Saturday, August 30, 2014

ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ ምን ይመስላል?




(ክፍል አንድ)

በዓለማችን ላይ ባሉ በኦርቶዶክሳዊያንና በካቶሊካዊያን  ቤተ እምነቶች ውስጥ  ከሰማያውያን ፍጥረቶች ውስጥ መላእክት በእምነት ህግጋቶቻቸው ከፍተኛውን ስፍራ ይዘው ይገኛሉ።  እንደጥንታውያኑ ቤተ እምነቶች አይሁን እንጂ በወንጌላውያን ቤተ እምነቶችም ውስጥ ከተወሰኑቱ በስተቀር ስለመላእክት ያላቸው እምነትና እውቀት ጥቂት አይደለም።   የሰው ልጆች ስለቅዱሳን መላእክት ያለን እውቀት ከፍ እንዲልና ትኩረት እንድንሰጥ የሚያደርገን ምክንያት መኖሩ እርግጥ ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችንም ስለመላእክት ምንነትና ተግባር  በብዙ ቦታ ላይ ጠቅሶ የሚገኘው ያለምክንያት ባለመሆኑ በዚያ መነሻነት ስለመላእክት ያለን ግምት ከፍ ቢል የሚያስደንቅ አይሆንም። እግዚአብሔር በቅዱስ ቃሉ ውስጥ ይህንን ዓይነት መልእክት ማስቀመጡም ስለመላእክት ያለን ግንዛቤ እንዲያድግ ስለፈለገ በመሆኑ ዘወትር ቃሉን በማንበብ እንመረመራለን። መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን መገለጥም ስለመላእክት ያለን እውቀት ከፍ ይላል። ምክንያቱም በሰው ልጆችና በመላእክት መካከል ያለው ግንኙነት እጅግ የጠበቀ በመሆኑ ስለመላእክት ማወቁ እጅግ ጠቃሚ ነው።
      በተመሳሳይ መልኩም ስለመላእክት ያለን እምነትና በቅዱስ ቃሉ ላይ ያልተመሠረተ እውቀት እንደዚሁ የሚኖረንን ግንኙነት ከማበላሸቱም በላይ የሰው ልጆችንም ይሁን መላእክትን በፈጠረው በእግዚአብሔር ላይ ያለንን የአምልኰ መንገድ ከመስመሩ ሊያወጣ ስለሚችል እጅግ ብርቱ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ነገር መሆኑም ሊሰመርበት ይገባል። የአምልኰ ስህተት እንደጊዜያዊ እክል የማይታይና በቀላሉ ሊታረም እንደሚችል የሚታሰብ ባለመሆኑ ስህተቱ ዘላለማዊነት ባላት በነፍስ ላይ ዘላለማዊ ዋጋን የሚያስከፍል ጉዳይ ስለሆነ እጅግ ብርቱ ጥንቃቄ ሊደረግበት ይገባል። 
  ስለሆነም  የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት ባደረገ መልኩ ስለመላእክት ያለን እውቀት መልካም የመሆኑን ያህል ቃሉን በሳተ መንገድ ያለን እውቀትም በተቃራኒው የጎደለ ከሆነ ጎጂነቱ የከፋ መሆኑን ለማስገንዘብ እንዲቻል በተለያየ አቅጣጫ ስለመላእክት የሚሰጠውን ትርጉምና የእምነት አስተምህሮን በተመለከተ ቅዱስ መጽሐፍን ዋቢ በማድረግ ለማሳየት እንሞክራለን።

1/ ስለመላእክት ማወቅ ለምን አስፈለገ?

እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ያስተምረናል።  የቃሉ ምንጭ በሆነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለመላእክት እግዚአብሔር በብዙ ቦታ ተናግሯል፤ ተግባራቸውንም በተወሰነ መልኩ አሳይቶናል። እግዚአብሔር በቃሉ የሚነግረን ለእኛ እንዲበጀን ስለሆነ ስለመላእክት እንድናውቅለት ይፈልጋል ማለት ነው። በመሆኑም ስለመላእክት ማወቅ ያስፈለገን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ስለመላእክት እንድናውቅ ስለነገረን  ነው። ስለመላእክት ማንነትና ተግባር የነገረንን ካወቅን እግዚአብሔር ለምን እንደፈጠራቸው እንረዳለን። በዚህም የተነሳ ስህተት ላይ ከመውደቅ እንጠበቃለን። ስለመላእክት ነግሮን ሳለ በእኛ ስህተት የተነሳ ከእውቀት ብንጎድል እግዚአብሔር ስላልነገረን ሳይሆን ቃሉን ለመስማት ካለመፈለጋችን የተነሳ ይሆናል ማለት ነው። ማንም ስህተትን ቢያደርግ በተሰጠው ቃል መሠረት ተጠያቂነት አለበት። ስለሆነም ከተጠያቂነት ለመዳን ስለመላእክት ማንነት ማወቅ ያስፈልገናል። ችግሩ ስለመላእክት ያለን ስህተት የሚነሳው እግዚአብሔር በቃሉ ከተናገረው ውጪ የራሳችንን ግምትና ስሜት ስንጨምርበት ነው። ስለዚህ በዚህ ጽሁፍ የሚዳሰሰው ክርስቲያኖች ሁሉ በእጃቸው የያዙትን መጽሐፍ ቅዱስ ዋቢ በማድረግ ነው። ሌላ የትኞቹም ስለመላእክት የተጻፉ አስረጂዎች መነሻቸው ወይም መለኪያቸው ቅዱሱ መጽሐፍ ከሆነ ስለመላእክት የሚኖረው እውቀት ያልተዛነፈ ይሆናል።
«ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል አንተም እውቀትን ጠልተሃልና» ሆሴዕ 4፤6 እንዳለው እንዳንጠፋ ስለመላእክት ማንነትና ምንነት ማወቅ አለብን።

2/ የመላእክት ተፈጥሮ

የመላእክትን ተፈጥሮ በተመለከተ በመጽሐፍ ቅዱስ  ሰፊ የሆነ ማብራሪያ አይሰጠንም።    ያ ማለት ግን ስለመላእክት ተፈጥሮ ለአማኞች የሚበቃ ትምህርት የለውም ማለት አይደለም። በመሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ የዘመን መነሻና ፍጻሜ ከሌለው ከእግዚአብሔር እውቀት ውስጥ ለሰው ልጅ በሚመጥነው መልኩ የተሰጠው ቃል በመሆኑ ብዙ ማብራሪያ መስጠት አይጠበቅበትም። በዮሐንስ ወንጌል ላይ መጽሐፍ ቅዱስ ዓለም ራሷ ሰሌዳ፤ ውቅያኖሶች ሁሉ የብርዕ ቀለም ቢሆኑ መያዝ እንደማይችሉ ያስረዳናል።
ዮሐ 21፥25 «ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል»
ስለዚህ የመላእክትን ማንነትና ተፈጥሮ ለማወቅ መጽሐፍ ቅዱስ የነገረንን ይዘን እየተማርን፤ ያልነገረንን ደግሞ በእምነት እንደተነገረን ያህል ተቀብለን እንጓዛለን እንጂ ያልተነገረውን ለመናገር የግድ የራሳችንን ስሜቶችና ፍላጎቶች በመናገር በማንወጣው አዘቅት ውስጥ ገብተን አንዳክርም። «ለጠቢብሰ አሐቲ ቃል ትበቍዖ» እንዲሉ።
 ስለዚህ መላእክት በቁጥር ስንት ናቸው? አፈጣጠራቸው እንዴት ነው?  ሥልጣናቸው?  ስማቸው? ወዘተ የተመለከተውን ነጥብ ከተወሰኑት በስተቀር  መጽሐፍ ቅዱስ ዝም ስላለ እኛም ዝም እንላለን እንጂ  መጽሐፍ ቅዱስ ያልጠራቸውን በጕስአተ ልብ አንጠራቸውም።  ይልቅስ መጽሐፍ ቅዱስ የነገረንን መረጃ እንመልከት። በመዝሙረ ዳዊት ላይና በዕብራውያን መልእክት ላይ የተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ስለመላእክት ተፈጥሮ  ያስተምረናል።
መዝ 104፥4  «መላእክቱን መንፈስ የሚያደርግ፥ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል»
 ዕብ 1፥7 «ስለ መላእክትም። መላእክቱን መናፍስት አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል የሚያደርግ» ይላል።
ከዚህ የእግዚአብሔር ቃል ተነስተን መላእክቱ መንፈስና የእሳት ነበልባል መሆናቸውን እንረዳለን።  መናፍስትም፤ የእሳት ነበልባልም ያደረጋቸው እግዚአብሔር ነው። እነዚህ መንፈሳውያንና እሳታውን መላእክት ከፍጥረታት መካከል አንዱ ክፍል ናቸው ማለት ነው። መላእክቱ መናፍስት (ረቂቃን) እና እሳታውያን  መሆናቸው የሚያሳየን ነገር ቢኖር እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በፈጠረበት መንገድ አልፈጠራቸውም ማለት ነው። መንፈስም፤ እሳትም በመሆናቸው  መላእክት እንደሥጋውያን  እርጅናና ሞት አያገኛቸውም።
ኢዮብ 34፥15 «ሥጋ ለባሽ ሁሉ በአንድነት ይጠፋል፥ ሰውም ወደ አፈር ይመለሳል» እንዳለው።
በሌላ ቦታም  መላእክት ሕያው መንፈሳዊ ፍጥረታት መሆናቸውን ቅዱስ ቃሉ ሲነግረን፤ ሥጋውያን የሆንን  እኛ ትንሣዔ ሙታን እንደማይመለከታቸው እንደመላእክት እንደምንሆን ተነግሮናል።
ማር 12፥25  «ከሙታንስ ሲነሡ በሰማያት እንዳሉ መላእክት ይሆናሉ እንጂ አያገቡም፥ አይጋቡምም»
    ስለመላእክት አፈጣጠር የሚናገር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ  በተለምዶ «አክሲማሮስ» ወይም  በመጠሪያው «ሔክሳሄሜሮስ» የተባለ መጽሐፍ አለ። በስድስት ቀን ውስጥ እግዚአብሔር ስለፈጠራቸው ሃያ ሁለቱ ስነፍጥረታት አመጣጥ የተነገረበት ይህ መጽሐፍ በዘፍጥረት መጽሐፍ ላይ ያልተነገረውን  በዝርዝር ይተርካል።  በጽርዕ ቋንቋ «ሔክሳ» ማለት «ስድስት» ማለት ሲሆን «ሄሜር» ማለት «ቀን» ማለት ነው። ይህም የስድስቱ ቀናት ሥነ ፍጥረትን ለማመልከት የገባ ቃል ነው።  ሔክሳ ሄሜሮስን የበረሺት መጽሐፍ ባለቤቶች የሆኑቱ  ዕብራውያን የማያውቁትን ይህን ከ4ኛው ክ/ዘመን በኋላ የተጻፈውንና ስለሥነ ፍጥረት የሚናገረውን መጽሐፍ መጠቀም ሳያስፈልግ እግዚአብሔር በቅዱስ ቃሉ በገለጠው በመጽሐፍ ቅዱስ  ብቻ መላእክት ሞት የማያገኛቸው፤ እሳታውያንና መንፈሳውያን ፍጥረቶች ናቸው ብሎ አፈጣጠራቸውን በአጭር ቃል መግለጽ ይቻላል።

3/ የመላእክት ጠባይና ግብር

ከላይ ባነሳናቸው ርእሶች ላይ ስለመላእክት ማወቅ የሚገባንን ምክንያትና የመላእክትን ተፈጥሮ ከተረዳን ዘንዳ በቀጣይነት ሥራቸውን ልናውቅ ይገባል። ይህም ማንነታቸውንና ከሰው ልጆች ጋር ያላቸው ግንኙነት ምን እንደሆነ እንድናውቅ ያግዘናል። በዚህ መጠይቃዊ ርእስ ስር የሚካተቱ ንዑስ ርእሶች አሉን።

        ሀ/ የመልአክ ስማዊ ትርጉም 

ቁጥራቸውን ብዙ መሆኑን ለማመልከት «መላእክት» የምንላቸው ፍጥረቶች በነጠላ  ስያሜ «መልአክ» ስንል ምን ማለታችን ነው? የሚለውን መረዳት ይገባናል። ይህም የመላእክትን ሥራ ለማወቅ ይጠቅመናል። ሥራቸውን ካወቅን መላእክት ከእኛ ጋር እኛም ከመላእክቱ ጋር ያለንን ግንኙነት ለመለየት ያግዘናል። ያለበለዚያ ከላይ ስናነሳ የቆየንባቸው የማወቅ እድላችን እርስ በእርሱ ይምታታና ባለማወቅ ውስጥ ሆነን የምናውቅ ሊመስለን ይችላል። ይህም ትልቅ ጉዳት ያስከትላል።
 አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ (በማኅበረ ቅዱሳን ተሃድሶ ተብለዋል) «መጽሐፈ፡ሰዋስው፡ወግስ፡ወመዝገበ፡ቃላት፡ሐዲስ» በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 549 ላይ እንዲህ ሲሉ  ስለ«መልአክ» ግሳዊ ትንታኔን  አትተዋል።
ድርጊቱን ሲገልጡልን «ልኢክ፤ ልኢኮት(ለአከ፤ይልእክ) መላክ፤መስደድ»  ማለት  እንደሆነ በመግለጽ አድራጊውን ሲነግሩን «ለአኪ ማለት ላኪ ወይም ሰዳጅ ማለት ነው ይሉናል። ተደራጊውን ደግሞ «መልአክ ማለት በቁሙ ሹመኛ፣ አለቃ ሲሆን  የእግዚአብሔር መላእክቶችን  ነጠላ የወል ስም  «መልአክ» የሚለው እንደሚወክል ያብራሩልናል።
በሌላ ቦታም የሰባ ሊቃናት ትርጉም እንደሚያስረዳን «ἄγγελος» የሚለው የልሳነ ጽርዕ ትርጉም «ኤንጄሎስ» ማለት «መልእክተኛ» ማለት እንደሆነ እናገኛለን። ዕብራይስጡም «מלאך אלהים » «ሜሌኽ ኤልሂም» ይለዋል። የእግዚአብሔር መልዕክተኛ ማለት ነው።
 ከዚህ የትርጉም  ጽንሰ ሃሳብ የምንረዳው መላእክት ማለት የሚላኩ፣ የሚታዘዙ ፍጥረታት ሲሆኑ ላኪያቸው ወይም ሰዳጃቸው የፈጠራቸው እግዚአብሔር ነው ማለት ነው።  ስለዚህ መልአክ ማለት የሚላክ፤ የሚታዘዝ፤ ተላኪ፤ አገልጋይ፤ አመስጋኝ ማለት ነው።  የአለቃ ኪዳነ ወልድ ትርጉም ከጽርዑና ከዕብራይስጡ ጋር ይስማማል። 

     ለ/ መላእክት በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?

