Monday, June 30, 2014

በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሊቀጳጳስ በብፁዕ አቡነ ዳንኤል ላይ የገዳሙ መነኮሳት አድመው በረሃብ እየቀጧቸው መሆኑ ተሰማ!



( ምንጭ፤ አባ ሰላማ ድረ ገጽ)



በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቀጳጳስ በሆኑት በብፁዕ አቡነ ዳንኤል ላይ አባ ገብረ ወልድ በተባሉ መነኩሴ አሳዳሚነት ሊቀጳጳሱ ላይ ልዩ ልዩ የአድማ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆናቸውንና ሊቀጳጳሱ ላይ አደጋዎች መደቀናቸውን ከስፍራው የደረሰን ዜና አመለከተ፡፡ ብፁዕነታቸው የሲኖዶስን ስብሰባ ለመካፈል ከመጡ ወዲህ ተመልሰው ቢመጡ አናስገባቸውም በሚል የተጀመረው አድማ ምግብ እንዳይቀርብላቸው፣ ሾፌራቸውም መኪናቸውን እንዳያንቀሳቅስ እስከ ማሳደም የደረሰ አሳዛኝ እርምጃ እየተወሰደባቸው መሆኑን ምንጮቻችን የገለጹ ሲሆን ይህም ድርጊት በአንዳንድ ክፉ ቀን ግብጻውያን መነኮሳት ኢትዮጵያውያን መነኮሳት በበሽታና በረሃብ እንዲያልቁ ለማድረግ በራቸውን ዘግተውባቸው እርዳታ ሳያገኙ እንዲሞቱና ገዳማቶቻችን ያለ ሰው እንዲቀሩ ለማድረግ ከሚጠቀሙባቸው በጭካኔ የተሞሉ ስልቶች ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ ከዚህ እርምጃ በስተጀርባ የማን እጅ እንዳለ ለጊዜው የታወቀ ነገር ግን የለም፡፡


ብፁዕ አቡነ ዳንኤል የስኳር በሽተኛ ከመሆናቸው አንጻር በረሃብ እንዲቀጡ አድማ መመታቱ እጅግ አሳዛኝ ተግባር መሆኑ እየተነገረ ሲሆን፣ በብፁዕነታቸው በኩል እስካሁን ነገሩን በትዕግስት ማሳለፋቸው የቤተክርስቲያን ስም በዚህ መንገድ እንዳይነሣ ከማሰብ እንደሆነ የተናገሩት ምንጮች፣ ብፁዕነታቸው የዲፕሎማት ፓስፖርት ያላቸውና እንደዲፕሎማት ስለሚታዩ ለሚመለከተው አካል አቤት ቢሉ ይህን ባደረጉት መነኮሳት ላይ ሕጋዊ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚችል ስለጉዳዩ የሚያውቁ ይናገራሉ፡፡
በአባ ገብረወልድ የተመራው የአድማ ማኅበር እንዲህ ለማድረግ ያነሳሳው ምን እንደሆነ እስካሁን የታወቀ ነገር ባይኖርም ብፁዕነታቸው የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ ሆነው ከተሾሙ በኋላ በዚህ ወቅት ሊሆን የማይችለውን በጎልጎታ ምዕራፍ ስምንት የተባለውን ቦታ ለቤተክርስቲያናችን በመግዛት ትልቅ ስራ መስራታቸው ይነገራል፡፡ የመነኮሳቱ ቅናትና አድማ የተነሳው ከዚህ መልካም ስራ ሳይሆን እንደማይቀር አንዳንዶች ይገምታሉ፡፡ የመነኮሳቱ ማኅበርም አይዟችሁ ያላቸው አካል ሳይኖር አይቀርም የሚል ግምት አለ፡፡

Sunday, June 29, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!


(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

ክፍል አራት

አንዳንድ  ሰዎች  ማርያምን  እንደሚያከብሩ  እንጂ  እንደማያመልኩ  የሚናገሩት  የቃል  ጨዋታ  ነው።  መጽሐፍ  ቅዱስን  እየጠሉ  ራዕየ ማርያምን  በቃል  እየሸመደዱ  “እንወዳታለን  እንጂ፥  እናከብራታለን፥  የጸጋ ስግደት  እናቀርብላታለን  እንጂ  . . .  አናመልካትም”  ማለት  የራስ  ድለላ ነው።  እንዲህ  ከላይ  እንደጠቀስኳቸው  ያሉቱ  ምዕራፎች  የሚናገሩት  እየተከበረች  ሳይሆን  እግዚአብሔርን  ተክታ  እየተመለከች  መሆኗን  ነው። ደግሞ  ማክበርስ  ከሆነ  መከበር  የሚገባው  ማን  ብቻ  ነው?  ይህ  እኮ አንድን  ባለሙያ  ሰው  ለማድነቅና  ለማመስገን  ከስዕሎቹ   ወይም  ከቅርጾቹ  አንዱ  ፊት  ሄጄ  ለሥራው  ውጤት  ምስጋናና  ውዳሴን  ብደረድር እንደማለት  ነው።  ይህ  እንዲህ  በሚለው  በሮሜ  1፥25  ቃል  ፈጽሞ  የተወገዘ  ነው፤  ይህም  የእግዚአብሔርን  እውነት  በውሸት  ስለ ለወጡ በፈጣሪም  ፈንታ  የተፈጠረውን  ስላመለኩና  ስላገለገሉ  ነው፤  እርሱም ለዘላለም  የተባረከ  ነው፤  አሜን።  ማክበር  ወይም  ማምለክ  የቃል  ጉዳይ አይደለም።  መስተዋል  ያለበት  ተግባሩና  ድርጊቱ  ነው።  ለእግዚአብሔር ብቻ  እንጂ  ለሌላ  ለማንም  መደረግ  የሌለበትን  ነገር  ለሌላ  ማድረግ፤ ለምሳሌ፥  ጸሎትንና  ልመናን፥  ውዳሴና  ስግደትን  ማቅረብ  ማምለክ  እንጂ ሌላ  አይደለም። በአፌ  አላመልካትም  ብል  እና  ውዳሴና  ልመናን ስዕለትንና  ስግደትን  ባቀርብላት  ራሴን  እየደለልኩ  ነኝ።  ወይም  በእርሷ መጋረጃ  ውስጥ  እየተደበቅሁ  ከእውነት  እየሸሸሁ  ነኝ።  ራእ.  4፥10-11፤ 15፥3-4፤  ነህ.  9፥6  ሁሉ  ሊሰግዱለት፥  ሊያከብሩት፥  ሊያመልኩት፥ ሊወድሱት፥  ሊያመሰግኑት  የተገባ  ብቻውን  የሆነ  አምላክ  እግዚአብሔር  ብቻ  መሆኑን  ከሚነግሩኝ  ጥቅሶች  ጥቂቱ  ናቸው።

4.  የተፈናቀለ  ታሪክ።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ታሪክ  የሚያውቃቸው፥  በታሪክ  ውስጥ  ስማቸው  የተጠቀሰና  ዘጋቢዎች  ያወሷቸው፥  ራሳቸውም ታሪካቸውን  የጻፉ  በንጽጽር  እውነቱን  ማረጋገጥ  የሚቻልባቸው  ሦስት ሰዎች  ተጠቅሰዋል።  መጽሐፉ  እነዚህን  የመሰሉ  ታሪካዊ  ገጸ  ባህርያትን  የከተተው  እና  አንድ  ሁለት  ምዕራፎች  ውስጥ  ዓመተ  ምሕረቶችን  ያስገባው  ታሪካዊ  ስርና  መሠረት  ያለው  ለመምሰል  ይህናል  ብዬ እገምታለሁ።  ይህ  መጽሐፍ  እነዚህን  ሰዎች  ሊጠቅሳቸው  ከደፈረ  እኔም ከታሪክ  አንጻር  ልጥቀሳቸው።  እነዚህ  ሰዎች  ንጉሥ  ማርቆስ፥  ዮሐንስ  አፈወርቅ፥  እና ዮስጢን  ሰማዕት ናቸው። ኋላ ላይ  ጥጦስም  ወንበዴ ሆኖ ተጠቅሶአል። ግን ይህ ጥጦስ ኋላ ኢየሩሳሌምን  ያወደመው  ይሁን  ወይም ሌላ  ቀጣይ  ታሪኩ  በዚህኛው  ተአምረ  ማርያም  ውስጥ  አልተነገረም።
ሦስቱን ግን እንመልከት።

ሀ.  ዮሐንስ  አፈወርቅ። 

ታሪኩን  ከእንግሊዝኛ  መዛግብት  የምታውቁ  በተጨማሪ  ከሌላ  ምንጮች  ለመመርመር  ለምትሹ  ይህ  ሰው  እንግሊዝኛው  አጠራር  John  Chrysostom  የሚባለው  ነው።  የዮሐንስ  አፈወርቅ  ተአምረ  ማርያምኛ  ታሪክ  በምዕ.  48  ተጽፎአል።  ታሪኩ  በአጭሩ ምዕመናንን  ሥጋ  ወደሙን  ሲቀበሉ  አንዲት  ሴት  በመርገመ  ደሟ ሳለች  መጣች።  ሕዝቡም  የመንፈስ  ቅዱስ  ረድዔት  እንደራቃት  አውቀው  ወደ  ንስጥሮስ  ፊት  አመጧት።  ጠይቆ  ከተረዳ  በኋላ  ራቁቷን  ተዘቅዝቃ  እንድትሰቀልና  ሕዝቡም  በኀፍረተ  ሥጋዋ  ጢቅ  እንዲሉ  አዘዘ።  እንደ ተአምረ  ማርያም  ጸሐፊ  ንስጥሮስ  ይህን  ያደረገው  እግዚአብሔር  እንዲህ  ከመሰለ  ቦታ  የሚወለድ  እንደሆነ  የሚያምን  የተረገመ  ነው  አሰኝቶ  ነው። ዮሐንስ  የሚባል  ቄስ፥  “እኔ  እግዚአብሔር  በሴት  ሥጋ  እንደተወለደ  አምናለሁ”  ብሎ  ኃፍረተ  ሥጋዋን  ባፉ  ሳመ።  በዚህ  ጊዜ  የማርያም  ስዕል በቤተ  መቅደስ  ውስጥ  ነበረችና፥  “አፈወርቅ”  ብላ  ጠራችው።  ቄሱ ዮሐንስ አፈወርቅ  የተባለው  እንዲህ ነው። ይህ  ምዕራፍ  የንስጥሮስን  ክፋት  ለመግለጥና  ማርያምን  ያለስፍራ ለማግነን  ተብሎ  ረጅም  ርቀት  የተሄደበት  ትረካ  ነው።  መርገመ  ሴትን  አርክሶ  ሥጋ  ወደሙን  ከከለከለ  ኀፍረተ  ሥጋን  ማየትና  በላዩ  መትፋት ዮሐንስን  ከማስመስገን  ይልቅ  የአድራጊዎችን  ሁሉ  ኅሊናን  አያረክስም?  ንስጥሮስ  ኋላ  በ431  በተደረገው  በኤፌሶኑ  ጉባኤ  እርሱም  ትምህርቱም የተወገዙበትን  ክርስቶስ  ሁለት  አካል  የሚል  ትምህርትን  ያስተማረ  ሰው ነው።  ለዚህ  ምላሽ  ሆኖ  ኋላም  በክርክር  የቆየ  የሁለት  ባህርይ (dyophysitism)  እና  አንድ  ባህርይ  (monophysitism)  ጉዳይ ቀጥሎአል።  ሁለት  ባህርይ  ኢየሱስ  ክርስቶስ  አንድ  አካል  ሁለት  ባህርይ ሲል  ተዋህዶ  የኢየሱስ  ስብእና  በመለኮትነቱ   የተዋሃደ  ወይም  ተዋህዶ  ነው  የሚሰኘው  ንድፈ  አሳብ  ነው።  የንስጥሮስ  ትምህርት  ግን  ኢየሱስን  ሁለት  ባህርይ  ሳይሆን ሁለት  አካል  የሚያደርግ  ነው።

 ንስጥሮስ  የማርያምን  ወላዲተ  አምላክነት  (θεοτόκος  ቴኦቶኮስ  መሆን)  የሚቃወም  ሰው  ነው።  ማርያም  ቢበዛ  ሥጋ  የለበሰው  ክርስቶስ  እናት (ክሪስቶቶኮስ)  እንጂ  የአምላክ  ወይም  የእግዚአብሔር  እናት  መባል የለባትም  ያለ  ሰው  ነው።  θεοτόκος  ባለፈው  መጣጥፍ  በመጠኑ የጠቀስኩት  ወላዲተ  አምላክ  ተሰኝቶ  በስሱ  የተተረጎመ  ቃል  ይሁን  እንጂ ትርጉሙ  ከዚህ  የጠለቀ  ነው።  ቀጥተኛ  ትርጉሙ  “የአምላክ  ተሸካሚ፥ የአምላክ  አምጪ፥  አምላክን  ያመጣች፥  ወይም  እንዲመጣ  ያደረገች”  (bringer forth of God)  ማለት  ነው።  Theotokosን  ያጸደቀው  በ431  የተደረገው  የኤፌሶኑ  ጉባኤ  ነው።  ከዚያ  በኋላ  ነው  የማርያም  ስዕሎች ስፍራ  ሊያገኙ  የበቁት።  ቀድሞ  ስዕሎች  የነበሩ  ቢሆኑም  ከስነ  ጥበብ አንጻር  የሚታዩ  እንጂ  ከአምልኮ  ጋር  የተቆራኙ  አልነበሩም።  ኋላ ንስጥሮስ  በስደት  በአንጾኪያ፥  በዐረቢያ  እና  በግብጽ  ኖሮ  በ451 ሞቶአል። 12 የንስጥሮስ  ትምህርት  ዋና  ስሕተት  በክርስቶስ  የመስቀል  ላይ ሞት  ከሁለቱ  አካላት  አንዱ  ሰው  የሆነው  አካል  ብቻ  ከሆነ  የሞተው ለኃጢአት  የተከፈለውን  ዋጋ  መለኮታዊ  ልቀት  ያሳጣዋል የሚል ነው።

ወደ  ዮሐንስ  አፈወርቅ  ስንመለስ፥  ይህ  ሰው  በታሪክ  በጣሙን  የታወቀ ሰው  ነው።  ከሰበካቸው  ስብከቶች  600  ያህል  በጽሑፍ  እና  ወደ  200  ደብዳቤዎቹ  እስከዛሬ  ተጠብቀው  ይገኛሉ።  እንዲህ  እንደ  ተአምረ  ማርያሙ  የመሰለ  ታሪክ  ግን  ከቶም  የለም።  ዮሐንስ  ነበልባል  የሆነ  ሰባኪ ነው።  እነዚህ  ስብከቶቹ  ናቸው  አፈወርቅ  የሚል  ቅጽል  እንዲሰጠው  ያደረጉትም።  ዮሐንስ  ከንስጥሮስ  ጋር  በአንድ  ዘመን  የነበረ  ሰው  ነው። ዘመናቸው  በአጭር  ይገናኝ  እንጂ  የሚተዋወቁና  በአንድ  ላይ  ያመለኩ ሰዎች  ግን  አልነበሩም።  ዮሐንስ  ከ347-407  ዓ.  ም.  13 ንስጥሮስ  ደግሞ ከ386-451  ዓ.  ም.  የኖሩ  ናቸውና  ዘመናቸው  በ21  ዓመታት  ብቻ ይገናኛል።  ንስጥሮስ  ሲወለድ  ዮሐንስ  39  ዓመቱ  ሲሆን  ዮሐንስ  ሲሞት ደግሞ  ንስጥሮስ  ገና  21  ዓመቱ  ነው።  ሁለቱም  በቁስጥንጥንያ  ሊቃነ ጳጳሳት  የነበሩ  ሲሆኑ  ዮሐንስ  ጵጵስና  የተሾመው  በ397  በአምሳ  ዓመቱ ነው።  ንስጥሮስ  የቁስጥንጥንያ  ሊቀ  ጳጳስ  የሆነው  ደግሞ  በ428 (ከ428-431)  ነው።  ዮሐንስ  ከሞተ  ከ21  ዓመታት  በኋላ  ማለት  ነው።  ዮሐንስ  በሚሞትበት  ጊዜ  ንስጥሮስ  ገና  21  ዓመቱ  ነበርና  በተአምረ  ማርያም   እንደ ተጻፈው ጳጳስም  በአንብሮተ  እድ የሚሾም  ሰውም  አልነበረም። ኋላ  የተጻፉ  ምንጭ  የሌላቸው  ታሪኮች  ቢኖሩም  ዮሐንስ  በቀረቤታ  ሲታይ  በተአምረ  ማርያም  የጻፈውን  ማድረጉ  በታሪኮቹ  ሁሉ  የማይገኝ ብቻ  ሳይሆን  እንዲያውም  በተቃራኒው   ዮሐንስ  ሴትን  የመናቅና  ያለማድነቅ  አዝማሚያ  የሚታይበት  ሰው  ነው።  የሴትን  አብዝቶ  ማሸብረቅ  ይጠላ ነበርና  በጵጵስናው  ዘመን  ከንጉሡ  ሚስት  ከአውዶክሲያ  ጋር  ዓይንና  ቁልቋል  ሆነው  ኖረዋል።  ይህችን  ሴት  ከሄሮድያዳ  ጋር እያነጻጸረ  ስለተናገረባት  ሌሎችን  አስተባብራ  ለስደት  የዳረገችውም  እርሷ ናት።  “ከዱር  አራዊት ሁሉ እንኳ  ሴትን  የሚያህል  ጎጂ  ፍጡር አይገኝም”  ብሎ  ስለ  ሴት  ጾታ  ያተተ  አንድ  መጽሐፍ  ዮሐንስን  ተጠቃሽ አድርጎታል። 14 እንዲህ  ለአንስታይ  ጾታ  ወደ  ጥላቻ  የተጠጋ  ንቀት እንዳለው  የሚባልለት  ሰው  ነው  በተአምረ  ማርያም  መርገመ  ደም  ያለባትን  ሴት  ኀፍረተ  ሥጋ  የሳመውና  ስዕሊቱ  አፈወርቅ  ብላ  የሰየመችው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የማርያም  ስዕል  እስኪሰለች  ድረስ  ነው  ድምጽ  እያሰማች  የምትናገረውና  ይህ  ሲጨመርበት  ታሪክ ወደ  ተረትነት  በቀላሉ  ይሻገራል።  እነዚህ  እርስ   በርሳቸው ከተጋጩ  እንደ ባለ  አእምሮ  በመዛግብት  የተጻፈውን  ተጨባጭ  ታሪክ  እንቀበል  ወይስ  በተአምረ ማርያም   የተጻፈውን  ከታሪክ   ጋር የሚጣላ ፈጠራ?

ለ.  ንጉሥ  ማርቆስ።

 የንጉሥ  ማርቆስ  ታሪክ  በተአምረ  ማርያም  በምዕ.  100  የተጻፈው  እንደሚተርከው  ድንግል  ሳለ  በሮም  መንገሡ  ተጽፎአል። 10 ዓመታት  ከነገሠ  በኋላ  ሠራዊቱ  ሚስት  ማግባት  ሞገስ  የሚያስገን  ቁም  ነገር  ስለሆነ  ሚስት  እንዲያገባ  ማለዱት።  እርሱም  ማርያምን  ልማከር  ብሎ  በስዕሏ  ፊት 7 ቀን  ቆሞ ጸለየ።  በጸሎቱ  መጨረሻ  የስዕሊቱ  ፊት  ቦግ  ብላ  በራችና  በድምጽ  እንዳያገባና  በድንግልና   እንዲኖር፥  እንዲያውም  መንግሥቱን  ትቶ  ደብረ  ቶርማቅ  ገዳም  ሄዶ  እንዲኖር  ነግራው  እዚያ  ለመኖር  ማንም  ሳያየው  ጠፍቶ  ሄደ።  በተአምረ  ማርያም  ድንግልና  እጅጉን  የተወደደ  ከመሆኑ  የተነሣ  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያምና  የማርያም  ስዕል  ሰው  ሁሉ  ሳያገባ  እንዲኖር  ይፈልጋሉ።  ይህ  ከመጽሐፍ ቅዱስ  ጠቅላላ አሳብ ጋር በትጋት የሚጣላ ነው።
ማርቆስን  በተመለከተ  በሮም  ግዛት  ውስጥ  በታሪክ  የታወቀ  በዚህ  ስም የተጠራ  ንጉሥ  ማርቆስ  አውራልዮስ (Marcus Aurelius)  ነው።  ይህ ሰው  ሳይሆን  ሌላ  ነው  ከተባለ  ታሪካዊ  ማስረጃ  ያስፈልገዋል።  በተአምረ ማርያም  ውስጥ  ስም  ሳይጠቀስም  ‘በአንድ  አገር  የነገሠ  ንጉሥ’  ይባልና  የንጉሡ  ስም  ሳይነገር  መተረክ  የተለመደና  ቀላል  ነገር  ነው።  ስለ  ማርቆስ በታሪክ  መዛግብት  የተጻፈ  ታሪኩ  የሚናገረው  ግን  ከዚህ  የተለየ  ነው።
ማርቆስ  ከ161-180  ለሃያ  ዓመታት  የነገሠ  ንጉሥ  ነው።  ከ20ው  ውስጥ 9ኙን  አብሮት  የነገሠ  ሉቂዮስ  ቬሮስ  የተባለ  ሰው  አለ።  ንጉሥ  ማርቆስ ከታሪኩ  እንደምናነብበው  ሳያገባ  የኖረ  እና  መንግሥት  ትቶ  ገዳም  የገባ መነኩሴ ሳይሆን  14 ልጆች ከወለደችለት ፋውስቲና  ከተባለች  ሚስቱ  ጋር  ለ30  ያህል  ዓመታት  ተጋብቶ  የኖረ  ሰው  ነው።  የቱ  ነው  ትክክል?  በማረጋገጫ  የሚፈትሹትና  ማስረጃ  የሚያቀርቡለት  ታሪክ?  ወይስ ከታሪክ  ጋር  የሚጋጭና  ምንጩ  የማይታወቅ  ተረት?

