Saturday, September 17, 2016

ለምናምንቴ እረኛ ወየውለት!

ሕዝቅኤል 34
"የሰው ልጅ ሆይ፥ ትንቢት ተናገር፥ በእስራኤል እረኞች ላይ ትንቢት ተናገር፥ እረኞችንም እንዲህ በላቸው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ራሳቸውን ለሚያሰማሩ ለእስራኤል እረኞች ወዮላቸው! እረኞች በጎችን ያሰማሩ ዘንድ አይገባቸውምን? ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።እረኛንም በማጣት ተበተኑ፥ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፥ ተበተኑም። በጎቼ በተራሮች ሁሉና በረዘሙ ኮረብቶች ሁሉ ላይ ተቅበዝብዘዋል፥ በጎቼም በምድር ፊት ሁሉ ላይ ተበትነዋል፤ የሚሻም የሚፈልግም አልነበረም። ስለዚህ፥ እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝና እረኛ ስለሌለ እረኞቼም በጎቼን ስላልፈለጉ እረኞችም ራሳቸውን እንጂ በጎቼን ስላላሰማሩ፥ በጎቼ ንጥቂያ ሆነዋልና፥ በጎቼም ለምድር አራዊት ሁሉ መብል ሆነዋልና"



Monday, September 12, 2016

ኦርቶዶክስ ሆይ ድምፅሽ ወዴት አለ?


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የወቅቱን የሀገሪቱን ቀውስ ከጸሎት ባሻገር በመምከርና በመገሰጽ ወደሰላማዊና የተረጋጋ ሁኔታ በመመለስ ረገድ ልትጫወተው የምትችለው ድርሻ ትልቅ እንደሆነ ይገመታል። ነገር ግን "መጽሐፉም ዝም፣ ቄሱም ዝም" እንዲሉ ሆነና እያየች እንዳላየች፣ እየሰማች እንዳልሰማች መሆንን የመረጠችው ለምን ይሆን?
ከሰማያዊው መንግሥት  ምድራዊውመንግሥት አስፈርቷት ነው? ወይስ ዝም እንድትል ከሰማያዊው መንግሥት መልእክት መጥቶላት ይሆን?
ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ ሆና ቤተ መንግሥቱንም፣ ሕዝቡንም ልትገስጽ፣ ልትመክር ካልቻለች ወደምድራዊ ውግንና ወይም ሥጋዊ ፍርሃት ገብታለች ማለት ነው። የተሰጣትን እውነት የመናገር ብርሃናዊውን መቅረጽ የምትቀማው መናገር ሲገባት ዝምታን ከመረጠችና ዝምታ በሚገባት ሰዓት መናገር ከፈለገች ብቻ ነው። እናም ዝምታዋ ዞሮ ዞሮ የተሰጣትን መንፈሳዊ ሃብት እንድትቀማ ያደርጋታል። ለሌላው አሳልፎ እንዲሰጥ ይሆናል። ለልክ እንደጥንታዊዋ የኤፌሶን ቤተክርስቲያን ማለት ነው። ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ሳይፈጸም አይቀርም። ደግሞም እያየን ያለንበት ወቅት ላይ ነን።
መንግሥት ሆይ፣ ሕዝብህን በሕግና በፍርሃት ግዛ። ሕዝብ ሆይ፣ ለመንግሥትህ በሕግና በፍርሃት ተገዛ ማለት የእርቅ አንደበት እንጂ ለማንም መወገን አይደለም። ምን ጊዜም ብጥብጥና ሁከት ለሕግና ለተአዝዞት ፈቃደኛ ካለመሆን የሚመጣ ስለሆነ የትኛውም አካል ለሕግ ተገዢ ይሁን ብሎ መናገር የሚያስፈራ ጉዳይ አልነበረም። ገዳይም፣ ሟችም፣ ሕግ አፍራሽም፣ ሕግ ደንጋጊም ሁሉንም እንደ ልጆቿ አድርጋ በማየት ለሕግ ተገዙ ልትል ሲገባት የኦርቶዶክስን አንደበት ሌሎች እየተናገሩበት ይገኛል። ልጆቿን ልጆቻቸው አድርገው አንደበቷን ወስደው እየተናገሩበት ይገኛሉ። ይሄ መነሳት የነበረበት ከእርሷ ቢሆንም የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጎዶሎ ወንጌል የሌላት ሆኖ ሳለ የወንጌል ሙሉ ነን የሚሉ ቀድመው የአስታራቂነት ሽምግልናውን ወስደዋል። ለመሆኑ የሀገር ቤቱ ሲኖዶስ በሕይወት አለህ?