መላእክት ፍጡራን ናቸው ካልን ከፍጡርነት ባህርይ አንጻር ውሱንነት መኖሩ እርግጥ ነው። በዚያ ላይ የሚላኩ፤ የሚታዘዙ፤ አገልጋዮች መሆናቸው በራሱ መነሻና መድረሻ እንዳላቸው ያሳያል። መልእክት ከሚቀበሉበት መንበረ ጸባዖት ተነስተው ከሚደርሱበት የተልእኰ ሥፍራ ድረስ መውጣትና መውረድ አለባቸው ማለት ነው።  መላእክት የሚወጡበትና የሚወርዱበት መሰላል የእግዚአብሔር ኃይል እንደመሆኑ መጠን መላእክቱን የፈጠረ አምላክ እንዲህ ሲል ይነግረናል።
ዮሐ1፥52  «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ አለው»
በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃት ስለሌላቸው የመውጣትና የመውረድ አገልግሎት ይፈጽማሉ ማለት ነው። መላእክቱ ከታዘዙበት ሲወጡ ከነበሩበት ሥፍራ  ለቀው ወደሌላ ሥፍራ ይሄዳሉ። ስለዚህ  ለቀው ከወጡ በኋላ በምስጋና ከተማቸው ውስጥ በመልአካዊ ባህርያቸው አይገኙም ማለት ነው። ከተልእኮአቸውም ሲመለሱ ከፈጸሙበት ሥፍራ ወደቀድሞ ቦታቸው ይመለሳሉ እንጂ በምስጋና ከተማቸውም ሆነ በተልእኰ ስፍራቸው በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃት የላቸውም። ይህንን በደንብ የሚገልጽን የትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ነው።
አንድ ስሙ ያልተገለጸ የእግዚአብሔር መልአክ በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ ሳለ ወደነብዩ ዳንኤል በተላከ ጊዜ የፋርስ መንግሥት አለቃ (የፋርስ መንግሥትን የያዘ ተቃዋሚ መንፈስ ማለት ነው) ከተላከው መልአክ ጋር ለ21 ቀናት በመዋጋት ከዳንኤል ዘንድ ቶሎ እንዳይደርስ አግዶት ነበር። በኋላም ቅዱስ ሚካኤል ሊረዳው ከመጣ በኋላ ከሌሎች የፋርስ መንግሥታት መናፍስት ጋር ሚካኤልን በዚያ ትቶት ወደተልእኰ ሥፍራው ወደ ነብዩ ዳንኤል መሄዱን ይነግረናል።
ዳን 10፤12-14  «እርሱም እንዲህ አለኝ። ዳንኤል ሆይ፥ አትፍራ ልብህ ያስተውል ዘንድ፥ ሰውነትህም በአምላክህ ፊት ይዋረድ ዘንድ ካደረግህበት ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ቃልህ ተሰምቶአል እኔም ስለ ቃልህ መጥቻለሁ። የፋርስ መንግሥት አለቃ ግን ሀያ አንድ ቀን ተቋቋመኝ እነሆም፥ ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ እኔም ከፋርስ ነገሥታት ጋር በዚያ ተውሁት። ራእዩም ገና ለብዙ ዘመን ነውና በኋለኛው ዘመን ለሕዝብህ የሚሆነውን አስታውቅህ ዘንድ አሁን መጥቻለሁ»
 (የፋርስ መንግሥት አለቃ ማለቱ በፋርስ መንግሥት ላይ አድሮ ዳንኤልንና ወገኖቹን የሚዋጋው መንፈስ አለቃ ማለት ነው) የዚህን እንዴትነት ወረድ ብለን በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ እንመለከታለን።
ነገር ግን ከላይኛው ጥቅስ ውስጥ የምንረዳው ቁም ነገር፤
የተላከው መልአክ ለ21 ቀናት በውጊያ ላይ በመዘግየቱ ወደተላከበት ሥፍራ ለመድረስ አለመቻሉ፤
 * ሚካኤል ለእርዳታ ከመጣለት በኋላ ወደዳንኤል ከመሄዱ በስተቀር  ከሚካኤል ጋር በውጊያውም እየተሳተፈ፤ ወደዳንኤልም መልእክት እያደረሰ ባንድ ጊዜ በሁለቱም ሥፍራ አለመገኘቱ የመላእክትን ውሱንነት ይገልጥልናል።
«ሚካኤልን በዚያ ተውኩት» ማለቱ የነበረበትን ሥፍራ ለቆ መሄዱን ይገልጣል። ስለዚህ መላእክት በሁሉም ሥፍራ አይገኙም። መእክተኛ እንደመሆናቸውም መጠን ሳይላኩ አይሄዱም።  በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት /Omnipotent/ የእግዚአብሔር የብቻው ባህርይ ነው።
መላእክት የእግዚአብሔር ፍጥረት እንደመሆናቸው መጠን ሁሉን የማወቅ ሥልጣን አልተሰጣቸውም፤ በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃትም የላቸውም። በፈጣሪያቸው ሲላኩ ወይም ሲታዘዙ ለአገልግሎት የሚሄዱት እግዚአብሔር ብቻ ስለሚያውቀው ሃሳብና ዓላማ ብቻ በመሆኑ ነው።  የእግዚአብሔርነት ሙላት በሆነው ባህርይ መሠረት ሁሉን የመስማት፤ ሁሉን የማየት፤ ሁሉን የማወቅ ብቃት የላቸውም።  ይልቁንም መላእክቱን በነዚህ ሦስት ጥቅሶች ምስጋናን፤ ተአዝዞንና ተልአኪነትን ሲፈጽሙ እናያለን።
v  መዝ 148፤2  «መላእክቱ ሁሉ፥ አመስግኑት ሠራዊቱ ሁሉ፥ አመስግኑት»
v  መዝ 91፥11 «በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋል»
v  ማቴ 13፥41  «የሰው ልጅ መላእክቱን ይልካል፥ ከመንግሥቱም እንቅፋትን ሁሉ ዓመፃንም የሚያደርጉትን ይለቅማሉ»

    ሐ/ የመላእክት ሥልጣንና ተልእኰ

መላእክት ተፈጥሮአቸው አንድ ዓይነት ቢሆንም በክብርና በሥልጣን ልዩነት እንዳላቸው  ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። ስለዚህ በክብር፤ በሥልጣንና በአገልግሎት የተለያዩ እንደመሆናቸው መጠን የመላእክቱ ተልዕኰና ሥልጣንም የተለያየ ነው። ለምሳሌ ቅዱስ ሚካኤል የመላእክት አለቃ እንደሆነ በይሁዳ መልእክት (ምዕ 1፤ቁጥር9) ላይ ሚካኤል ከዲያብሎስ ጋር ስለመከራከሩ በተጠቀሰበት አንቀጽ ላይ «የመላእክት አለቃ» ተብሎ ሥልጣኑ ተጠቅሷል።
 በሌላ መልኩም  ምንም እንኳን ስሙ በትክክል ባይገለጽም ለእግዚአብሔር በማይታዘዙ፤ በበደልና በኃጢአት ሙት በሆኑ በዚህ ዓለም ልጆች ላይ ለሚሠራው መንፈስ አለቃ የሆነ በአየር ላይ ሥልጣን የተሰጠው አለቃ እንዳለም ቅዱስ ወንጌል ይነግረናል።   ( ኤፌ 2፤1-2 ) በሌላ ቦታ «ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፤ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና»  1ኛ ዮሐ 3፤8  ስለሚል በስም የተጠራውና በኃጢአት ላይ የሰለጠነው ይህ አለቃ ዲያብሎስ ነው ማለት ነው።
ከዚህ ቃል ተነስተን መላእክትን ሥልጣንና ተግባራቸውን በመመልከት የሚያመሰግኑ፤ የሚላኩትንና የሚታዘዙትን «ቅዱሳን» መላእክት ስንል፤  ለእግዚአብሔር በማይታዘዙ ላይ የሰለጠኑትና በኃጢአት ላይ ሥልጣን ያላቸውን ደግሞ «ርኩሳን» ብለን ልንከፍላቸው እንችላለን። ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝበትን አገልግሎት የሚፈጽሙ ሲሆኑ ርኩሳኑ መላእክት ደግሞ በጥፋት ላይ የተሰማሩ ናቸው ማለት ነው።
 ንስሐ በሚገባ አንድ ኃጢአተኛ የተነሳ በሰማይ ባሉ መላእክት ዘንድ ደስታ እንደሚሆነው ሁሉ ( «እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት ደስታ ይሆናል» ሉቃ 15፤10 )
 እንደዚሁ ሁሉ ኃጢአተኛ ሲቀጣ ለተልዕኰው የሚወጡ ክፉዎች መላእክት ስለመኖራቸውም («የመዓቱን መቅሠፍት በላያቸው ሰደደ መቅሠፍትን መዓትንም መከራንም በክፉዎች መላእክት ሰደደ » መዝ 78፤49  ) ሲል ክፉዎች መላእክት መኖራቸውን እንረዳለን።
ስለዚህ በሰው ልጆች ወደእግዚአብሔር መመለስ የሚደሰቱ  ቅዱሳን መላእክት እንዳሉ ሁሉ መቅሰፍትን፤ መዓትንና መከራን የሚያመጡ ክፉዎች መላእክትም አሉ ማለት ነው። ከዚህ ተነስተን መላእክትን በሁለት ልንከፍል እንችላለን።