ሐ.  ዮስጢን  ሰማዕት። 

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የተጻፈው  በምዕ. 99  ሲሆን ከዮስጢን  ይልቅ  ስለሚስቱ  ታውክልያ  በተጻፈው  ውስጥ  የተካተተ ነው።  የተአምረ  ማርያሙ  ታሪክ  ታውክልያ  የዲቅልጥያኖስን  ክህደት ስለማወቅ  በጸሎት  ላይ  ሳለች  ማርያም  ከእናቷና  ከኤልሳቤጥ  ጋር ትገለጥላታለች።  የዲዮቅልጥያኖስ  ክህደት  በልጇ  (በኢየሱስ)  ዘንድ  የታወቀ  መሆኑን፥  ኢየሱስ  ለዮስጢን  በሰማይ  ስለሚደረገው  ሠርግ (ተዋህዶ)  ሊነግረው  እንደሄደና  እርሷ  ደግሞ  ወደ  እርሷ  እንደመጣች፥ ሁለቱም ከልጃቸው  ጋር  እንደሚሰዉ  ነግራት አበረታታት  ተሰወረች።
እዚህ  ያለው  ትልቅ  ታሪካዊ  ግጭት  ዮስጢን  ከ100-165  የኖረ  መሆኑ የታወቀ  ሆኖ ታውክልያ  የምትጸልየው  ስለ ዲዮቅልጥያኖስ ክህደት  መሆኑ ነው።  ሌላ  ዮስጢን  ካልሆነ  በቀር  ይህ  በታሪክ  የታወቀው  Justin  Martyr  ነው።  ዲዮቅልጥያኖስ  ክርስቲያኖችን  በእጅጉ  ያሳደደ  ሰው ቢሆንም  የኖረበት  ዘመን  ከ244-311  ሆኖ  የነገሠው  ደግሞ  ከ284-305  ድረስ  ነው።  ታውክልያ  ከ120  ዓመታት  በኋላ  ስለሚመጣው  ከሐዲ እያሰበች  ነበር  ካልተባለ  በዚያን  ዘመን  ዲዮቅልጥያኖስ፥  ክህደቱና  አሳዳጅነቱም  አልነበሩም።  ዲዮቅልጥያኖስ  የተወለደው  ዮስጢን  ከሞተ ከ80  ዓመታት  በኋላ  ነውና  ዮስጢን  የተሰዋው  በዲዮቅልጥያኖስ  ሳይሆን  ከላይ  በተጠቀሰው  ማርያም  ከንጉሥነት  ወደ  ገዳም  አስኮበለለችው  በተባለው  በማርቆስ  አውራልዮስ  ዘመነ መንግሥት  ነው።

5.  የተምታታ  ሲዖልና  መንግሥተ  ሰማያት።

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የሚታዩት  ከሞት  በኋላ  የሚሆኑት  ነገሮች  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ከተነገሩት  የተለዩ  ናቸው።  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ሰዎችንና  ነፍሳትን  ከሲዖል ታወጣና  ወደ  መንግሥተ  ሰማያት  ታስገባቸዋለች።  ሥጋዋ  ወይም  በድኗ በገነት  በሕይወት  ዛፍ  ስር  ተደርጎ  ነበር።  ያደረጉት  ደግሞ  ሬሳውን  ተሸክመው  የነበሩት  ሰዎች  ናቸው።  ስለዚህ  በአካል  ወደ  ገነትና  ወደ ሕይወት  ዛፍ  ይደረሳል  ማለት  ነው።  ሰዎች  ሲሞቱ  ማርያም  አንዳንዴ  ከመላእክት  ጋር፥  አንዳንዴ  ደግሞ  ከደናግል  ጋር  እየታጀበች  ትመጣና  ትወስዳቸዋለች፤  ለሌሎችም  ትታያለች።
ሰዎች  ከሞቱ  በኋላ  ማርያም  መልሳ  አምጥታ  ታሳያለች።  በምዕ. 18-19 እነ ጊዮርጊስ፥  ቴዎድሮስ፥  መርቆሬዎስ፥  የተመልካቾች  ዘመዶቻቸው  ሁሉ፥ በሕዝቡ  ጥያቄ ደግሞ  አዳምና  ሔዋን፥  አብርሃም፥  ይስሐቅ፥  ያዕቆብ፥  እነ ሙሴና  ዳዊት፥  ነቢያትና  ሐዋርያት፥  ወዘተ  እየተሰለፉ  መጥተው  ከመጋዘን  እያመጡ  ለሸማች  እንደሚያሳዩት  ዕቃ  ይታያሉ።  ከዚያ  በኋላ ምን  እንደሚሆኑ  አልተጻፈም።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ሰዎች  ከሞት የተነሡባቸው  ጊዜያት  አሉ።  ግን  በሰልፍ  መጥተው  ሊሰወሩ  ሳይሆን ታይተው  ኖረው ሞተዋል።  የዓይንዶሯ  መናፍስት  ጠሪ  ለሳኦል ሳሙኤልን  አስነሥታለች።  በአስማት  የምትሠራ  ሙታን  ሳቢ  ናትና  እንዳስነሣች  መሰለ  እንጂ  ሳሙኤልን  በእርግጥ  አላስነሣችም፤  ልታስነሣም  አትችልም። ሳሙኤል  ተነሥቶ  ኖሮ  ቢሆን  ሳኦልም  ያየው  ነበር  እንጂ  ምን  እንዳየች  አይጠይቃትም  ነበር።  ይህ  በነዚህ  ምዕራፎች  የሚታየው  የመናፍስት ጠሪዎች አሠራር  ሆኖ ልዩነቱ  ለጥቂት  ጊዜ መታየታቸው  ነው።
በምዕ.  28  ጌታ  ለሐዋርያት  በገነት  ተገለጠላቸው  ይላል።  በአካል  ገነት ገብተው  ማለት  ነው።  በምዕ.  54  የአንድ  ደብር  አለቃን  ወደ  ሰማይ አሳረገችው።  ሳይሞቱ  የሚነጠቁበትም  ነው።  በ77  የለማኙን  ፊት  በዳቦ  የገመሰው  ሰው  ሞቶ  ሲዖል  ሄደ።  ማርያም፥  “የለም  ይህ  የኔ  ነው”  ብላ ወደ ሲዖል  እንዳይወርድ  ተከራከረች። ዳቦውን  የተቀበለው  ፊቱ  የተገመሰ  ለማኝ  ሄዶ  መሰከረና  ሰውየው  ሲዖል  መግባት  ቀርቶለት  ነፍሱ ተመለሰችና  ከሞት  ዳነ።  ጌታ  እየተሳሳተ  ወይም  እየተጸጸተ  አሳቡን የሚቀይር  ወይም  የሰው  ምስክር  የሚያስፈልገው  የሰው  ዳኛ  መምሰሉም መታለፍ  የሌለበት  ስሕተት  ሆኖ ሳለ ለማኙ  በምን  አካል  ወደ  ዙፋን  ቀርቦ መሰከረ? በአካል  ወይስ  ያለአካል?

12 ለታሪካዊ ሰዎቹ  Schaff, [electronic version] vol. 3, ch. 1-3. History  of the Christian Church, እና Schaff, Nicene and Post Nicene  Christianity, እንዲሁም ታሪካዊ ክርስትና ላይ ከሚያተኩሩ ድረ ገጾች ያገኘኋቸው ተጨምረውበታል፡
13 በዚህ መጣጥፍ ዓመተ ምሕረቶቹ በግዕዝ ቁጥሮች ካልተጻፉ በጎርጎራውያን አቆጣጠር ነው።
14 http://en.wikipedia.org/wiki/John_Chrysostom
ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,

Tuesday, June 24, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!


ካለፈው የቀጠለ (ክፍል ሦስት)
(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

በምዕ.  24  የተጻፈው  ለማርያም፥  ለመስቀልና  ለስዕል  የማይሰግዱ የተባሉት  የአባ  እስጢፋኖስ  እና  የነደቀ  እስጢፋ  ታሪክ  መጽሐፉ ተተረጎመ  በተባለበት  ዘመን  እንኳ  ተፈጽሞ  ያላለቀና  ገና  እየተከሰተ  ያለ ነገር  ሆኖ ሳለ  ገና  ያልተፈጸመውን  ነገር  ከብዙ  ዓመታት  በፊት  ግብጽ  አገር  እንደተፈጸመ ተደርጎ የመጣና  የተተረጎመ  ማለት  ጥሬ  ውሸት  ነው።  ዘርዓ  ያዕቆብን ንጉሣችን  እያለ  ከተናገረ  ደራሲው  የዘርዓ  ያዕቆብ  ዜጋ  ነው  ማለት  ነው። ተርጓሚው  ማለት የተጻፈውን  ተርጓሚ  እንጂ  ያልተጻፈውን  ጨማሪ  አለመሆኑ የታወቀ ነው።

2.  የተቃለለ  ክርስቶስ።

 በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  የምናየው  ኢየሱስ  ለመሞትና ለኃጢአታችን  ስርየት ደሙን  ለማፍሰስ  ከማርያም  ሥጋን  ነስቶ ሰው  የሆነ አምላክና  ፈጣሪ ጌታና  እግዚአብሔር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ከአምላክና  ጌታ  ይልቅ  የተነገረውን  በፍጥነት  የሚፈጽም ቀልጣፋ  ተላላኪና አገልጋይ  ሆኖ  ነው  የቀረበው። ከመጀመሪያ  እስከ  መጨረሻ  ክርስቶስ  የማርያም  ልጅ  ነው።  ኢየሱስ  ከድንግል  ማርያም  ሥጋን  መንሳቱ  እውነት  ቢሆንም  ማርያምን ጨምሮ የፍጥረታት ሁሉ  ፈጣሪ  በመሆኑ  በግዕዘ  ህጻናት ዘወትር እናቱን ለመላላክና ለማገልገል  የመጣ በማስመሰል አምላካዊ  ኃይሉን በሰውኛ ፈቃድ ፈጻሚነት ስር ማስቀመጥ ትክክል አይደለም።  ሥጋ  የለበሰው  ኢየሱስ  እናትነት  አንድ  ነገር ነው።  የዘመን  መጀመሪያ  ለሌለው  አምላክ  እናት መሆኗ ብቻውን  ማርያምን  ከፍጥረቷ  በላይ  ሊያደርጋት  የተገባ  አይደለም።

 ነገር ግን  በተአምረ  ማርያም ውስጥ  ከማርያም  ጋር  በተጻፈባቸው  ቦታዎች  ስትጠራው  ልጄ  ወዳጄ  ብላ  ነው።  ሰዎች  ደግሞ  ወደ  ማርያም  ሲጸልዩ  እርስዋን  እመቤታችን  (እግዝእትነ)  ብለው  ነው። ክርስቶስን ከመለመን ይልቅ ማርያምን በመለመን ከልጇ ምህረት ማግኘት የቀለለ ይመስላል። አንዳንድ የተአምራት ጽሁፎች ላይ ስንመለከት ኢየሱስ ለሰዎች ፈቃደኛ ያልሆነበትን ጉዳይ ማርያም ስትነግረው ቃሉን ሲያሻሽል ይታያል።  ከክርስቶስ ርኅራኄ ይልቅ የማርያም ልመና ምህረት ያስገኛል የሚል ሃሳብን የያዘ ነው። «ዓለም ያለማርያም አማላጅነት አይድንም» የሚለው አባባል ዓለም በኢየሱስ አምላካዊ ፈቃድ የተደረገለትን ድኅነት አምዘግዝጎ የሚጥል ነው።  ኢየሱስን  ግን  በቀጥታ  ሲያናግሩት  ወይም  ወደ  እርሱ  ሲጸልዩም  ሳይሆን  “ከልጅሽ  ከወዳጅሽ”  እያሉ እርሷኑ  ሲለምኗትና ሲጠይቋት ነው  የሚታየው።  «ለምኑ ይሰጣችኋል፤ አንኳኩ ይከፈትላችኋል» የሚለው የወንጌል ቃል ተሰርዞ በማርያም አማላጅነት ላይ ብቻ ተስፋ ጣሉ የሚለው ክህደት ትምህርት መነሻው ምንድነው?
የክርስቶስ ዘላለማዊ ኅላዌነት ማርያምን ያስገኘ ሳይሆን የማርያም መኖር ኢየሱስን እንዳስገኘ ከሚታሰብ ጭፍን ክህደት የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።  የፈጠረ፤ የቀደሰ፤ ያነጻና ሥጋን የለበሰው በአምላካዊ ፈቃዱ መሆኑ መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ ነው።  ይህንን መዘንጋት ኢየሱስ  በብዙ  የማርያም  ስዕሎች  ላይ  እንደሚታየው  የማርያም  አራስ  ልጅ፥  ጨቅላ  ልጅ፥  ወጣት  ልጅ፥  ታዛዥ  ልጅ፥ ሁሌ ጭኗ ላይ ሲቀመጥ የሚታይ፤ አንድ  ጊዜም  እርሷ የጠየቀችውን  ነገር  እንቢ  ያላለ፥  የተጠየቀውን  ሁሉ  በቅልጥፍና  የሚፈጽም፥  የተሳሳተ  ነገር ጠይቃ እንኳ  ቢሆን  አሳቡን  ስለ  ልመናዋ  ሲል የሚቀይር  ለስላሳ  ልጅ  ነው።

 አንዳንዴ  ስታስፈራራው፥  ለምሳሌ፥ ኢየሱስን  ክዶ ማርያምን  ያመነን  አንድ ሰው  ይቅር እንዲለው በለመነችው ጊዜ  እንደማይሆን  ሲነግራት፥  ልብሷን  ቀዳ፥  “እኒህን  ጡቶቼን እቆርጣቸዋለሁ”  ብላ  ፍርዱን  አስቀይረዋለች፤  (ምዕ.  110ን  ተመልከቱ )። ኢየሱስም  አሳቡን  ቀይሮ  ይቅር  አለው።  በታሪኮቹ  ሁሉ፥  ከትንሣኤ  በኋላ እንኳ፥  ኢየሱስ  በሚታይባቸው  ጊዜያት  ሁሉ  እንደ  ባለ  ግርማ  አምላክ ሳይሆን እንደ ሕጻን  ሆኖ ነው የሚታየው። እዚሁ ምዕራፍ 110 ላይ እንኳ ኢየሱስ  ከዙፋኑ ተነሥቶ  በደረቷ  ላይ ተቀምጦ ተብሎ ተጽፎአል። በምዕ.  90  ልጇ  የተሰቀለባት  አንዲት  ሴት  ማርያም  ልጇን  ከተሰቀለበት ካላወረደችው  እሷም፥  “ልጅሽን  (ኢየሱስን)  ከጭንሽ  እወስደዋለሁ”  አለች።  ኢየሱስ  ሁሌ  በማርያም  ጭን  ተቀምጦ  የሚኖር  ብቻ  ሳይሆን ነጥቀው የሚወስዱትም  ዓይነት ነው። በምዕ. 43  ጴጥሮስ  ለተባለ  ቤተ  ክርስቲያንን  ላነጸ  ሰው  መልኩ  ያማረ ልጅ  ሆኖ  ተገለጠለት።  ‘ቤተ  ክርስቲያን  ያሠራ  ሰው’  ስለተባለ  ምናልባት  በብዙ  መቶ  ዓመታት  በኋላ  ነው  ቢባል  እንኳ  በዚያን  ጊዜ  ጌታ  ሕጻን  አለመሆኑ  ግልጽ  ነው።  ግን ልጅ  (የግዕዙ ሕጻን ነው የሚለው) ሆኖ ነው የተገለጠው።  ኅብስቱ  ሲቆረስ  ደግሞ  የዚህ  ሕጻን  ደም  ፈሰሰና  ታቦቱንና  ልብሱን ሁሉ  አራሰ።  በምዕ. 82  ኢየሱስ በዓለም  ሁሉ ገዢ  የነበረ ንጉሥ  ሳቤላ  የምትባል  ሴት  አስጠርቶ  (ሴቲቱ  በስም  ስትጠቀስ  ንጉሡ አልተጠቀሰም፤  ይህ  የመጽሐፉ አንድ  ደካማ ገጽታ ነው) ምክር  ሲጠይቅ ሴቲቱ  ራእይ አይታ  ለንጉሡ  አሳየችው፤ ያም ማርያም  ሕጻን  አቅፋ  ነው። ኢየሱስ  ሁሌም  ሲታይ፥  ዛሬም  ጭምር፥  በእቅፍ  ያለ  ሕጻን  ሆኖ  ነው ለማርያም  አምላኪዎች  የሚታየው። ኢየሱስ የቀረበበት  አቀራረብም  ከማንነቱ  አውርዶ  ያቃልለዋል።

 በተአምረ ማርያም  ሕጻኑ  ኢየሱስም  ሲራገም  አይጣል  ነው፤  ማርያምም  ስትበቀልና  ስትራገም  የተለመደ  መሆኑ  በቀጣዩ ነጥብ  ይታያል።  በምዕ. 101  ቁ. 108፥ ያፈለቀውን  ውኃ  ለአገሩ  ሰዎች  «መራራ  ይሁንባቸው  የጠጣውም  አይዳን  ብሎ  ባረከው»  ይላል።  ረገመው  ላለማለት  ባረከው  አሉት  እንጂ  ቃሉ ግልጽ  እርግማን  ነው።  በቁ.  125  ግመሎችን  ድንጋይ  ሁኑ  ብሎ  አደነገያቸው።  [“እስከ  ዛሬ  ድረስ  ደንጊያ  ሆኑ”  ይላል።  ኋላ  ኢትዮጵያ ቆይተው  ሲመለሱ  ነፍስ  ተዘርቶባቸው  ተመልሰው  ግመል  ሆነው  ዕቃ ተጭነው እንደሄዱ  የተረሳ  ይመስላል።] በቁ.  159  ኢየሱስ  የግብጽን  አገር  ምድሩንም  ሕዝቡንም  መርገሙ  ተጽፎአል።  ይህ  እዚህ  መርገም የሚያፈስሰው  ኋላ  ላይ  ገና  አፉንም  አልፈታም  የተባለው  ኢየሱስ  ነው። ግጭቱን  ብንተወው  እንኳ  ይህ  የተአምረ  ማርያም  ፈጣሪዎች  የፈጠሩት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  አይደለም።  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  ያስተማረውም  ያደረገውም  ጠላትን መርገም  ሳይሆን  መውደድ ነው። «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ ወደባህርይ አባቱ የጸለየው ኢየሱስ የአገሩ ውሃ መራራ ይሆንባቸው፤ የጠጣውም አይዳን፤ ድንጋይ ሁናችሁ ቅሩ» እያለ በጭራሽ  አይራገምም።

3. የተጋነነች ማርያም።

 ተአምረ ማርያም  እንደ ስሙ የማርያም  ተአምራት  መጽሐፍ ነው። ተአምራቱ  ብዙና የተለያዩ  ናቸው። ማርያም  ብቻ  ሳትሆን በስሟ  የሚደረጉ  ነገሮች  ሁሉ  ክብራቸውና  ክብደታቸው  እጅግ  ነው።
ለምሳሌ፥  በተአምር  12  ውስጥ  78  ሰዎች  የበላ  ጭራቅ  በማርያም  ስም ውኃ  ስላጠጣ  ሞቶ  ወደ  ሲዖል  እንዲሄድ  ጌታ  ፈረደበት።  ማርያም  ቀርባ  78ቱ  ነፍሳትና  ውኃው  በሚዛን  ይደረጉ  ብላ  ተደርጎ  የውኃው  ክብደት  እንዲመዝን በዘዴ ጥላዋን እንዳሳረፈችበት፤ የሞቱት ሰዎች ነፍሳት ስለቀለሉ  ጌታ  አሳቡን  ቀይሮ  ወደ  መንግሥቱ  ያስገባዋል ሲል እናገኘዋለን። ይህ እንግዲህ የፈለጋችሁትን ዓይነት ኃጢአት ብትፈጽሙና አምላክን ስለበደላችሁ ቢፈረድባችሁ እንኳን «ማርያምን ካመናችሁ ትድናላችሁ» ለማለት የተዘየደ የመዳኛ ምክንያት ነው።  የተአምሯ ማርያም ፍርዱን ለመቀየር በጥላዋ ሳይቀር እስከማታለል የመሄድ ብቃት እንዳላት ጥንካሬዋን ለማጎልበት ሲጠቀሙበት ይታያል። በአምሳለ እግዚአብሔር  የተፈጠሩ  78  ሰዎች  ነፍሳት  ከጥርኝ  ውኃ  መቅለላቸው አሳዛኝ ነው።  በምዕራፎቹ  ሁሉ  ማለት  እስከሚቻል  ማርያም  ከእግዚአብሔር  ጋር ተስተካክላ  ነው  የምትገለጠው።  ለምሳሌ፥  በ41፥13  “በእግዚአብሔር  አምነው፥ በወለደችውም  በእመቤታችን  አምነው  ከቤተ  ክርስቲያን ወጡ”  ይላል።  በማን  አምነው?  በእግዚአብሔርና  በማርያም!  እዚሁ  ምዕራፍ  ቁ.  25፥  “እምነቱን  በናቱና  በእግዚአብሔር  ላይ  ያደረገ  ሁሉ  አያፍርምና”  ይላል።  እዚህ  እንዲያውም  ማርያም  ቀድማ  እግዚአብሔር  ተከተለ!  ምዕ.  76  መነኮሳቱ  ሲጸልዩ  እግዚአብሔርንና  ማርያምን  ነው፤  “እንለምንሃለን  .  . .  እንለምናታለን”  ቁ. 15።

