Tuesday, September 15, 2015

ተከስተ ጌትነት ለተወራበት የወሲብ ቅሌት፤ ዋሽንግተን ዲሲ ለሚታተመው ዘኢትዮጵያ ጋዜጣ የሰጠው ምላሽ

እኔ ወ/ሮ ሆሳዕናን አስገድጄ አልደፈርኩም። በፍርድ ቤትም አልተከሰስኩም። ለዚህም ማስረጃ አለኝ።”
የወ/ሮ ሆሳዕና ባለቤት ባለፈው በቪ ኦ ኤ በቀረበው ፕሮግራም መግቢያ ላይ “በሚስቴ ላይ የጾታ ጥቃት ተፈጽሞባታል” ያለውና ወይዘሮ ሆሳዕናም በዚያው ፕሮግራም ላይ ቀርባ “ጉዳዩ በህግ የተያዘ ነገር ነው” ያለችው ነገር ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው። እኔ ማንንም ሰው አስገድጄ አልደፈርኩም ምንም አይነት ክስም አልቀረበብኝም። ከወንጀል ነፃ መሆኔን የሚያሳይ ህጋዊ ማስረጃ በአሜሪካን አገር ጉዳዩ ከሚመለከተው መስሪያ ቤት በጠበቃዬ አማካይነት ያገኘሁት እሷ በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ቀርባ ከስሸው ጉዳዩ በህግ ተይዟል ብላ በተናገረች በሚቀጥለው ቀን ነው።

 ይባስ ብሎ በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ፓስተር ተከሰተ ባለትዳር ሴት ደፍሮ ተከሰሰ የሚለውን ዜና ውሸት እና የፈጠራ ወሬ መሆኑን የሚያሳየው እኔ እነሱ ከሚኖሩበት ሚንያፖሊስ ከተማ እኔ ወደምኖርበት ወደ ዋሽንግተን ስመለስ ወደ አውሮፕላን ጣቢያ የሸኘችኝ እራስዋ ወይዘሮ ሆሳዕና ነች። በብዙ ጭቅጭቅ የ1000 (አንድ ሺህ) ዶላር የእጅ ሰዓት በራስዋ ክሬዲት ካርድ ገዝታልኛለች። ለዚህም ሌላ ህጋዊ ማሰረጃ አለኝ። በዚያን ሰአት እንኳን ልትከስኝ ቀርቶ ለወንድ ልጅ ሰዓት መስጠት እወዳለሁ ብላ እኔ ሰአት አልፈልግም እያልኳት እሷ ግን እኔ የወንድ ልጅ ሰዓት ስለሚስደስተኝ ልግዛልህ። አንተ ብትፈልግ ወደፊት በሌላ ነገር ቀይረው በማለት ከነደረሰኙ ሰጠችኝ።

አንተና ወይዘሮ ሆሳዕና እንዴት ተገናኛችሁ ጉዳዩስ እንዴት እዚህ ደረጃ ደረሰ? ብለን ላቀረብነው ጥያቄ የሰጠው ምላሽ፡ ወ/ሮ ሆሳዕናና የእኔ ባለቤት የአንድ ሰፈር ሰዎች ናቸው። ከዚያም በራስዋ በወይዘሮ ሆሳዕና ተደጋጋሚ ግፊትና ጥረት ተቀራረብን። የቤተሰባችን አካል ሆነችና አገልግሎትህን ስለምወድ እንድደግፍ ጌታ አሳሰበኝ በሚል መንፈሳዊ አካሄድ ለእኔና ለቤተሰቦቼ በተለያየ ጊዜ ስጦታ ሰጥታናለች። የቤተክርስቲያን አገልጋዮች በምዕመናን በጎ ፈቃድ የፍቅር ስጦታና የአገልግሎት ድጋፍ ማግኘት የተለመደ ስለሆነ እኔም በአገልግሎት ዘመኔ እኔንና አገልግሎቴን የሚደግፉ ብዙ ደጋግ ሰዎች ስላጋጠሙኝ ወይዘሮ ሆሳዕና ያለችውንም በቅንነት ተቀበልኩት። በመጨረሻም እኔ ባለቤትህና አንተ ለምን የጋራ ቢዝነስ አንጀምርም? እኔ ገንዘብ አለኝ፣ የቤተሰብ የቢዝነስ ልምዱም ስላለኝ አንተ ደግሞ ኢትዮጵያ ታዋቂ ስለሆንክ ሦስታችን አብረን ኢትዮጵያ ቢዝነስ ብንሰራ ሊሳካልን ይችላል ብላ ጠየቀችን። እኔም ማንኛውም ዘማሪ አንደሚመኘው ከቤተክርስቲያን ምንም ነገር ሳልጠብቅ ራሴን እና ቤተሰቤን በግሌ እየሠራሁ በማስተዳደር በነፃ የማገልገል ከፍተኛ ፍላጎት ስለነበረኝ እኔና ባለቤቴ በሀሳቡ ተስማማን። እኔ እነሱ ወደሚኖሩበት ከተማ የሄድኩት እና ሆቴል ያረፍኩት ራስዋ ወይዘሮ ሆሳዕና በአሜሪካን ድምፅ ሬድዮ ቀርባ እንደተናገረችው በጋራ ስለምንጀምረው ቢዝነስ ለመነጋገር ነበር። ይህን ሀሳብ ያመጣችው እራሷ ወይዘሮ ሆሳዕና ነች።