   መ/ ቅዱሳን መላእክትና ክፉዎች መላእክት 

« ንቁም በበኅላዌነ እስከ ንረክቦ ለአምላክነ» በማለት ያረጋጋው ገብርኤል ነው፤ የካደውና እኔ ፈጣሪ ነኝ ብሎ የታበየው ሣጥናኤል ነው የሚል አስተምህሮ አለ።  በሌላ ጊዜም ይህ ገብርኤል መልአክ የወረወረው ሰይፍ እስከምጽአት ድረስ ወደመሬት ውስጥ እየተምዘገዘገ እየወረደ ነው የሚልም ትምህርት ይሰማል። ገብርኤል «ንቍም በበኅላዌነ» ማለቱን በወቅቱ የሰማና ጽፎ ያቆየልን የለም። መጽሐፍ ቅዱሳችንም ይህን ስለማለቱ አልገለጸውም። ስለዚህ እግዚአብሔር በፈቃዱ ሳይነግረን ወደተወው ጉዳይ ገብተን አንዳክርም። ነገር ግን በክፋትና በኃጢአት ላይ የሰለጠነው ዲያብሎስ በትዕቢት ከማዕርጉ መውረዱን መጽሐፍ ስለሚነግረን ያንን በመቀበል «አለቃ» እንደመባሉ መጠን በአለቅነቱ አብረውት የተሰለፉ ሠራዊት መኖራቸውንም እንገነዘባለን  
   ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ቅዱሳን መላእክት የእግዚአብሔርን ፈቃድና ደስ የሚያሰኘውን አገልግሎት ፈጻሚዎች ሲሆኑ ክፉዎቹ መላእክት ደግሞ የጥፋትና የዐመጻ ኃይሎች ናቸው። ቅዱሳኑ መላእክት ቅዱሳን ያሰኛቸው ዋናው ምክንያት እግዚአብሔርን በመፍራት የሚያገለግሉ፤ ፈቃዱንም ለመፈጸም ፈቃደኞች የሆኑ፤ በተቀመጡበትን ሥፍራ በአምልኰ ጸንተው የተገኙ ናቸው። ክፉዎቹ መላእክት ደግሞ በእግዚአብሔር ሥልጣን ሥር ቢሆኑም ከእግዚአብሔር ፈቃድ ያፈነገጡ፤ የተቀመጡበትን ሥፍራ ትተው የወጡ የጥፋት ኃይሎች ናቸው።
ይሁዳ 1፤6 «መኖሪያቸውንም የተዉትን እንጂ የራሳቸውን አለቅነት ያልጠበቁትን መላእክት በዘላለም እስራት ከጨለማ በታች እስከ ታላቁ ቀን ፍርድ ድረስ ጠብቆአቸዋል»
በቅዱሳኑ መላእክት ላይ የአለቅነት ሥልጣን ያለው ቅዱስ ሚካኤል ነው።
ራእይ12፥7 «በሰማይም ሰልፍ ሆነ፤ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ። ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ፥ አልቻላቸውምም»
ዳን 12፥1 «በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል ሕዝብም ከሆነ ጀምሮ እስከዚያ ዘመን ድረስ እንደ እርሱ ያለ ያልሆነ የመከራ ዘመን ይሆናል በዚያም ዘመን በመጽሐፉ ተጽፎ የተገኘው ሕዝብህ ሁሉ እያንዳንዱ ይድናል»
በክፉ መናፍስት ላይ ሥልጣን ያለው ደግሞ ሰይጣን (ተቃዋሚ)፤  እባብ (ጠላት)፤ ዲያብሎስ (ከሳሽ) የተባለው ዓለሙን ሁሉ የሚያስተው ዘንዶ ነው። ( ራእይ 12፤9 )  ከቅዱሳኑ መላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልና ከመላእክቶቹ ጋር ይኼው ዲያብሎስ  ተዋግቶ ተሸንፏል።
ስለዚህም ይህ የተሸነፈው ዲያብሎስ በዚህ ዓለም ላይ ከነሠራዊቱ አሳች ሆኖ ይገኛል። በዚህ ምድር ላይ ለሚፈጸመው ጥፋት፤ ኃጢአትና ዐመጻ ሁሉ ዋናው አስፈጻሚ ይህ ሰይጣን የተባለውና ሠራዊቱ ናቸው።

3/ የቅዱሳን መላእክት አገልግሎት

ይቀጥላል%

Thursday, August 28, 2014

«ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ የተሰወረ ሊሆን አይችልም» አምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ለአፄ ኃ/ሥላሴ በ1957 ዓ/ም ከጻፉት ደብዳቤ







ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ

አዲስ አበባ

ግርማዊ ሆይ፣

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት የሚታየውን ምሬትና ግፍ፣ የፍትሕም መጓደል ምክንያት በማድረግ ወደ አገሬ ለመግባት ያለኝን አሳብ ማቆየት ግድ እንደሆነብኝ ለግርማዊነትዎ መግለጥ አስፈላጊ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ይህ ሁኔታ የሚታረምበትን በኅብረት ለመሥራት ባንሞክር ታላቅ ብጥብጥ እንደሚያስከትልብን ከታሪክ መማር ካልቻልን፣ ከተከታዩ መቅሰፍት የምናመልጥበትና የምንከለልበት ሰው ሠራሽ ዘዴ ይገኝለታል ብሎ ራስን መደለል በሕልም ዓለም ውስጥ ለመኖር እንደ መፈተን ይቆጠራል፡፡
ከዚህም በቀር ለተተኪው ትውልድ አቋም ይሆናሉ ብለን ተከባክበን ልናሳድጋቸው አላፊነት ያለብንን ሕፃናትና ውለታ ትተው ለማለፍ የተደራጁትን ሽማግሎቻችንንም ደህና ዕረፍት እንዳያገኙ ከአገሪቱ በተፈጥሮ ያገኙትን ዕድል መንፈግ ያሰኛል፡፡ በዚህም ምክንያት በፈጸምነው ስህተት ታሪክ ምሕረት ሊያደርግልን በፍጹም አይችልም፡፡
ይህን የመሳሰለው ሁኔታ በብርቱ የሚያሳስበን መሆኑን ስንገልጥ ምንም እንኳ አንዳንድ ሰዎች ‹‹አንተ ምን አገባህ?›› በማለት በጉዳዩ ባለቤትነት ክፍያ ድርሻችንን ለማሳነስ ቢሞክሩም በኢትዮጵያዊነት ትክለኛ መብት ላይ አጥብበው ያሰመሩትን የወሰን ክልል አሜን ብሎ ለመቀበል ከቶ ስለሚያስቸግር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አላፊነቱን የማስወረድ ተግባር እንዳለበት አይካድም፡፡ እኔም ይህን ምክንያት አድርጌ በአሁኑ የመንግሥት አስተዳደር የደረሰውን ሕገ ወጥ አፈጻጸም ሁሉ ለማረምና ፍትሕን ለማደላደል የሚቻልበትን አሳብ በነፃ ለመግለጥ ስል እውጭ አገር መቆየትን መረጥሁ፡፡
በአሁኑ አያያዝ እንዲቀጥል የተተወ እንደሆነ በኢትዮጵያ የወገን መለያየትና የደም መፍሰስ እንደሚያሠጋ የመላው ኢትዮጵያውያን ግምት የወደቀበት ነው፡፡ ዋናው አላማ ይህ እልቂት የሚወገድበት መድኃኒቱ ምንድነው? ለተባለው ጥያቄ ለመመለስ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ መቸም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በሚመስለውና በሚያምንበት ረገድ መልሱን ለመስጠት ሞክሯል፡፡ አሁን የጐደለ መስሎ የሚታየው ከዙፋኑ በኩል የሚጠበቀው ይሁንታ ብቻ ነው፡፡ ነገሩን በመጠኑ ለማብራራት ያህል በሚከተሉት መስመሮች አስተያየቴን ለመግለጥ እሰነዝራለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዙፋኑ የሰጠው ልባዊ አክብሮት ዘላቂ ሆኖ በታሪካዊ ቅርስነት እንዲጠበቅ በቤተ መንግሥቱ በኩል አልታሰበበትም ለማለት ያስደፍራል፡፡ ባለፈው ‹‹መለኮታዊ መብት›› የተባለው የዘውድ ቴዎሪ የተሳሳተ መሆኑን ቢረዳውም፣ ሕዝቡ፣ ዘውዱን ታሪካዊ ሲምቦል ወይም ምሳሌ አድርጐ በክብር ሊያኖረው ሲፈቅድ ወደ መለኮታዊ መብት አስተያየት እንደገና እንዲመለስና ጣኦታዊ ስግደት እንዲያደርግ ማስገደድ፣ በእልህ ዘውዱን ለማስረገጥ ካልሆነ በቀር ለሌላ አያገለግልም፡፡
ጃንሆይ፣ ባለዘውድ፣ አስተዳዳሪ፣ ሕግ አውጭ፣ ዳኛ፣ ምስለኔ፣ ፖሊስ፣ ጭቃ ሹም ሆኜ ልሥራ ሲሉ፣ በ፳ኛው [20ኛው] ክፍለ ዘመን የሚገኝ ሕዝብ ይህን መብት አጠቃሎ በፈቃዱ ለዘውዱ ብቻ ይለቃል ማለት የማይታመን ነው፡፡ መቸም እየተደጋገመ የሚሰጠው ምክንያት ‹‹ሕዝቡ ኃላፊነትን ለመቀበል አልደረሰም›› የሚል መሆኑን በየጊዜው ሰምተናል፡፡ በውነቱ ከአፍሪካና ከኤሻ ሕዝብ መካከል አልደረሰም ተብሎ በኢትዮጵያ ሕዝብ መፍረድ ይገባልን? ደግሞስ ያለመድረስ ትርጓሜው ምንድነው? ምናልባት የማሰብ፣ የመምረጥ፣ የማመዛዘን፣ የመፍረድ ሴንስ አልተፈጠረለትም ማለት ነው? እንደዚህማ ከሆነ በ፫ሺሕ [በ3 ሺሕ] ዘመን ውስጥ ለዚህ ሕዝብ ጭንቅላት ሆኖ ያሰበለት፣ ዓይን ሆኖ ያየለት፣ ጆሮ ሆኖ የሰማለት የዛሬው ዘውድ ነው ማለት ነዋ! የሚፈተነው ይህን የመሰለ አስተያየት ለማቅረብ እንደሆነ ምሕረት የሌለው በደል ነው፡፡
ይልቁንስ ጃንሆይ የሕግ ጠባቂነትን ልብስ ተጐናጽፈው በዚህ መንፈስ ፍትሕን ከሚያጓድሉ፣ ሥልጣኑን ለሕዝብዎ ሰጥተው እርሱ ቢጨነቅበት እንደሚሻል ጥርጥር የለውም፡፡ ያለዚያ ከዚህ ማስታወሻዬ ውስጥ ለስማቸው እንኳ ሥፍራ ለመስጠት ዋጋ የሌላቸውና ሕሊና ቢሶች የሚያቀርቡልዎትን ‹‹ደህና ታይቷል›› እያሉ ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ እንደሚኖር የተሰወረ ሊሆን አይችልም፡፡
ይህን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ለማሻሻል የሚቻለው ጃንሆይ ዘውዱን ለራስዎ አስቀርተው አስተዳደሩን ለሕዝብ በመስጠትና የዴሞክራሲን መንፈስ በማስገባት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አስተያየት ለግርማዊነትዎ ሰውነት አለርጂ ሆኖ ቢያስቸግርም እንኳ ሌላ ማማረጫ ይኖራል፡፡ ይኸውም ዘውዱን ለልዑል አልጋ ወራሽ ማስተላለፍና አብዲኬት ማድረግ ነው፡፡ እርሳቸው ሕገ መንግሥት ጠብቀው ለመኖር ፈቃደኛ እንደሆኑ አያሌ ሰዎች ሲመሰክሩላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ያለዚያ ተከታዩ ትርምስና ደም መፋሰስ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡
ይህ አቤቱታ ከኔ ብቻ የቀረበ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍርኃት ታፍኖ ነጋም መሸም የሚያጕተመትመው ይህንኑ ነው፡፡ ድምፁን ከፍ ለማድረግ ግን አካባቢው አልፈቀደለትም፡፡ እኔም ከርሱ የተለየሁ መስዬ ታይቼ እንደሆነ ያጋጣሚ ነገር ብቻ ነው፡፡ አዲስ አበባ የታፈንኩትን ያህል እዚህ ከተነፈስሁ በኋላ ወደ አገሬ እንድመለስ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምናልባት ይህን አቤቱታ በመጻፌ እወነጀል ይሆናል፡፡ ግድ የለም፡፡ የሆነ ሆኖ በትእዛዝ ሳይሆን በነፃ የሚፈርድና በግልጽ የሚያስችል ፍርድ ቤት ተቋቁሞ ራሴን በሕጋዊ ጠበቃ አማካይነት ለመከላከል ጃንሆይ የሚፈቅዱልኝ ከሆነ በአገሬ ውስጥ ለመተንፈስ ዕድል ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡
ከዚህም ሁሉ ጋር ላስታውሰው የምፈቅደው፣ ይህን ማስታወሻ በመጻፌ ተቀይመው የእኔን ሕይወት ለማስጠፋት በሺሕ የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚወጣ ጥርጥር የለውም፡፡ አዝናለሁ፡፡ እኔ ለሞት የተዘጋጀሁ ስለሆነ ገንዘቡ ባይባክንና ለነፍሰ ገዳይ በመስጠት ፈንታ ለጦም አዳሪ ችግረኛ ቢውል የበለጠ እንደሚጠቅም ጥርጥር የለውም፡፡ በበኩሌ በአገራችን ሬሾሉሽን እንዲነሣና የማንም ደም እንዲፈስ አልፈቅድም፡፡ በዚህ ባቤቱታዬ የምወተውተውም ሰላማዊ ለውጥ እንዲሆንና የምንፈራው ደም መፋሰስ እንዳይደርስ ስለሆነ ጃንሆይ አንድ ቀን ‹‹ለካ ብርሃኑ ውነቱ ኖሯል!›› ሳይሉ አይቀርም፡፡
እንኳን ዘውድ የጫነ ሰውነትንና ማናቸውንም ሰው የማክበር ልምድ ስላለኝ፣ ይህ አቀራረቤ ክብርን ለመድፈር እንደማያስቆጥርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ውነት ሁል ጊዜ መራራ ናት፡፡ የመድኃኒት ፈውሱ እንጂ ምሬቱ አይታሰብም እንደተባለው ይህ በቅን ልቡና የቀረበው ውነተኛ አቤቱታዬ የግርማዊነትዎን ልብ አራርቶ ለኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት አንድ ፈውስ እንዲያመጣለት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ጃንሆይ! በኢትዮጵያ ወጣቱ ሽማግሌው ሴቱ ወንዱ የአኗኗሩ ዘዴ ውሉ ተዘባርቆበታል፡፡ አምላካችን፣ ፈጣሪያችን እያለ ቢደልልዎት አይመኑት፡፡ ጨንቆት ነው፡፡ ከልብ የሚመርቅዎት ግን ራስህን አስተዳድር ብለው አርነት ሲያወጡትና ወደ ዴሞክራሲ ሲመሩት ነው፡፡ ይህንንም ስል ሕዝብ በራሱ ሲተዳደር ችግር አይገጥመውም ማለቴ አይደለም፡፡ እስከዚህ አልሳሳትም፡፡ ነገር ግን ሌላው ለፍቶ ከሚጥለውና ላንሣህ ከሚለው፣ ራሱ ወድቆ በራሱ መነሣትን ይመርጣል፡፡ ይኽም በሥሕተት መማር ይባላል፡፡ ስለዚህ ጃንሆይም ተሳሳቱ እያለ ከሚከስዎት እርሱ ለሥሕተት እንዲጸጸትና እንዲማር ቢያደርጉት ትልቅ ውለታ ይቆጠራል፡፡
የዛሬው ሕገ መንግሥት ዴሞክራሲን ለማስገንባት የሚረዳ ካለመሆኑም በላይ ያንኑም ቅሉ አክብሮ ለመጠበቅ በአንቀጽ ፳፩ [21] እንደተመለከተው ከንጉሠ ነገሥቱ በመሐላ የተሰጠው ቃል ፈርሷል እያሉ አያሌ ኢትዮጵያውያን እንደሚያማርሩ ግርማዊነትዎ ሳይሰማው አይቀርም፡፡ መቸም ሕገ መንግሥቱን፣ ለመጣስ አንድ የጽሕፈት ሚኒስቴር ደብዳቤ ይበቃል፡፡ እንግዴህ ሕዝቡ ወይም ሹማምቱ ለንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ነኝ እያሉ ቢምሉም፣ ንጉሠ ነገሥቱ በበኩሉ መሐላውን የሚጠብቅ ካልሆነ በመሐላቸው ታስረው እንደማይኖሩ በልጅ ኢያሱ ጊዜ የደረሰው ሁኔታ ምሳሌ ሊሆን ይችል ይመስለኛል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የገጠመንን ፕሮብሌም እንደ መጠኑ ለመግለጥ ‹‹በግርማዊነታቸው መንግሥት ያገኘሁት ኤክስፔሪያንስ›› የሚለው መጽሐፌ በሙሉ ታትሞ እስከወጣ ድረስ ፲፪ኛውን [12ኛውን] ምዕራፍ ከዚህ ጋር አያይዤ ለግርማዊነትዎ በትህትና አቀርባለሁ፡፡