  አንዱ  ቄስ  ደግሞ  የማርያምን  ውዳሴ  ብቻ እንጂ  ሌላ  የማያውቅ  ነው፤  ምዕ.  76።  ይህንን  ቄስ  ሌላ  ካላወቀ እንዳይቀድስ  የከለከለውን  ኤጲስ  ቆጶስ  ወደ  አገልግሎቱ  ካልመለሰው በ30  ቀን  ትሞታለህ  አለችው።  ከግዝቱ  ፈታውና  እርሱም  ማርያምን እያደነቀ  አብረው  ኖሩ።  እዚህ  የምትታየው  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም እርሷ እስከተወደሰች ድረስ  እግዚአብሔር  ባይመሰገንም  ደንታ  እንደሌላት ነው።
በምዕ. 86 ማርያምን በፍጹም አሳቧ፥ በፍጹም ልቧ የምትወድ የተባለላት ሴት  ታሪክ  ይገኛል።  እንዲህ  ባለ  መውደድ  መወደድ  ያለበት እግዚአብሔር  ብቻ  መሆኑን  ነው  መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚያስተምረን።  እና በቃሉ  (ዘዳ. 10፥12-13፤  ማቴ. 22፥37፤  ማር. 12፥30-32፤  ሉቃ. 10፥27)  እንደተጻፈው ሰው በፍጹም ልቡ መውደድ ያለበት  እግዚአብሔርን  ነውና  ማርያም  ይህንን  ማሳወቅ  ሲኖርባት  አለማድረጓ  የመለኮትን  ፍቅር ማስቀነሷ ነው። በዚህ  ምዕራፍ  የተጠቀሰው ሰው ጠንቋይን  ምክር  የጠየቀ ሰው  ሆኖ  ምንም  ወንጌል  ሳይሰማ  ግን  የማርያምን  ስም  ሲነገረው  በነፋስ  ፊት  እንዳለ  ገለባ  ሆነ።  ሲሞትም  ማርያም  ሬሳውን  አንሥተው  በገዳም እንዲቀብሩት ተናገረችለት።  ማርያም ሰው  የሚሞትበትን  ቀን  የምታውቅ ናት።  ከላይ ለቄሱ  በ30 ቀን እንደሚሞት  ተናግራው  እንደነበር  አይተናል።  ሌላ  ምሳሌ፥  በምዕ.  81  አንድ  መነኩሴን  በአንድ  ሌሊት  ተገልጣ  ወደ  ኢየሩሳሌም  ወስዳ  አዙራ አስጎብኝታ፥  በዮርዳኖስም  አጥምቃ  የሚሞትበትን  ጊዜ  ነገረችው፤ እንደተናገረችው  ጊዜ  ዐረፈ።  ከእግዚአብሔር በቀር የሚያውቃቸው የሌሉ ነገሮችን  ካወቀች  ሁሉን  አዋቂ  ናት  ማለት  ነው?  ሁሉን  አዋቂ  ከሆነች አምላክ ናት ማለት ነው? የዚህ  መጽሐፍ  ማርያም  ስትፈልግ  ርኅሩኅ  ሳትፈልግ  በቀለኛ  ናት።

  ለምሳሌ፥  በምዕ  35  አንድ  እስላም  ዘራፊ  የዘረፈው  በገዳም  የሚኖር  ቄስ ወደ  ማርያም  ስዕል  ሄዶ  ተማጸነ፤  ጸልዮ  ሲወጣ  ዘራፊው  ወድቆ  እጁ ተሰብሮ  አጥንቱ  ገጦ  ወጥቶ  አየው።  እስላሙ  ይቅርታ  ሲጠይቀው ሽማግሌው  ማርያም  ይቅር  ብትልህም  ባትልህም  እንደወደደች  አለው፤ ይህ  ሰው  ቄስ  ሆኖ  ስለ  ይቅርታ  አያውቅም።  ቄስ  ነው  እንጂ  ክርስቲያን  አይደለም  ማለት  ነው።  ክርስቲያን  ቢሆን  ክርስቶስን  ሊመስል  ይሞክር ነበር።  እስላሙ ስላደረገው ጥፋት ይቅርታ ሲጠይቅ፤ ቄሱ «ይቅር ብትልህ ባትልህ» ካለ  እስላሙን ማን አስተምሮና አሳምኖ ሊለውጠው ነው? የሚገርመው ደግሞ ቄሱ ብቻ ሳይሆን የተአምሯ የማርያም  ስዕል  አፍ አውጥታ  «በቄሱ  ላይ  ደፍሯልና  ይቅርታ አይገባውም  አለችው»  የሚለው የበለጠ አስገራሚ ነው።  ስለዚህ  እስላሙ  በቄሱም፤ በተአምሯ  ስዕል አንደበት ወንጌልም  ሳይሰማ፥  ይቅርታም ሳያገኝ ሞተ።  ነገር ግን በተአምር 33፥39 ላይ ደግሞ ማርያም የይቅርታ ሳጥን ተብላለች።  እዚህ ላይ ደግሞ ተቃራኒ ናት። በቀለኛና  የደግነት ባህርይዋ  በወንጌል ላይ ሳይሆን በድርጊቱ  የአተራረክ ሁኔታ ላይ የሚደገፍ ነው።

 በምዕ. 39 ላይ ደግሞ በቀለኛ ማርያም ትታያለች። ሌላ  እስላም  ዘራፊ  ገዳም  ዘርፎ  ሲሄድ  ሰዎች  አግኝተው  ገደሉት፤  ከቤተ  ሰቡ  10  ሰዎች  ከዘመዶቹ  18  ገደሉና  የተዘረፈውን  አምጥተው  ለገዳሙ  ሲመልሱ  በቁ.  35፥ “ልቡናችንን  እርሱን  ለመግደል  ያነሣሳችን  ማርያም  እንደሆነች  ፈጥነን አወቅን”  አሉ።  «መጎናጸፊያህን ለሚወስድ እጀ ጠባብህን ተውለት» ለሚለው የወንጌል ቃል ግድ የሌላቸው መነኮሳቱ  ዘራፊውን  ከመግደላቸውም በላይ በቦታው ያልነበሩትን 10 ቤተሰቦቹንና 18 ዘመዶቹን በመግደላቸው ደስ ተሰኝተዋል። ይህንን የግድያ ስራ እንዲፈጽሙ ያነሳሳቻቸው ማርያም ናት ይላሉ። የተአምሯ ማርያም  ሰዎችን  አስነሥታ  ታስፈጃለች። የሚያሳዝነው  መነኮሳቱም  በዚህ  ነገር  ፍጹም  ደስታ  ተደሰቱ።  ኃጢአተኛ ሲድን  ሳይሆን  ሲሞት  የሚደሰቱ  መነኮሳት  ወንጌልን  ያውቃሉ  ይባላል?  በምዕ.  98  ከአንድ  ሽማግሌ  አስተማሪያቸው  ጋር  ፍልሰቷን  ለማክበር ሲሄዱ  አስተማሪያቸውን  ወደ  ገደል  የጣሉ  40  ተማሪዎች  በእሳት  ጦር እየወጋ  የሚገድላቸው  መልአከ  ሞት  አዘዘችና  በአንዴ  አለቁና  ሽማግሌውን  ግን  ወደ  በዓሏ  መከበሪያ  አደረሰችው።

  በምዕ.  15  አንድ  ግመል  ጫኝን  ጎድኑን  ወግታ  ስትገድለው  ትታያለች።  ደራሲዎቹ  ማርያምን  በቀለኛ  ሲያደርጓት  እርሷን  ለማግነን  ሲሉ  አስቀያሚ  ቀለም እየቀቧት  መሆናቸውን  እንኳ  አያውቁም።  ወይስ  አውቀው  ነው  አያደረጉ ያሉት? የተአምረ ማርያሟ  ማርያም  በቀለኛ ብቻ  ሳትሆን ቀናተኛም  ናት።  በምዕ.  92  የአንድ  ንጉሥን  ወጣት  ልጅ  እርሱ  ከሚወዳት  የበለጠ  እርሷ እንደምትወደውና  እንደምትቀናበት፥  ሚስት  ሳያገባ  እንዲኖርም እንደመከረችውና  በእጇ  ስዕሏን  እንደሰጠችው  ተጽፎአል።  ንግግራቸው  የሁለት  ፍቅረኞች  ይመስላል።  ልጁ  ሲሞትም  ብዙ  መላእክት  እና  ደም ግባቷ  ያማረች  ማርያም  መጥተው  በሰው  ሁሉ  እየታዩ  ይዛው  ሄደች። በእግዚአብሔር  የተደነገገ  ጋብቻ  የተናቀበትና  የተዋረደበት  እንደዚህ  ያለ መጽሐፍ  አላነበብኩም።  ያላገቡ  እንዳያገቡና  ድንግልናቸውን  ለማርያም  ስዕለት  አድርገው  እንዲሰጡ  የሚበረታቱበት  ብቻ  ሳይሆን  የተጋቡ  እንኳ  ከተቀደሰ  መኝታ  የሚከለከሉበት  ነው። መመነን፥ መመንኮስ፥ ተሰባስበው  በገዳም  መኖር  በመጽሐፍ  ቅዱስ  የተደነቀና  የተመሰገነ  ልምድ አይደለም።
ምንኩስናና  ገዳማዊነት  በክርስትና  ታሪክ  ውስጥ  ብቅ  ያለው  ቤተ ክርስቲያን  ከምድራዊ  መንግሥት  ጋር  እንደ  ውኃና  ወተት በተደባለቀችባቸው  ዘመናት  ከምድራዊ  ርኩሰትና  መንግሥታዊ  ሃይማኖት  ጋር  ላለመርከስ  የተደረገ  ሽሽት  ነው።  በዚህ  መጽሐፍ  ግን  ነባር  ልማድ  ብቻ  ሳይሆን  የተሞገሰ  አኗኗር፥ እጅጉን  የተጋነነ ሥርዓትም  ሆነ። ተአምራት  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ብዙ  ጊዜያት  የተደረጉ  ሲሆን የተአምራት  ዋነኛ  ግብ  የእግዚአብሔር  ክብር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  በተደረጉት  ተአምራት  ግን  ክብር  እግዚአብሔር  ሲሰጥ  ከቶም  አይታይም።  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ሲጀምር  የእመቤታችን  ተአምር  .  .  .  ብሎ  ይጀምርና  ሲጨርስ  በረከቷና  .  .  .  ይደርብን  ይላል።  ሲጀምር ማርያም፥  ሲጨርስ  ማርያም።  ክብር  ለማርያም  እንጂ  ለእግዚአብሔር  የሚባል  ቋንቋ የለም።
 የኢትዮጵያ  ሰዎች  ለማርያም  የተሰጡ  ዐሥራት  ሆነው  ቀርበዋል።  ዐሥራት ማለት ከዐሥር አንድ እጅ ማለት ነው። ይህ አጠያያቂ  ቃል ነው። የኢትዮጵያ  ሕዝብ እንዴት ነው  1/10ኛ የሆኑት?  9ኙ እነማን  ናቸው?  ሕዝብ  እንደሕዝብ አስራት  ተደርጎ  የተሰጠበት  ታሪክ  ኖሮ  ያውቃል?  እንኳን  ሕዝብ  በሙሉ  ይቅርና  ከአዳም  ጀምሮ  ፈቃድ ያለው  አንድ ሰውስ  ያለ  ፈቃዱ  በመንፈሱ  ላይ  ሌላ  ሊሰለጥን  እንዴት ይገደዳል?  ደግሞስ  አስራት የሰጠው  ኢየሱስ ከሆነና ማርያም  አስራት ተቀባይ ከሆነች በተአምረ  ማርያም  ላይ  ምን  እየተነገረ  ነው?  አስራት ለማን  ነው  የሚሰጠው?  አምላክ  አስራት  ሰጪ፤  ማርያም  ደግሞ  አስራት ተቀባይ  ከሆነች ማርያምን መለኮት ማድረጋቸውም  አይደል? ከመለኮትም  በላይ እንጂ!  እግዚአብሔር ነዋ!  አስራት ሰጪው።
 በምዕ. 84 ሰንበትን  የሻረ አንድ አገልጋይ  ድዳ ሆነ። ጌታው ወደ ማርያም  ጸለየና  ፈወሰችው።  የተሻረው  ሰንበት  ነው።  የምትጠየቀው  ደግሞ ማርያም  ከሆነች  እርሷ  የሰንበት  ባለቤት  ናት  ማለት  ይመስላል።   «የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነውና» ማቴ 12፤8 የሚለው ቃል በተአምረ ማርያም ላይ ተቀባይነት የለውም።
በምዕ.  110  «እግዚአብሔርን  ክዶ  ማርያምን  ግን  አልክድም»  ያለ  ሰው  በማርያም  ኢየሱስን  አስፈራሪነት  ይቅርታ  ሲያገኝ  ይታያል።  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  ማምለክ  ክቡር  ቦታ  አግኝቶአል።  ጌታ  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  አለመካድ  ወይም  ማምለክና ማንን  የማግነን  ጉዳይ ነው?  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ማዕረጓ  ብዙ  ነው።  እመቤት  ናት፤  የአርያም ንግሥት  ናት  ወዘተ፤  ችሎታዋ  ድንቅ  ነው፤  ተፈጥሮ  በቁጥጥሯ  ስር  ነው፤ ተአምራት  ታደርጋለች፤  በሰው  ልብ  የታሰበውን  ታውቃለች፤  በሞትም  ላይ  ሥልጣን  አላት  ወዘተ፤  ሥልጣኗ  የመለኮት  ነው፤  መላእክት ይገዙላታል፥  ፍጡራን  ሁሉ  ያገለግሏታል፤  የመመረቅ፥  የመርገም፥ የመግደል፥  ከሞት  የማንሣት፥  ከእግዚአብሔር  ጋር  በእኩል  የምትለመንና የምትመሰገን  ናት  ወዘተ።  እንዲያውም እግዚአብሔርን የካዱ እርሷን ካመኑ ማዳን የሚያስችል አቅም አላት። እግዚአብሔርን ማመን አያስፈልግም። ማርያምን ብቻ ማመን በቂ ነው። ተአምረ  ማርያም  እንዲህ  በመሰሉ  ማርያምን በመጽሐፍ  ቅዱስ  ካላት  ትክክለኛ  ስፍራ  ፈንቅሎ፥  ተገቢ  ቦታዋን  ነጥቆ፥ ያልሆነችውን  አድርጎ፥  ያልተሰጣትን  ሰጥቶ፥  ያልለበሰችውን  ደርቶ የሚጸለይላት፥  የምትለመን፥  የምትመለክ  አድርጎ  መለኮታዊ  ሥልጣንና ኅልውና  ሰጥቶአታል። 

 ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,

Friday, June 20, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነጽሁፍ ዘላለም መንግሥቱ)

ካለፈው የቀጠለ (ክፍል ሁለት)

4.  ይህ  ደራሲ  ማርያምን  መለኮታዊ  ክብርን  ለማቀዳጀት  የጣረ  ወይም እንዲያደርግ  ያነሣሱት  ሰው  ነው።

 ምናልባት  መጽሐፉ  ስለራሱ እንደሚናገረው  ከግብጽ  ተገኝቶና  በዐረብኛ  ተጽፎ  ከሆነ  ክርስቲያኖች ማርያምን  እንደ  አምላክ  ያዩአታል  የሚያሰኝ  ዐረባዊ  ጫና  ሊኖርበትም ይችላል። ለምሣሌ፥ በኢስላም ግምት ክርስቲያኖች አብ፥ ወልድ፥ መንፈስ ቅዱስ  አንድ  አምላክን  ሳይሆን  ማርያምንና  ኢየሱስን  ከአላህ  ጋር  እኩል አድርገው  እንደሚያመልኩ  ይነገራል፥  ተጽፎአልም።  “የመርየም  ልጅ  ዒሳ ሆይ  አንተ  ለሰዎቹ፥  እኔንና  እናቴን  ከአላህ  ሌላ  ሁለት  አምላኮች አድርጋችሁ  ያዙ  ብለሃልን?  በሚለው  ጊዜ  (አስታውስ) . . .”( ቁርአን አልማኢዳህ ቁጥር 116)

   በተአምረ ማርያም  ደግሞ  ማርያም  ያላት  ሥልጣንና  የምታደርጋቸው  ትንግርቶች መለኮት  ብቻ  እንጂ  ማንም  ፍጡር  ሊያደርጋቸው  የማይችላቸው  ነገሮች ናቸውና እውነትም  ከመለኮት  ያልተናነሰ  ኃይልና  ችሎታ፥  ሞገስና  ክብር፥ሥልጣንና ስግደት ተጎናጽፋ ትገኛለች። እርግጥ  ነው  ጌታን  ያመኑና  የሚከተሉ  ተአምራትን  እንደሚያደርጉ ተጽፎአልና  በክርስትና  ታሪክ  ተአምራት  አዲስ  መሆን  የለባቸውም። የማርያም  ግን  የተለየ  ነው።  የሞተን  ማስነሣት  አንድ  ነገር  ነው፤  ግን፥ ለምሳሌ፥  በምዕራፍ  18  እና  19  ውስጥ  እንደሚነበበው  በደብረ  ምጥማቅ ተገልጣ  በዚያ  የነበሩ  ዘመዶቻቸውን  ብቻ  ሳይሆን  ጥንት  የሞቱትን ሙታን፥ አዳምና ሔዋንም ሳይቀሩ እያስነሱ አምጥቶ ለተመልካች ማሳየት መለኮትን  መጋራት  አይባልም?  ምክንያቱም  ትንሣኤ  የሰው  ሳይሆን የእግዚአብሔር  ብቻ  ሥራ  ነው።  ማርያም  ይህንና  ሌሎችንም  ሁሉ የምታደርገው  ደግሞ  እንደ  ጌታ  ደቀ  መዝሙር  በሕይወት  ሳለች  ሳይሆንከሞት  በኋላ  እየተገለጠችና  በአካል  እየመጣች  ነው።

  በዚህ  በተጠቀሰው ክፍል  እንደታየው  ያለ  ከሞተ  በኋላ  ከሞት  እየተነሣ፥  እየታየ፥  እየዳሰሰ፥ እያቀፈ፥  እየሳመ  ገባሬ  ተአምራት  ሆኖ  ከሰው  ጋር  የተባበረ  ኖሮ አያውቅም።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  የተጻፈ፥  በትንሣኤ  አካል  ከሞት የተነሣ  ጌታ  ክርስቶስ  ብቻ  ነው።  ከእርገቱ  በኋላ  እርሱ  ራሱም የተገለጠው  ለሁለት  ሰዎች  ብቻ  ነው፤  ለጳውሎስና  ለዮሐንስ።  ሁለቱም ባዩት  ጊዜ  ምን  እንደሆኑ  ተጽፎልናል፤  ሐዋ.  9  እና  ራእ.  1።  በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ትንሣኤ ሙታን እንደ ቁርስና ምሳ ተራ ጉዳይ ነው። በተአምረ  ማርያም  ጌታ  ኢየሱስ  በተጠቀሰባቸው  ቦታዎች  በ97  ወይም 98%  ያህሉ  ልጇና  ወዳጇ  ነው።  ፈጣሪዋ፥  አምላኳ፥  ጌታዋ  ከመሆኑ ይልቅ  ማለት  ነው።  ይህ  ፈጽሞ  አልተጠቀሰም  ማለት  ሳይሆን የተጠቀሰው  1  ወይ  2%  ብቻ  ነው።  በመጽሐፉ  የቀረቡት፥  ልክ  እንደ ስዕሉ  ሁሉ፥  የተሳሉት  እንደ  እናትና  ሕጻን ልጅ  ነው።  እናትና  ሕጻን ልጅ ብቻ  ሲታዩ  ክብደትና  ክብር  የተገባት  እናት  እንደምትሆን  ሆኖ  ነው አቀራረቡ።  ወደ  መጽሐፉ  መደምደሚያ  አንድ  ጊዜ  የ5  ዓመት፥  አንዴ የ8፥  አንዴ  የ12  ዓመት  የተጠቀሰ  ሲሆን  መጽሐፉ  ሲደመደም በመጨረሻው  ምዕራፍ  ኢየሱስ  የ18  ዓመት  ልጅ  ሆኖ  ገና  አሁንም የተጠየቀውን  አድራጊ  ሆኖ  ማርያም  የግሪክን  አገር  መጎብኘት  መፈለጓን ነግራው  እዚያ  ወስዷት  ታሪኩ  እዚያ  ይፈጸማል።  ከነዚህ  የመጨረሻ  4  ምዕራፎች  በቀር  በመጽሐፉ  ውስጥ  ኢየሱስ  በእናቱ  እቅፍ  ያለ  ሕጻን ነው። ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ እንኳ ሲታይ እንደ ሕጻን ሆኖ ነው።