በራሷ ገንዘብ የአውሮፕላን ትኬት ቆርጣ እራሱዋ ሆቴል ይዛ፣ (ለዚህም ማስረጃ አለኝ)። ከዚያ በኋላ አሁንም ራሷ በአሜሪካን ድምፅ ቀርባ እንደተናገረችው ያረፍኩበት ክፍል ውስጥ ገብታ ልብሷን አወለቀች። ብዙ ተፈታተነችኝ። የምሄድበት መንገድ ትክክል እንዳልሆነና ሆን ተብሎ የገባሁበት ወጥመድ እንዳለ ሲገባኝ ፍላጎቱ ባይኖረኝም እሷን ሳላሳዝን ሞራልዋን ሳልነካ በሰላምና በእርጋታ ለመውጣት “በቃ አሁን እኔ መረጋጋት አልቻልኩም ፍላጎቱ የለኝም ሌላ ጊዜ ተመልሼ ልምጣና ያንቺን ፍላጐት አሟላለሁ” ብዬ ቃል ገባሁ። እሷም ተመልሼ ወደእሷ ከመጣሁና መሻቷን ከፈጸምኩ አብረን ልንሠራ ከተነጋገርንበት ቢዝነስ በተጨማሪ ለግሌ ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንደምትሰጠኝ ነግራኝ ተለያየን። ካረፍኩበት ሆቴል ወደ አውሮፕላን ጣቢያ ስንሄድ ለወንድ ልጅ የሰዓት ስጦታ መስጠት ያስደስተኛል ብላ ከላይ እንደጠቀስኩት የአንድ ሺህ ዶላር ሰዓት መንገድ ላይ ወደሚገኝ ሞል ኦፍ አሜሪካ የገበያ ማዕከል ውስጥ ሜሲስ የሚባል ስቶር ወስዳ ገዛችልኝ።

አየር ማረፊያ አውርዳኝ ስንለያይ ለመጀመርያ ጊዜነጻነት ተሰማኝ። ዋሽንግተን ዲሲ ተመልሼ እቤቴ ስገባም የሆነውን ነገር ሁሉ ለባለቤቴ አንድም ነገር ሳልደብቅ ነገርኳት። ከዚያም እንደ አንድ ክርስቲያን እና እንደ አንድ አገልጋይ ከእኔ የማይጠበቅ ነገር አድርጌአለሁ ብዬ ያለማንም አስገዳጅነት በራሴ ፈቃድ ለቤተክርስቲያን ተናግሬ ወዲያውኑ ራሴ አገልግሎት አቆምኩ። በራሴ ቤተክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የአሜሪካን ክፍለግዛቶች በሚገኙ አብያተክርስቲያናት እንዳገለግል የተጋበዝኩባቸውን አገልግሎቶች በሙሉ በራሴ ፈቃድ ሰረዝኩ። እኔ ወደዋሽንግተን ከመጣሁ በኋላ ወይዘሮ ሆሳዕናም እኔን በስልክ ለማግኘት ተደጋጋሚ ሙከራ አደረገች ግን አልተሳካላትም። ከዚያ በኋላ የበቀል እርምጃው ግራ በሚያጋባ መልኩ መጣ።
መጀመሪያ ለእኔ ባለቤት ለወ/ሮ የምስራች ባለቤቱዋ አቶ መላኩ ደውሎ ሚስቴ ከአንቺ ባል ጋር አብራ ስለተኛች ይቅርታ ልትጠይቅሽ ነው ብሎ ስልኩን ለወይዘሮ ሆሳዕና ሰጣት። ወይዘሮ ሆሳዕናም እኔ ከባለቤትሽ ከተከስተ ጋር ተኝቻለሁ ይቅርታ አድርጊልኝ ብላ በስልክ ለእኔ ባለቤት የድምፅ መልእክት ተወችላት (ደውለው ለባለቤቴ የተውት የእሱም የእሷም የድምፅ መልዕክት ማስረጃው አለኝ)። ከዚያ ደጋግመው ደውለው ባለቤቴን አገኟትና ባልሽ ከሚስቴ ጋር ተኛ ብሎ ነገራት። ባለቤቴም በቃ ካጠፉ ይቅር እንበላቸው እና ነገሩ ይቁም አለችው።

