋቸውን ሞልተው አሁን አምላክ ብቻ ነው እንጂ ሰውም አይደለም አይሉም፤ ክርስቶስ ዛሬም ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን እናምናለን ይላሉ። ክርስቶስ አሁን በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ ግብረ አምላክን (የአምላክን ሥራ) እንጂ ግብረ ትስብእትን (የሰውነትን ሥራ) አይፈጽምም ስለሚሉ ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእትን ያስተባብላሉ። ለምሳሌ፣ “… ነቢረ የማን (በአብ ቀኝ መቀመጥ) ክርስቶስ ግብረ ትስብእት ከፈጸመ በኋላ እንደ ገና የሰውነትን ሥራ የማይሠራ፥ ነገር ግን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በክብር መለኮታዊ ሥራውን እየሠራ የሚኖር መሆኑን የሚያስረዳ ቃል ነው”[1] ያሉ ይገኛሉ። አባባሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በአብ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ሥራውን ለትስብእት ትቶ ትስብእት ብቻ ይሠራ ነበር፤ ትስብእት ደግሞ አሁን በተራው የሥራ ጊዜውን ስለ ፈጸመ ሥራውን ለመለኮት ተወ ያሰኛል። እንዲህ ከሆነም ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ግብረ ትስብእትን ብቻ እንጂ ግብረ መለኮትን አይፈጽምም ነበር የሚል አንድምታ ያለው ይመስላል። ቅዱሳት መጻሕፍትና በእነርሱ ላይ የተመሠረቱ የአበው ምስክርነቶች ግን የሚነግሩን ከዚህ የተለየ እውነት ነው።

“አንሶሰወ ከመ ሰብእ እንዘ ይገብር ከመ እግዚአብሔር። ርኅበ በፈቃዱ ከመ እጓለ እመ ሕያው ወአጽገቦሙ ለርኁባን ብዙኃን አሕዛብ እም ኅዳጥ ኅብስት ከመ ከሃሊ። ጸምአ ከመ ዘይመውት ወረሰዮ ለማይ ወይነ ከመ ማሕየዌ ኵሉ። ኖመ ከመ ውሉድ ዘሥጋ ነቅሐ ወገሠጾሙ ለነፋሳት ከመ ፈጣሪ። ደክመ ወአዕረፈ ከመ ትሑት ወሖረ ዲበ ማይ ከመ ልዑል። ወኰርዕዎ ርእሶ ከመ ገብር ወአግዐዘነ እም አርዑተ ኀጢአት ከመ እግዚአ ኵሉ።”
ትርጓሜ፥ “እንደ እግዚአብሔር እየሠራ እንደ ሰው ተመላለሰ። ሰው እንደ መሆኑ በፈቃዱ ተራበ፤ ከሃሊ እንደ መሆኑ የተራቡ ብዙ አሕዛብን ከጥቂት እንጀራ አጠገባቸው። የሚሞት እንደ መሆኑ ተጠማ፤ ሁሉን የሚያድን እንደ መሆኑ ውሃውን ወይን አደረገው። እንደ ሥጋ ልጆች ተኛ፤ ፈጣሪ እንደ መሆኑ ነቅቶ ነፋሳትን ገሠጻቸው። ትሑት እንደ መሆኑ ደክሞ ዐረፈ፤ ልዑል እንደ መሆኑ በባሕር ላይ ሄደ። እንደ ተገዢ ራሱን መቱት፤ የሁሉ ጌታ እንደ መሆኑ ከኀጢአት ቀንበር ነጻ አደረገን።”[2]
በዚህ ቃለ ቅዳሴ ውስጥ አንዱ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ይመላለስ በነበረ ጊዜ በሰውነቱ የተከናወነውንና ያከናወነውን ግብረ ትስብእትን፣ በአምላክነቱም የሠራውን ሥራ (ግብረ መለኮትን) በንጽጽር እንመለከታለን።
· መራብ የሰውነት ግብር ነው (ማቴ. 4፥2፤ 21፥18)፤ - በጥቂት እንጀራ ብዙዎችን ማጥገብና ዐሥራ ሁለት መሶብ ተረፍ ማስነሣት ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ዮሐ. 6፥10-13)።
· መጠማት የሰውነት ግብር ነው (ዮሐ. 4፥7፤ 19፥28)፤ - ውሃውን ወደ ወይን መለወጥ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ዮሐ. 2፥7-11)።
· ማንቀላፋት የሰውነት ግብር ነው (ማቴ. 8፥24፤ ሉቃ. 8፥23)፤ - ነፋሱንና ባሕሩን መገሠጽና ጸጥ ማድረግ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ማቴ. 8፥26-27፤ ሉቃ. 8፥24-25)።
· መድከምና ማረፍ ግብረ ትስብእት ነው (ዮሐ. 4፥6)፤ - በባሕር ላይ መሄድ ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (ማቴ. 14፥25-26)።
· ተኰርዖተ ርእስ (ራስን በዘንግ መመታት) ግብረ ትስብእት ነው (ማቴ. 27፥29-30)። - ሰውን ከኀጢአት ማዳን ደግሞ ግብረ መለኮት ነው (1ጢሞ. 1፥15፤ ዕብ. 2፥14-15)።
ክርስቶስ አሁን ያለው በክብር እንጂ በዚህ ምድር በነበረበት ሁኔታ አይደለምና በዚህ ምድር በሰውነቱ የተቀበለው ግብረ ትስብእት ማለትም፦ መራብ፣ መጠማት፣ መድከም፣ ማረፍ፣ ማንቀላፋት፣ ወዘተ. አሁን የለበትም። ይሁን እንጂ ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ አንድ ጊዜ በፈጸመውና ለዘላለም በሚያገለግለው የአድኅኖት ሥራው አሁን በክብር ባለበት ሁኔታ፣ በእርሱ በኩል አምነው ለሚመጡትና ከመጡም በኋላ ጠላት የሆነው ሰይጣንና ኀጢአት ለሚከሷቸው ሁሉ ዋስትናቸውና መታረቂያቸው ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለ መሆኑን መካድ አይቻልም። የሚከተሉት መጽሐፍ ቅዱሳውያን ጥቅሶች ይህን ያስረዳሉ፤
· “እግዚአብሔር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነው፥ የሚኰንንስ ማን ነው? የሞተው፥ ይልቁንም ከሙታን የተነሣው፥ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለው፥ ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” (ሮሜ 8፥33-34)።