5.  ይህ  ደራሲ  ወይም  ይህን  የመጽሐፉን  ይዘት  የተቀበሉትና  ያስጻፉት ሰዎች  በሰይጣን  የተታለሉ  ሰዎች  ናቸው።

 ይህ  ሁሉ  በመጽሐፉ  ውስጥ የተጠቀሱት  ነገሮች  ታይተዋል፤  ማርያምም  ተገልጣ  ተናግራቸዋለች፤ የተጻፈውም  ነገር  በትክክል  የታያቸውና  የተገለጠላቸው  ነው  ተብሎ ቢወሰድ  እንኳ  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ትምህርት  አንጻር  ሰዎችን  እውነትና መንገድ  ሕይወትም  ከሆነው  ከክርስቶስ  የሚያርቅ  ነገር  ስላስተላለፉ በማርያም  እየተመሰለ  የተገለጠ  ሰይጣን  ያሳታቸው  ሰዎች  ናቸው  ብሎ መደምደም  ይቻላል።  በ2ቆሮ. 11፥14  ሰይጣን  ራሱን  የብርሃንን  መልአክ እንዲመስል  እንደሚለውጥ  ተጽፎአል።  ይህች  ተገለጠች  የተባለችው  ማርያም ሐዋርያት የሰበኩትን  እውነተኛ ወንጌል እንኳ ብትሰብክ ይህንም መቀበል ግዴታ  አይሆንም፤ ምክንያቱም እውነተኛው  ወንጌል  ቀድሞውኑ ተሰብኮ፥  ተጽፎ  ተላልፎአላ!  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  የሚተላለፈው ትምህርት  ደግሞ  ከእውነት  ፈቀቅ  የሚያደርግ  ነው።  ይህን  በተመለከተ ጳውሎስ  በገላ.  1፥8  ነገር  ግን  እኛ  ብንሆን  ወይም  ከሰማይ  መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ  ወንጌል  የሚለይ  ወንጌልን  ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ  ይሁን አለ።  አዲስና  ወንጌል  የሚመስል  ግን  ያልሆነ  ነገር  የሚሰብክና  ታይቶ የሚገልጥ የዚህ ውግዘት ተሸካሚ ነው።

6. የተአምረ ማርያም ደራሲ  ደኅንነትን  የማያውቅ ሰው  ነው።

 በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ፥  በተለይም  በአዲስ  ኪዳን  በግልጽ  ተጽፎልን  የምናየው ደህንነት  ወይም  ድነት  ውብ  ነው!  የእግዚአብሔር  ድንቅ  የሆነው አሠራሩ፥  ኃጢአተኛውን  ሊያጸድቅ  አንድያ  ልጁን  መላኩ፥  ጌታችን መድኃኒታችን  ኢየሱስ  ክርስቶስም  በፈንታችን  በመስቀል  መሞቱና  እኛን ከዘላለም  ሞትና  ከኃጢአት  ባርነት  ነፃ  ማውጣቱ፥  ይህ  ድንቅና  ክቡር የሆነ  ግን  ግልጥና  ቀላል  ሆኖ  የቀረበው  ሥራው  አስገራሚ  ነው።  አቤት ደኅንነት  ውበቱ!  አቤት  ደኅንነት  ግልጽነቱና  ቀላልነቱ!  አቤት  ውስብስብ ያለመሆኑ!  አቤት  እርግጠኝነቱ!  ደህንነት  የሂደት ሳይሆን  የቅጽበት ለውጥ ነው።  ደኅንነት  ይታወቃል፤ አንድ  ኃጢአተኛ  ሲድን  መዳኑን  ያውቀዋል። እንዲያውቅ የሚያደርጉት ዋና ዋና ምስክሮች አሉ። 1ኛው የማይዋሽ ቃሉ ነው፤  በዳንንባት  ቅጽበት  የእግዚአብሔር  ልጆች  ሆነናል፤  ዮሐ. 1፥11-12፤
ልጁ  ያለው  ሕይወት  አለው፤  ይህ  ደግሞ  የሚታወቅ  ነው፤  1ዮሐ. 5፥12-13።  2ኛ  በዳንንባት  ቅጽበት  በውስጣችን  መኖር  የጀመረው  መንፈስ ቅዱስ  የእግዚአብሔር  ልጆች  መሆናችንን  ይመሰክርልናል፤  ሮሜ  8፥14-17።  3ኛው  ምስክር  የተለወጠ  ሕይወታችን  ነው።  ቀድሞ  የነበርነውን አይደለንም፤  ያልነበርነውን  ደግሞ  ሆነናል።  ሰው  ሲድን  አቤት  እረፍት!  አቤት  እፎይታ፥  አቤት  ሰላም!  አቤት  ነፃነት!  በመስቀል  ላይ  ከተፈጸመው የጌታ  ሥራ  የተነሣ  ደኅንነት  በእምነት  ብቻ  ነውና  በሥራ  እግዚአብሔርን አስደስቶ  መዳንንና  ጽድቅን  ለመቀዳጀት  መፍጨርጨር  የለም።  ይህ ደኅንነት  ደግሞ  ይጠፋል  ተብሎ  በስጋትና  በሰቀቀን  ሳይሆን  በታማኙ ታምኖ የሚኖሩት ኑሮ ነው። ክርስትና ይህ ቀላል የሆነ መዳን ነው። መ/ር ምህረተአብ  ምላሽ  በሰጠበት  ስብከት  ፓስተር  ዳዊት  “አታክብዱብን” ያለው  ይህንን  ነው።  መዳን  ይህንን  ያህል  ቀላል  ሆኖ  ነው  በአዲስ  ኪዳን የቀረበው።  ቀላል  ነው  ማለት  ግን  ርካሽ  ነው  ማለት  አይደለም።  ክቡር ዋጋ የተከፈለበት ነውና ርካሽ አይደለም፤ ግን ነፃ ነው! ነፃ! በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ግን  ይህንን  ነፃ፥  ቀላል፥  የሚያሳርፍ  ደኅንነት አናይም።  የማናይበት  ምክንያት  ግልጽ  ነው።  አንድ  ደራሲ  የሚያሳየው ያየውን  ነው።  እነዚህ  ሰዎች  ይህንን በጸጋው ብቻ  መዳንን  አልቀመሱም።
የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ከቶም አይደለችም።  ይህች  ማርያም  የክርስቶስ  ማዳን  እንዳይታይ  መጋረጃ ተደርጋለች።  ስለዚህ  ኢየሱስን  እስከ  መስቀሉ  እንኳ  ሳይሆን  እስከ አገልግሎቱም  ጅማሬ  ሳያደርሱት  በእናቱ  ስር  ያለ  ታዛዥ  ወጣት አድርገው  በ18  ዓመቱ  መጽሐፋቸውን  ደመደሙ።  ደኅንነት  ያለው መስቀሉ  ላይ  ነዋ!  በውስጡ  የሚታዩ  ሰዎችም  መዳንን  ያልተለማመዱ በነፍሳቸውም  የተቅበዘበዙ  ሰዎች  ናቸው።  በመጽሐፉ  ጥላቻ፥  ቂምና በቀል፥ መግደል፥ ፍርሃት፥ የሥልጣን ጥም፥ ውሸት፥ ወዘተ ይታዩበታል።  በምዕ.  61  ማርያምም  ውሸታም  ተደርጋ  ቀርባለች።  በአንዲት  ባልቴት ተመስላ  ወደ  አንድ  ሹም  ዘንድ  ሄዳ  የዋዳ  አገር  ሴት  መሆኗን  ነግራው ነበር።  የተአምረ ማርያሟ ማርያም መዋሸትም ትችላለች።

7.  ይህ ደራሲ  ያልተዋጣለት ልብ ወለድ ደራሲ  ነው። 

የተዋጣለት  ቢሆን መጽሐፉ ልብ ወለድ መሆኑን ይገልጥ ነበር። ነገር ግን፥ መጽሐፉ እውነት ሳይሆን  እውነት  ተደርጎ  ቀርቦአል።  እውነት  ያለመሆኑን  የሚያረጋግጡ ማስረጃዎች በቀጣዩ  ንዑስ ርእስ  ይቀርባሉ። በመጽሐፉ  ውስጥ  ከእውነት ጋር የተጠጋጋው  ብቸኛ ክፍል በዘርዓ ያዕቆብ  ዘመን ለማርያምና ለስዕል፥ ለመስቀልም  ስግደት  የተገባ  አይደለም  ብለው  ስቃይ  የደረሰባቸው  ሰዎች  (ደቀ እስጢፋኖስ)  ጉዳይ  የተጻፈበት  ተአምር  24  ብቻ  ነው።  ለዚያውም ከተሰደዱቱ  አንጻር  ከተጻፈው  ጋር  ሲተያይ  በውስጡ  የተጠቀጠቁውሸቶችም  አሉበት።  በሌሎች  ምዕራፎች  የተጠቀሱ  ታሪካዊ  ሰዎችም እንኳ  በታሪክ  ማኅደር  ሲፈተሹ  በተአምረ  ማርያም  የሚታየው ማንነታቸው ከእውነተኛ ማንነታቸው ጋር አይገጥምም። ተረቶችና  የፈጠራ  ሥራዎች  የእውነት  መልክ  ሊይዙ  የሚችሉባቸው ዘመናት  ያኔ  ብቻ  አይደለም፤  ዛሬም  ያው  ነው።  ለምሳሌ፥  የዳቪንቺ  ኮድ ልብ  ወለድ  መጽሐፍ  ነው።  መጽሐፉ  ተናፍሶለት  ፊልምም  ሆኖ ለተመልካች  ሲበቃ  ያዩት  አላዋቂ  ሰዎች  ታሪኩ  እውነትና  ቤተ  ክርስቲያን እንዳይወጣ  ደብቃ  የያዘችው  ምስጢር  እንደሆነ  ሽንጣቸውን  ገትረው ተከራክረዋል።  በሕይወት  ያለው  ደራሲ  መጽሐፉ  ልብ  ወለድ  መሆኑን እየመሰከረም  እንኳ  ልብ  ወለዱን  እውነት  ነው  ብሎ  መከራከር  ጅልነት ሳይሆን  እብደት  ነው።  ተአምረ  ማርያምም  ሆን  ተብሎ  ባለበት  መልኩ ተጽፎ  ካልሆነ  ምናልባት  በመጀመሪያ  እንደ  አጫጭር  ተረቶች  መድብል ተጽፎ ኋላ ማርያማዊ  ቀለም የተቀባበት  ይመስላል፤ ሊሆንም ይችላል።
እነዚህ  ጥቂት  ነጥቦች  ከቁጥር  ሊገቡ  የተገባቸው  የደራሲዎቹ  ወይም የደራሲው  ባህርያት  ናቸው።  እንደ  ደራሲው  መጽሐፉ  ራሱ  ደግሞ ሲፈተሽ ይህ መጽሐፍ የራሱ ውስጣዊ ባህርያት አሉት።

የመጽሐፉ ባህርያት / ይዘት

ራሱን  በየጊዜው  ለማረምና  ለማስተካከል  ወይም  ከዘመኑ  ጋር ለመመሳሰል  ከሚጥር  በቀር  በየትኛውም  ሃይማኖትም  ይሁን  ፍልስፍና ዘንድ  አንድ  ዋና  መሠረታዊ  መጽሐፍ  ይኖራል።  ሌሎች  ጥቃቅን መጻሕፍትም  ደግሞ  ይኖራሉ።  ሁልጊዜ  ጥቃቅኖቹ  የዋናውን  አሳብና ፈለግ  እየተከተሉ  ያንን  ያጠነክሩታል፥  ያብራሩታል  እንጂ  አይጻረሩትም። ዋናው  መጽሐፍ  ስሕተት  ያለበትና  የሚስተካከል፥  ወይም  በየጊዜው የሚሻሻል  ሆኖ  ካልተገኘ  በስተቀር  በጥቃቅኖቹ  መጻሕፍት  ውስጥ የሚገኙት  አሳቦች  በሙሉ  ወይም  በከፊል  ስሕተት  የተገኘባቸው እንደሆነ፥  ወይም  ከዋናው  መጽሐፍ  ጋር  የተጋጩ  ሆነው  ቢገኙ  ዋናው ትክክል ጥቃቅኖቹ እንደ ስሕተተኛ ይቆጠራሉ። ወደ  ክርስትና  እምነት  ስንመጣ  ምንጩ  መንፈስ  ቅዱስ  የሆነ  አንድ  ዋና፥ የማይለወጥ፥  ትክክለኛ፥  ሙሉ  ሥልጣን  ያለው  መጽሐፍ  አለን።  ይህ መጽሐፍ  ማናቸውም  ሌላ  መጽሀፍ፥  ስብከት፥  እና  ትምህርት  ብቻ ሳይሆን  አኗኗርም፥  ልምምዶችም፥  የሚፈተሹበት  ነው።  ይህ  መጽሐፍ መጽሐፍ  ቅዱስ  ነው።  ማንም  ክርስቲያናዊ  ካባ  የደረበ  መጽሐፍ ከካባው በታች ያለው ሰውነቱ በዚህ መጽሐፍ መርማሪነት መፈተሽ አለበት።
ተአምረ  ማርያም  ምንጩ  ምንድርነው?  ትውፊት  ነው  ወይስ  አፈ  ታሪክ ወይስ  ተረት?  ለምን ምንጩ  መጽሐፍ  ቅዱስ አልሆነም? መጽሐፍ  ቅዱስ መጽሐፍ  ቅዱስ  የወጡ  ጥቂት  ምንባቦች  መጽሐፉን  ክርስትና  እንዲሸት ተብለው  ከዐውዳቸው  ተፈንቅለው  በውስጥ  ተስገዋል።  ይህን  የሚያህሉ ግዙፍ  ትምህርቶች  ሲሰጡ  በመጽሐፍ  ቅዱስ  መፈተሽ  አያስፈልግም ነበር? ሌሎችም መፈተሻዎች አሉ። መጽሐፉ እርስ በርሱ ይጋጫል ወይስ አይጋጭም?  ከሌሎች  መሰል  መጽሐፎች  ጋርስ  ይስማማል  ወይስ ይጣላል?  በአፈጣጠሩስ  ተዓማኒነትን  የጨበጠ  ነው?  ከታሪክና  ከተረት ወደ  የቱ  ይቀርባል?  ወደ  የቱስ  ያዘነብላል?  ታሪካዊ  ከሆነ  ታሪኩ  ከሌላ ምንጭ ጋር ሊስተያይ ይችላል?  ተአምረ  ማርያምን  አንብቤ  ከፈጸምኩ  በኋላ  በውስጡ  ካገኘኋቸው ሕጸጾች መካከል ዋና ዋና የምላቸው እነዚህ ናቸው፤
የደፈረሰ ምንጭ፥
የተቃለለ ክርስቶስ፥
የተጋነነች ማርያም፥
የተፈናቀለ ታሪክ፥
የተምታታ ሲዖልና መንግሥተ ሰማያት፥
የተጣረሰ ደኅንነትና የተቃወሰ ክርስትና፥
የተላቀቀ መልክዓ ምድር፥
የተዋረደ ጋብቻ፥
ያፈነገጠ ተፈጥሮ።

እነዚህን  ነጥቦች  በቀጣዮቹ  ገጾች  በነጥብ  አወሳቸዋለሁ።  እንዲህ የከፋፈልኩት  መጽሐፉን  በየምዕራፉ  ከመሄድ  ይልቅ  በነጥብ  መሄዱ የተሻለ  ሆኖ  ስላገኘሁት  ነው።  ከነጥቦቹ  አንድ  ሁለቱ  በቀደሙት  ገጾች የተነካኩ  ናቸውና  በነዚህ  እጀምራለሁ።  በየክፍሉ  ውስጥ  የተወሱት በአብዛኛው  ናሙና  ምሳሌዎች  ናቸው  እንጂ  ሕጸጾቹ  በሙሉ  ቢዘረዘሩ በትክክል ራሱን መጽሐፉን የሚያህል መጽሐፍ ይወጣዋል።

1.  የደፈረሰ  ምንጭ። 

ቀደም  ሲል  እንደተጠቀሰው  የእትሙ  አሳታሚው አይታወቅም።  መታወቁ  መልካም  የሚሆነው  ጥያቄንና  አጠያያቂ ጉዳዮችን  ለመነጋገር  እንዲያስችል  ነው።  አሳታሚውን  በተመለከተ መጽሐፉ  ከእትም  ወደ  እትም  የሚሸጋገረው  ከገቢ  ምንጭ  ጋር  በተያያዘ መልኩ  ሊሆን  ይችላል።  የደፈረሰው  ምንጭ  ግን  የመጀመሪያ  ደራሲውን የሚመለከት ነው።  የደፈረሰ  ሲባል  የጠራ  ነገር  ተቃራኒ  መሆኑን  ለማሳየት  ነው።  በዝርዝር እንደምናየው  መጽሐፉ  ከግብጽ  የመነጨ  ለመምሰል  ያልተሳካ  ሙከራ ያደርጋል።  በመምህር  ባዩ  ታደሰ  የተጻፈ  መጽሐፍ  ምንጩን  በተመለከተ፥ “በ1989  ዓ.ም.  የታተመው  ተአምረ  ማርያም  በዚህ  ጊዜ  ተጻፍሁ  ብሎ በግልጽ  ባይነግረንም  በውስጡ  ከያዛቸው  ዘመኑንን  ከሚያመላክቱ ታሪኮች  ተነስተን  ድምዳሜዎች  ላይ  መድረስ  የሚያስችሉንን  ፍንጮች ይዟል።”  ብሎ  ሦስት  ትልልቅ  ነጥቦችን፥  ማለትም፥  በዘመኑ  በርካታ መጻሕፍት  መደረሳቸውን፥  የተተረጎመበትን  የአባ  ሚካኤልንና  አባ ገብርኤልን  ዘመነ  ጵጵስና፥  በዘመኑ  የተደረገውን  የነአባ  እስጢፋ  ስደት ዘርዝሮ  ይህንኑ  አሳብ  ሲደመድም  እንዲህ  ይላል፥  “መጽሐፉን  ትኩረት ሰጥተን  ስንፈትሸው  ግን  በ15ኛው  ክፍለ  ዘመን  ጳጳሳቱ  ኢትዮጵያ  ውስጥ ከገቡ  በኋላ  አከናወኑት  የተባለውን  ኢትዮጵያዊ  ታሪክ  በውስጡ  ይዞ ስለሚገኝ  ከግብጽ  ነው  የመጣው  መባሉን  ለማመንና  ከዚያ  ክፍለ  ዘመን በፊት  የተጻፈ  ነው  ለማለት  የሚያስችለንን  ድፍረት  እንድናጣ ያደርገናል።"
ዲያቆን  ጽጌ  ሥጦታው  ባስተማራቸው  ትምህርቶች  ላይ  በኢኦተቤክ ቅዱስ  ሲኖዶስ  የሊቃውንት  ጉባኤ  በተደረገበት  ሃይማኖታዊ  ምርመራ ወይም  ክርክር  አንዱን  የክስ  ጥያቄ፥  “ተአምረ  ማርያም  የተጻፈው  አባ እስጢፋኖስን  ለመቃወም  ነው  ብለሃል  ተባልሁ”  በማለት  ያነሣና መጽሐፉ  በእርግጥ  የተሠራው  እዚሁ  አገር  ውስጥ  መሆኑን  በዝርዝር መልሶአል።  ይህንንና  ሌሎችንም  ተቀራራቢ  ጥያቄዎች  በጻፈው  መጽሐፍ ውስጥ አካትቶአል።
ተአምረ  ማርያም  በውስጡ  እንደተጻፈው  በእርግጥ  ከመንበረ  ማርቆስ ከተገኘ ከዚያ ወዲህ በመንበረ ማርቆስ ይህ መጽሐፍ መኖሩ የታወቀ ነው ይሆን?  ወደ  መንበረ  ማርቆስ  ከመግባቱ  በፊትስ  የት  ነበር?  ወይስ  እዚያ ነው  የመነጨው?  የግብጽ  ቤተ  ክርስቲያን  ይህ  መጽሐፍ  ኖሮአት ያውቃል? ወይም ይህን መጽሐፍ ንብረቴ ነው ብላ ታውቃለች? በዐረብኛ የተጻፈ  ብዙ  መቶዎች  ዓመታት  ያስቆጠረ  የምንጭ  መጽሐፍስ  አለ?