Thursday, September 8, 2016

"ሳይቃጠል በቅጠል"




by ኢትዮ - አፖሎጂስት

አክራሪ እስልምና አፋጣኝ መፍትሄ ይሻል

ይህ ጊዜ ዓለማችን በከፍተኛ ሁኔታ እየተናጠችና እየታመሰች ያለችበት ጊዜ ነው፡፡ ሰላሟን እያናጉ የሚገኙ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ቢኖሩም አብይ መንስኤው ግን ለሰው ልጆች ሰላምና ደህንነት እንደቆመ የሚሰብከው የእስልምና ሃይማኖት መሆኑ የሚያከራክር አይደለም፡፡ በሦርያ፣ በኢራቅ፣ በየመን፣ በሊብያ፣ በናይጄሪያ፣ በሶማሊያ፣ በፓኪስታን፣ በአፍጋኒስታንና በሌሎችም ብዙ የዓለም ሃገራት የሚታዩት ሁኔታዎች ይህንኑ የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ በሌላ ወገን ደግሞ እስልምና “የሰላም” ሃይማኖት መሆኑ በተደጋጋሚ ይነገረናል፡፡ እንዲህ ዓይነት ስብከቶች ከሙስሊሞች ዘንድ ብቻ ሳይሆን ሙስሊም ካልሆኑት እና እንዲያውም የሽብር ተግባራቱ ሰለባዎች ከሆኑት ግለሰቦችና ሃገራት ዘንድ መሰማታቸው ጉዳዩን አደናጋሪ ያደርገዋል፡፡ እስልምና የሰላም ሃይማኖት ከሆነ እምነቱን አክርረው የያዙ ሙስሊሞች ስለምን እጅግ ሰላማውያን ከመሆን ይልቅ እጅግ ነውጠኞች ሆኑ? እንዲህ ዓይነት ተግባራትስ ስለምን የእምነቱ መታወቂያዎች ሆኑ? በማለት ተገቢ የሆነውን ጥያቄ የሚሰነዝሩ ወገኖች “እስላሞፎብያ” የሚል “የአዕምሮ ህመም” ስም ይለጠፍላቸዋል፡፡ እስልምና የሰላም ሃይማኖት እንዳልሆነ በድፍረት የሚናገሩ ሰዎች ሕይወታቸውን ለአደጋ ያጋልጣሉ፡፡ ታዋቂ ግለሰቦች እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑን ሲናገሩ ከተደመጡ ፅንፈኛ ሙስሊሞች አደባባይ በመውጣት ንብረት ያወድማሉ፣ የንፁኀንን ደም ያፈስሳሉ፣ በእምነት ተቋማት ላይ ቦምብ ይጥላሉ፣ የሰላም ሃይማኖት መሆኑን ለማሳመን ሰላምን ያደፈርሳሉ፡፡ የሙስሊሞች ተግባርና ስለ እምነቱ የሚሰበከው ስብከት አራምባና ቆቦ ሆኖብን ግራ ተጋብተን ሳናበቃ እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑንና “ካፊሮችን” ማሸበር እስላማዊ መሆኑን የሚናገሩ ሙስሊም ሊቃውንት ይገጥሙናል፡፡ በአንድ ወቅት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊዩ ቡሽ “እስላም ሰላም ነው” በማለት መናገራቸውን ተከትሎ አቡ ቀታዳ የተሰኘ በጂሃድ የሚያምን ሙስሊም አስተማሪ የሚከተለውን ብሎ ነበር፡- “ፕሬዚዳንት ቡሽ በእስልምና ስም የሚደረገውን የጂሃድ ሽብር የሚደግፍ ምንም ዓይነት ነገር በቁርአን ውስጥ አለመኖሩን መናገሩ በእጅጉ አስገርሞኛል፡፡ ለመሆኑ እርሱ የሆነ ዓይነት የእስልምና ሊቅ ነውን? እንደው በእድሜ ዘመኑ ቁርአንን አንብቦ ያውቃልን?”[1]
ሙስሊሞች በሚበዙባቸው ሃገራት ውስጥ የሚገኙት ብዙ ሙስሊም ሊቃውንት እስልምና የሰላም ሃይማኖት አለመሆኑን ይናገራሉ፡፡ በምዕራብ ሃገራት እና ሃገራችንን በመሳሰሉ የሙስሊሞች ቁጥር ከአጠቃላዩ የሕዝብ ቁጥር በሚያንስባቸው ሃገራት ውስጥ የሚገኙት ደግሞ እስልምና የሰላም ሃይማኖት መሆኑን ይሰብካሉ፡፡ የፖለቲካ መሪዎቻችንና የሃይማኖት አባቶቻችንም ከእነርሱ ጋር ይስማማሉ፡፡ እውነቱ የቱ ነው? ማንን እንስማ? የቱን እንቀበል? ከዚህ ግራ መጋባት ለመውጣት እስላማዊ የሃይማኖት መጻሕፍትን ማጥናት አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው፡፡