                          ዋሽንግተን ግንቦት ፳፭/፶፯ [ግንቦት 25/57]
                                ከታላቅ አክብሮታዊ ፍርሐት ጋራ
                                          ብርሃኑ ድንቄ


Friday, August 22, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

 (ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ

ስለ አምላክ  ሕግና ስለ ሰው ሕግ

እግዚአብሔር  የገዛ  ሕዝቡን  እንዲያስቷቸው  ስለምን  ዋሾ  ሰዎችን  ይተዋል  ብዬ  አሰብኩ፡፡  እግዚአብሔር  ግን  ለሁሉም
ለእያንዳንዱ  እውነትንና  ሐሰትን  እንዲያውቅ  ልቦና  ሰጥቶናል፡፡  እውነት  ወይም  ሐሰት እንደፈቃዱ  የሚመርጥበት
መምረጫም ሰጠው፡፡ እውነትን ብንወድ ለፍጥረት ሁሉ አስፈላጊና ተገቢ የሆነውን እርሱም እንድናይበት እግዚአብሔር
በሰጠን ልቦናችን ውስጥ እንፈልጋት፡፡ ሰው ሁሉ ዋሾ ነውና እውነትንም በሰዎች ትምህርት አታገኟትም፡፡ ከእውነት ይልቅ
ሐሰትን ብንመርጥ ስለዚህ እኛ በስህተታችን እንጠፋለን እንጂ ለፍጥረት ሁሉ የተሰራው የፈጣሪ ሥርዓትና ሕግ አይጠፋም፡፡
እግዚአብሔር ማንንም በሠራው ሥራ ይጠብቀዋል፡፡ ከሰው ሥራ ግን የእግዚአብሔር ሥራ ይጸናል፡፡ የሰው ሥራ ሊያጠፋው
አይችልም።  ስለዚህም  ከጋብቻ  ይልቅ  ምንኩስናን  ይበልጣል  ብለው  የሚያምኑ  እነርሱ  በፈጣሪ  ሥራ  ጽናት  ወደ  ጋብቻ
ይሳባሉ፡፡ ፆም ነፍስን እንደሚያፀድቅ የሚያምኑ እነርሱ ደግሞ ረሃብ በበዛባቸው  ጊዜ ይበላሉ፡፡ ገንዘቡን የተወ ፍፁም
እንዲሆን  የሚያምኑ በገንዘብ  ለሚያገኙት   ጥቅም  ወደ  ገንዘብ  መፈለግ  ይሳባሉ፡፡  ብዙዎች  የሀገራችን  መነኩሴዎችም
እንደሚደርጉት ከተዉት በኋላ እንደገና ይፈልጉታል፡፡ እንደዚሁ ዋሾዎች ሁላቸው የተፈጥሮን ሥራ ሊያፈርሱ ይፈልጋሉ፡፡
ነገር ግን ደካማነታቸውን ያሳያሉ እንጂ አይችሉም፡፡ ፈጣሪም ይስቅባቸዋል፡፡ የፍጥረት ጌታም በላያቸው ይሳለቅባቸዋል፡፡
እግዚአብሔር የእግዚአብሔርን ፍርድ ማድረግ ያውቃልና ኃጥአንም በእጁ ሥራ ወጥመድ  ተጠመደ፡፡ ስለዚህም የጋብቻን
ሥርዓት የሚያስነውር መነኩሴ በክፉ በሽታና ፍጥረቱ ባልሆነ በሌላ የሴት አበሳ በዝሙት ተጽዕኖ ይጠመዳል፡፡ ገንዘባቸውን
የሚንቁ  ገንዘብ  እንዲያገኙ  በሀብታሞችና  በነገሥታት  ዘንድ  ግብዞች  ይሆናሉ፡፡  ለእግዚአብሔር  ብለው  ዘመዶቻቸውንም
በሽምግልናቸውና በችግራቸውም ረዳት ባጡ ጊዜ የተዉ በነሱ ሽምግልና ጊዜ ሰውና እግዚአብሔርን ወደ ማማት፤ መሳደብ
ይደርሳሉ፡፡  እንደዚሁም  የፈጣሪን  ሥርዓት   የሚያፈርሱ  ሁሉ  በእጃቸው  በሰሩት  ወጥመድ  ይወድቃሉ፡፡  እንደገናም
እግዚአብሔር  ክፋትን፤ ስህተትን  በሰው  መካከል  ይተዋል፡፡  ነፍሶቻችን  በዚህ  ዓለም  የእግዚአብሔር ጥበብ  የፈጠረውን
የፈተና ቀን ይኖራሉ፡፡

ጠቢቡ ሰለሞን

"እግዚአብሔር  ፃድቃንን  ፈተናቸው፡፡  ወርቅ  በእሳት  እንደሚፈተን  ይፈትናቸዋል፡፡  ለእርሱ  የተዘጋጁ  ሆነውም
አግኝቷቸዋልና፡፡ እንደተወደደ ዕጣን መዐዛም ይቀበላቸዋል" ይላል፡፡
ከሞታችን በኋላም ቢሆን ወደፈጣሪያችን በገባን ጊዜ እግዚአብሔር በእውነትና በትልቅ በጥበብ ከሠራው ሁሉ እውነትና ቅን
የሆነውን መንገድ ሁሉ እንለያለን፡፡ ነፍሳችንም ከሥጋዊ ሞታችን በኋላ እንደምትድን ይታወቃል፡፡ በዚህ ዓለም ውዴታችን
አይፈፀምምና የሌላቸው ይፈልጋሉ፤ ያላቸው ባላቸው ላይ እንደገና ሊጨምሩ ይፈልጋሉ፡፡ሰው በዚህ ዓለም ያለው ሁሉ
እንኳን  ቢኖረው  እንደገና  ይወዳል  እንጅ  አይጠግብም፡፡  ይህም  የፍጥረታችን  ጠባይ  ለሚመጣው  ንብረት  እንጂ  ለዚህ
ዓለም ንብረት ብቻ እንዳልተፈጠርን ያመለክታል፡፡ በዚያውም የፈጣሪያቸውን ፈቃድ የፈፀሙ ነፍሳት ፍፁም ይጠግባሉ
እንጂ ከእንግዲህ ሌላ አይወዱም፡፡ አለዚያ ግን የሰው ፍጥረት አስፈላጊውን ሁሉ አላገኝምና ጎዶሎ በሆነ ነበር፡፡ እንደገናም
ነፍሳችን  እግዚአብሔርን  ማሠብ  ትችላለችና  በሃሳቧም  ታየዋለች፡፡  እንደገናም  ለዘላለም  መኖር  ማሰብ  ትችላለች፡፡
እግዚአብሔርም ይህን ማሰብ በከንቱ አልሰጣትም፡፡ ነገር ግን እንደሰጣት ልታስብና  እንድታገኝም ሰጣት፡፡ ደግሞ በዚህ
ዓለም ፅድቅ ሁሉ አይፈፀምም፡፡ ክፉ ሰዎች ከዚህ ዓለም መልካም ይጠግባሉ፡፡ ደጋጎች ይራባሉ፡፡ የሚደሰት ክፉ አለ፣
የሚያዝን ደግ አለ፣ የሚደሰት ዐመፀኛ አለ፣ የሚያለቅስ ፃድቅም አለ፣ ስለዚህም  ከሞታችን በኋላ ለሁሉ እንደየምግባሩ
የሚከፍለው  ሌላ  ኑሮና  ፍፁም  ፅድቅ  ያስፈልጋል፡፡  በብርሃን  ልቦናችን  ተገለፀላቸው፡፡  የፈጣሪን  ፈቃድ  የፈፀሙና
በተፈጥሯቸውም ፀባያዊ ህጉን የጠበቁ ዋጋቸው ይከፈላቸዋል፡፡ የተፈጥሮን ሕግ ከመረመርን የተረጋገጠ መሆኑን ልቦናችን
በግልፅ  ይነግረናል፡፡  ነገር  ግን ሰዎች  ሊመረምሩ  አልፈለጉምና  የፈጣሪያቸውን  ፈቃድ በእውነት  ከመፈለግ  የሰዎችን  ቃል
ማመን መረጡ፡፡