እንዲያው  በዐረብኛ  ተጽፎ  ከሆነ  ተብሎ  ከታሰበ  ለማለት  ነው  እንጂ የምንጩ  ጽሑፍ  በግብጽ  ስለመኖሩ  የሚናገር  ምንም  አመላካች  ነገር በመጽሐፉ  ውስጥ  የለም።  ከግብጽ  ውጪ  ስለመኖሩም  አመልካች  ነገር የለም። የምችለውን ያህል ውጪያዊ ምንጮችን ከመጻሕፍትም፥ ከመረጃ መረብም  በመፈለግ  ይህን  የአገራችንን  ተአምረ  ማርያም  የሚመስል ወይም  እንደ  ምንጭ  ሆኖ  ሊጠሩት  የሚቻል  ቀራቢ  ሰነድ  ላገኝ አልቻልኩም።  ተገልጠው  ከተሰደሩ  የግብጽ  ቤተ  ክርስቲያን  የሰነድ ስብስቦችም  ውስጥ  እንኳ  ይህ  ተአምር  የለም።  በዲያቆን  ጽጌ  መጽሐፍ በግብጽ  ውስጥ  ተአምረ  ማርያም  በግብጽ  አለመኖሩን  በተመለከተ  ብዙ ዓመታት (10 እና 13 ዓመታት) በዚያ ተቀምጠው የመጡ መነኮሳት ይህን መሳይ  ተአምር  [ተአምረ  ማርያም]  በግብጽ  ያለመኖሩን  ማረጋገጣቸውን ዘግቦአል። ምንጩ  ጠፍቶ  ቅጅው  ብቻ  ነው  አሁን  ያለው  ወይም  በዚህ ዘመን  የቀረው  ካልተባለ  ምንጩ  ካለበት  ተገኝቶ  ቢፈተሽ  ስለምንነቱ ከቅጅው ይልቅ እውነቱን የመግለጥ ጉልበት ይኖረዋል። ከሌለም፥ ‘ዋናው እነ  አባ  አብርሃም  የጻፉት  ከገጸ  ምድር  ጠፍቶ  አሁን  የሚገኘው  ይህ በእጃችን ያለው የኛ ቅጅ ብቻ ነው’ ተብሎም መገለጥ አለበት።  በሌላ  ገጽታው  ግን  ተአምረ  ማርያም  የተተረጎመ  ሳይሆን  በኢትዮጵያ ውስጥ  የተሠራ  አገር  በቀል  መጽሐፍ  መሆኑን  የሚገልጡ  እጅግ  በርካታ ማስረጃዎችን በውስጡ የታቀፈ ጽሑፍ ነው። ይህ ማለት የወዲያ ታሪኮች ከግብጽ  ከመጡት  የተሰሙ  ወይም  የተነገሩ  ሊኖሩ  መቻላቸው  ሳይዘነጋ ነው።  በግብጽ  ውስጥ  ያሉ  ገዳማትና  ግልጽና  የታወቁ  ያልሆኑ  ቦታዎችም ጭምር  ተጠቅሰዋል።  ግብጽና  ግብጻውያን  ግን  እየተደነቁ  ሳይሆን እየተወገዙ  የተነገረባቸው  ታሪኮች  ያይላሉ።  በአንጻሩ  ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን  እየተመሰገኑ  ተጽፈዋል።  ግብጻዊ  ምንጭ  ግብጽን ሲያኮስስና ሲያዋርድ፥ ኢትዮጵያን ሲያገንንና ሲያሞግስ ይነበባል። በግብጽ  ውስጥ  በዐረብኛ  ቋንቋ  ስለ  ማርያም  እየተጻፈ  የኢትዮጵያ ቦታዎች እጅግ ተዘርዝረው ተጽፈዋል። እነሽሬ፥ ተከዜ፥ ዋሊ (ዋልድባ?)፥ ሸዋ፥  ደዋሮ፥  ሙገር፥  ወግዳ፥  መርሐ  ቤቴ፥  ኢፋት፥  ትግራይ፥  የረር፥ አግዓዚ፥  ደብረ  ብርሃን፥  ዳሞት፥  ጎጃም፥  አክሱም፥  መጠራ፥  ጣና፥ ሀዘሎ፥ ደብረ ወገግ፥ ዝቋላ፥ ወዘተ፥ የኢትዮጵያ ሰዎች እነ ሠረቀ ብርሃን፥አስከናፍር፥  ዘሚካኤል፥  ዘርዑ፥  ያሬድ  (ባለ  መዝሙሩ  ያገራችን  ሰው)፥ ዘርዓ ያዕቆብ፥ ዘርዓ ክርስቶስ፥ ዘርዓ ሐዋርያት፥ ወዘተ፥ በኢትዮጵያ የሆነ ታሪካዊ  ክስተት  ለማርያምና  ለመስቀል መስገድ  የተገባ አይደለም ያሉ  የነ ደቀ  እስጢፋ  ዝርዝር  ታሪክ  ሁሉ  መጽሐፉ  ከውጭ  ሆኖ  ስለ  ኢትዮጵያ እየዘገበ  የነበረ  ሳይሆን  እውስጥ  ሆኖ  እየተናገረ  ያለ  መጽሐፍ  መሆኑን ይፋ ያደርገዋል።

የኢትዮጵያ  ግዛቶች  ስሞች  እነ  ማርያም  የኖሩባቸውና  ከሄሮድስ  ሸሽተው ወደ  ኢትዮጵያ  መጥተዋል  ተሰኝቶ  ነው።  ይህም  ራሱ  ራሱን  ማቆም እስከማይችል  ድረስ  የገዘፈ  ፈጠራ  ነው።  እውነተኛው  ታሪክ  የተጻፈው በማቴ. 2፥13-23  ብቻ  ሲሆን  በትንቢት  እንደተጻፈው  የሄዱትና  የቆዩት በግብጽ፥  የተመለሱትም  ከግብጽ  ነው።  ተአምረ  ማርያም  ኢትዮጵያ ውስጥ  በደብረ  መጠራ  ሳሉ  የሄሮድስ  ሞት  ተነገራቸው  የሚለው  ከአዲስ ኪዳን  ጋር  ይጋጫልና  ትልቅ  ውሸት  ነው።  ወደ  ኢትዮጵያ መጥተው  ኖሮ ቢሆን ማቴዎስ  ይህን ለምን አይነግረንም ነበር? ከሆነ ምንም አሳፋሪ ነገር የለበትም።  ይህ  የተሳገ  ትረካ  መጽሐፉ  እዚሁ  አገራችን  ተቦክቶ የተጋገረበት  አንድ  አመላካች  ነው።  መመለሳቸውን  በተመለከተ  ማቴዎስ ከግብጽ  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ከመጠራ  (ኢትዮጵያ)፥  ማቴዎስ  ለዮሴፍ ተነገረው  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ለማርያም፥  ማቴዎስ  መልአክ  በሕልም ነገረው  ሲል  ተአምረ  ማርያም  ገብርኤል  ለዮሴፍ  ነግሮት  ያረጋገጠላት ደግሞ  ልጇ  ኢየሱስ  ነው  ይላል።  እነዚህ  ሁለት  ምንጮች  እንዲህ ከተጣሉ  ማን  ይደመጥ?  ከተረት  የሚያንሱ  ነገሮች  የታጨቁበት  ተአምረ ማርያም ወይስ መጽሐፍ ቅዱስ? እዚህ  ተደርሶ  ወደ  ዐረብኛ  ተተርጉሞ  እንደገና  ወደ  ግዕዝ  የተመለሰ የግብጽ  ደርሶ  መልስ  ቲኬት  ተቆርጦለት  ሄዶ  እንደመጣ  የተደረገ  ሥራ ካልሆነ  ወይም  የጥንት  ባላባቶች  የአገልግል  ምግብ  ሲያምራቸው  እቤት የተሠራ  የአገልግል  ምግብ  አገልጋይ  ተሸክማ  በፀሐይ  ስትዞር  ውላ  መልሳ ወደተሠራበት  ቤት  እንደምታመጣው  ዓይነት  ካልሆነ  በቀር  ተአምረ ማርያም  የአገር  ውስጥ  ሥራ  ነው።  ይህ  መጽሐፍ  የተፈጠረበት  ዘመን አምልኮተ  ማርያም  የገነነበት  መሆኑ  ይህን  አገር  በቀልነት  ግልጽ ያደርገዋል።  የአገሪቱ  ጳጳሳት  እየተሾሙ  ይመጡ  የነበረው  ከግብጽ በመሆኑ  ግብጻዊ  ተጋቦት  እንዳለው  አይካድም።  ግብጻዊ  ተጋቦትና ከውጪ  የተጫሩ  ‘ታሪኮች’  ይኑሩበት እንጂ ተተረጎመ  የተባለበት  [ወይም የተጻፈበት]  ዘመንና  ሁኔታ  ምንጩን  አገራዊ  ያደርገዋል።  ምንጩን አገራዊ  ከሚያደርጉት  ነገሮች  ሌላው፥  በሌሎች  አገሮችና  ሃይማኖቶች በአፍቅሮተ  ማርያምና  በአምልኮተ  ማርያም  በተጠመዱቱ  መካከል  እንኳ ይህ መጽሐፍ ያለመገኘቱ ነው።
የመጽሐፉ  ደራሲዎች  ሦስት  ሆኑና  ከዚህ  የተነሣ  መጽሐፉ  እርስ  በርስ የሚጋጩ  ብዙ  ነገሮች  ኖረውበታል።  ቅራኔዎቹና  ግጭቶቹ  ከመጽሐፍ ቅዱስ  ብቻ  ሳይሆን  እርስ  በርሱም  ከታሪክም  ጋር  ነው።  ምናልባት ሲጠናቀቅ  አንድ  ሰው  ነው  የደበለውና  ቅራኔዎቹን  ሳያስታርቅ፥ ግጭቶቹንም  ሳይከረክም  በእያንዳንዱ  ምዕራፍ  ጅማሬና  ድምዳሜ ተመሳሳይ አንቀጾችን መለጠፉ መጽሐፉ የአንድ ሰው እጅ እንጂ የማኅበር እንዳይመስል አድርጎታል።

 የተጻፈበት ዘመን የዘርዓ ያዕቆብ ዘመን ነው። ቀደም ሲል  እንደጠቀስኩት  ተአምረ  ማርያም  ተተረጎመ  የተባለበት  የነገሠበት  7ኛ ዓመቱ  1434 ዓ.  ም.  መሆኑ  ነው።  ይህ  ዘርዓ  ያዕቆብ  የማርያምና የመስቀል  ስግደትን  ተግባራዊ  ያደረገ  ሰው  ነው።  ይህ  አዲስና  ኋላ  መጥ  ከመጽሐፍ  ቅዱስም  ያፈነገጠ  ትምህርት  መሆኑን  የተረዱና  እንቢ  ያሉ እስጢፋኖስ  በሚባል  መነኩሴ  የተመሩ  ሰዎች  መኖራቸው  አበሳጭቶት  ዘለፋ እስጢፋ  የሚባል  መጽሐፍም  የጻፈ ንጉሥ  ነው።  እነ  እስጢፋኖስን  በመቃወም  ብቻ  ሳይሆን  ሕዝቡንም  በጠንካራ  ማስፈራራት  ለመጠፈር  የማርያም  አምልኮ  አዋጅ  ታወጀ። አዋጁ  ደቂቀ እስጢፋን  የተቀበለ በቤቱ  ያኖረ  ርስት  ያለው  ከርስቱ  ሊነቀል፥  ሹሙ  ከሹመቱ  ሊሻር፥  እነዚህ  ደቀ እስጢፋ  ለድንግል  ማርያምና  ለአንድ  ልጇ  መስቀል  እንቢ  ያሉ ናቸውና አይሁድ  እንደሆኑ  ቅጣታቸውም  ሞት  መሆን  እንዳለበት  ነው።
እውነትም  አዋጁ  ገዳይ  ብቻ  ሳይሆን  አሰቃይቶ  ገዳይ  ሆነ።  አፍንጫ  እየተፎነነ፥  ምላስ  እየተቆረጠ፥  በግርፋትና  የከብት  አጎዳ  በላያቸው እየተነዳ፥  በድንጋይ  እየተወገሩ  ብዙዎች  በስቃይ  ተሰዉ።  ሃይማኖታዊ  ጥያቄዎችን  ለመጠየቅ  በቂ  እውቀት  ከሌለ፥  ቃሉን  አንብበው  መንፈሳዊ  ዓይናቸው  በርቶ  እውቀቱን  ያገኙትም  ሲጠይቁ  ወይም  ሲቃወሙ በንጉሥ ሥልጣንና  አቀነባባሪነት  ይህ  ግድያ  ከተፈጸመባቸው  ሕዝቡ  በመንፈሳዊ  ጨለማ እየዳከረ ቢኖር ምን ያስገርማል?

ለእንዲህ  ያለው  አምልኮተ  ማርያም  ቀዳሚው  ሁኔታ  ምን  ነበር  የሚለው ጥያቄ  ጥናት  የሚፈልግና  ከዚህ  መጣጥፍ  አሳብ  ያለፈ  ጉዳይ  ነው። በአጭር  ቃል  ግን  ስለ  ማርያምና  ወላጆቿ፥  ስለ  ኢየሱስ  ሕጻንነትና  ከዚያ ጋር  ስለተያያዙት  ነገሮች  የተጻፉት  በታሪክ  የሚታወቁት  መጻሕፍት የተጻፉት  ማርያም  ካረፈች  ከ100 ዓመታት በኋላ ነው። ታሪኩን  የሚናገሩ  በሌሉበት  የተፈጠረ  ሥራ  ነው።  ተአምረ  ማርያምማ  ራሱም  ስለ  ራሱ እንደሚመሰክረው  ከዚያ  መደብ  የሚገባም  አይደለም።  ማርያም በሕልምና  በራእይም እየተገለጠች  ያስጻፈችው ነውና። በዐፄ  ዘርዓ  ያዕቆብ  ዘመን  ከዚያ  ዘመን  በፊት  ኖሮ  ያልታወቀ  እንዲህ የመሰለ  መጽሐፍ  ቢጻፍ  ወይም  ቢተረጎም  ግን  አይደንቅም።  የዐፄ  ዘርዓ ያዕቆብ  ዘመን  ከሚታወቅባቸው  መልኮች  አንዱ  የስነ  ጽሑፍ  ፍንዳታ ነው።  ራሱ  ንጉሡም  አስቀድሞ  በገዳም  የኖረ  መነኩሴ  ሲሆን  መንግሥት በአጭር  ጊዜ  ከአባቱ  ሞት  በኋላ  ወደ  ወንድሞቹ  እየተላለፈ  ኋላ ከወንድም  ወደ  ወንድም  ልጅ  ሲያልፍ  ቆቡን  ጥሎ  ዘውድ  ሊደፋ ከምንኩስና  ወደ  ንግሥና  የመጣ  ሰው  ነው።  እንደ  ክርስቲያን  የተቀደሰ ኑሮ  በመኖር  ምሳሌ  የሆነ  ሰው  ሳይሆን  ደርቦ  እያገባና  እንደወደደ  የኖረ፥ እንደ  ክርስቲያን  በእግዚአብሔር  በመታመን  ሳይሆን  ጥንቆላን በመፍራትና በመሳቀቅ የኖረ ሰው ነው። እንደ  ገዳም  ሰውም  እንደ  ንጉሥም  ራሱም  እየጻፈም  ሌሎችንም እያስጻፈና  ከሌሎች  ቋንቋዎች  እየተተረጎመም፥  ዜጋው  በግዴታ የሃይማኖትና  የኅሊና  ጫና  እየተደረገበትም  ብዙ  ሠርቶአል።  ከእርሱ ዘመን  ቀደም  ሲል  መጡ  የተባሉ  ስዕሎችና  ግማደ  መስቀልም  ገናና ሆነዋል።  በዚህ  ጊዜ  ነው  ለማርያም  ስዕል  መስገድ  የመንግሥት  ግዴታ የሆነው።  እነ  መጽሐፈ  ምዕላድ፥  አርጋኖነ  ድንግል፥  ይኸው  በዚህ መጣጥፍ  የምንመለከተው  ተአምረ  ማርያም፥  ይህን  አዲስ  ጫና ላለመቀበል  በቆረጡት  ላይ  የተጻፈ  ዘለፋ  እስጢፋ፥  መጽሐፈ  ብርሃን እና መጽሐፈ  ጽልመት  ሌሎችም  ብዙ  በዚህ  ዘመን  ተጽፈዋል።  ነገረ ማርያምን  በተመለከተ  እንዲህ  የበዙ  መጻሕፍት  በተደረሱበት  ዘመን  ላይ ይህም መጽሐፍ ተተረጎመ ሳይሆን ተደረሰ ቢባል ተገቢ ነው። ሃይማኖቱ የንጉሥ  ጫና  ያለበት  ሲሆንና  ንጉሡ  ራሱም  ደራሲ  ይህን  መሳይ  ጽሑፍ የሚያስሸልምና  ባለሟል  የሚያስደርግ  ከሆነ  ለመጽሐፉ ፈጣሪዎችም  ይህ ዘመን ምቹ ዘመን ነው።

ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,
ማሳሰቢያ፤
 በመልእክት ሳጥናችን ገንቢ ያልሆኑና ስህተት ካለ ለእርማት የማያመቹ አስተያየቶችና ስድቦች እየደረሱን ነው። ጸሐፊው የተሳሳተው ነገር ካለ ወይም ጽሁፉ በቀረበበት ርዕስ ላይ በቂ ምላሽ መስጠት የፈለገውን በቀጥታ ለጸሐፊው በማቅረብ ወይም በመካነ ጦማራችን ላይ በማውጣት ለማስተናገድ ዝግጁ መሆናችንን እየገለጽን ለጸያፍ ቃላት ከተዘጋጀ የስመ ክርስትና አንደበት በመራቅና  ከኔ ወዲያ እውነተኛ ጸዳቂ  የለም!  ከሚል ሌላውን የመኮነን ግብዝነት መለየት የተሻለ እንደሆነ እንመክራለን ። ከዚያ በተረፈ  ብንቀበለውም፤ ባንቀበለውም ያለው እውነት በወንጌል የተነገረላት የክርስቶስ ኢየሱስ እናት ቅ/ማርያምና በተአምረ ማርያም ያለችቱ ማርያም አንድ አይደሉም። የክርስቶስ እናት ድንግል ማርያም ሁሉን ነገር በትዕግስትና በትህትና ትጠብቅ የነበረች ፍጹም ትሁትና የመሀሪ እናት ስትሆን (ሉቃስ 2፤19) የተአምረ ማርያሟ ማርያም ግን ሲኦል የምታወርድ፤ የምትሰነጥቅ፤ እንደእንጨት የምታደርቅ፤ የሰባት ዓመት መንገድ ያህል የሰው ሬሳ እንዲገማ የምታደርግ፤ ሥሉስ ቅዱስን የሚክድ የምትወድ፤ ጥላዋን ጥላ ሚዛን የምትሸውድ፤ ስሟንና ሀገሯን ሳይቀር በመደበቅ የምትዋሽ፤ እሁድ እሁድ ተአምሯን ያልሰማውን የምታወግዝና በአጠቃላይ አንዳችም ክርስቲያናዊ ጠባይ የሌለባት፤ ከክርስቶስ ይልቅ እኔ ልግነን የምትል፤ ጭካኔ የሚታይባት ናት። ይህች ኢትዮጵያ ውስጥ በዘርዓ ያዕቆብ የተፈጠረችው ማርያም፤ በየትኛውም መንፈሳዊ መመዘኛ መንፈስ ቅዱስ ያነጻትና የቀደሳት ድንግል ማርያምን አትወክልም።