ባለቤቴም ሁሉንም ነገር አልቀበል ስትል ወደ ቤተክርስቲያን ሄዱ። አቶ መላኩ ቤተክርስቲያን ሄዶ ፓስተር ተከስተ ከሚስቴ ጋር ተኝቷል አገልግሎት ማቆም አለበት ይቅርታ መጠየቅ አለበት አለ። እኔም የእግዚአብሔር ቃል እንደሚለው እና መንፈስ ቅዱስ እንደሚወቅሰኝ ከአንድ አገልጋይ የማይጠበቅ ጥፋት አጥፍቻለሁ። እግዚአብሔርንም በድያለሁ ለዛም እራሴን ከአገልግሎት አስቁሚያለሁ። እናንተንም ይቅርታ እጠይቃለሁ አልኩኝ። ሰዎቹ ዓላማቸው ክርስቲያናዊ ዕርቅ እንዳልሆነና አሳባቸውን በመቀየር ለሌላ ለተሻለ የበቀል እርምጃ ሊጠቀሙበት እንደሆነ አስቀድሜ ለሦስቱ ሽማግሌዎች ነግሬአቸው ነበር። ነገሩ በሰላም እንዲያልቅና ክርስቲያናዊ አካሄድ ነው ብዬ ስለማምን ሙሉ ኃላፊነት ወስጄ ይቅርታን ጠይቄአለሁ። አቶ መላኩ ግን የግብረሥጋ ግንኙነት ፈጽመሃልና እመን የሆነውንም ዝርዝር ነገር ንገረኝ ብሎ ጠየቀኝ። እኔም ሙሉ ኃላፊነት ወስጄ ይቅርታንም ጠይቄ የወይዘሮ ሆሳዕናን ስሜትና ስብእና የሚነካ ዝርዝር ነገር ውስጥ ግን እንደማልገባ አሳወቅሁኝ። ምክንያቱም እንደዚህ ዓይነት ነገር ያልተለመደ በመሆኑና አቶ መላኩ ማወቅ የሚፈልገውን መረጃ በሙሉ ከገዛ ሚስቱ ማግኘት ስለሚችል ነው። ቤተክርስቲያንም ፓሰተር ተከስተ ከአንድ አገልጋይ የማይጠበቅ ጥፋት አጥፍቻለሁ ብሎ በራሱ ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ገብቶአል አገልግሎትም አቁሞአል ፣አንተንም ይቅርታ ጠይቋል ነገሩ እዚህ ጋር ይለቅ ብለው ጠየቁት ። እነሱ ግን እኔን ለማጥፋት ቆርጠው ስለተነሱ ነገሩ እንዲቆም አልፈለጉም።

ቤተክርስቲያን መጥተው ያሰቡትን ያህል እኔን የጎዱኝ እና ያዋረዱኝ ስላልመሰላችው ቪ ኦ ኤ ሄደው ፓስተር ተከስተ አስገድዶ ደፍሮኛል ጉዳዩም በህግ ተይዞአል የሚል በሽምግልናው ወቅት በጭራሽ ያልተነሳ ሌላ ተጨማሪ የውሸት ታሪክ ፈጠሩ። ይህን አላማ እንዲያስፈጽም ጋዜጠኛ አዲሱ አበበን ይዘው መጡ። አቶ አዲሱ ጋር ስንነጋገር ሆን ብሎ እኔን ለማጥቃት እንዳሰበና እውነቱን ማወቅ እንደማይፈልግ ስለገመትኩ በጉዳዪ ለይ ምንም አይነት ኢንተርቪው ላንተ አልሰጥም፣ ጉዳዪም በቤተክርስቲያን ሽማግሌዎች ተይዟል አልኩት። የቤተክርስቲያን መሪዎች እና ጉዳዩን የያዙትም ሽማግሌዎችም አቶ አዲሱን ይሄ የቤተክርሰቲያን ነገር ነው በዚህ ነገር ላይ ምንም አይነት ፕሮግራም በሬዲዩ ላይ መሥራት የለብህም ብለው እየነገሩትና እየተለመነ በማን አለብኝነት ጉዳዩን አጣሞ ሁላችሁም እንደሰማችሁት እኔን በሚያዋርድ ፣ስሜን በሚያጠፋ፣ ሕይወቴንና አገልግሎቴን በሚያበላሽ መልኩ ፕሮግራሙን ሰርቶ በሬድዮ አቀረበው። አሁንም የምለው እኔ የበደሉኝን ሁሉ ይቅር ብያለሁ። እንደ ክርስቲያንና እንደ አገልጋይ አጉድዬ በተገኘሁባቸው ጉዳዮች ላይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምህረትን ከባለቤቴና ከቤተክርስቲያኔ ደግሞ ይቅርታን አግኝቻለሁ። ዛሬ ደግሞ በእኔ ምክንያት ያዘናችሁትን ሁሉ ይቅርታ እጠይቃለሁ ብሏል።
አሁን እያሳየኸኝ ያለውን ማስረጃ ይዘህ ለማስተባበልና በሕግ ለመፋረድ እስከዛሬ ለምን ሙከራ አላደረግህም? ለሚለው ጥያቄም መልስ ሰጥቷል።