ከፊት ለፊታችን ከባድ አደጋ የተጋረጠ ቢሆንም ብዙዎቻችን የአደጋውን ግዝፈት ማየት አለመቻላችን ወይም ለማየት አለመፈለጋችን የሚያሳዝን ነው፡፡ በአክራሪ ሙስሊሞች በዚህች ሃገር ውስጥ ለደረሱት ጉዳቶች የኛ ቸልተኝነትና ዝምታ አስተዋፅዖ ማበርከቱን መካድ አንችልም፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ነገሮች ከልክ አልፈው ሃገሪቱ ከገደሉ አፋፍ ደርሳ ከመውደቋ በፊት እግዚአብሔር መንግሥትን ባያነቃ ኖሮ መፃዒ እጣ ፋንታችን ምን ሊሆን እንደሚችል ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን የማስታገሻ እርምጃ እንደተወሰደ እንጂ ትክክለኛ መፍትሄ እንደተሰጠ በልበ ሙሉነት መናገር አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የህመሙ ምልክት እንጂ መንስኤው አልታከመምና፤ መንስኤው እስካልታከመ ድረስ ደግሞ ጊዜ ጠብቆ መልሶ ማገርሸቱ የማይቀር ሃቅ ነው፡፡ የአክራሪነት ሥረ መሰረት በቁርአን፣ በሐዲሳትና በሌሎችም እስላማዊ ምንጮች ውስጥ ሰፍረው የሚገኙት ትምህርቶች መሆናቸውን መካድ አያዋጣንም፡፡ ሽብርተኝነት የዛፉ ፍሬ በመሆኑ ሥራ መሰራት ያለበት ከፍሬው ይልቅ በግንዱ ላይ ነው፡፡ ይህንን የተረዱት የግብፁ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ ኧል-ሲሲ የዓለም ግምባር ቀደም እስላማዊ ዩኒቨርሲቲ እንደሆነ በሚነገርለት በአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ ሙስሊም ሊቃውንት ፊት ያደረጉት ዓለምን ያስደመመ ንግግር ጥሩ ምሳሌ ይሆነናል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ያለ ምንም መሸፋፈን ችግሩ የሚገኘው እድሜ ጠገብ በሆኑት እስላማዊ ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ መሆኑን በማስገንዘብ በዓለም ላይ ለሚገኘው የሽብርተኝነት ችግር መፍትሄ እንዲመጣ ከተፈለገ እነዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት መስተካከል እንዳለባቸው ጥብቅ ማሳሰብያ ሲሰጡ ተደምጠዋል፡፡ ሙስሊሞች በዓለም ላይ የሚገኙትን ሕዝቦች ሁሉ በማጥፋት እራሳቸው ብቻ ለመኖር መፈለጋቸው የሚያስከትለውን አደጋ በመጠቆም የማስጠንቀቂያ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ የሚከተለው ከንግግራቸው ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው፡-
“… እዚህ ጋ እየተናገርኩ ያለሁት የእምነት አባቶችን ነው፡፡ እየተጋፈጥን ስላለነው ነገር በአንክሮ ማሰብ ያስፈልገናል – በእርግጥ ይህንን ጉዳይ ከዚህ ቀደም አንድ ሁለት ጊዜ አንስቻለሁ፡፡ በጣም ክቡርና ቅዱስ አድርገን የያዝነው አስተሳሰብ አጠቃላይ ኡማውን [እስላማዊውን ማሕበረሰብ] ለዓለም ማሕበረሰብ የጭንቀት፣ የአደጋ፣ የግድያ እና የጥፋት ምንጭ እንዲሆን ማድረጉ የማይታመን ነው፡፡ ይህ ሊሆን አይችልም!