Tuesday, June 17, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

ተአምረ  ማርያም  የተባለው  መጽሐፍ  እንደ  ስያሜው  ሁሉ  ማርያም እንዳደረገቻቸው  የሚነገሩ  የብዙ  ተአምራት  መድብል  ነው።  ከተአምራቱ በጣም  ጥቂቱን  ሕጻኑ  ኢየሱስ  ያደረጋቸው  ሲሆኑ  ብዙዎቹን  ማርያምና የማርያም  የተለያዩ  ስዕሎች  ናቸው  ያደረጉት።  አንዳንዱ  ምዕራፍ  ምንም ተአምርነት  የሌለበት  የተደረጉ  ነገሮች  የተዘገቡበት  ዘገባ  ቢሆኑም በእያንዳንዱና  በሁሉም  ምዕራፎች  መግቢያ  ወይም  አናት  ላይ  ማርያም ያደረገቻቸው  ተአምራት  እንደሆኑ  በቀይ  ቀለም  እየተጻፈ  በአንቀጽ ተቀምጦአል።  ተአምር  ባልሆኑት  ላይ  በአናቱ  ላይ  የማርያም  ተአምር መሆኑን  መጻፉ  የግድ  መሆን  ስላለበት  የተደረገ  ይመስላል።  ለምሳሌ፥ ሁለተኛው  ተአምር  ወይም  ምዕራፍ  ማርያም  ስለ  መጸነሷና  ስለ  ልደቷ የተነገረ  ሲሆን  ያው  የግዴታ  ልማድ  ሆኖ  ክብርት  እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ተብሎ ተጽፎአል። ያለዚያ እንደ ምዕራፍ 2 መግቢያ ማርያም  ገና  ከመጸነሷና  ከመወለዷ  በፊትም  ተአምር  ታደርግ  ነበርና ከልደቷ  በፊትም  ቀዳሚ  ኅልውና  ነበራት  ማለት  ይሆን?  አጻጻፉ ይመስላል። ከሆነ ዘላለማዊት ናት ሊሰኝ ይመስላል።  የመጽሐፉ አሳታሚና ባለቤት ማን ነው? ይህኛውን  (እኔ  ያነበብኩትን)  እትም  ያተመው  ተስፋ  ገብረ  ሥላሴ ማተሚያ  ቤት  ሲሆን  አሳታሚው  አልተጻፈም።  ከመግቢያው እንደሚነበበው  ግን  አሳታሚው  ተስፋ  ገብረ  ሥላሴ  ዘብሔረ  ቡልጋ ነው።  ይህ  መጽሐፍ  በኢኦተቤክ  ሰፊ  ተቀባይነት  ያለው  የነገረ  ማርያም ሰነድ  መሆኑ  አጠያያቂ  ባይሆንም  በማን  ቡራኬ  መታተሙ  አልተጻፈም። በበርካታ የኢኦተቤክ መጽሐፎች እንደሚታየውም የሊቀ ጳጳስ ምስል እና መልእክትም  የለበትም።  ስለዚህም  አይቶ፥  መርምሮ  አጽድቆ  ለአንባቢ የተገባ  ነው  ብሎ  ያሳለፈ  ተጠያቂ  አካል  የለውም  ማለት  ነው።  በእውኑ የኢኦተቤክ  ይህን  መጽሐፍ  እንደ  ቅዱስ  መጽሐፍ  አድርጋ  ትቀበለዋለች?  መቼም  ከተቀበለችው  በቂ  የሆነ  ታሪካዊ  ምንጭ  ያለው  ሆኖ  መገኘት አለበት?  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋርም  መጋጨት  የለበትም።  ምክንያቱም ማንም  ክርስቲያናዊ  መጽሐፍ  አስተምህሮአዊ  ተደርጎ  ከተወሰደ  ምንጩ መጽሐፍ ቅዱስ መሆን አለበት። ታሪካዊ ከሆነ ደግሞ ታሪካዊ ብቻ ነውና ሥልጣን  ያለው  መጽሐፍ  መሆን  የለበትም።  ደግሞም  ከዋናው ክርስቲያናዊ  መጽሐፍ  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ተያይቶ  ሊቀበሉት  ወይም ሊጥሉት የተፈቀደ መሆን የተገባው ነው። የኢኦተቤክ ይህን መጽሐፍ የኔ ብላ ትቀበለው ወይም አትቀበለው እንደሆነም  ግልጽ  አይደለም። በአንድ ድረ  ገጽ  ላይ  በቅርብ  ያነበብኩት  ሁለቱ  ሲኖዶሶች  ከሚነጋገሩባቸው ነጥቦች አንዱ ይህ መጽሐፍ እንደሆነም ነው። መጽሐፉ  አሁን  በታተመበት  ቅርጹ  አማርኛው  ከግዕዙ  ጋር  ጎን  ለጎን በመሆን  ተጽፎአል።  አንዳንዱ  የአማርኛ  ቃላት  ሆን  ተብለው  የተለሳለሱ ሲመስሉ  አንዳንዱን  አማርኛ  ለመረዳት  ደግሞ  ራሱ  ግዕዙ  ለዘመናችን አማርኛ  የቀረበ  የሚመስልባቸው  ቦታዎችም  አሉ።  አንዳንዱ  ጥቅስ ከትርጉም  ይልቅ  ማብራሪያ  የሚመስልባቸው  ቦታዎችም  ብዙ  ናቸው። የተአምራቱ  ቁጥራቸውም  ከአንዱ  እትም  ወደ  ሌላው  ይለያያል  ይባላል። እኔ  ባነበብኩት  መጽሐፍ  (የŦ ŹƃƂƆ  ዓመተ  ምሕረት  እትም)  ተአምራቱ ወይም  ምዕራፎቹ  123  ናቸው።  አንዳንድ  ተአምራት  ወይም  ምዕራፎች በአንዱ  የመጽሐፉ  እትም  ይገኙና  በሌላው  እትም  የማይገኙ  ከሆኑ መጠኑና ይዘቱ ከእትም እትም ይለያያል ማለት ነው። በመምህር  ባዩ  ታደሰ  መጽሐፍ ውስጥ  ከተቀነሱት  ተአምራት  አንዱን ‘ተአምር  97’  የተባለውን  በመጥቀስ  ከቀድሞዎቹ  እትሞች  በአንዱ (ለምሳሌ፥  ከ1924ቱ  እትም)  ተጽፎ  ከኋለኞቹ  እትሞች  (ለምሳሌ፥ ከ1989ኙ እትም) እንደቀረ በማውሳት ይህ የሆነው ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በግልጽ  በመጋጨቱ  ምክንያት  እንደሆነ  ታትቶ  ቀርቦአል።  ለውጥ የሌለበት  ለማስመሰል  ግን  ‘በድጋሚ  የታተመ’  እየተባለ  መቅረቡተወስቶአል። በሌላ  አንድ  መጽሐፍ  ውስጥ  የተጠቀሰ  ተአምረ  ማርያም ደግሞ  ተአምራቱ  አንድ  መቶ  አሥራ  አንድ  መሆናቸውን  ይጠቅሳል። ቁጥሩ  ወጣ  ገባ  ነው።  በአንድ  ድረ  ገጽ  ስለ  ተአምረ  ማርያም  በተጻፈ አጭር  መልእክት  ላይ  ምላሽ  ከሰጡት  ሰዎች  አንዱ  ተአምር  19  ላይ  ስለ መሐመድ  የተጻፈ  ነገር  እንዳለበት  ጠቅሶአል። እኔ  ባነበብኩት  ምዕ. 19ማርያም  ሙታንን  እያስነሳች  ለሰዎች  ስታሳይ  ነው  የተጻፈው  እንጂ  ይህ ስለሌለ  በድረ  ገጹ  የተጻፈው  ትክክል  ከሆነ  ምዕራፎቹ  ተሸጋሽገው፥ ታጥፈው፥ ወይ ተሰርዘው ይሆናል? ምናልባት አንዳንዱ እትም ምዕራፎቹ እየተመረጡና  የሚያጠያይቁት  እየተነቀሱ  የታተመ  ሊሆን  ይችላል፤  ግን ከላይ  እንደተጠቀሰው  ‘በድጋሚ  የታተመ’  እየተባለ  ከውስጡ  እየተገመሰ ከቀረ ይህ ስነ ጽሑፋዊ እብለትና አንባቢን መደለል ነው።

 የመጽሐፉ ምንጭ / ደራሲው ማን ነው?

ተአምረ ማርያም በመጀመሪያ በግብጽ አገር ከመዓልቃ ከመንበረ ማርቆስ (መንበረ  ማርቆስ  በእስክንድርያ  ነው  የሚገኘው)  የተገኘ  በዐረብኛ  ቋንቋ የተጻፈና  በኋላ  ወደ  ግዕዝ  ተተረጎመ  የተባለ  መጽሐፍ  ነው።  የጻፉት  አባ አብርሃም፥  አባ  ማርቆስና  አባ  ማቴዎስ  የተባሉ  [መነኮሳት]  ሲሆኑ የጻፉትም  ማርያም  አንዳንዴ  ራሷ  እየተገለጠች፥  ሌላ  ጊዜ  በሕልም፥  ሌላ ጊዜ  በራእይ  እየታየች  እየተነጋገረቻቸው  እንደሆነም  በመቅድሙ ተጽፎአል።  እነዚህ  ሦስት  መነኮሳት  እነማን  ስለመሆናቸው፥  መቼ ስለመኖራቸው፥  የት  ስለመኖራቸው፥  የምን  አገር  ወይም  የየትኛው ዐረብኛ  ተናጋሪ  አገር  ሰዎች ስለመሆናቸው የሚናገርም ምንም  ማብራሪያ በመጽሐፉ  የለም።  እነዚህ  ጸሐፊዎች  እነማን  ናቸው  ቢባል መታወቂያቸው  ቢያንስ  በመጽሐፉ  ውስጥ  የሚገኝ  መሆን  ነበረበት፤  ግን የለም። በምዕ.  1  ደቅስዮስ  የተባለ  ሰው  ታሪኳን  ሲሰበስብ  እንደተገለጠችለትና ስለጻፈላት  እንዳመሰገነችውም  ተጠቅሶአል።  ይህ  ደቅስዮስ  ሰብሳቢም ጸሐፊም  ተብሎአልና  እንደ  ሰብሳቢ  ብቻ  ሳይሆን  ከነአባ  አብርሃም  ጋር እንደ  ጸሐፊም  የሚቆጠር  ነው።  በምዕ.  6  ደግሞ  አንድ  ሰው  ሌላ መጽሐፍ፥ የፍልሰት መጽሐፍ እንዳገኘ ይናገራል። ቁ. 23 ላይ ይህን የጻፈ ዮሐንስ ነውም  ይላል።  ቁ. 18  ላይ እርሱ ራሱ  የጻፈውን ነገረኝም ይላል። ስለዚህ  ከነአባ  አብርሃም  በፊት  የተጻፈ  ያውም  በሐዋርያው  ዮሐንስ የተጻፈ  የፍልሰት  መጽሐፍም  የነበረ  ይመስላል።  በምዕ.  7  ደግሞ ስንክሳርን  በመጥቀስ  ያንንም  እንደ  ምንጭ  በመጥቀስ  የማርያምን  ዕርገት ይተርካል።  ስለ  ደራሲዎቹ  ከስማቸው  ውጪ  ከመጽሐፉ  ውስጥ  የምናገኝላቸው  ነገር የለም።  ስምና  ማዕረግ  ብቻ  ‘አባ  እገሌ’  ተብሎ  ከመጠቀሱ  በቀር  ሌላ ያለመኖሩ  ምንጩን  ሆን  ተብሎ  የተድበሰበሰ  ያደርገዋል።  ‘አባ  እገሌ’ ደግሞ  የመነኩሴ  ሁሉ  መጠሪያ  ነው።  በማን  ዘመን  መንግሥት  ወይም በማን  ዘመነ  ጵጵስና  ነበሩ?  የት  ነበሩ?  እነዚህ  ሴዎች  ሌላ  ምን  ጻፉ?  ቢባል  አጥጋቢ  ቀርቶ  የማያጠግብም  ማስረጃ  አይገኝም።  ምናልባት  ኖሮ ቢሆን  ከዚያ  በመንደርደር  የዘመኑን  ታሪካዊ  ስነ  መለኮት  በመቃኘት ነባራዊ  እውነታ  መጨበጥ  ይቻል  ነበር፤  ወይም  ሌላ  የጻፏቸው  ሥራዎች ቢኖሩ  የሰዎቹን  ስነ  መለኮታዊ  አቋም  በንጽጽር  መገምገም  ይቻል  ነበር። ግን እነዚህ ነገሮች የሉም። የዐረብኛው  የምንጭ  ጽሑፍም  መቼ  እንደተጻፈ  የሚያረጋግጥ  ውጪያዊ ምስክር  ወይም  ውስጣዊ  ማስረጃ  አይገኝለትም።  ከመጽሐፉ  መግቢያ እንደሚገመተው  የመጀመሪያውን  የጻፉት  በዐረብኛ  ሳይሆን  አይቀርም። እንደሚገመተው  ያልኩት  ግዕዙ  ተተረጎመ  የተባለው  ከዐረብኛ  መሆኑ እንጂ  የምንጭ  ቋንቋው  ዐረብኛ  ይሁን  ወይም  ራሱ  ዐረብኛው  ከሌላ ቋንቋ  የተተረጎመ  መሆኑን  ስለማይናገር  ነው።  ከሆነ  ዐረብኛ  የግብጽ ቋንቋ የሆነውና ቅብጥ ወደ ኋላ ተገፍቶ ከመነጋገሪያ ቋንቋነት የተወገደው ከእስልምናና  የዐረቦች  ወረራና  መስፋፋት  በኋላ  ስለሆነ  ከ8ኛው  ምዕት  ዓመት  በኋላ  ይሆናል  ማለት  ነው።  እንግዲህ  በዐረብኛ  መጻፋቸውና የተገኘው  ከግብጽ  መሆኑ  የኢትዮጵያና  የግብጽ  አብያተ  ክርስቲያናትን ቁርኝት  ተንተርሶ  አገሩን  ግብጽ፥  ዘመኑንም  ከእስልምና  ወረራ  በኋላ ጀምሮ እስከ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን ባለው ጊዜ ነው ብሎ ሰፊ ግምት መቸር ይቻላል።  በመቅድሙ  ይህ  የተተረጎመው  መጽሐፍ  የተገኘው  ከመንበረ ማርቆስ መሆኑ ተነግሮአል።  ተአምረ  ማርያም  ተተረጎመ  የተባለበት  ዘመኑም  ተጽፎአል።  ግን  ዋናው ከተጻፈ  ከስንት  ዘመናት  በኋላ  ስለመተርጎሙ  ግምትም  እንኳ  መገመት አይቻልም።  ተርጓሚዎቹ  አባ  ሚካኤልና  አባ  ገብርኤል  የተባሉ  ናቸው። አሁንም  ከስማቸው  ውጪ  ስለሰዎቹ  ከመጽሐፉ  ውስጥ  የምናገኘው ማንነታቸውን  ገልጦ  የሚያስረዳ  ነገር  የለም።  ተረጎሙት  የተባለበት  ጊዜ “ቆስጠንጢኖስ  የተባለ  ንጉሣችን  በዘርዓ  ያዕቆብ  ዘመን  በነገሠም  በ፯ ዓመት”  ተብሎ  ተጠቅሶአል።  ቆስጠንጢኖስ  ወይም  ዐፄ  ዘርዓ  ያዕቆብ የነገሠው በኛ አቆጣጠር ከ 1427-1461 ዓመተ ምሕረት ነው። የነገሠ 7ኛ  ዓመቱ  1434  ዓ.  ም.  ነው  ማለት  ነው።  በኋላ  ላይ  የምንጩን ድፍርስነት  በተመለከተ  አወዛጋቢና  አጠያያቂ  ነጥቦች  አነሣለሁ።  በአጭሩ ግን  በመጽሐፉ  ውስጥ  ከተጻፈው  የሚገኘው  የተአምረ  ማርያም  ምንጭ፥ መነሻና ዘመን ይህ ነው።

የጸሐፊው / የጸሐፊዎቹ ባህርያት

በአንዳንድ  መጽሐፎች  አንዳንዴ  እውስጡ፥  አንዳንዴ  በሽፋኑ  ስለ ደራሲው የተጻፈ አጭር ወይም ረጅም ታሪክ ወይም ግለ ታሪክ ይገኛል። ከመጽሐፉም  ከሌላ  ስፍራም  ካልተገኘ  በመጽሐፉ  ውስጥ  ከተነገሩት ነገሮች  በመነሣት  አንባቢው  የደራሲውን  የተለያዩ  የእምነትና  ማኅበራዊ አቋሞች እንዲሁም ስነ ልቡናዊ ከባቢና ስፍራ ማወቅ ይችላል።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ስለመጽሐፉ  ደራሲዎችም  ሆነ  ተርጓሚዎች ማንነት፥  አገልግሎት፥  እምነት፥  ዘመን፥  ገጠመኝ፥  ቦታ፥  ቤተ  ሰብ  ወዘተ የተጻፈ  ነገር  የለም።  ከመጽሐፉ  በመነሣት  ግን  ተአምረ  ማርያምን  የጻፉት ደራሲዎች  ወይም  ደራሲ  እምነቱ፥  የመጽሐፍ  ቅዱስ  መረዳቱ፥  የታሪክ እውቀቱ፥  ከክርስቶስ  ቁርኝቱ፥  ወዘተ፥  ምን  እንዲመስል  መገንዘብ ይቻላል። ጥቂቶቹ እነዚህ ናቸው።

 1.  የተአምረ  ማርያም  ደራሲ  እግዚአብሔርን  የሚንቅ  ሰው  ነው።

እግዚአብሔር  በነቢዩ  ኢሳይያስ  አድርጎ፥  እኔ  እግዚአብሔር  ነኝ ስሜ  ይህ ነው  ክብሬን  ለሌላ፥  ምስጋናዬንም ለተቀረጹ  ምስሎች  አልሰጥም  ብሏል፤ ኢሳ.  42፥8።  ክብሩን  ለሌላና  ለተቀረጹ  ምስሎች  አሳልፎ  አለመስጠት ብቻ ሳይሆን የተቀረጹ ምስሎች መደረግም የለባቸውም። ከ10ቱ ትእዛዛት 2ኛው  ይህ  ነው፤  በላይ  በሰማይ  ካለው፥  በታችም  በምድር  ካለው፥ ከምድርም  በታች  በውኃ  ካለው  ነገር  የማናቸውንም  ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም  ምስል  ለአንተ  አታድርግ፥  አትስገድላቸው፥ አታምልካቸውምም።  ዘጸ.  20፥4።  የዚህ  መጽሐፍ  ጸሐፊ  ግን  በግልጽ ይህንን  አምላካዊ  ትእዛዝ  በመተላለፍ  የእግዚአብሔርን  ክብር  ለሌላ፥ ማለትም፥  በፈጣሪ  ለተፈጠረች  ለማርያም  እና  በሰዎች  እጅ  ለተሳሉ የማርያም ስዕሎች ሸንሽኖ አሳልፎ ይሰጣል። በመጽሐፉ  ውስጥ  እግዚአብሔር  የተገለጠበትን  ክብር  እና  ማርያምየተገለጠችበትን  ክብር  ስናነጻጽር  በጉልህ  እግዚአብሔር የማርያም ፈቃድ ፈጻሚ  ነው።  ወሳኟ፥  አድራጊዋ፥  ቀጪዋ፥  ሸላሚዋ፥  ተበቃይዋ፥  ወደ ሲዖል  አውራጇ፥  ከሲዖል  ነጣቂዋ  እርሷ  ናት።  አዳምና  ሔዋን  እና  ሰው ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብር ሳይሆን ለእርሷ ክብር እንደተፈጠሩ ይናገራል መጽሐፉ።  በመጽሐፉ  ውስጥ  የሚታዩት  የማርያም  ስዕሎች  እጅ  ዘርግተው የመሥራትና  የማድረግ፥  አፍ  ከፍቶ  ድምጽ  አውጥቶ  የመናገር፥  ብያኔ የመስጠት፥  ሲወጉት  የመድማት፥  ተመልሰው  ሲለጠፉ  ጠባሳ  ሆኖ የመቅረት  ባህርይ  ያላቸው  ምስሎች  ናቸው።  ተአምራት  ማድረግ የእግዚአብሔር  ሀብት  ቢሆንም  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  እግዚአብሔር ሳይሆን  ማርያም  እና  ምስሎቿ  ናቸው  ተአምር  አድራጊዎቹ።  ከእግዚአብሔር  ኃይል  እና ከጌታ  ከኢየሱስ ስም  ሥልጣን ውጪ  ተአምር ከተደረገ  የዚያ  ተአምርና  ምልክት  ምንጭ  እግዚአብሔር  ሳይሆን  ሰይጣን መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል።