 ስለ ባህሪያዊ ዕውቀት

የፈጣሪ ፈቃድ ግን ለእግዚአብሔር ለፈጣሪህ ስገድ ፣ ሰውንም ሁሉ እንደነፍስህ አፍቅር ይላል፡፡ ይህ በልቦናችን እውነት
መሆኑ  ይታወቃል፡፡  እንደገናም  በልቦናችን  እውነትነቱ  የሚታወቅ  ሌላ  እውነት  "ሊያደርጉብህ  የማትፈልገውን  በሰው
አታድርግ፡፡  ላንተ  ሊያደርጉልህ  የምትፈልገውን  አድርግላቸው"  ይላል፡፡  የሰንበትን  ማክበር  የሚለው  ካልሆነ  በቀር  ዐሥሩ
የኦሪት  ትዕዛዛት  የፈጣሪ  ናቸው፡፡  ሰንበትን  ለማክበር  ግን  ልቦናችን  ዝም  ይላል፡፡ ልንገድልና  ልንሰርቅ፣  ልንዋሽና  የሰው
ሚስት  ልንሰርቅ  ይህን  የሚመስለውን  ልናደርግ  እንደማይገባን  ልቦናችን  ይነግረናል፡፡ እንዲሁ  ስድስቱ  የወንጌል  ቃላት
የፈጣሪ  ፈቃዶች  ናቸው፡፡  እኛ  ይህን  የምህረት  ሥራ  ሊያደርጉልን  እንፈልጋለን፡፡  በሚቻለን  ለሌሎች  ልናደርግላቸው
ይገባናል፡፡ ደግሞም በዚህ ዓለም ሕይወታችን፣ ንብረታችን እንድንጠብቅ የፈጣሪ ፈቃድ ነው፡፡ ከፈጣሪ ፈቃድ ወጥተን
በዚህ ሕይወት እንኖራለን፡፡ በተቀደሰ ፈቃዱ ካልሆነ በቀር ልንተወው አይገባንም፡፡እርሱ ፈጣሪያችን ለሁሉ ልቦናና ችሎታ
ስለሰጠ ኑሯችንን በዕውቀትና በሥራ እንድናሳምረው ይፈቅድልናል፡፡ ይህ ካልሆነ በቀር የሕይወታችን ፍላጎት አይገኝም፡፡
እንዲሁ  አንዱ  ካንዷ  ጋር  መጋባትና  ልጆች  ማሳደግን  ፈቅዷል፡፡  ደግሞም  ከልቦናችን  ጋር  የሚስማማ  ለህይወታችንም
ለሁሉም  የሰው  ልጆች  ኑሮ  የሚያስፈልጉ  ሌሎች  ብዙ  ሥራዎች  አሉና  የፈጣሪ  ፈቃድም  እንዲሁ  ስለሆነ  ልንጠብቀው
ይገባናል፡፡ እግዚያብሔር ፍፁማን አድርጎ እንዳልፈጠረን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ለመፈፀማችን የተዘጋጀን አዋቂዎችና በዚህም
ዓለም  እስካለን  ድረስ  እንድንፈፅምና  ፈጣሪያችን  በጥበቡ  ላዘጋጀልን  ዋጋ  የተዘጋጀን እንድንሆን  አድርጎ  ፈጠረን፡፡  በዚህ
ምድር ፍፁማንና ብፁዓን አድርጎ ሊፈጥረን ለእግዚአብሔር ይቻለው ነበር፡፡ ነገር ግን ለመፈፀማችን የምንዘጋጅ አድርጎ
ፈጠረን እንጅ እንዲሁ ሊፈጥረን አልፈቀደም፡፡ ከሞታችን በኋላ ፈጣሪያችን ለሚሰጠን ዋጋ የተዘጋጀን ፍፁማን እንድንሆን
በዚህ የፈተና ዓለም መካከል አኖረን፡፡ በዚህ ዓለም እስካለንም ወደ እርሱ እስኪወስደን ድረስ እየታገስን ፈቃዱን እየፈፀምን
ፈጣሪያችን  ልናመሰግነው  ይገባል፡፡  የፈተናችንንም  ጊዜያቶች  እንዲያቀልልን  ባለማወቃችን  ሠራነውን  የእብደት  አበሳ
እንዲተውልን የተፈጥሮ ሕግጋትን አውቀን እንድንጠብቃቸው ልቦና እንዲሰጠን ወደቸርነቱ እንለምን፡፡ ፀሎት ደግሞ ላዋቂ
ነፍስ  አስፈላጊ  ነውና  ዘወትር  ልንፀልይ  ይገባናል፡፡  አዋቂ  ነፍስ  ሁሉን  የሚያውቅና ሁሉን  የሚጠብቅ  ሁሉን  የሚገዛ
እግዚአብሔር እንዳለ ታውቃለች፡፡ ወደ እርሱ እንድትፀልይም ከእርሱ መልካም እንድትለምን፣ ከክፉ እንድትድንና ሁሉን
ወደሚችል እጅ እንድትማፀን ወደ እርሱ ትሳባለች፡፡ እግዚአብሔር ምሁርና ትልቅ ነው፡፡ የሚሳነውም የለም፡፡ ከበታቹ
ያለውን ያያል፣ ሁሉንም ይይዛል፣ ሁሉን ያውቃል ፣ ሁሉን ይመራል፣ ሁሉን ያስተምራል አባታችን ፈጣሪያችን ጠባቂያችን
ነው፡፡  የነፍሳችን  ዋጋ  ቸርና  ይቅር  ባይ  ችግራችንን  ሁሉ  የሚያውቅ  ነው፡፡  ለሕይወት  እንጂ  ለጥፋት  አልፈጠረንም፡፡
በትዕግስታችን ይደሰታል፡

Thursday, August 14, 2014

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሥርዓተ አልበኝነት ነግሷል!

  • የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲፈራርስ ዝምታው እስከመቼ?
  •  
  •  ቅዱስ ፓትርያርኩ በዚህ ጉዳይ ምላሻቸው ምን ይሆን?

ዛሬ ዛሬ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሚለው ቃል ከወረቀት ባለፈ በመሬት ላይ ተፈሚነቱ የሚታየው በጣም በጥቂቱ ነው። በተለይም ቤተ ክርስቲያኒቱ አለኝ በምትለው ማእርገ ክህነት በኩል ዲቁና፤ ቅስና ( ምንኩስና) ቁምስና በሙሉ የሚሰጠው ለማንና መስፈርቱ ምን እንደሆነ በማይታወቅ መልኩ ሥርዓተ የለሽ ሆኖ ይታይበታል። እነ መቶ አለቃ ግርማ ወንድሙ ሳይቀሩ በር የሚዘጋ መስቀል ተሸክመው እያሳለሙ በአጥማቂነት ተሰማርተው ገንዘብ ይሰበስባሉ። ከዚህ በፊት ወደእስራኤል አቅንቶ የነበረው ግርማ ወንድሙ ገና ገንዘብ መሰብሰብ ሲጀምር አንዷን ሴት ሲያጠምቅ ጎረቤቷ ቡዳ ሆና በላቻት በማሰኘቱ፤ ቡዳ ናት የተባለችው ሴት ፍርድ ቤት በስም አጥፊነት ከሳው መጥሪያ ብታመጣበት ሌሊቱኑ ፈርጥጦ ወደኢትዮጵያ ማምለጡን ጉዳዩን በቅርበት ከሚያውቁ ሰምተን ተገርመን ነበር። ባለቤት የሌላትን ቤተ ክርስቲያን እየተዘዋወረ በክፉ መንፈስ የሚበጠብጠው ግርማ አሁን ደግሞ ወደአውሮፓ ዘልቆ በጣሊያን የዘረፋውንና የቡዳ በላሽ ዜማውን እያስነካው ይገኛል። እነባህታዊ ገብረ መስቀል ማርያምን ተገለጸችልኝ እያሉ ህዝቡን ሲያጭበረብሩ እንዳልነበር ብህትውናውን እርግፍ አድርገው ቆንጆ መርጠው ሚስት አግብተው ልጆች ወልደው ማርያም ተገለጸችልኝ፤ ገብርኤልን አየሁት ከሚል ማደናገሪያ ነጻ ወጥተዋል። ከማጭበር በር ይህኛው የተሻለ አማራጭ ይመስለናል።
ይህ ማእርገ ክህነት የሚባለው ሹመት በአንዳንዶች ዘንድ የክብር ዶክትሬት ይመስል ከስም ባለፈና የሕዝቡን ግንባር ከሚገጩበት በስተቀር እንደማኅበረ ቅዱሳን ባሉ ማኅበራት ዘንድም የአገልግሎት ዋጋ የሌለው መሳሪያ ሆኖ ይገኛል። በየትኛውም ቤተ ክርስቲያን ሲያገለግሉበት አይታይም። የማዕረጉን ስም የሚፈልጉት ክህነት የላቸውም እንዳይባሉና በክህነት ሽፋን በሚገኘው ክብር የመበለቶችን ቤት ለመዝረፍ ስለሚረዳ እንጂ ከመጀመሪያው በድንግልና ጸንተው ለማዕርገ ዲቁና በቅተው «ተንሥኡ፤ ጸልዩ» እያሉ ሲያገለግሉበት ቆይተው፤ በኋላም በስርዓተ ቤተ ክርስቲያን በተክሊል በድንግልና የጸናች አግብተው አይደለም። ሲጀመር ጀምሮ ዲቁናም ይሁን ቅስና የተቀበሉት ሰዎች ድንግላቸው የፈረሰበትን ጊዜ ራሳቸው በትክክል አያውቁትም። ራሳቸው በድንግልና ሳይቆዩ፤ ድንግልና እንደፈንጣጣ በጠፋበት ዘመን ድንግል አግብተው አይቀስሱም።  በተለይ ወንዶቹ አጭበርባሪዎች፤ ቀሳጮችና መልቴዎች ናቸው። በዚህ ዙሪያ ሀገር ሰፈሩን ሲያዳርሱ የኖሩ የዘመኑ ቀሳውስትና መነኮሳት ነን ባዮች ቅስናን እንደማጭበርበሪያ ይጠቀሙበታል። ቅዱስ በተባለው መቅደስ ገብተው በርኩስናቸው ሕዝቡን ያታልሉበታል። ይህ ዐመፃና ማታለል በሀገር ላይ ጥፋትን፤ በሕዝብ ላይ ቁጣን ማምጣቱ አይቀርም። ማንም እመራበታለሁ ብሎ ላወጣው ለራሱ ሕግ የማይታዘዝ ከሆነ የሚጠፋው በዚያው በራሱ ሕግ ነው።
«ያለ ሕግ ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለ ሕግ ደግሞ ይጠፋሉና፤ ሕግም ሳላቸው ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ በሕግ ይፈረድባቸዋል» ሮሜ 2፤12
ዛሬ ሁሉም ከዚህ ከራሳቸው የሕግ ክብር ስለወረዱ ማንም ምንንም አይቆጣጠርም። ሥርዓት ፈረሰ፤ ሕግ ተጣሰ የሚል አንድም ስንኳ የለም። «ኩሉ ዐረየ፤ ወኅቡረ ዐለወ» እንዳለው ዳዊት በመዝሙሩ ሁላቸውም ተሳስተዋል፤ ሁላቸውም በዐመጻ ስለተስተካከሉ ዲቁና ሰጪውም ተቀባዩም ከሥርዓት ውጪ ሆነዋል።  ከዚህ በታች የቀረበውም ጽሁፍ ይህንን መሠረት ያደረገ ነው።
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነን «እንበለ አሐዱ ኄር፤ ኢይኀድጋ ለሀገር» ለሀገር እንዲሉ አንድ ተቆርቋሪ ኤርትራዊ ቄስ ከሀገረ እስራኤል-ቴል አቪቭ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ለልዩ ልዩ ድረ ገጾች በግልባጭ ሲልክ ለእኛ የደረሰውን ጽሁፍ እንዳለ አቅርበነዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምን ሆነች?

በታሪክ አጋጣሚ ኢትዮጵያና ኤርትራ ከመለያየታቸው በስተቀር በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ዛሬም ድረስ አንድ ነን። ሥርዓቱና ሕግጋቱ የተለያየ አይደለም። በማዕረገ ክህነት አሰጣጥ ልዩነት ያለን አይመስለንም።  ነገር ግን እጅግ አሳዝኝና አስገራሚ ነገር ስናይ የምንጠይቀው አጥተናል። በተደረገው ሁኔታ እኛ በእስራኤል የምንገኝ ኤርትራውያን በተደረገው አድራጎት ተጎድተናል። ይኸውም ለሰሚ የሚከብድና ከምናውቃት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ህግጋት ውጪ ማዕረገ ክህነት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳም ውስጥ ሲሰጥ በማየታችን በጣም አዝነናል። ነገሩን በአጭሩ አስረዳለሁ።
ሰውየው በትግራይ ክፍለሀገር ሰንቃጣ እንደተወለደ አውቀነዋል። ስሙም ሓጎስ አስገዶም ይባላል። በትግራይ ክፍለ ሀገር ይህ ሓጎስ አስገዶም የተባለ ሰውዬ አባ ሰላማ የሚባል ማኅበር አቁሞ ህዝብ ለህዝብ ሲያጋጭ ተይዞ ሶስት አመት ወኅኒ ታስሮ ነበር። በአቡነ መርሐ ክርስቶስ ማኅበሩ በትእዛዝ ፈረሰ። በሲኖዶስም ተወሰነበት። ተስፋ ያልቆረጠው ይህ ሓጎስ አሰገዶም የተባለ ሰውዬው ወደ ሽመልባ የኤትራውያን ስደተኛ ካምፖ በመግባት ባሕታዊ ወልደ ሥላሴ እባለሎህ በማለት ማደናገር ጀመረ።
ባህታዊ ነኝ የሚለው ሓጎስ አስገዶም

በዚያም በእሱ የተጀመረ ረብሻ በሽመልባ ባሉ የኤርትራ ቤተክርስቲያን በመበራከቱ ጥቂት ተከታዮች አስከትሎ በሱዳን አድርጎ ሊቢያ ገባ። ሊቢያ ሲገባም አባ ሰላማ መልዕክት ነግረውኛል ከዛሬ ጀምሮ አንተ ሞኖክሴ ነህ ብለውኛል ብሎ አባ ሳሙኤል ነኝ አለ። ከዚያም ይህ ሓጎስ አስገዶም ከሊቢያ ወደእስራኤል ሀገር ከኤርትራውያን ጋር ገብቶ ኤርትራዊ ነኝ ብሎ የስደተኛ ወረቀት ከወሰደ በኋላ ሳይሞኖክስ አባ ሳሙኤል ተብሎ እየተጠራ ቆየ። አጠምቃለሁ እያለ ሲያታልል፤ ህዝብ ሲያሳብድ፤ ገንዘብ ሲሰበስብ ቆይቶ ብዙ ኤትራውያን ደግሞ አንተ ሞኖክሴ አይደለህም፤ ለምን አባ ትባላለህ። ክህነት የለህም ለምን ታሳልማለህ።  ንስሀ ለምን ትሰጣለህ ስንለው የእኔ ክህነት በአባ ሰላማ ፍሬምናጦስ አማላጅነት ከሰማይ ነው የተሰጠኝ፤ የእናንተ ክህነት ግን ከኃጢአተኛ ጳጳስ እጅ የተሰጠ ነው እያለ ሲሳደብ በማየታችን ህዝቡ በዚህ አታላይ ሰው እንዳይታለል ስናስተምር ተናዶ ወደኢየሩሳሌም በመሄድ ከኢትዮጵያ ሊቀጳጳስና አንዳንድ መነኮሳት ጋር በስውር መገናኘቱን ቀጠለ።
ባህታዊ ወልደ ሥላሴ ነኝ እያለ በሽመልባ ሲያታልል