ሥሜንና ክብሬን በተመለከተ እኔ ሥምና የሚዋረድ ክብር የለኝም። እኔን ከጎዳና ላይ አንስቶ ሰው ያደረገኝ እግዚአብሔር ነው። ከእርሱ ውጭ በሰው የሚዋረድም የሚከብርም ማንነት የለኝም። ፍትህን በተመለከተ ደግሞ የምንኖርበት አሜሪካ የፍትህ አገር መሆኑን አውቃለሁ። የትኛውም ድርጅት፣ ባለሥልጣንም ሆነ ግለሰብ ከሕግ በታች መሆኑንም አውቃለሁ። ወንጌል አምኖ እንደዳነ ክርስቲያን ግን እግዚአብሔር ሁሉንም በጽድቅ ስለሚፈርድ ፍትህን ከእግዚአብሔር እንጂ ከማንም ሰው አልጠብቅም። ባለቤቴም ቢሆን ሁሉም ነገር በሰላምና በይቅርታ እንዲያልቅ ስለምትፈልግ ወደ ፍርድ ቤትም አልሄድንም። በዚህ አጋጣሚ ሳሚ በማያውቀውና በሌለበት ነገር በኔ ምክንያት ስለተሰቃየ ና በውሽት ስሙ ስለጠፋ በጣም ያዘንኩ መሆኔን እገልጻለሁ።

Thursday, September 10, 2015

ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ሰዎች በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?

ክፍል ሁለት
በክፍል አንድ ያቆምንበትን ሃሳብ ይዘን ከመቀጠላችን በፊት አንዳንድ ተቺዎች ባነሱልን ሞገት ዙሪያ ለዛሬ ጥቂት ማለት እንደሚያስፈልግ ስላመንን በዚያ ዙሪያ እንቆያለን።
 ሞጋቾቹ የሚያቀርቡት ማስረጃ በመዝሙር 34፤7 ላይ ያለውን ጥቅስ ነው።

«የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል»

ይህንን ጥቅስ በመያዝ ቅዱሳኑ መላእክት ሁልጊዜ በሰዎች ዙሪያ ሰፍረው ስለሚገኙ ማዳን፤ ጸሎት መቀበልና መልስ መስጠት የዘወትር ሥራቸው ነው ይላሉ። በሌላ ደግሞ መላእክት የሚኖሩበት ከተማ ኢዮር፤ ራማና ኤረር እንደሆነም ይናገራሉ። መላእክት ዘወትር በዚህ ምድር ባሉ ሰዎች ዙሪያ ሰፍረው የሚገኙ ከሆነ በኢዮር፤ ራማና ኤረር የሚኖሩት መላእክት ምንድናቸው? ወይስ መላእክት በሰማይም በምድርም በአንድ ጊዜ ይገኛሉ ማለት ነው? ተብለው ሲጠየቁ የመላእክትን ውሱን ተፈጥሮ ለማመን ይዳዳሉ። ነገር ግን በተግባር ይህንን ይቃረናሉ። ለምሳሌ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በተፈጥሮ ሥፍራው በሰማይ እያመሰገነ ሳለ በማእዘነ ዓለሙ ሁሉ ስሙን የሚጠሩትን  ሰዎች ልመና ይሰማል? መልስም ይሰጣል ወይ? ተብለው ሲጠየቁ አዎ ይሰማል ለማለት አያፍሩም። እንዲያማ ከሆነ ቅዱስ ሚካኤል በአንድ ጊዜ በሁሉም ሥፍራ ይገኛል ማለት ነው። ይህ ደግሞ ትልቅ ስህተት ነው። ፍጡር በተፈጥሮው ውሱን የመሆኑን ማንነት ይንዳል።