· “ልጆቼ ሆይ፥ ኀጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኀጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። እርሱም የኀጢአታችን ማስተስረያ ነው፥ ለኀጢአታችንም ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኀጢአት እንጂ” (1ዮሐ. 2፥1-2)።
በክብር የሆነውና ክርስቶስ በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ የሚያከናውነው ግብረ ትስብእት ከሊቀ ካህናትነቱ ጋር የሚያያዝ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያት ያለፈ በድካማችንም ሊራራልን የሚችል ታላቅ ሊቀ ካህናት ነው (ዕብ. 4፥14-15)። “ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኀጢአት መባንና መሥዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ ጌታ ሊቀ ካህናት የሆነው በሰውነቱ ነው (ዕብ. 5፥1)። ስለዚህም በሰማያዊቱ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ የሚከናወነው የሊቀ ካህናትነቱ ተልእኮ ግብረ ትስብእት ነው። እርሱ “በሥጋው ወራት (በዚህ ምድር ሳለ) ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ … ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆነላቸው” (ዕብ. 5፥7፡9-10)። በዚህ ጥቅስ ውስጥ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በነበረበት ጊዜ ጸሎትንና ምልጃን እንዳቀረበና እንደ ተሰማለትም ተገልጿል። ከዚያ በኋላ ባለው ጊዜ ደግሞ በሊቀ ካህናትነቱ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ አለ።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአድኅኖት ሥራውን ፈጽሞ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጧል (ማር. 16፥19፤ ሐ.ሥ. 2፥33፤ 7፥55-56፤ ሮሜ 8፥34፤ ቈላ. 3፥1፤ ዕብ. 10፥12፤ 1ጴጥ. 3፥22)። በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠውም በዚህ ምድር ሳለ ይፈጽም የነበረውን ግብረ ትስብእትን የማይፈጽም ሆኖ፣ ነገር ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእት እየፈጸመ ነው። የዕብራውያኑ ጸሓፊ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፤ “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛዪቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት” (ዕብ. 8፥1-2)። ልብ እንበል! በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠው ሊቀ ካህናት፣ በዚያው ሁኔታ በሰማይ ያለችውና በእግዚአብሔር የተተከለችው የእውነተኛዪቱ ድንኳን አገልጋይ ነው። ወደዚያች የገባውም፣ ስለ እኛ ቀዳሚ ሆኖ በእግዚአብሔር ፊት አሁን ይታይልን ዘንድ ነው (ዕብ. 6፥20፤ 9፥24፡28)። ይህም በክብሩ ሆኖ ግብረ ትስብእትን እንደሚፈጽም ያመለክታል።
ከዚህ ቀደም በተከታታይ ለማስገንዘብ እንደ ሞከርነው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ እንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃ (ዮሐ. 17፥9፡20-21) እና አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት (ዕብ. 10፥12፡14) ለዘላለም መካከለኛችን ነው። ይህም ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም በሰማይ ምልጃና መሥዋዕት ያቀርባል ማለት ሳይሆን፣ አንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃና መሥዋዕት ዛሬም አስታራቂያችንና መታረቂያችን እርሱው ብቻ ነው ማለት ነው። ዛሬ አንድ ኀጢአተኛ ሰው የወንጌልን ቃል ሰምቶ፣ በክርስቶስ አዳኝነት ቢያምንና በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ቢጸልይ ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቀውና የኀጢአቱን ስርየት የሚቀበለው፣ ክርስቶስ አንድ ጊዜ ባቀረበው ምልጃና መሥዋዕት (በደሙ) አማካይነት ነው። በክርስቶስ ያመነውና በልዩ ልዩ ምክንያት በኀጢአት የወደቀ ክርስቲያንም ንስሓ ሲገባ ስርየተ ኀጢአትን የሚቀበለው በዚሁ መንገድ ነው። በእርሱ በኩል አምነው ለሚመጡት ለዘላለም የመዳን ምክንያት ሆነላቸው ተብሎ የተነገረውም ስለዚህ ነው (ዕብ. 5፥9-10፤ 7፥25)።
ክርስቶስን አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም፤ ወይም የአምላክነቱ ግብር እንጂ የሰውነቱ ግብር ቀርቷል ማለት ያስፈለገው ታዲያ ለምን ይሆን? ብለን መጠየቅ ይገባናል። የምናገኘው ምላሽም ከሁለቱ ውጪ እንደማይሆን እንገምታለን። የመጀመሪያው ‘ክርስቶስ አሁንም መካከለኛ ነው ካልን የሰውነቱን ግብር መግለጻችን ነውና እርሱን ዝቅ ማድረግ ይሆናል’ ከሚል ሥጋት ነው። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፣ ‘ክርስቶስን አሁንም መካከለኛ ካደረግነው እኛ መካከለኛ ያደረግናቸው ቅዱሳን ምን ሊሆኑ ነው?’ የሚል ይመስላል።