2.  ይህ  ደራሲ  መጽሐፍ  ቅዱስን  የማያውቅ  ሰው  ነው። 

በጣም  በጥቂት ቦታዎች  አልፎ  አልፎ  የተጠቀሱ  የመጽሐፍ  ቅዱስ  ክፍሎች  አሉ።  እነዚህ የተጠቀሱ  ጥቂት  ጥቅሶች  የተጠቀሱት  ያለቦታቸው  በመሆኑ  ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጋጩና የሚጣሉ ነገሮች ናቸው። መጽሐፉ የተደመደመው ኢየሱስ  18  ዓመቱ  ሆኖ  በግሪክ  ሳለ  ሲሆን  በወንጌል  ውስጥ  ያደረጋቸው አንዳንድ  ነገሮች  ገና  አገልግሎቱን  ሳይጀምርም  እንደተፈጸመ  ሆነው ተጠቅሰዋል።  የደራሲው  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ያለው  ግንኙነት  እነዚህን ጥቅሶች ለመውሰድ ብቻ ይመስላል። የመጽሐፍ ቅዱስ ዋና መልእክት ሰው ንጹሕ ሆኖ ተፈጥሮ ሳለ ኃጢአተኛ መሆኑና  እግዚአብሔር  ይህን  የወደቀ  ሰው  ለማዳን  በብሉይና  በአዲስ ኪዳን ያደረገው  ነገር  ነው።  ይህ ደግሞ በጣም  ግልጽ  ተደርጎ  ተጽፎአል። በብሉይ  ዘመን  ከሲና  ኪዳን  በፊት  በልቡና  ሕግ፥  ከሕገ  ልቡና  ዘመን በኋላ ደግሞ  ሕግ  ተሰጥቶ  ሰዎች  የመዳንን መንገድ  የሚሄዱበት  ያን  ሕግ በመፈጸም ሆነ። ሕጉም ራሱ ሊመጣ ያለው ነገር ምሳሌና ጥላ ነው እንጂ በዘላቂነት  ተጠብቆ  የሚዳንበት  አልነበረም።  ያ  ሁሉ  መስዋዕት  ጥላ  ሆኖ የሚያመለክተው  አካል  ነበረ፤  ያም  በመስቀል  ላይ  የሞተው  የክርስቶስ መስዋዕትነት  ነው።  ወንጌል  በአንድ  ጥቅስ  ቢጠቀስ  በዮሐ.  3፥16  የተጻፈው፥  በእርሱ  የሚያምን  ሁሉ  የዘላለም  ሕይወት  እንዲኖረው  እንጂ እንዳይጠፋ  እግዚአብሔር  አንድያ  ልጁን  እስኪሰጥ  ድረስ  ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና የሚል ነው።  የተአምረ  ማርያም  ደራሲ  የሸፈነው  ትልቅ  እውነት  ይህ  አንጡራው ወንጌል  ነው።  ተአምረ  ማርያም  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  እንደተጻፈው የሰውን  ልጆች  ለማዳን  እግዚአብሔር  ያደረገውን  እውነት  የጋረደ መጽሐፍ  ነው።  በዮሐ.  14፥6  ጌታ፥  እኔ  መንገድና  እውነት  ሕይወትም ነኝ፤  በእኔ  በቀር  ወደ  አብ  የሚመጣ  የለም  ያለውን  የተጻረረ  መጽሐፍ ነው።  በሮሜ  10፥13፥  የጌታን  ስም  የሚጠራ  ሁሉ  ይድናልና  የሚለው የምሥራች  በሌላ  ጫና  ተተካ።  መንገዱ  ኢየሱስ  ሳይሆን  ማርያም፥ መጠራት  ያለበት የጌታ  ሳይሆን የማርያም ስም  ተደረገና  ተለወጠ።  ለዚህ ነው  ይህ  ደራሲ  ደኅንነት  የሚገኝበትን  መንገድ  ያልተገነዘበ፥  መጽሐፍ ቅዱስን  የማያውቅ  ሰው  ነው  ያልሁት።  ካወቀ  ደግሞ  ሳያውቅ  የዘላበደ ሳይሆን አውቆ ያሳተ አሳች ነውና የባሰ አጥፊ ነው።  ይህ  መጽሐፍ  የተጻፈበት  ዘመን  ምእመናን  መጽሐፍ  ቅዱስን  እንደልብ የማያገኙበትና  የማያስተያዩበት  ዘመን  ነውና  የተነገረውን  ሁሉ  እንደ እውነት  ለመቀበል  ሃይማኖታዊና  ስነ  ልቡናዊ  ጫና  የሚደረግባቸው ስለሆነ  እውን  ከመጽሐፍ  ቅዱስ  ጋር  ይጋጫል  ወይስ  አይጋጭም የሚለውን  የሚጠይቅ  አይኖርም።  የተማሩት  የሚባሉት  አለማሳወቃቸው ግን  የአዋቂ  አጥፊ  ያደርጋቸዋል።  ባለፉት  300  ዓመታት  ተራው  ሕዝብ ሊገባው  በሚችለው  ቋንቋ  መጽሐፍ  ቅዱስን  እንዲያገኝ  በመርዳትና  በማስተርጎም ፈንታ  ሌሎች  ጥረው  የተረጎሙት እንኳ  እንዳይደርስ  ታላቅ ተጋድሎ  ታደርግ  የነበረችው  ቤተ  ክህነት  መሆኗም  አስተዛዛቢ  ጉዳይ ነው።  ይህ  ራሱን  የቻለ  ሌላ  ጉዳይ  ቢሆንም  እዚህ  ያነሣሁት  ከሕዝብ መጽሐፍ  ቅዱስን  አለማወቅና  የተጻፈውን  ሳያስተያዩ  ከመቀበል  ጋር መነሣት  ስለተገባው  ነው።  እስከ  ቅርብ  ዓመታት  ድረስ  በኢኦተቤክ ስብከትና  ትምህርት  ለተራው  ምእመናን  በሚገባቸው  ቋንቋ  አይሰበክም ነበር።  ያኔ  ይህ  መጽሐፍ  በተጻፈበት  ዘመንማ  ሰው  በተስኪያን  ገብቶ ግድግዳ  ላይ  የተሳሉ  ስዕሎችን  ‘አንብቦ’  ነበር  የሚመለሰው  እንጂ  ሮሜ 10፥17  እንግዲያስ  እምነት  ከመስማት  ነው  መስማትም  በእግዚአብሔር ቃል  ነው  የሚለውን  አምኖ  እንዲድን  ሊሰማ  አልተደረገም።  የምእመናኑ አለማወቅ  ብቻ  ሳይሆን  ያውቃሉ  ተብለው  ሊያሳውቁ  የሚጠበቁትም ከቃሉ  ጋር  ጀርባና  ጀርባ  የሆነ  እንደዚህ  ያለ  መጽሐፍ  ሲያቀርቡ  አሳዛኝ ታሪክ  ነው።  ምን  ይደረግ!  ቃሉን  አያውቁትም።  ቢያውቁት  ኖሮ አይቃረኑትም ነበር።

3.  ይህ  ደራሲ  ክርስቲያንና  የክርስቶስ  ምስክር  ያልሆነ  ሰው  ነው።

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ክርስቲያናዊ  ባህርያት፥  ቃሉን  ማንበብ፥ እግዚአብሔርን  በመንፈስና  በእውነት  ማምለክ፥  ወንጌልን  ላልዳኑት ማሳወቅ፥  ክርስቶስን  መምሰል፥  የደቀ  መዝሙርነት  ኑሮ፥  የመንፈስ  ፍሬ፥ ጠላትን  መውደድ፥  የቅዱሳን  በቅድስና  መኖርና  በእምነት  መጽናት፥ ወዘተ፥  አይታዩበትም።  ይልቁን  በቀል  ይታይበታል።  የማያምኑትን መበቀል፥  በወንጌል  እውነት ተመርተው ሊኖሩ የሚወድዱትንም  መበቀል ይታዩበታል።  ክርስቲያን  ክርስቲያን  የተባለው  የክርስቶስ  ስለሆነ  ነው። አዳኙ፥  መሪው፥  ጌታው  ክርስቶስ  ነው።  በዚህ  መጽሐፍ  ግን  ማርያም አዳኝ፥  ኮናኝ፥  አጽዳቂ፥  ወደ  ሲዖል  አውራጅ፥  ወደ  መንግሥተ  ሰማያት አስገቢ፥  እየተገለጠች  መመሪያ  የምትሰጥ  ናት።  ይህ  እርሷን  ያለምንም ጥያቄ የሚከተል ሰው ክርስቲያን ነው መባል ያለበት ወይስ  ‘ማርያን’? ክርስቶስን  የሚያውቅ  ክርስቲያን  ያለ  ልክ  ከፍ  ያለውን  ጌታ  ስላወቀ በፊል. 2፥11  መላስም  ሁሉ  ለእግዚአብሔር  አብ  ክብር  ኢየሱስ  ክርስቶስ ጌታ እንደ ሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው እንደተባለ እርሱን የሚመሰክር ነው። ደግሞም  ጌታ  ከማረጉ  በፊት  በመጨረሻ  የተናገረው  ቃል፥  ምስክሮቼ ትሆናላችሁ  የሚል  ነው፤  ሐዋ. 1፥8።  ክርስቲያን  የክርስቶስ  ምስክር  ነው እንጂ  የሌላ  የማንም  ምስክር  አይደለም፤  ሊሆንም  የተገባ  አይደለም። እንዲህ  ያለ  መጽሐፍን  የጻፉና  ያስጻፉ፥  ከተጻፈ  በኋላም  የሚያሳትሙና የሚያሰራጩ  ክፉኛ  የሳቱት  ክርስቲያን  የማን  ምስክር  የመሆኑን  እውነት ባለመረዳት  ነው።  ይህ  ብቻ  ሳይሆን  የክርስቶስ  ሳይሆን  የሌላ  ምስክር መሆን  የሐሰት  ምስክር  ሆኖ  መገኘት  መሆኑን  ባለመረዳት  ወይም  አውቆ ከሐሰት ጋር ለመቆም ነው።  ምስክር  ያየውንና  የሰማውን  የሚናገር  እንጂ  ያዩና  የሰሙት  የጻፉትን የተነገረውን  እውነት  የሚሸፍን  አይደለም።  በዚህ  መጽሐፍ  ውስጥ  ግን ጌታ  ክርስቶስ  ተለጣፊ  ሆኖ ነው  የሚታየው። ጌታ ከራሱ  ጋር  ሌላ  ደባል የሚያቆምና  የሚጋራ  አምላክና  አዳኝ  አይደለም።  በነዚህ  ጥቂት  ጥቅሶች ውስጥ  “ብቻውን”  የሚሉትን  ቃላት  እናጢን፤  ብቻውን  አምላክ  ለሚሆን ለማይጠፋው  ለማይታየውም  ለዘመናት  ንጉሥ  ምስጋናና  ክብር  እስከ ዘላለም ድረስ ይሁን፤ አሜን። 1ጢሞ. 1፥17። ያንም መገለጡን በራሱ ጊዜ ብፁዕና  ብቻውን  የሆነ  ገዥ፥  የነገሥታት  ንጉሥና  የጌቶች  ጌታ፥  ያሳያል። 1ጢሞ. 6፥15።   ከብዙ  ጊዜ  በፊት  ለዚህ ፍርድ የተጻፉ  አንዳንዶች  ሰዎች ሾልከው  ገብተዋልና፤  ኃጢአተኞች  ሆነው  የአምላካችንን  ጸጋ  በሴሰኝነት ይለውጣሉ ንጉሣችንንና ጌታችንንም ብቻውን ያለውን ኢየሱስ ክርስቶስን ይክዳሉ።  .  .  .  ብቻውን  ለሆነ  አምላክና  መድኃኒታችን  ከዘመን  ሁሉ በፊት  አሁንም  እስከ  ዘላለምም  ድረስ  በጌታችን  በኢየሱስ  ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤  አሜን።  ይሁ. 1፥4፥25።  ይህ ብቻውን  የሚል  ቃል  (movnoß)  የሚጋራው፥  የሚዳበለው፥  አብሮት የሆነ  የሌለ  መሆኑን  ገላጭ  ቃል  ነው።  ለደኅንነት  ኢየሱስን  ከማርያምም ሆነ ከሌላ ከማንም ማዳበል ፍትሕ ሳይሆን ክህደት ነው።

ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,

Wednesday, June 11, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን በፓትርያርኩ ላይ የመጨረሻ የስም ማጥፋት መርዙን መርጨት ጀመረ!!

ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ስንል እንደቆየነው ከማኅበረ ቅዱሳን ስውር መሰሪ ተግባር ውስጥ አንዱ ጉዳይ የሊቃነ ጳጳሳቱን የሕይወት ታሪክ ባለው የገንዘብና የስለላ አቅም አስቀድሞ በመሰብሰብ ለችግር ቀን ሊጠቀምበት ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ የማስቀመጥ ጥበቡ ነው። ሊቃነ ጳጳሳቱ ማኅበሩ ለሚፈልገው አገልግሎት የጎበጠ ጀርባ ለማቅረብ ፈቃደኝነት ሲጎድላቸው ወይም ሲያገለግሉት ቆይተው የጎበጠ ጀርባቸውን ቀና በማድረግ የነጻነት አየር ለመተንፈስ ሲፈልጉ ያንን ከመሳቢያው ውስጥ ቆልፎ ያስቀመጠውንና ስም ለማጥፋት ይጠቅመኛል ብሎ ያሰበበትን የቆሸሸ ሥራ እንደአዲስ ግኝት ብቅ በማድረግ በሕዝብ ዘንድ እንዲጠሉ የክፋት መርዙን በልዩ ልዩ አቅጣጫ መርጨት ይጨምራል።
እነሆ « የለውጥ አባት፤ ሙስናን ለመዋጋት ቃል የገቡ ፓትርያርክ» በማለት በማሞካሸት ጉሮሮው እስኪነቃ ውዳሴ ከንቱ ማብዛቱ ሳያንስ  በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለማስረግ ሞክሮ ያልተሳካለትን «የሕግና የለውጥ አተገባበር መመሪያ» በማለት ያንቆለጳጰሰውን የቅጥፈት ስርዋጹን ሰነድ፤ ፓትርያርኩ «በመላ ሀገሪቱ ሊተገበር የሚገባው» በማለት አድናቆት እንደቸሩት ሲደሰኩር እንዳልነበር ሁሉ ፓትርያርኩ የማኅበሩን አካሄድ አይተው ፊታቸውን ሲያዞሩበት  በመረቀበት አፉ እርግማኑን ለማውረድ የተፋው ምራቅ ገና አልደረቀም ነበር።
የማኅበሩ የክፋት ጥግ ርኅራኄ የለሽ መሆኑን የሚያሳየን ሲያገለግሉት የቆዩት ሰለቸን ማለት ከጀመሩ ወይም ፊት ሰጥተው ሲያሳስቁት የነበሩት አባቶች ቅጭም ያለ ገጽታ ወደማሳየት ከተሸጋገሩ ስማቸውን በማጥፋት የነበራቸውን ስም ከአፈር በመደባለቅ እንዳይነሱ አድርጎ የመምታት ልኬታው ከባድ ነው።
ሰሞኑን በፓትርያርክ ማትያስ ላይ በግል ጋዜጦች፤ በአፍቃሬ እንዲሁም ስውር ብሎጎቹና በመንግስት ተቃዋሚ ድረ ገጾች ሳይቀር እየተቀባበሉ «ፓትርያርኩ የደርግ አገልጋይ ናቸው» ወደሚል የጋራ የስም ማጥፋት ዘመቻ ወርደዋል። «አንድ ሰሞን ማመስገን፤ አንድ ሰሞን መራገም» የማኅበረ ቅዱሳን «ሲመች በእጅህ፤  በማንኪያ ሲፈጅህ» መፈክር መገለጫ መሆኑ ነው።
አይሆንም እንጂ ቢሆንለት ፓትርያርኩ ነገ አዲስ ሀሳብ ይዘው ብቅ ቢሉና »ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያናችን የዓይን ብሌን ነው» የሚል መግለጫ ቢሰጡ  «12 ክንፍ ያላቸው ቅዱስ ፓትርያርኩ የክፍለ ዘመኑን አዲስ መግለጫ ሰጡ» በማለት እንደ ደብረ ብርሃኑ መብረቅ በብርሃን ወረደልን የፈጠራ ዜና ይለውጠውና ለፓትርያርኩ ገድል ይጽፍላቸው ነበር።
ይሁን እንጂ ይህ እንዳይሆን ለማኅበረ ቅዱሳን ህልም በመሰለ የእውነታ ውጥረት በፓትርያርኩ ስለተያዘ እርግማኑንና ስም ማጥፋቱን ስራዬ ብሎ ገፍቶበታል። ነገሩ ሲታይ «የማያድግ ጥጃ እንትን ይበዛበታል» እንዲሉ የስም ማጥፋት ዘመቻው የእስትንፋሱ የመጨረሻ ምዕራፍ እንደሆነ አመላካች ይመስለናል።
ፓትርያርክ ማትያስ«የደርግ ተላላኪ ነበሩ፤ አሁን ደግሞ የኢህአዴግ ተላላኪ ሆነው ተገልብጠዋል» በማለት ማጣጣሉ የሚያሳየን ነገር  የማኅበረ ቅዱሳን ተላላኪ ለመሆን በጭራሽ ፈቃደኝነት ቀርቶ ሃሳብ እንደሌላቸው ስላየ እንጂ ማኅበሩን እያሞጋገሱና ከወንበራቸውም ትንሽ ከፍለው ቢሰጡት ኖሮ ይህንን ወደመሰለ የብስጭት ማሳያ ነቀፋ ባልወረደም ነበር። እውነትን ለሕዝብ ለመግለጽ ፈልጎ ቢሆንማ ኖሮ አባ ገብርኤልን የመሰሉ የማኅበሩ ደጋፊ ጳጳስ በአንድ ወቅት አቶ ኢያሱ የመባላቸውን ዜና፤ አቡነ ጳውሎስን አውግዘው ወደአሜሪካ መፈርጠጣቸውን፤ እዚያም ሄደው የኢህአዴግ የተቃውሞ ሰልፍ አስተባባሪ ሆነው በአደባባይ መጮሃቸውንና 360 ዲግሪ ተሽከርክረው ወደጠሉት ሀገር መመለሳቸውን ዜና አድርጎ ለምን አይሰራም ነበር? ይህንንማ እንዳያደርግ አባ ገብርኤል የማኅበሩ ቀኝ እጅ ሆነው ስለሚያገለግሉ  ብቻ ነው።  ነገ ተነስተው «በዚህ ማኅበር ታምሰን የምንሞተው፤ እስከመቼ ነው?» የሚል ጥያቄ አቡኑ ቢያነሱ የታወቀና ያልታወቀ ኃጢአታቸውን እንደሸረሪት ድር ይዘከዝክላቸው ነበር።
በዘንድሮውም የሲኖዶስ ጉባዔ ላይ እንዳገኘው መረጃ ከሆነ የማኅበሩ ደጋፊ መሆናቸው በደንብ የሚታሙት ጳጳሳት ሳይቀሩ የድጋፍ ቀንዳቸውን አቁመው ሊከራከሩለት አለመድፈራቸው አንድም የማኅበሩ የእድሜ ዘመን ማጠሩን ከመገመት አንጻር አለያም በማኅበሩ ጥፋት የተነሳ ከኑግ እንደተገኘች ሰሊጥ እንዳይወቀጡ ከመስጋት የተነሳ ይመስለናል። ጥቅም ዓይናቸውን ካሳወራቸው መካከል ጥቂቶች ለመንጫጫት ከመሞከራቸው በስተቀር ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው ማኅበሩ አጀንዳ አስረቅቆ፤ ሲያስጸድቅ የነበረውን ጉልበት ዘንድሮ ሳያገኝ መክኖ ቀርቷል። አቡነ ጳውሎስን ተባብረው በአድማ ሲያዳክሙና ለራስ ምታት ሲዳርጓቸው የነበረው የሴራ አቅም በፓትርያርክ ማትያስ ተቀልብሶ በተገላቢጦች የማኅበሩና የደጋፊዎቹ ራስ ምታት ሆኖ የጫወታው ሜዳ ተጠናቋል።
ከዚህ በፊት ስንል እንደቆየነው አሁንም ደግመን የምንለው «የማኅበረ ቅዱሳን አባል መሆን መብት ሲሆን ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ወደማኅበር አባልነት ወይም ደጋፊነት ከወረደ ያለበትን መንፈሳዊ ሥልጣን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስረክቦ በተራ አባልነቱ እንዲቀጥል የማስድረጉ ነገር መዘንጋት የለበትም» እንላለን። ሊቀ ጳጳስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ መንፈሳዊ ሥልጣን ላይ ተቀምጦ ከመንጋው ውስጥ በተለየ መልኩ የሚወደው ወይም የሚንከባከበው ወይም በጥብቅና የሚከራከርለት የተወሰነ የቤት ልጅ እና የእንጀራ ልጅ የሚባል ሊኖረው አይችልም። በሀዋሳ ታይቶ የነበረው ሁከት መነሻው በአባ ገብርኤል በኩል ማኅበረ ቅዱሳንን የቤት ልጅ አድርጎ የማየትና ማኅበሩን የሚቃወሙትን ደግሞ የእንጀራ ልጅ አድርጎ በማቅረብ መንጋውን በእኩል ለማገልገል ያለመቻል የጳጳሳት አባል የመሆን ልክፍት የተነሳ ነው። ይህ ችግር በቦረና፤ በሐረር፤  በመንፈሳዊ ኮሌጆችና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ውስጥ ሳይቀር በተግባር ታይቷል። ማኅበሩ «ከኛ ጋር ያልቆመ ጠላታችን ነው» በሚል ፈሊጥ በአባልነት የያዛቸውን ጳጳሳት እንደዱላ በክርስቶስ መንጋ ላይ እየወረወረ ይጠቀምባቸዋል።
ስለዚህ ፓትርያርክ ማትያስ በስም አጥፊው ማኅበርና ለማኅበሩ በተለየ አድረው መንጋውን በእኩል ዓይን ማየት በተሳናቸው ላይ ፍትሃዊና የተጨበጠ እርምጃ ለመውሰድ ማቅማማት እንደሌለባቸው ለማስገንዘብ እንወዳለን።
የስም ማጥፋት ዘመቻው የማኅበሩን ማንነት ገላጭ ሲሆን በንስሐ ተመልሶ ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው ልክ ከመንቀሳቀስ ይልቅ ክፋቱን ለመተው ያለመፈለጉ ማሳያ መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።

Sunday, June 8, 2014

«የዓላማ ሰው ከመሆን የሚከለክል ማንነትና መፍትሄው»

[«ከዓላማ መር መጽሐፍ» ለንባብ እንዲመች ተደርጎ የተወሰደ]