  እርግጥ ነው፤ ቅዱሳኑ መላእክት ሰዎችን ይራዳሉ፤ ያግዛሉ። ይህንን ስንል መጋቤ ፍጥረታትየሆነውን  እግዚአብሔርን በሥራ ያግዙታል ማለት አይደለም።  ይህች ያለንባት ምድር ትሁን ዓለማት በሙሉ የሚተዳደሩት በእግዚአብሔር ብቃትና ሥልጣን እንጂ በመላእክት አጋዥነት አይደለም። እግዚአብሔር ብቻውን በቂ ነው። ሁሉን ተአምራት የሠራ እርሱ ብቻውን ነው።
«እርሱ ብቻውን ታላቅ ተኣምራትን ያደረገ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና» መዝ 136፤4
የተአምራትና የድንቅ ነገር ሁሉ ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ ነው። ስለሆነም መላእክቱ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ አንጻር ያደረጉትን እያየን መላእክቱን በውዳሴና በስባሔ የምናቀርብላቸው አምልኮ የለም። ደግሞም ቅዱሳኑ መላእክት የሚኖሩባቸውን ዓለመ መላእክት ትተው በዚህ ምድር የሚዞሩበትም ሁኔታ እንዳለ መጽሐፍ ቅዱስ አይነግረንም። ይልቁንም ይህችን ምድር ያለመታከት የሚዞርባት ሰይጣን ብቻ ነው።
 ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ የፈረጠጠ እሱ ብቻ ስለሆነ ተቆጣጣሪ አልቦ ሆኖ ይኖራል። በራሱ ፈቃድ የት፤ የት እንደሚዞር ለፈጣሪው እንዲህ ሲል እናገኘዋለን።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም፤ ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ምድርን ለመዞር፤ በእሷ ላይም ለመመላለስ ፈቃድ አይጠይቅም። «ከወዴት መጣህ?» የሚለው የእግዚአብሔር ጥያቄ የሚያስረዳን አፈንጋጭና በፈቃዱ ያለትእዛዝ የሚዞር መሆኑን ነው። ቅዱሳን መላእክቱ ግን እንደዚህ አይደሉም። በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሥራ አላቸው፤ ትእዛዝ ይቀበላሉ፤ ትእዛዝ ይተገብራሉ እንጂ እንደሰይጣን በሰዎች ስለተጠሩ ወይም ባይጠሩም ስለፈለጉ የትም አይዞሩም፤ ያለትእዛዝም አይንቀሳቀሱም። በሁሉም ሥፍራም በምልዓት አይገኙም።

  መጽሐፍ ቅዱስ በትንቢተ ዳንኤል ላይ የመላእክትን ውሱንነት፤ መውጣት፤ መውረድ በደንብ የሚያስረዳን ቃል እንዲህ ይላል።
«እነሆም፥ አንዲት እጅ ዳሰሰችኝ፥ በጕልበቴና በእጄም አቆመችኝ። እርሱም፦ እጅግ የተወደድህ ሰው ዳንኤል ሆይ፥ እኔ ዛሬ ወደ አንተ ተልኬአለሁና የምነግርህን ቃል አስተውል፥ ቀጥ ብለህም ቁም አለኝ። ይህንም ቃል ባለኝ ጊዜ እየተንቀጠቀጥሁ ቆምሁ። እርሱም እንዲህ አለኝ። ዳንኤል ሆይ፥ አትፍራ ልብህ ያስተውል ዘንድ፥ ሰውነትህም በአምላክህ ፊት ይዋረድ ዘንድ ካደረግህበት ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ቃልህ ተሰምቶአል እኔም ስለ ቃልህ መጥቻለሁ። የፋርስ መንግሥት አለቃ ግን ሀያ አንድ ቀን ተቋቋመኝ እነሆም፥ ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ እኔም ከፋርስ ነገሥታት ጋር በዚያ ተውሁት» ዳን 10፤10-13
ነቢዩ ዳንኤል ያከናወነው መንፈሳዊ ተጋድሎ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተወደደ ስሙ ያልተጠቀሰ አንድ መልአክ የተሰጠውን መልእክት ሊነግረው መጥቷል።   መልእክቱ ለዳንኤል ከመድረሱ በፊት የፋርስን መንግሥት የተቆጣጠረው የተቃዋሚ መንፈስ አለቃ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከውን መልአክ 21 ቀን መንገድ ላይ እየተዋጋ አዘግይቶታል። ያንንም የእግዚአብሔር መልአክ ሊያግዘው ቅዱስ ሚካኤል እንደመጣና ውጊያው ከቅዱስ ሚካኤል በዚያ እንደተወውና ወደእርሱ እንደወረደ መልአኩ ለቅዱስ ዳንኤል ሲነግረው እናነባለን።