 ከዚያም ከሊቀ ጳጳሱ አባ ዳንኤል ዘንድ ዲቁና ተቀበልኩ አለና በአስማቱ ለሚያታልላቸው ደጋፊዎቹ  ማዕረጉ ሲሰጠው የሚያሳይ ፎቶና ፊልም አሳየ። ትንሽ ቆይቶ ሞኖኮስኩኝ ብሎ እንደቦብ ማርሊ ያሳደገውን ጸጉሩን ቆርጦ ጥቁር ቆብና ቀሚስ አድርጎ መጣ። አንተን አመነኮሰች ቤተ ክርስቲያን? ብለን አዘንን። አለቀስን።
በአባ ሳሙኤል ስም ቄስና መነኩሴ ነኝ አለን ደግሞ

ከሱ ጋር የነበሩና ስናስተምራቸው የተመለሱ ሁለት ዲያቆናት ለመመንኮስ 50 ሺህ ሼቄል ከፍሏል አሉን። ለሊቀ ጳጳሱና ከመነኮሳቱ መካከል አባ ፍስሐና አባ ብርሃና መስቀል የተባሉም ገንዘብ መቀበላቸውን አሁንም ይመሰክራሉ። የሰው ማስረጃ አለን። ሌሎችም መነኮሳት የተቀበሉ አሉ። ይህ አታላይ አባ ሳሙኤል የተባለው ትንሽ ቆይቶ የቅስና ማዕረግ ከአባ ዳንኤል ተሰጠኝ ብሎ በደብረ ገነት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን የተፈጸመውን ሥርዓት በቢዲዮና በፎቶ  ቴልአቪቭ አምጥቶ ለተከታዮቹ አሳየ። ይህ ሁሉ ማስረጃ በእጃችን ይገኛል።
ምንም የቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሙያ ለሌለው፤ ዲቁና ሳይኖረው  ለሓገስ አስገዶም ቅስና ሲሰጡት አቡነ ዳንኤል ናቸው

 የዚህ ሁሉ አስተባባሪ አባ ፍስሐ ይባላሉ። አባ ብርሃነ መስቀል የተባሉት፤ አባ ተወልደ የተባሉትም አብረውት አሉ። ገንዘብ የተቀበሉ መኖክሴዎች ዝርዝር በእጃችን አለ። በቁጥር ትንሾች ቢሆኑም የቤተ ክርስቲያን ስርዓት ጠፋ ብለው የተናገሩ ቢኖሩም የሰማቸው የለም።  ገንዘብ የሁሉንም አፍ ዝም አሰኝቷል።



 እኛ የምናዝነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ሹማምንት በገንዘብ ስልጣነ ክህነት እየሰጡ ለምን ቤተ ክርስቲያንን ያሰድባሉ? የኢየሩሳሌም ገዳም ሞኖክሴዎችስ ለምን በገንዘብ ይደለላሉ? ክህነት እንደዚህ ነው? ሙንኩስናስ እንደዚህ ነው? በበኩላችን ይህን ሰውዬ ያለአግባብ እያታለለ ከኤርትራውያን እጅ የወሰደውን በብዙ መቶ ሺህ ሼቄል ለማስመለስና በህግ ፊት ለማቆም ማስረጃዎቻችንን ይዘናል። እናንተ በሰጣችሁት ክህነት አንታለልም። አንታወክም። ለነገሩ ቤተ ክርስቲያንን አዋርዳችሁታል። ሓጎስ አስገዶም ቄስ ሆነ? ሚስቱንም አምጥቶ አመነኮሰ። አንድ ቤት አንድ ላይ ይኖራሉ። አይ ኦርቶዶክስ፤ እንደዚህ መሆና ያሳዝናል። ሕግ ካለ፤ ዳኛ ካለ ኢየሩሳሌም ያሉ ሞነኮሳትን ከገዳሙ ማባረር ነበር። ለሓጎስ አስገዶም ቅስና የሰጡ ሊቀጳጳሱም መቀጣት ነበረባቸው።
ያሳዝናል። ያሳዝናል። በትክክልም ዘመኑ ተጨርሷል። ክህነትና ሙንኩስና  በገንዘብ ሆነ። ኤሎሄ ኤሎሄ ይባላል።

ለምእመን በገንዘብ ክህነት እንዲያገኝ ያደረጉ አባ ብርሃነ መስቀል የሚባሉት በቀኙ፤ አባ ፍስሐ የሚባሉት አባ ፍስሐ የሚባሉት በግራ በመሀል አቡነ ዳንኤልና ሲሆኑ በደብረ ገነት ቤተመቅደስ ውስጥ ሓጎስ አስገዶም ፤ ወልደሥላሴና አባ ሳሙኤል የተባለው ቅስና ሲቀበል የሚያሳይ ፎቶ። የዚህ ሥርዓት ሙሉ ቪዲዮ በእጃችን አለን።
             
                     ፍትዊ አንገሶም ቴልአቪቭ

Monday, August 11, 2014

ትክክለኛው ሃይማኖት የቱ ነው?



 ቀልጣፋ ሬስቶራንቶች በቀላሉ የሚስቡን የፈለግነውን ምግብ በምንወደው መንገድ እንድናዝ መንገድ ስለሚከፍቱልን ነው። ጥቂት ካፌዎች ደግሞ ከመቶ በላይ የተለያዩ የቡና ጣዕም እንደሚያቀርቡ በጉራ ይናገራሉ። መኖሪያ ቤቶችና መኪናዎችን ስንገዛ እንኳ የምንፈልገው ምርጫ እንዲያሟላ እንሻለን። በቼኮላት፣ በቫኒላና በእንጆሪ ዓለም ታጥረን መኖር አንፈልግም። ፍላጎት ንጉሥ ነው! እንደግላዊ ፍላጎትህና ምርጫህ የምታገኝበት ሁሉ የተሟላበት ዘመን ነው።
ለአንተ ብቻ ትክክለኛ ሃይማኖት የማግኘቱ ሁኔታስ ምን ይመስላል? ወቀሳ አልባ፣ ብዙ ጫና የሌለውና ይህንን አድርግ አታድርግ እያለ የማያስቸግር ሐይማኖት ብታገኝስ? ቀደም ብዬ እንደገለፅኩት ያውና እዚያ አለ ነገር ግን ሃይማኖት እንደሚወዱት አይስክሬም የሚመረጥ ነው እንዴ?
ትኩረታችንን ለመሳብ የሚሻሙ በርካታ ድምፆች ስላሉ ለምን ብሎ ነው አንድ ሰው ኢየሱስን ከሌሎች ማለትም ከመሐመድ ወይም ከኮንፊሸየስ፣ ከቡድሐ ወይም ቻርለስ ቴዝ ራስል ወይም ከጆሴፍ እስሚዝ አስበልጦ የሚመርጠው? ዞሮ ዞሮ ሁሉም መንገዶች የሚያደርሱት ወደ መንግስተ ሰማይ አይደለም እንዴ? በመሰረቱ ሁሉም ሃይማኖቶች አንድ አይደሉም እንዴ? እንደ እውነቱ ከሆነ ሁሉም ሃይማኖቶች ወደ መንግስተ ሰማይ አያመሩም። ሁሉም መንገዶች ወደ ኢንዲያና መቼም አያደርሱም።
ኢየሱስ ብቻውን በእግዚአብሔር ሥልጣን ይናገራል።
1/  ምክንያቱም ኢየሱስ ብቻ ነው ሞትን ያሸነፈው። እስካሁን ድረስ መሐመድ፣ ኮንፊሸየስና ሌሎች በመቃብር በስብሰው ይገኛሉ። ነገር ግን ኢየሱስ በራሱ ስልጣን በጨካኙ የሮማውያን መስቀል ከሞተና ከተቀበረ ከሦስት ቀን በኋለ መቃብሩን ፈንቅሎ ተነስቶአል። በሞት ላይ ስልጣን ያለው ማንኛውም ሰው ትኩረታችን ሊስብ ግድ ይላል። ማንም በሞት ላይ ስልጣን ያለው ግለሰብ ሲናገር ልናደምጠው አስፈላጊ ነው። ሞትን ማሸነፍ የቻለ ከፍጥረታት መካከል ማንም የለም። ከሰማይ የመጣው ብቻ ሞትን አሸንፎ ወደሰማይ ወጥቷል።ስለዚህ እንዲህ ያለው አሸናፊ የተናገረው የእምነት መሠረት መሆን አለበት። ሰው ሟች መሆኑን ያውቃል። ሟች ደግሞ ከሞት ለማምለጥ የሚችለው በሞት ላይ ባለሙሉ ሥልጣን በሆነ ክንድ ላይ ሲያርፍ ነውና ኢየሱስን ማመን የግድ ይለዋል። ሌላ ማንም አዳኝ የለም።
2/ የኢየሱስ ሕይወትና ትንሣዔ ምስክር ያለውና እውነት ነው።  የኢየሱስን ትንሣዔ የሚደግፈው መረጃ የሚያጥለቀልቅ ነው።   ሮማውያንና ሰቃልያኑ ካህናት የኢየሱስን መቃብር ማስጠበቅ ያስፈለጋቸው «በሦስተኛው ቀን እነሳለሁ» ያለውን ቃሉን ይዘው እንጂ የሞተ ሰው መቃብር ስለሚጠበቅ አልነበረም።  አዎ ትንሣዔውን ለመከላከል ወታደሮች ከመቃብሩ ማንም እንዳይወጣ፤ ወደመቃብሩም ማንም እንዳይደርስ አድርገው አስጠብቀው ነበር። ነገር ግን የመቃብሩ ቦታ ባዶ ሆኗል!  እንደተናገረው አልተነሳም እንዳይሉ የኢየሱስ ጠላቶች ያን ሁሉ ስለትንሣዔው የተነዛውን ወሬ ለማክሸፍ የበሰበሰውን አካሉን በማቅረብ በቀላሉ ያስታግሱት ነበር። ግን አልቻሉም፤ መላው ሲጠፋባቸው ደቀመዛሙርቱ ሬሳውን ሰርቀውት ይሆን? አሉ።  ከሐዋርያቱ መካከል ከዮሐንስ በስተቀር ሌሎቹ የሸሹት በጊዜ ነው። የሸሹ ሰዎች ተመልሰው ከሮማ ወታደሮች ጋር ተዋግተው ሰረቁት ማለት የማይመስል ነገር ነው። ቀላሉ ሃቅ ግን የኢየሱስ ትንሳኤ እንዲሁ ተነግሮ ተገልፆ የሚያልቅ መች ሆነና! ትንሣዔውን ያለምስክር ያልተወ ኢየሱስ ግን በአንድና በሁለት ሰዎች ፊት ብቻ ሳይሆን በአምስት መቶ ሰዎች ፊት ትንሣዔውን አስመስክሯል።

«መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ፥ለኬፋም ታየ በኋላም ለአሥራ ሁለቱ፤ ከዚያም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታየ፤ ከእነርሱም የሚበዙቱ እስከ አሁን አሉ አንዳንዶች ግን አንቀላፍተዋል፤ከዚያም በኋላ ለያዕቆብ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ ታየ፤ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ» 1ኛ ቆሮ 15፤4-8