ያ አስተሳሰብ – “ሃይማኖት” እያልኩ አይደለም ነገር ግን “አስተሳሰቡ” – ከእርሱ ማፈንገጥ የማይቻልበት ደረጃ ላይ እስክንደርስ ድረስ ለክፍለ ዘመናት አክብረን የያዝነው የመጻሕፍትና የአስተሳሰብ ስብስብ መላውን ዓለም እየተፃረረ ይገኛል፡፡ ዓለምን በሞላ እየተፃረረ ነው!
እነዚህን ቃላት እዚህ በአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ፣ በዚህ የሊቃውንትና የኡላማ ጉባኤ ፊት እየተናገርኩ ነው – አሁን እየተናገርኩ ያለሁትን ነገር በተመለከተ ሁሉን ቻይ የሆነው አላህ በፍርዱ ቀን ስለ እውነተኛነታችሁ ምስክር ይሁንባችሁ፡፡
እየነገርኳችሁ ያለሁትን ይህንን ሁሉ ነገር በዚህ አስተሳሰብ ውስጥ ተጠምዳችሁ የምትኖሩ ከሆነ ልትረዱት አትችሉም፡፡ በትክክል መገምገም እንድትችሉና የበለጠ አብርሆት ካለው ፅንፍ ማየት ትችሉ ዘንድ ከራሳችሁ ሁኔታ መውጣት ያስፈልጋችኋል፡፡
ደግሜ ደጋግሜ እላለሁ ሃይማኖታዊ አብዮት ያስፈልገናል፡፡ እናንተ ኢማሞች በአላህ ፊት ተጠያቂዎች ናችሁ፡፡ መላው ዓለም፣ እደግመዋለሁ መላው ዓለም የእናንተን ቀጣይ እርምጃ እየተጠባበቀ ይገኛል… ምክንያቱም ይህ ኡማ እየፈረሰ ነው፣ እየወደመ ነው፣ እየጠፋ ነው – እየጠፋ ያለው ደግሞ በገዛ እጃችን ነው፡፡[2]
በዚህ ንግግር ውስጥ ፕሬዚዳንት ኧል-ሲሲ በእስላማዊ ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ የተሰገሰገው የነውጠኝነት አስተሳሰብ የዓለም ስጋት ምንጭ መሆኑን በግልፅ አስረድተዋል፡፡ በዚህ ገፅ ላይ በተከታታይ ስናወጣ እንደቆየነው የሽብርተኝነት ሥረ መሰረት እስላማዊ መጻሕፍት እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ (አይ ኤስ የተሰኘው የሽብር ቡድን እየፈፀማቸው የሚገኙት የሽብር ተግባራት በእስላማዊ ምንጮች የተደገፉ መሆናቸውን ማስረጃዎችን በመጥቀስ ያሳየንበትን ጽሑፍ ለአብነት ያህል ማየት ይቻላል፡፡) ካለማወቅም ይሁን ከፖለቲካዊ ትክክለኝነት (Political Correctness) በመነጨ አስተሳሰብ እስላማዊ መጻሕፍት ሰላምን እደሚያስተምሩ በመስበክ ለእስልምና ጥብቅና ሲቆሙ የነበሩ ወገኖች ይህንን ማድረጋቸው ምንም አልፈየደም፡፡ አንድን ከሥነ ምግባር የወጣ ሰው ሥነ ምግባሩ ጥሩ እንደሆነ ደጋግሞ በመንገር ፀባዩን እንዲያርም ማድረግ እንደማይቻል ሁሉ ሽብርን የሚሰብክ ሃይማኖት ሰላምን እንደሚሰብክ በመናገር ሰላማዊ ማድረግ አይቻልም፡፡ ይልቁኑ ስህተቱን ነቅሶ በማውጣት እንዲያስተካከል መንገር እንጂ መፍረግረግና መለማመጥ አጥፊው የልብ ልብ እንዲሰማው ማድረግ ነው፡፡ እውነትን ሸሽጎ ውሸትን በመናገር ችግሩን ማፈርጠም መፍትሄ አይሆንም፡፡ የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ንግግሮች