ከዚህ ምንባብ የምንረዳው ፤
1/ መላእክት የሰዎች መልካም ሥራና ተጋድሎ በእግዚአብሔር ሲወደድ የማናውቀው መልአክ ሊረዳን፤ ሊያግዘን፤ ሊያድነን ከእግዚአብሔር ዘንድ ሊላክ እንደሚችል፤
2/ መላእክቱን ለእገዛና ለረድኤት የሚያመጣቸው የኛ ስራ በመላእክቱ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት በማትረፉ እንዳልሆነ፤
3/ አንድ መልአክ ወደተላከበት ስፍራ ሲሄድ የነበረበትን ሥፍራ እንደሚለቅ፤ በቦታ እንደሚወሰን፤ ባለጋራ ሊዋጋው እንደሚችል፤
4/ መላእክት እንደሚተጋገዙ፤ አንዱ ከአንዱ በኃይልና በሥልጣን እንደሚበልጥ፤
5/ መውጣትና መውረድ እንዳለባቸው፤ በሁሉም ስፍራ እንደማይገኙ ያስረዳናል።
ስለሆነም ቅዱሳን መላእክት ይራዱናል፤ ያግዙናል፤ ያድኑናል ሲባል ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ባላቸው ግንኙነት የተነሳ በተልእኮ ሲመጡልንና ሲደርሱልን ብቻ ነው። ከዚያ ባሻገር ሰዎች ስም እየመረጡ፤ የኃይል ሚዛን እያበላለጡ ስለጠሯቸው የሚመጡ አይደለም።
እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች የሚያስረዱን በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሚላኩ መሆናቸውን ነው።
«የሰማይ አምላክ እግዚአብሔር፥ እርሱ መልአኩን በፊትህ ይሰድዳል» ዘፍ 24፤7  «እግዚአብሔር መልአኩን ከአንተ ጋር ይልካል፥ መንገድህንም ያቀናል»ዘፍ 24፤40  «እግዚአብሔርም መልአኩን አዘዘው፥ ሰይፉንም በአፎቱ ከተተው» 1ኛ ዜና 21፤27  «እግዚአብሔርም ጽኑዓን ኃያላኑንና መሳፍንቱን አለቆቹንም ከአሦር ንጉሥ ሰፈር እንዲያጠፋ መልአኩን ሰደደ» 2ኛ  ዜና 32፤21  «መልአኩን የላከ፥ ከአምላካቸውም በቀር ማንም አምላክ እንዳያመልኩ» ዳን 3፤28  «አምላኬ መልአኩን ልኮ የአንበሶችን አፍ ዘጋ» ዳን 6፤22
አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የማልኮስን ጆሮ ለቆረጠው ጴጥሮስ እንዲህ ብሎት ነበር። «
«ወይስ አባቴን እንድለምን እርሱም አሁን ከአሥራ ሁለት ጭፍሮች የሚበዙ መላእክት እንዲሰድልኝ የማይቻል ይመስልሃልን?» ማቴ 26፤53
 ለኢየሱስ በስቅለቱ ሰሞን የመያዝ፤ የመገፋት፤ የመንገላታት የመገረፍ መከራ ሁሉ ከአብ ዘንድ ትእዛዝ ሳይወጣ የሚያግዙት መላእክት አይመጡም ነበር። ፈቃዱን ሳይሆን የአብን ፈቃድ ለመፈጸም የመጣውም ይህንን ሁሉ ሊቀበል ነውና። ከዚህ ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት የምንረዳው እውነታ ቅዱሳን መላእክቱ ከአብ ትእዛዝ ሳይሰጣቸው የትም መሄድ የማይችሉት ወልድ የመጣው የአብን ፈቃድ ሊፈጽም ስለሆነ ነው። ተገቢ ለሆነው የሰዎች ልመናና ጸሎት የሚያስፈልገውን የሚያደርገው ሁሉን አዋቂ በሆነው በእግዚአብሔር ትእዛዝ ሲላኩ ብቻ ነው።
የሰዎች ድርሻ ወደእግዚአብሔር መጮኽና መለመን ሲሆን ምላሹን ደግሞ የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው። «መላእክቱን በስማቸው ስንለምንና ስንማጸናቸው ይሆንልናል፤ ይደረግልናል»የሚሉ ሰዎች ቆንጽለው የሚያቀርቧት የመዝሙር 34፤7 ጥቅስ «የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል» የሚለውን ነጥለው በማውጣት ቢሆንም የዚህ አጋዥ መከራከሪያ ጥቅስ ሙሉ ማስረጃ ግን ከላይ ከፍ ባለው ቁጥርና ከታችም ዝቅ ብሎ በተጻፈው የምንረዳው፤ እግዚአብሔር ላይ ብቻ እንድንታመን የሚያደርጉ ናቸው። ሙሉ ጥቅሱ ይህንን ይመስላል።
«ይህ ችግረኛ ጮኸ፥ እግዚአብሔርም ሰማው፥ ከመከራውም ሁሉ አዳነው።
የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።
እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው።
የሚፈሩት አንዳችን አያጡምና ቅዱሳኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፍሩት» መዝ 34፤ 6-9