ስለዚህ ሰዎች ኢየሱስን ለማመን የሚያስችላቸው በቂ የእምነት ማስረጃ ስላላቸው ነው። በዚህ ምድር ላይ ካሉ ሃይማኖቶች ውስጥ እንደኢየሱስ ሞትን ያሸነፈ፤ ትንሣዔውን በምስክር ያረጋገጠ ማንም የለም። ስለዚህ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው ማንም ሰው ሊደመጥ ይገባል። ኢየሱስ በሞት ላይ ያለውን ሥልጣን አረጋግጧል። ስለዚህ የሚናገረውን መስማት ይገባናል። ለድነት ብቸኛው መንገድ ኢየሱስ መሆኑን ራሱ ይናገራል።(ዮሐንስ 14፡ 6)። ካሉትም ብዙ መንገዶች አንዱ አይደለም። ኢየሱስ ብቸኛ የድነት መንገድ ነው። ሌላ መንገድ ሁሉ በትንሣዔና በሕይወት ላይ ሥልጣን የሌለው የሞት መንገድ ነው።
3/ ኢየሱስ ከሸክም ያሳርፋል። በዚህ ምድር ላይ ከሸክም አሳርፋችኋለሁ ብሎ ቃል የገባ አንድም ሥጋ ለባሽ የለም። ይህ ብቸኛ ኢየሱስ እንዲህ ይላል “እናንተ ደካሞች፤ ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፣ ወደእኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ።” (ማቴዎስ 11፡ 28)። ሕይወትም አስቸጋሪ ነው። ብዙዎቻችን ደምተናል፣ ቆስለናል፣ ጦርነትንም እንፈራለን። ዓለምም አስጨናቂ እየሆነች ነው። ስለዚህ የሚያሳርፈንን ብንፈልግ ተገቢ ነው። ነገር ግን ከኢየሱስ በቀር ሸክም የከበዳችሁ ወደእኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ ያለ ማንም ሌላ የለም። በትንሣዔውና በሕይወቱ የታመነ ኢየሱስ ይህንን የማለት ብቃት ስላለው በእርሱ ላይ ማረፍ ከአስጨናቂው ዓለም ለመዳናችን ዋስትናችን ነው።
ስለዚህ ምን ትፈልጋላችሁ? ከኃጢአት፤ ከድካም፤ ከተስፋ መቁረጥ በንስሐ መታደስ ወይስ  የአንዱ ሃይማኖት አባል በመሆን ብቻ መኖር? ሕያው የሆነ አዳኝ ወይስ “ከሞቱት በርካታ ነቢያት ወይም ጻድቅ” አንዱን ተስፋ ማድረግ? ትርጉም ያለው ግንኙነት ወይስ ተራ የአምልኮ ሥነ-ሥርዓት መከተል?
ኢየሱስ አማራጭ ሳይሆን ምርጫ ነው! ሃይማኖት ማለት አንድ መንፈሳዊ ድርጅት ወይም የአንዱ ተቋም ስያሜና የዚያ አባል ሆኖ መኖር ማለት አይደለም።  ከእግዚአብሔር  አብ ጋር ትርጉም ያለው ግንኙነት ትፈልግ እንደሆን ሃይማኖትህ ኢየሱስን ማመን ነው። «በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው»  ይላል መጽሐፍ። (ዮሐንስ 3፡ 36) አንዳንዶች ይህንንማ እናምናለን ነገር ግን ትክክለኛው እምነት ያለው በኛ ሃይማኖት ውስጥ ስለሆነ አባል ሁነን ይላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ በማኅበር ስለመጸለይ ይነግረናል እንጂ ኢየሱስን ለማመን የዚህ ወይም የዚያ ሃይማኖት ተቋም አባል ሁን የሚል ትዕዛዝ የለውም። ኢየሱስ በሱ የሚያምኑ ሁሉ እንዲድኑ እንጂ የሃይማኖት ድርጅት ሊመሠረት አልመጣም።

«የምንለምነውንም ሁሉ እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመነውን ልመና እንደ ተቀበልን እናውቃለን» 1ኛ ዮሐ 5፤15

(www.Gotquestions.org)ተሻሽሎ የተወሰደ

Friday, August 1, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

(ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ) ክፍል ሁለት

የሰው  ፍጥረት  ታካችና  ደካማ  መሰለኝ፡፡ ሰው  ግን ፍቅርን  ቢወዳትና  በጣም  ቢያፈቅራት  የተሸሸገውንም  ፍጥረትን  ቢያውቅ ይወዳል፡፡ ይህም  ነገር  እጅግ  ጥልቅ  ነውና  በትልቅ  ድካምና  ትዕግስት  ካልሆነ  በስተቀር  አይገኝም፡፡ ጠቢቡ ሰለሞን፡ “ከፀሐይ  በታች  ስለተደረገው  ሁሉ  ጥበብን  ለመፈለግና  ለመመርመር  ልቤን  ሰጠሁ፡፡  እግዚአብሔር  ለሰው  ልጆች  እንዲደክሙበት የሰጣቸውን  ክፉ  ስራ  አየሁ”ይላል፡፡

   ስለዚህ  ሰዎች  ሊመረምሩት  አይፈልጉም፡፡  ሳይመረምሩ  ከአባቶቻቸው  የሰሙትን  ማመን  ይመርጣሉ፡፡  ነገር  ግን እግዚአብሔር  ሰውን  የምግባሩ  ጌታ  ክፉ  ወይም  መልካም  የፈለገውን  እንዲሆን  ፈጠረው፡፡  ሰውም  ክፉና  ዋሾ  መሆንን  ቢመርጥ ለክፋቱ የሚገባውን  ቅጣት  እስኪያገኝ  ድረስ  ይችላል፡፡ ነገር  ግን  ሰው ሥጋዊ  ነውና  ለሥጋው  የሚመቸውን  ይወዳል፡፡ ክፉ  ይሁን  መልካም  ለስጋው  ፍላጎት የሚያገኝበትን  መንገድ  ሁሉ  ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር  ሰው  የፈለገውን  እንዲሆን  ለመምረጥ  መብት  ሰጠው  እንጂ  ለክፋት  አልፈጠረውም፡፡ ስለዚህ  መምረጥ  ክፉ  ቢሆን  ለቅጣት  መልካም  ቢሆን  ደግሞ  የመልካምነት  ዋጋ  ለመቀበል  የተዘጋጀ  እንዲሆን  እድል  ሰጠው፡፡

  በሕዝብ  ዘንድ  ክብርና  ገንዘብ  ለማግኝት  የሚፈልግ  ዋሾ  ሰው  ነው፡፡  ዋሾ  ሰው  ይህን  በሐሰተኛ  መንገድ  ሲያገኝ  እዉነት አስመስሎ ሀሰት  ይናገራል፡፡ ሊመረምሩ  የማይፈልጉ  ሰዎች  እውነት  ይመስላቸውና  በእርሱ  በጽኑ  ሃይማኖት  ያምናሉ፡፡ እስኪ  ሕዝባችን  በስንት  ውሸት  ያምናል?  በጽኑ  ሃይማኖት  ያምናል፡፡  በሃሳበ  ከዋክብትና  በሌላም  አስማት፣  አጋንንት  በመሳብና በመርጨት፣ አስማት በማድረግ፣ በጥንቆላ  ሁሉ  ያምናሉ፡፡ ይህንን  ሁሉ  መርምረው  እውነቱን  አግኝተው  አያምኑም፡፡ ነገር  ግን  ከአባቶቻቸው  ሰምተው ያምናሉ፡፡ እነዚያስ  የፊተኞቹ  ገንዘብና  ክብር ለማግኝት  ካልሆነ በቀር ስለምን  ዋሹ?  እንዲሁ  ህዝብን  ሊገዙ  የሚፈልጉ  ሁሉ  እውነት  እንነግራቸኋለን  እግዚአብሔር  ወደናንተ  ላከን  ይሏቸዋል፡፡  ሕዝቡም  ያምናሉ፡፡
ከነርሱም  በኋላ  የመጡት  እነርሱ  ሳይመረምሩ  የተቀበሏትን  የአባቶቻቸውን  እምነት  አልመረመሩም፡፡  ከዚያ  ይልቅ  ለእውነትና ለሃይማኖታቸው  ማስረጃ  ታሪክን፣ ምልክቶችን ፣ ተዓምራትን  እየጨመሩ እውነት  አስመስለው  አጸኑት፡፡  በነገሩ ሁሉ እግዚአብሔርን  ስም ጨመሩ።  እግዚአብሔርንም የሐሰኞች ተካፋይና  የሐሰት  ምስክር  አደረጉት፡፡

  ጥልቅ   ምርመራ  ስለ  ሙሴና  መሐመድ  ሕግጋት

 ለሚመረምር  ግን  እውነት  ቶሎ  ይገለፃል፡፡  ፈጣሪ  በሰው  ልብ  ያስገባውን  ንጹህ  ልቦና  የፍጥረት  ሕግጋትና  ስርዓትን  ተመልክቶ የሚመረምር  እርሱ  እውነትን  ያገኛል፡፡ ሙሴ  ፈቃዱንና  ሕጉን  ልነግራችሁ  ከእግዚአብሔር  ዘንድ  ተልኬ  መጣሁ  ይላል፡፡ ከሆነ ታዲያ «ሴት በወር አበባ ወቅት የረከሰች ናት» ለምን ይላል? የሙሴ  መጽሐፍ  ከፍጥረት  ሕግ  ሥርዓትና  ከፈጣሪ  ጥበብ  ጋር  አይስማማም፡፡  ከውስጡ  የተሳሳተ  ጥበብ  ይገኛል፡፡ ለሚመረምር  ግን  እውነት  አይመስለውም፡፡  በፈጣሪ  ፈቃድና  በፍጥረት  ህግ  የሰው  ልጅ  እንዳይጠፋ  ልጆችን  ለመውለድ  ወንድና  ሴት  በፍትወተ  ሥጋ  እንዲገናኙ  ታዟል፡፡  ይህም  ግንኙነት  እግዚአብሔር  ለሰው  በሕገ  ተፈጥሮ  የሰጠው  ነው፡፡ እግዚአብሔርም  የእጁን  ሥራ  አያረክስም፡፡ እግዚአብሔር  ዘንድ  እርኩሰት  ሊገኝ  አይችልም፡፡  ፈጣሪ የፈጠረውን መልሶ አያረክሰውም እላለሁ። 

  እንደገናም  የክርስቲያን  ሕግ  ለማስረጃዋ  ተአምራቶች ተገኝተዋልና  ከእግዚአብሔር  ናት  ይላሉ፡፡  ነገር  ግን  የወሲብ  ሥርዓት  የተፈጥሮ  ሥርዓት  እንደሆነ  ምንኩስና  ግን  ልጆች ከመውለድ  ከልክሎ  የሰውን  ፍጥረት  አጥፍቶ  የፈጣሪን  ጥበብ  የሚያጠፋ  እነደሆነ  ልቦናችን  ይነግረናልና  ያስረዳናል፡፡ የክርስቲያን  ሕግ  ምንኩስና  ከወሲብ  ይበልጣል  ብትል  ሐሰት  ትናገራለችና  ከእግዚአብሔር  አይደለችም፡፡  የፈጣሪን  ሕግ  የሚያፈርስ  እንዴት  ከጥበብ በለጠ ?  ወይስ  የእግዚአብሔርን  ስራ  የሰው  ምስክር ሊያስተካክለው ይቻለዋልን ? ሰዎች ግን ሳይመረምሩ ምንኩስና ከጋብቻ ትበልጣለች ይላሉ። ዘርን የሰጠ ፈጣሪ ዘር አያስፈልግም አይልም። ቀጣፊዎች በእግዚአብሔር ስም  እውነት አስመሰሉት እንጂ።

እንዲሁም  መሐመድ  የማዛችሁ  ከእግዚአብሔር  የተቀበልኩትን  ነው  ይላል፡፡  መሐመድን  መቀበል  የሚያስረዱ  የተዓምራት  ፀሐፊዎች  አልጠፉምና  ከሱም  አመኑ፡፡ እኛ  ግን  የመሐመድ  ትምህርት  ከእግዚአብሔር  ሊሆን  እንደማይችል  እናውቃለን፡፡ የሚወለዱ  ሰዎች  ወንድና  ሴት  ቁጥራቸው  ትክክል  ነው፡፡ በአንድ  ሰፊ  ቦታ  የሚኖሩ  ወንድ  ሴት ብንቆጥር  ለእያንዳንዱ  ወንድ አንዲት  ሴት  ትገኛለች  እንጂ  ለአንድ  ወንድ  ስምንት  ወይም  ዐሥር  ሴቶች  አይገኙም፡፡ የተፈጥሮ  ህግም  አንዱ  ከአንዲት  ጋር እንዲጋቡ  አዟል፡፡ አንድ  ወንድ  ዐሥር  ሴት  ቢያገባ  ግን  ዘጠኝ  ወንዶች  ሴት  የሌላቸው  ይቀራሉ፡፡ ይህም  የፈጣሪን  ስርዓትና  ሕገ ተፈጥሮን  የጋብቻንም  ጥቅም  ያጠፋል፡፡ አንድ  ወንድ ብዙ ሴቶች ሊያገባ  ይገባዋል  ብሎ  በእግዚአብሔር  ስም  ያስተማረ  መሐመድ  ግን  ትክክል  ነው አልልም፡፡ ከእግዚአብሔር  ዘንድ  አልተላከም፡፡  ጥቂት  ስለጋብቻ  ሕግ  መረመርኩ  ፡፡ ከመጀመሪያም  ለአዳም አንድ ሴት ከመፍጠር ይልቅ ዐሥር ሴት ያልፈጠረለት ለምንድነው? ይህን የፈጣሪ ሕግ  ሳይመረምሩ የመሐመድን  ሕግ መቀበል ስህተት ነው። ከእግዚአብሔር እንደተገኘ  ብመረምርም  በህገ  ኦሪትና  በክርስትናና  በእስልምና  ሕግ  ፈጣሪ  በልቦናችን  ከሚገልጽልን  እውነት  እና  እምነት ጋር የማይስማማ ብዙ ነገር አለ  አልኩ።