ዘላቂ መፍትሄ ሊያመጡ ይቅርና ጊዜያዊ መፍትሄ እንኳ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡ የሃይማኖት አባቶችና የፖለቲካ መሪዎች የእስልምናን ሰላማዊነት አጥብቀው ቢሰብኩንም ነገር ግን ችግሮች እየተባባሱ ሄዱ እንጂ ሲቀንሱ አልታዩም፡፡ እውነትን በመናገር ሊፈጠር የሚችለውን ጊዜያዊ ችግር በመፍራት ዝንተ ዓለም በሽብር እየተናጡ ከመኖር እውነቱን አፍረጥርጦ በመናገር ዘላቂ መፍትሄ መፈለግ ይበጃል፡፡ “ጅቡ እግሬን እየበላው ነውና እንዳይሰማን ዝም በል” እንዳለው ሞኝ ሰው መሆን ይበቃናል፡፡
ማሕበረሰባችንን ከዚህ አስከፊ የጥፋት ማዕበል ለመታደግ የመጀመርያው እርምጃ መሆን የሚገባው የችግሩን ምንጭ ለመረዳት ጥረት ማድረግ ነው፡፡ በአንድ ወቅት የምንጊዜም ምርጥ ሳይንቲስት የሆነው አንስታይን ዓለምን ከጥፋት ለመታደግ አንድ ሰዓት ብቻ ቢሰጠው የተሰጠውን ጊዜ እንዴት እንደሚጠቀም ተጠይቆ ሲመልስ 55 ደቂቃዎችን ችግሩን ለመረዳትና 5 ደቂቃዎችን ብቻ መፍትሄ ለማፈላለግ እንደሚጠቀም ተናግሮ እንደነበር ይነገራል፡፡ የብዙ ችግሮቻችን መፍትሄ ያለማግኘት ምክንያቱ ችግሮቹን ራሳቸውን በትክክል አለማወቃችን መሆኑ እሙን ነው፡፡ ሽብርተኝነት በህዝባችን ላይ አደጋን የደቀነ የዘመናችን ችግር መሆኑን እናውቃለን፡፡ ነገር ግን የሽብርተኝነት ምንጭ ምን እንደሆነ ስለማናውቅ የችግሩ አሳሳቢነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ይገኛል፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ ሃገራችን በዙርያዋ ከሚገኙት ጎረቤቶችዋ ጋር ሊነፃፀር በማይችልበት ሁኔታ ከሽብር አደጋዎች ተጠብቃ ትገኛለች፡፡ ነገር ግን የሽብርተኝነት ምንጭ የሆነውን የእስልምናን ትምህርት በትክክል ተረድተን መፍትሄ ካላፈላለግን በስተቀር ይህ አንፃራዊ ሰላም በዚህ ሁኔታ ለመቀጠሉ ምንም ዋስትና አይኖረንም፡፡ ስለዚህ ዜጎችም ሆንን መሪዎች እስልምና ሽብርተኝነትን በተመለከተ ምን እንደሚያስተምር፣ ምን እንደሚያቅድ፣ የአፈፃፀም ስልቶቹ እንዴት እንደሆኑ፣ ወዘተ. ማጥናት ያስፈልገናል፡፡ እውቀቱ ካላቸው፣ በተለይም ደግሞ በእስልምና ትምህርቶች ከሰለጠኑና እስልምናን ለቀው ከወጡ ሰዎች መማር እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡
አክራሪ እስልምና ለዓለምም ሆነ ለሃገራችን አዲስ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የአክራሪ እስልምናን ተግዳሮቶች ስትጋፈጥ ኖራለች፡፡ አንዳንዶች አክራሪ እስልምና ፖለቲካዊ ችግር በመሆኑ መፍትሄው ፖለቲካዊ ነው ስለዚህ ችግሩ ለመንግሥት ብቻ መተው አለበት ይላሉ፡፡ ነገር ግን፡-