ነቢዩ ዳዊት በደረሰው ችግር ወደእግዚአብሔር ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤ ከመከራውም አዳነው። የእግዚአብሔርም መልአክ እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ በታዘዘም ጊዜ ያድናል። ምክንያቱም በእግዚአብሔር የሚታመኑና እሱንም የሚፈሩት አንዳች አያጡምና። ቁጥር 8 እና 9  በእግዚአብሔር መታመንና መፍራትን ገንዘብ ያደረጉ ሁሉ ምላሽ እንደሚያገኙ ያስረዳናልና።

«ቅዱሳን መላእክቱ በዚህ ምድር እየዞሩ ለሰዎች የሚራዱና የሚያግዙ በመሆናቸው በስማቸው የሚደረገውን የሰዎችን ልመናና ጸሎትም ይሰማሉ» የሚል ክርክር የሚያነሱ ሰዎች መላእክቱ በቀጥታ ታዘው ያደረጉትን መነሻ በማድረግና በማድነቅ እንጂ ቅዱሳኑ መላእክት ራሳቸው ምሥጋናንና ውዳሴን ተገቢያቸው እንደሆነ ሽተው እግዚአብሔርን ከሚያውቁ ሰዎች ሲቀበሉ አናይም። እንዲያውም በራእይ መጽሐፍ ላይ እንደምናነበው ቅዱስ ዮሐንስ፤ እግዚአብሔር በመልአኩ በኩል ስላደረገለት፤ ስለነገረውና ስላሳየው ነገር ሁሉ በፊቱ ወድቆ በሰገደ ጊዜ የተሰጠው ማስጠንቀቂያ እንዲህ የሚል ነበር።

«ልሰግድለትም በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እርሱም፦ እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና አለኝ»       ራእ 19፤10
ዛሬ ግን ሰዎች «ለእግዚአብሔር ስገድ» የሚለውን የመልአኩን የማስጠንቀቂያ መልእክት ወደጎን ትተው «ለመልአኩም ስገድ» እያሉ ሲሰብኩ ይገኛሉ። መልእክት አድራሹ መልአክ ከዮሐንስ በተሻለ ስለመልእክቱ ምንነት እውቀት እንዳለው እርግጥ ነው። ከዐውደ ንባቡ እንደምንገነዘበውም ስለመልአኩ ቢያንስ ሁለት ዐበይት ነገሮችን እንረዳለን። አንድ፤ መልእክቱን በቀጥታ ከእግዚአብሔር እየሰማ ለዮሐንስ የሚያደርስ መሆኑን። ሁለትም፤ መልአክቱ ከዮሐንስ ዘንድ ከመድረሱ በፊት በመልአኩ ዘንድ የተሰማና የታወቀ መሆኑን ነው። ስለሆነም ዮሐንስ ስግደትን ለመልአኩ መስጠት የፈለገው መልአኩ የፈጣሪ የቅርብ ባለሟል በመሆኑና የሚያየውን ግርማ በመፍራት እንዲሁም ይዞለት የሚመጣው መልእክቶቹ እጅግ ከባድና ከዚህ በፊት በሕይወቱ ሰምቶአቸው የማያውቅ ከባድ የሕይወት ልምምድን የሚያሳዩ በመሆናቸው የተነሳ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል።
ስለዚህ «ተጠንቀቅ» ያለውን ቃል መጠበቅ ብልህነት ነው።
ክፍል ሦስት ይቀጥላል …..