    ፈጣሪ  ለሰው  ልጅ  ክፉና  መልካም  የሚለይበት  ልቦና  ሰጥቶታል፡፡  «በብርሃንህ  ብርሃንን  እናያለን»  እንደተባለውም  የሚገባውን  የማይገባውን  ሊያውቅ፣  እውነትን  ከሐሰት እንዲለይ ነው፡፡ ስለዚህ የልቦናችን  ብርሃን  እንደሚገባ  በእርሱ  ብናይበት  ሊታይልን አይችልም፡፡ ፈጣሪያችን ይሄን ብርሃን  የሰጠን  በርሱ  እንድንድን  ነው እንጂ  እንድንጠፋ  አይደለም። የልቦናችን  ብርሃን  የሚያሳየን  ሁሉም  ከእውነት  ምንጭ  ነው፡፡ ሰዎች  ከሐሰት  ምንጭ  ነው  ቢሉን ግን  ሁሉን  የሰራ  ፈጣሪ  ቅን እንደሆነ  ልቦናችን  ያስረዳናል፡፡ ፈጣሪ  በመልካም ጥበቡ  ከሴት  ልጅ  ማህጸን  በየወሩ  ደም  እንዲፈስ አዟል፡፡  ሙሴና  ክርስቲያኖች  ግን  ይህን የፈጣሪ  ጥበብ  እርኩስ  አደረጉት፡፡
እንደገና  ሙሴ  እንዲህ  ያለችው  ሴት ከተቀመጠችበት የተቀመጠውንም፤ የተገናኛትንም  ያረክሳል፡፡  ይህም  የሙሴ  ህግ  የሴትን  ኑሮ  በሙሉና  ጋብቻዋን  ከባድ አድርጎታል፡፡ የመራባትንም  ህግ  አጥፍቷል፡፡ ልጆችንም  ከማሳደግ  ከልክሎ  ፍቅርንም  ያፈርሳል፡፡ ስለዚህ ይህ  የሙሴ  ሕግ  ሴትን  ከፈጠረ  ሊሆን  አይችልም  እላለሁ፡፡ «ሞተውን ሰው በድን የነካ ሁለመናውን ባያጠራ የእግዚአብሔርን ማደሪያ ያረክሳል ያ ሰው ከእስራኤል ዘንድ ተለይቶ ይጠፋል » የምትለው የሙሴ ሕግ ሞትን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር አይደለችም። እንደገናም  የሞቱትን  ወንድሞቻችንን  ልንቀብራቸው  ተገቢ መሆኑን ልቦናችን  ይነግረናል፡፡ በድኖቻቸውም  በሙሴ  ጥበብ  ካልሆነ  በስተቀር  ከመሬት  የተፈጠርንበት  ወደ መሬትም  ልንገባበት  በፈጣሪያችን  ጥበብ  እርኩሳን  አይደሉም፡፡ ነገር  ግን  ለፍጥረት  ሁሉ  እንደሚገባ  በትልቅ  ጥበብ  የሰራ  እግዚአብሔር ሥርዓቱን  አያረክሳውም፡፡ ሰው  ግን  የሐሰትን  ቃል  እንዲያከብር  ብሎ  ሊያረክሰው ይፈልጋል፡፡

  እንደዚሁም  እግዚአብሔር  የከንቱ  ነገር  አያዝም፡፡  «ጥረህ ግረህ በላብህ ወዝ ብላ» ያለው አምላክ ይህን  ብላ፣ ይህን  አትብላ፣ ዛሬ ብላ፣ ነገ  አትብላ  አይልም፡፡ ለክርስቲያኖች  እንደሚመስላቸውና  የጾም  ሕግጋት  እንደሚጠብቁ  ሥጋን  ዛሬ  ብላ፤  ነገ  አትብላ  አይልም፡፡  ለክርስቲያኖች እንደሚመስላቸውና  የጾም  ሕግጋት  እንደሚጠብቁ  ሥጋን  ዛሬ ብላ ነገ ግን  አትብላ  አይልም፡፡  እስላሞችንም  እግዚአብሔር  ለሊት  ብሉ  ቀን  አትብሉ  ብሎ  ይሄንና  የመሳሰሉትን  አይላቸውም፡፡ የፍጥረታችንን  ጤና  የማያውክ ነገር ሁሉ  ልንበላ  እንደሰለጠንን  ልቦናችን  ያስተምረናል።  አንድ  የመብል ቀን፤ አንድ  የጾም  ቀን ግን  ጤናን  ያውካል፡፡ የጾም ህግ መብላትን  ለሰው  ሕይወት  ከፈጠረና  ልንበላቸው  ከፈቀደ  ፈጣሪ የወጣ  አይደለም፡፡ በልተን ልናመሰግነው  እንጂ  በረከቱን  ልናርም አይገባንም፡፡ ሕገ  ፆም  የሥጋን  ፍትወት ለመግደል  የተሰራ  ነው  የሚሉም  ቢኖሩ  ፍትወተ  ሥጋ  ወንድ  ወደ ሴት  ሊሳብ  ሴትም ወደ  ወንድ  ልትሳብ  የፈጣሪ ጥበብ  ነውና  እርሱ  ፈጣሪ  በሰራው  በታወቀ  ማጥፋት  አይገባም  እላለሁ፡፡  ፈጣሪያችን  ይህን ፍትወት ለሰው፤  ለእንስሳት  ሁሉ  በከንቱ  አልሰጠም፡፡ ነገር ግን  ለዚህ  ዓለም  ሕይወትና  ለፍጥረት  የተሰራለት  መንገድ  ሁሉ  መሠረቱ  ሆኖ እንዲቆይ  ይህ  ፍትወት  ለሰው  ልጅ  ተሰጠ፡፡ አስፈላጊያችንን ልንበላ  ይገባናል፡፡ በእሁድ  ቀንና  በበዓል  ቀናት  በአስፈላጊው  ልክ  የበላ  እንዳልበደለ  እንዲሁ  በአርብ  ቀንና  ከፋሲካ  በፊት  ባሉት  ቀናት  ለክቶ  የሚበላ  አልበደለም፡፡  እግዚአብሔር  ሰውን  በሁሉ  ቀንና  በሁሉ  ወራት  ካስፈላጊ  ምግብ  ጋር  አስተካክሎ  ፈጥሮታል፡፡  አይሁድ፣  ክርስቲያንና  እስላም  ግን  የፆምን  ሕግ  ባወጡ  ጊዜ ይህን  የእግዚአብሔር  ሥራ  ልብ  አላሉም፡፡ እግዚአብሔር  ፆምን  ሰራልን፤  እንዳንበላም  ከለከለን  እያሉ ይዋሻሉ፡፡ እግዚአብሔር ፈጣሪያችን  ነው፡፡ ግን  የምንበላውን  ምግባችንን   እንድንመገበው ሰጠን  እንጂ  እርሱን  ልናርም  አይደለም፡፡  በሚያስተውል ልቡናችን  ለክተን  መኖር የኛ ፈንታ ነው።

 ስለ  ሃይማኖቶች    መለያየት

 ሌላ ትልቅ  ምርመራ  አለ፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በእግዚአብሔር  ዘንድ  ትክክል  ናቸው፡፡ እርሱም  አንድ  ሕዝብ ለሕይወት፤  አንድ  ሕዝብ ለሞት፤  አንድም  ለምህረት፤  አንድም  ለኩነኔ  አልፈጠረም፡፡  ይህም  አድሎ  በስራው  ሁሉ  ጻድቅ  በሆነ  በእግዚአብሔር  ዘንድ እንደማይገኝ  ልቦናችን  ያስተምረናል፡፡ ሙሴ  ግን  አይሁድን  ለብቻቸው  እንዲያስተምራቸው  ተላከ፡፡ ለሌሎች  ሕዝቦች  ፍርዱ አልተነገረም፡፡  እግዚአብሔር  ስለምን  ለአንድ  ሕዝብ  ፍርድ  ሲነግር  ለሌላው  አልነገረም፡፡  በዚህም  ጊዜ  ክርስቲያኖች  የእግዚአብሔር  ትምህርት  ከኛ  ጋር  ካልሆነ  በስተቀር  አይገኝም  ይላሉ፡፡ አይሁድና  እስላም  የህንድ  ሰዎችም  ሌሎችም  ሁሉ እንደነሱ  ይላሉ፡፡ እንዲሁ  ደግሞ  ክርስቲያኖች  እርስ  በርሳቸው  አይስማሙም፡፡ ካቶሊኮች  እግዚአብሔር  ከኛ  ጋር  ነው  ያለው እንጂ ከናንተ  ጋር አይደለም  ይሉናል፡፡ እኛም  እንዲሁ  እንላቸዋለን፡፡ ሰዎች  እንደምንሰማቸው  ግን  የእግዚአብሔር  ትምህርት  እጅግ  ጥቂቶች  ወደ ሆኑት  እንጂ  ለብዙዎቹ  አልደረሰም፡፡  ከእነዚህ  ሁሉ  ደግሞ  ወደ  ማን  እንደደረሰ  አናውቅም፡፡ እግዚአብሔር  ከፈቀደ ቃሉን  በሰው  ዘንድ  ማጽናት ተስኖት  ነውን?  ሆኖም  ግን  የእግዚአብሔር  ጥበብ  በመልካም  ምክር  ይህ  ነገር  እውነት እንዳይመስላቸው  ሰዎች  በሐሰት  ሊስማሙ  አልተወም፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በአንድ  ነገር  በተስማሙ  ጊዜ  ይህ  ነገር እውነት ይመስላል፡፡ ሰዎች  ሁሉ  በሃይማኖታቸው  ምንም  እንደማይስማሙ  በሃሳብም  ሊስማሙ  አይችሉም፡፡
    እስኪ  እናስብ  ሰዎች  ሁሉ  ሁሉን  የፈጠረ  እግዚአብሔር  አለ  በማለታቸው  ስለምን  ይስማማሉ?  ፍጡር  ያለ  ፈጣሪ  ሊገኝ  እንደማይችል፤ ስለዚህም  ፈጣሪ  እንዳለ እውነት  ነውና  ነው፡፡ ይህ  የምናየው  ሁሉ  ፍጡር  እንደሆነ  የሰው  ሁሉ   ልቦና  ያውቃል ፡፡ ሰዎች ሁሉ በዚህ  ይስማማሉ፡፡  ነገር  ግን  ሰዎች  ያስተማሩትን  ሃይማኖት  በመረመርን  ጊዜ  በውስጡ  ሐሰት  ከእውነት  ጋር  ተቀላቅሎበታል፡፡  ስለዚህ  እርስ  በርሱ አይስማማም፡፡ ሰዎች  እርስ በርሳቸው  አንዱ  ይህ  እውነት  ነው ሲል፤ ሁለተኛው  አይደለም፤  ሐሰት  ነው  ሲል  ይጣላሉ፡፡ ሁሉም  የእግዚአብሔርን  ቃል  የሰው  ቃል  እያደረጉ  ይዋሻሉ፡፡  እንደገናም  የሰው  ሃይማኖት  ከእግዚአብሔር  ብትሆን  ክፉዎችን   ክፉ  እንዲያደርጉ  እያስፈራራች  መልካም  እንዳያደርጉ ትፈቅድላቸው  ነበር፡፡ ደጎችንም በትዕግስታቸው ታጸናቸው ነበር፡፡

  ለኔም እንዲህ ያለው  ሃይማኖት  ባሏ  ሳያውቅ  በምንዝርና  የወለደች ሴትን ትመስለኛለች፡፡ ባሏ ግን  ስለመሰለው  በሕፃኑ  ይደሰታል፡፡ እናቲቱንም ይወዳታል፡፡ በዝሙት  እንደወለደችው  ባወቀ  ጊዜ  ግን  ያዝናል፡፡ ሚስቱንም  ልጅዋንም  ያባርራል፡፡ እንዲሁም  እኔም  ሀይማኖቴን አመንዝራና  ዋሾ  መሆኑዋን  ካወኩ  በኋላ  ስለርሷ  በዝሙት  ስለተወለዱ   ልጆቿ አዘንኩ ፡፡ እነሱ  በጠብ፣ በማሳደድ፣ በመማታት፣ በማሰር፣ በመግደል  ወደዚህ  ዋሻ  ያባረሩኝ  ናቸው፡፡  ከውሸታቸው ጋር ስላልተባበርኩ ጠሉኝ። ነገር  ግን  የክርስቲያን  ሃይማኖት  ሀሰት  ናት እንዳልል  በዘመነ  ወንጌል  እንደተሰራ  ክፉ  አልሆነችም፡፡  የምህረትን  ሥራ  በሙሉ  እርስ   በርስ መፋቀርን ታዛለች፡፡  እነሱ ግን ፍቅርን ፈጽሞ አያውቋትም። በዚህ ዘመን  ግን  የሀገራችን  ሰዎች  የወንጌልን  ፍቅር  ወደ ጠብና  ኃይል  ወደ  ምድራዊ  መርዝ  ለወጡት፡፡  ሃይማኖታቸውን  ከመሰረቱ  ዐመጻ  እየሰሩ  ከንቱ  ያስተምራሉ፡፡  በሐሰትም  ክርስቲያኖች ይባላሉ፡፡