መንግሥት ሥልጣንና ጉልበት ቢኖረውም የትምህርቱን ውጤት እንጂ ትምህርቱን መጋፈጥ አይቻለውም፡፡ የመንግሥት አካላት ብዙ ጊዜ በሃይማኖት ካባ ተሸፍኖ ለክፍለ ዘመናት የኖረውን አይ የእስልምናን ፖለቲካ ለመረዳት ሲቸገሩ ይስተዋላሉ፡፡ ስለዚህ ትክክለኛ መፍትሄ ለመስጠት ይቸገራሉ፡፡
የመንግሥት አካላት የነገሩን ውስጠ ሚስጥር ቢረዱትም እንኳን መንግሥት ሁሉን አቀፍ በመሆኑ ገለልተኛነትን ይመርጣሉ፡፡ ስለዚህ የችግሩ መንስኤ የሆነውን የእስልምናን መሰረት መንካት አይፈልጉም፡፡
አክራሪ እስልምና አይዲዎሎጂ በመሆኑ በጉልበት አይቀለበስም፡፡ ስለዚህ መንግሥት አክራሪ እስልምና የጦር መሳርያ ይዞ አደባባይ ሲወጣ በጦር መሳርያ ማስታገስ ቢችልም ነገር ግን ትምህርቱን የሚጋፈጥበት ሥነ መለኮታዊ መሳርያ የለውም፡፡
ባለፉት ጥቂት ዓመታት እንደታዘብነው አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ይባስ ብለው ከአክራሪ እስልምና ጋር በመተባበር አጀንዳውን ሲያራግቡና ጥብቅና ሲቆሙለት ታይተዋል፡፡ ይህ የሚያመለክተው አንዳንድ ፖለቲከኞች የዛሬ ጥቅማቸውን እንጂ የነገውን አደጋ ማየት አለመፈለጋቸውን ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰዎች ሥልጣን ቢይዙ ችግሩን ከማባባስ ውጪ መፍትሄ መስጠት አይችሉም፡፡
የመገናኛ ብዙኃንን ስንመለከት እንኳንስ መፍትሄ ሊሰጡ ይቅርና ጥያቄውን እንኳ በትክክል የተረዱት አይመስልም፡፡ በትክክል ቢረዱትም እንኳን ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ስለሚጫናቸው የችግሩን ስረ መሰረት በመንካት መፍትሄ ማፈላለግ አይችሉም፡፡
ምሑራን ጥያቄውን የተወሰነ ያህል ይረዱታል ነገር ግን የችግሩን ስረ መሰረት በመጥቀስ የመፍትሄ ሐሳቦችን እንዳይሰነዝሩ በፍርሃትና በፖለቲካዊ ትክክለኝነት ተሸብበዋል፡፡
አንዳንድ ለዘብተኛ አመለካከት ያላቸው ምዕራባውያን የሚከተሉትን “መፍትሄዎች” ያስቀምጣሉ፡-
ለአክራሪ ሙስሊሞች ምንም ትኩረት አለመስጠትና ችላ ማለት፡፡ ነገር ግን ችላ የሚባሉት እምን ድረስ ነው? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ሰይፍ አንገታችን ላይ ተቀምጦ ትኩረት አንሰጠውም ማለት የሞኝ መፍትሄ ነው፡፡
ባሉበት እንዲሆኑ ማገድ (ወደ ክልላችን እንዳይገቡ ማድረግ፡፡) o አሁን ካለው የሕዝቦች እንቅስቃሴና የመረጃ ቴክኖሎጂ ደረጃ አኳያ አያስኬድም፡፡ የውጪዎቹ እንዳይገቡ ማገድ ይቻል ይሆናል፣ ውስጥ የሚገኙትንስ? መግደል? ማሰር? ከሃገር ማባረር? አያዋጣም፡፡
እስልምናን ከፖለቲካዊ ይዘቱ በማፋታት ምዕራባዊ መልክ ያለውን እስልምና መፍጠር [ለምሳሌ ኪልያም (Quilliam) ፕሮጀት]፡፡[3]