Saturday, September 5, 2015

ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው !!


ከዚህ በፊት ስለተከስተ ጌትነት የአሜሪካው አማርኛ ድምጽ አየር ላይ ካዋለው መረጃ ተነስተን ዐመጻውን በንስሐ እንዲተው የሚያሳስብ ዘገባ አውጥተን ነበር። በንስሐ ስለመመለሱ እየተናገረ ባለበት ሁኔታ የባለቤቱን ጽናትና ያላትን የይቅርታ ልብ ተመልክተን ወደፍቺና የግድያ ተግባር ላለመሄድ የተጓዘችበትን የክርስትና አርአያነት «አሌክስ አብርሃም» የዘገበውን ልናስነብባችሁ ወደድን።
 


ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው !!
 (አሌክስ አብርሃም )

ይቅርታ መቸም እንደሚወራው ቀላል ነገር አይደለም !! በተለይም በባልና በሚስት ማሃል በአንድኛው ወገን ለትዳር አለመታመን ሲከሰት የተበደለው አጋር ይቅር ለማለት ይቸገራል …እንዲህ አይነቱ ነገር ሲከሰት ሚስት ባሏን በመፍለጫ …በተኛበት አቅምሳው እጇን ለመንግስት የሰጠችበት ዜና ሰምተናል ….ባልም በገጀራ ሚስቱን አመሳቅሎ ዘብጥያ የወረደባቸውን በርካታ ዜናዎች በቲቪ ተመልክተን አማትበናል ! የራሱ ጉዳይ ያሉም ትዳራቸውን በትነዋል !
ይህን ነገረ ካለነገር አላነሳሁትም …. በዚያ ሰሞን ከወደአሜሪካ የሰማነው ዜና የሚታወስ ነው …..ዘማሪ ተከስተ ጌትነት ሚስቴን አማግጦብኛል ያለ አንድ ሰው በየሚዲያዎቹ ቀርቦ ፍረዱኝ ሲል ሁላችንም ሰምተን ጉድ ጉድ ብለናል ! ማገጠች የተባለችውም ሴት በየሚዲያው እንዴት ካንድ አይሉ ሁለት ሶስት ጊዜ ወዳረፈበት ክፍል ጎራ እያለች ‹‹ሳትፈልግ ›› አብረው እንደተኙ በዝርዝር መግለፅዋ ይታወሳል ….ፓስተር ተከስተ ጌትነትም ይህንኑ አምኖ ይቅርታ መጠየቁ እንደዛው ..ሚዲያውም እስኪበቃው አናፍሶታል !ዘማሪ /ፓስተር ተከስተ በሚያገለግልበት ቤተክርስቲያንም አገልግሎቱን እንዳቆመ ተዘግቦ ነበር !!
ታዲያ ያኔ አገር ይያዝ ያለው ሚዲያ ለዚችኛዋ ዜና ጭጭ ማለቱ ስለገረመኝ …ያው ችግሩን ካወራን መጨረሻውስ ምን ሆነ የሚለውን ዝም ማለቱ ተገቢ አይደለም በሚል ይችን ፅሁፍ እነሆ አልኩ ……. ትላንት ‹‹የእውነት ቃል ጎስፕል ሚዲያ›› ‹‹የእንደገና አምላክ›› በሚል ርእስ እንደዘገበው ከሆነ ዘማሪ ጌትነት ባለፈው ቅዳሜ በምእመኑ ፊት ቁሞ ስለሁኔታው ምስክርነቱን ሰጥቷል … ባለቤቱ የምስራችም የሆነውን ሁሉ ይቅር እንዳለች በሚገልፅ አጭር ቃል እንዲህ ብላለች ‹‹ ባለቤቴን አፈቅረዋለሁ ትዳራችንም ፅኑ ነው ›› ፓስተር ጌትነትም ወደአገልግሎቱ ተመልሷል !! መቸስ ይቅርታ ጥሩ ነው … መልካም የትዳርና የአገልግሎት ጊዜ ይሁን እያልኩ ….ምንም እንኳን የመጀመሪያ ተጎጅዋ እርሷ ብትሆንም እንዲህ በችግር ጊዜ የራሷን ብሶት ትታ ከባሏ ጎን የምትቆም ሚስት ማግኘት መታደል ነው የሚል የግል አስተያየቴን ጨምሬ ላብቃ !!