ማንኛውም ሰው ሕይወት በአንድ ነገር ግፊት ይመራል። ብዙ መዝገበ ቃላት «አንቀሳቀሰ» ለሚለው ግሥ፦ መራ፤ ተቆጣጠረ ወይም አቅጣጫን ወሰነ» የሚል ፍቺ ይሰጡታል። መኪናም ነዳህ፤ ሚስማር በመዶሻ መታህ ወይም ኳስ አንከባለልህ፤ በዚያን ወቅት ያንን ነገር እየመራህ፤ እየተቆጣጠርክና አቅጣጫውን እየወሰንክ ነው። ታዲያ ልክ እንዲሁ ሕይወትህን የሚመራው ኃይል ምንድነው?
   በአሁኑ ጊዜ በአንድ በሆነ ችግር በሆነ ጫና፤ ወይም ማለቅ ያለበትን ሥራ ለመጨረስ በጥድፊያ በመራመድና በመንቀሳቀስ ላይ ትገኝ ይሆናል። በክፉ ትዝታ፤ በአስበርጋጊ ፍርሃት ወይም በቅጡ ባልገባህ አንድ ኅሊናዊ እምነት ትመራ ይሆናል። ሕይወትህን ሊያንቀሳቅሱና ሊመሩ የሚችሉ ብዙ ሁኔታዎች፤ የሕይወት ፋይዳዎችና ስሜቶች አሉ። ቀጥሎ የተዘረዘሩት አምስቱ /5/ በጣም የተለመዱና የታወቁ ናቸው።

1/ ብዙ ሰዎች በበደለኛነት ስሜት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ዘመናቸውን ሁሉ ጸጸትና ቁጭት ከወለደው ሃፍረታቸው ለመሸሸግ ሲሸሹ ይኖራሉ። ቁጭትና ጸጸት የሚመራቸው ሰዎች የትዝታ ተጠቂዎች ናቸው። ያለፈው ሕይወታቸው መጪውን ህይወታቸውን እንዲቆጣጠረው ይፈቅዱለታል። ብዙውን ጊዜ ሳያውቁት የሕይወት ስኬታቸውን እያበላሹ እራሳቸውን ይቀጣሉ። ቃየል ኃጢአትን በሠራ ጊዜ በደሉ ከእግዚአብሔር ህልውና ለየው፤ እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፦ «በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ» ዘፍ 4፤12። ይህ ቃል በዘመናችን ያለ ዓላማ በሕይወት ጎዳና የሚንከራተቱ ብዙ ሰዎችን ይገልጣል።
  ምንም እንኳን የዛሬ ኑሯችን የትናንት ውጤት ቢሆንም፤ የትናንት ኑሯችን ግን የዛሬ እስረኞች ሊያደርገን አይገባም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓላማ ባለፈው ሕይወትህ የሚወሰን አይደለም። እግዚአብሔር ሙሴ የተባለውን ሰው ገዳይ የነበረ ወደ ሕዝብ መሪነት፤ ጌዴዎን የተባለው ፈሪ ደግሞ ወደ ደፋር ጀግና ለውጧቸዋል። በአንተ ቀሪ ሕይወትም እንዲሁ አስደናቂ ነገሮችን ሊያደርግ ይችላል። እግዚአብሔር ለሰዎች አዲስ የሕይወት ጅማሬ በመስጠት የተካነ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል። «መተላለፉ የተከደነለት፤ ኃጢአቱም የተሸነፈችለት እንዴት ብሩክ ነው» መዝ 32፤1

2/ ብዙ ሰዎች በቂምና በቁጣ ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ደረሰብን የሚሉትን ጉዳት ከማስወገድ ይልቅ አቅፈውት ይኖራሉ። የጉዳታቸውን ስቃይ በይቅርታ ከማስወገድ ይልቅ በመደጋገም ያብሰለስሉታል። አንዳንዶቹ ደግሞ ዝም በማለት ንዴታቸውን ውስጣቸውን  «አምቀው» ይይዙታል። የቀሩት ደግሞ የታመቀ ቁጣቸውን «በማፈንዳት» በሌሎች ላይ ያምባርቃሉ። እነዚህ ሁሉ አጸፋዎች ጤናማ ያልሆኑ የማይጠቅሙ ናቸው።
  የአንተ ቂም መያዝ፤ ቂም በያዝክበት ሰው ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ይበልጥ የሚጎዳው አንተን ነው። የጎዳህ ወይም ያስቀየመህ ሰው ድርጊቱን ረስቶ የራሱን ኑሮ እየመራ ይሆናል፤ አንተ ግን ያለፈውን ቂም አምቀህ በመያዝ በብስጭት ትብሰለሰላለህ።
 ልብ በል! ከዚህ በፊት የጎዱህ ሰዎች አልጥል ባልከው የገዛ ቂምህ ካልሆነ በቀር እየጎዱህ ሊኖሩ አይችሉም። ያለፈው ነገርህ አልፏል። ማንም ሊቀይረው አይችልም። በመራርነትህ ራስህን ብቻ ነው የምትጎዳው። በቃ ለራስህ ስትል ካለፈው ተማርና ተወው። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ «ሞኙን ሰው ብስጭት ይገድለዋል፤ ቂሉንም ቅናት ያጠፋዋል» ኢዮብ 5፤2

3/ ብዙ ሰዎች በፍርሃት ይመራሉ።

   እንዲህ ላሉ ሰዎች የሥጋታቸው ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉት ነገሮች በሕይወታቸው ያሳለፉት አስፈሪ ጉዳት በእውነት ላይ ያልተመሠረተ ምኞትና ጉጉት፤ ቁጥጥር ባለበት ቤተሰብ ውስጥ ማደግ፤ ወይም በተፈጥሮ የመጣ ፍርሃት ያለባቸው ይሆኑ ይሆናል። ምክንያቱም ምንም ሆነ ምን በፍርሃት የሚኖሩ ሰዎች ድፍረት ከማጣታቸው የተነሳ ሁኔታዎችን ስለማይጋፈጡ ብዙ እድሎች ያመልጧቸዋል። ፍርሃትን በድፍረት ከማሸነፍ ይልቅ ችግር ካለበት ሁኔታ መሸሽንና ባሉበት ሁኔታ ውስጥ መቆየትን ይመርጣሉ።
ፍርሃት እግዚአብሔር ያቀደልህን እንዳትሆን የሚያደርግህና እራስህን ያስገባህበት እስር ቤት ነው። በፍቅርና በእምነት መሣሪያነት ልትጋፈጠው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «በፍቅር ፍርሃት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሃት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።

4/ ብዙ ሰዎች ለመበልጸግ ባላቸው ምኞት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉት ሰዎች የሕይወታቸው ዋና ግብ ሀብት ማግኘት ነው። እንዲህ ያለው ሁልጊዜ ሀብት የመፈለግ ግፊት የሚመነጨው ብዙ ሀብት ሲኖረኝ ይበልጥ ደስተኛ፤ ይበልጥ ታዋቂና ዋስትና ያለኝ እሆናለሁ ከሚል የተሳሳተ አመለካከት ነው። እነዚህ ሦስቱም አስተሳሰቦች ስህተት ናቸው። ሀብት ሊያስገኝ የሚችለው ጊዜያዊ ደስታን ነው። ምክንያቱም ቁሳዊ ነገሮች ስለማይለወጡ ያሰለቹናል። በመሆኑም አዳዲስ ትልልቅና የተሻሉ ነገሮችን እንደገና እንፈልጋለን።
   ብዙ ሀብት ካለኝ ይበልጥ የተከበርኩና ተፈላጊ ሰው እሆናለሁ የሚልና የማይጨበጥ እምነትም አለ። እኛ እራሳችንን የተመንበት ዋጋ ከትክክለኛ ዋጋችን ጋር ተመሳሳይ አይደሉም። ዋጋህ አንተ አሉኝ ከምትላቸው ውድ ነገሮች አይወሰንም። በሕይወት እጅግ ዋጋ ያላቸው ቁሳዊ ነገሮች እንዳልሆኑ እግዚአብሔርም ይነግረናል።
  ስለ ገንዘብ በጣም የተለመደው የማይጨበጥ እምነት ብዙ ገንዘብ ካለኝ በሁሉ ነገር ዋስትናዬ በጣም የተጠበቀ ይሆናል የሚለው ነው። አይሆንም! በተለያዩና ከአቅም በላይ በሆኑ ምክንያቶች ሀብት ወይም ገንዘብ በቅጽበት ይጠፋል። እውነተኛ ድነት ወይም ዋስትና የምታገኘው ፈጽሞ ማንም ሊወስድብህ ከማይቻለው ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ካለህ ግንኙነት ነው።

5/ ብዙ ሰዎች በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት በመፈለግ ማንነት ይመራሉ።

እንዲህ ያሉ ሰዎች ወላጆቻቸው ወይ ልጆቻቸው  ወይ ደግሞ አስተማሪዎቻቸው አለዚያም ሌሎች ወዳጆቻቸው ከእነርሱ የሚጠብቁትን ነገር ለማሟላት የሚያደርጉት ጥረት ሕይወታቸውን እንዲቆጣጠር ይፈቅዳሉ። አንዳንድ ሰዎች ከጎለመሱ በኋላም እንኳን ለማስደሰት አስቸጋሪ በሆኑ ወላጆቻቸው ተቀባይነትን ለማግኘት ይፈልጋሉ። ሌሎች ደግሞ ሰዎች ስለ እነርሱ የሚያስቡት ነገር እያስጨነቃቸው በእኩዮቻቸው ተጽእኖ ይመራሉ። የሚያሳዝነው  ግን ብዙዎችን ለማስደሰት የሚሞክሩ ሰዎች በሂደቱ ራሳቸውን ያጣሉ።
ለስኬት የሚያበቁ ቁልፍ ነገሮችን በሙሉ ባላውቅም ለውድቀት የሚያበቃው ዋነኛ፤ ነገር ግን ሁሉን ለማስደሰት መሞከር ነው። በሌሎች አስተሳሰብ መመራት እግዚአብሔር ለሕይወትህ ያለውን ዓላማ እንድትስት የሚያደርግህ መንገድ ነው። አላስፈላጊ ጭንቀት፤ እርካታ ያጣ ሕይወት ጥቅም ላይ ያላዋልከው ችሎታና ሌሎች ብዙ ነገሮች ሕይወትህን ሊያሸከረክሩት ይችላሉ። ሁሉም ግን የትም የማያደርሱ ናቸው።

ማጠቃለያ፤

ከላይ የተዘረዘሩትን አስወግደህ በዚህ ምድር ላይ የምትኖርበትን ዓላማ ያወቅህ ከሆንህ፤
1/ ኑሮህን እያጨናነቅህ አትመራውም።
2/ ትኩረት ማድረግ የሚገባህን ለይተህ ታውቃለህ።
3/ ለዓላማህ ትጋት ትቆማለህ።
4/ ለዘላለም ሕይወት ዋጋ ትሰጣለህ።
5/ የዚህ ዓለም መሪህ፤ አሳብህ ወይም የሌሎች ጫና ሳይሆን እግዚአብሔር ብቻ እንዲሆን ትፈቅዳለህ።


ስለሆነም በዚህ ምድር ላይ የምትኖረው ለምን እንደሆነ አስቀድመህ እወቅ! የምትኖረው እንደሰው በልተህና ጠጥተህ ቀንና ሌሊትን በማንነትህ ላይ እያፈራረቅህ ለመኖር አይደለም። ይህንንማ ሌሎች እንስሳትም ያደርጉታል። አንተ ግን በእግዚአብሔር ዓላማ የተፈጠርክ፤ ለእግዚአብሔር ዓላማ የተሰራህ ነህና በዚህ ዓላማ ላይ ቆመህ መገኘት አለብህ!

በዚህ ምድር ላይ የተፈጠረከው ለየትኛው ዓላማ እንደሆነ ታውቃለህ? እርምጃህን እየወሰንክ ያለኸውስ እንዴት ነው?

Wednesday, June 4, 2014

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ችግር፤ የአንድ ጤናማ ሰው የጤንነት መስተጓጎልን ይመስላል!


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚገጥሟት ፈተናዎች ሁሉ ከውስጧ እንደሚነሳው ፈተና የሚከፋ የለም። ቤተ ክርስቲያኒቱ የኢኮኖሚ አቅሟ እያደገና ውጫዊው ተግዳሮቶቿ እየገዘፉ በመጡ ቁጥር የውስጥ ፈተናዎቿ መቀነስ ሲገባቸው በተቃራኒው እንደአዲስ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ መከራዋ ገዝፎ መልህቅ መጣያ ወደብ እንዳጣች መርከብ በእስራ ምእቱ የአስተዳደር እክል የባህር ማእበል እየተናጠች ትገኛለች። ይህንን ውስጣዊ ፈተና በቅድሚያ አትኩሮ የሚመለከት ዓይን የሌለው ማንም ቢሆን ውጫዊ ተግዳሮቶቿን ለመመከት የሚያስችል አቅም በምንም ተአምር ሊኖረው አይችልም። ስለሆነም ውስጣዊ ፈተናዎቿን ለይቶ በማስቀመጥ ለመፍትሄውም መንገድ ማስቀመጥ ተገቢ ይሆናል። በዚሁ መሠረት ተለይተው መቀመጥ የሚገባቸውን አንኳር ችግሮች እንደታየን መጠን ለማስቀመጥ ወደድን።

ዋና ዋና ችግሮቿ፤

1/ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ፤

2/ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ፤


3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤


በዋናነት የሚቀመጡ ናቸው ብለን እንገምታለን። ይህ ማለት አጠቃላይ ችግሮች እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት ሳይሆን ዘርፈ ብዙ ችግሮቿ መነሻ የሚያደርጉት እነዚህ ሦስት ዐበይት የአንድ ሰው የሕይወት እስትንፋስን የማግኘት ያህል ህልውና ያላቸው ነጥቦች ናቸው የሚል እምነት አለን።
አንድ ሰው ሕልውና አለው የሚያሰኘው ነፍስና ሥጋው ሲዋሃድ ነው። ሥጋውም ሕይወት አለው የሚባለው አእምሮው፤ አጥንትና ጅማት ከውስጥ ሕዋሱ ጋር ተገቢ ሥራውን ማከናወን ሲችል መሆኑ ይታወቃል። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሕይወት እንዳለው ሰው ለመቁጠር የሚያስችለን የቁመና መለኪያችን ዋና ዋና ችግሮች ከላይ በሦስት ልየታ ያስቀመጥናቸው ነጥቦች ናቸው። እንዴት? የሚለውን ቀጥለን እንመልከት።

1/ «ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የሚችል በመንፈስ፤ በእውቀት፤ በልምድና በችሎታ የዳበረ ላዕላይ መዋቅር አለመኖሩ» የሚለው የጉድለት ነጥብ የአንድን ሰው የአእምሮ አስተሳሰብ ይወክላል። ሰውን ከሌላው እንስሳ የሚለየው ይህ አእምሮና ከአእምሮው የተያያዘው የጀርባው አጥንት በሚያስተላልፉት ኅብለ ሰረሰራዊ መዋቅር የተነሳ ነው። አእምሮ ካልሰራ ሰው ሊያሰኝ የሚችለውን የማንነት መገለጫዎችን ለመሥራት አይችልም። ስለዚህ በዚህ ደረጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአእምሮ ማዕርግ የተቀመጠው «ቅዱስ ሲኖዶስ» የሚባለው ክፍል ነው። ይህ ላዕላይ መዋቅር ህልውና እንዳለውና ምሉዕ ሰው ሊሰራ እንደሚገባው እንደባለ አእምሮ መስራት ካልቻለ ሌላው የሰውነት ክፍል በተገቢው መንገድ ሊሰራ አይችልም። ይህ የአንድ ጤናማ ሰው ዋና ማዕከል የሆነው አእምሮ በዚህ ሰዓት በተገቢው መንገድ እየሰራ አይደለም። ስለዚህ አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን እክል ገጥሟታል ማለት ነው። እክሎቹ በምን በምን ይገለጻሉ? የሚለውን ጥያቄ በሌላ ጽሁፍ እንመለስበታለን። በጥቅሉ ግን እዚህ ላይ ማስገንዘብ የምንፈልገው ነገር አንድ ጤናማ ሰው እንዳለው አእምሮ መስራት ያለመቻል ችግሮች ነጸብራቅ የሚመሰለው «ቅዱስ ሲኖዶስ» ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደተሻለ ደረጃ ለማሳደግ አለመቻሉና የመንፈሳዊነት ብቃት፤ የእውቀት፤ የልምድና የችሎታ ጉድለት ስለሚታይበት የቤተ ክርስቲያኒቱ አእምሮ ችግር ላይ መሆኑን እንረዳለን ማለት ነው። አእምሮ ካልሰራ፤ ሰው ጤናማ ሊሆን አይችልም። ይህ አእምሮና የኅብለ ሰረሰር መዋቅሩ የሚታከመው እንዴት ነው? ጤናማ ካልሆነ ቤተ ክርስቲያን ታማለች ማለት ነው።

2/  «የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፤ ደንብና መመሪያ ጤናማ ሥራ የሚያሠራ ካለመሆኑም በላይ እንደአስፈላጊነቱ አለመሻሻሉ» የሚለው ነጥብ ምሳሌነቱን ወስደን ለአንድ እንደ ባለአእምሮ ጤናማ ሰው ግዘፈ አካል ብንወስድና ብንተረጉመው የሰውየውን ሥጋ የውስጥ አካሎቹን ያሳየናል። ሕግ፤ ደንብ፤ መመሪያና ሌሎች የማስፈጸሚያ ስልቶች ማለት «ልብ፤ ኩላሊት፤ ጉበት ወዘተ» ውስጣዊ የዝውውር ሕዋሳትን ይወክላል። ጤናማ አእምሮ የሌለው ሰው ካለበት ችግር በተጨማሪ ከእነዚህ ውስጣዊ አካላቱ ውስጥ በአንዱ ላይ ሌላ እክል ካለበት የሕመሙን መጠን የከፋ ያደርገዋል። ስለዚህ ሲኖዶሱ እንደባለ አእምሮ ፤ አእምሮውን ማሠራት አለመቻሉ እንዳለ ሆኖ በላይ የሰው ልጅ የሕልውና ክፍሎቹ እንደሆኑት የውስጥ አካላቱ ተጨማሪ እክል ዓይነት የሕግ፤ የደንብ፤ የመመሪያ ወይም የማስፈጸሚያ ስልቶች ዓይነትና መጠን ተገቢ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚያስችል ካልሆነ በሽታው አደገኛ ሁኔታ ውስጥ መሆኑን ለመረዳት አይከብድም። ከአእምሮው ላይ በተጨማሪ ከውስጥ ክፍሎቹ ባንዱ ላይ ችግር የገጠመውን አንድ ሰው እስኪ በዓይነ ልቡናዎ ይሳሉና ይመልከቱ! እጅግ አሳዛኝና አስጊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝ ለመረዳት የሚከብድዎ አይመስለንም። ቤተ ክርስቲያን አእምሮውን በታመመ አመራር ስር መሆኗ ሳያንስ ስራዋን በተገቢውን መንገድ የሚያስኬድላት የውስጥ አካላቷን መጠበቂያ ማዕቀፍ አለመኖሩ የችግሯን ውስብስብነት የሚያሳይ ይሆናል።

3/ በልምድ፤ በባህልና በትውፊት እንጂ በወንጌል እውነት የታነጸና ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ተከታይ ትውልድ መቅረጽ አለመቻሉ፤ የሚለውን ደግሞ የአንድ ምሉዕ ሰው ወሳኝ የክፍል እንቅስቃሴ ምሳሌያዊ መገለጫ አድርገን ብንወስደው  ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳን ይወክልልናል። ሰውየው ግዘፍ እንዲነሳ የሚያደርጉት፤ እንቅስቃሴውን የሚወስኑትና የዑደት ዝውውሩን የሚያገናኙት እነዚህ ዋና የሰውነት ክፍሎቹ ናቸው። ቤተ ክርስቲያን ስንል የክርስቶስ ጉባዔ ምዕመናን ማለታችን እንደመሆኑ መጠን ለቤተ ክርስቲያን ኅልውና ደም፤ አጥንት፤ ጅማትና ቆዳ ሆኖ ያስተሳሰረው ይህ የመዘወሪያ አካል ንጹህ፤ ያልተበከለ፤ ያልተጣመመና ጤናማ የህንጻ ክፍል ካልሆነ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ጤናማ ልትሆን በጭራሽ አትችልም። በነዚህ መሠረቶች ላይ የቆመው አካላዊ ህልውና የዝውውር ዑደቱ ከፈጣሪው በተቸረውና እፍ በተባለበት የሕይወት እስትንፋሱ በኩል አምላኩን በተገቢው ሊያመሰግን አለመቻሉ ጉባዔው የሚታወክ፤ የሚታመስ፤ በወሬ በሽታ የተጠመደ ይሆናል። በእድሜው መኖር በመቻሉና ነፍስያው አለመለየቷ ብቻውን አንድን ሰው ሕያው ሰው አያሰኘውም። በመንፈሱ የሞተ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ የለውም።
«በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና» ሮሜ 8፤14
በዚህም የተነሳ ጉባዔ አክሌሲያ እንደሆነ የሚታሰበው ትውልድ በልምድ፤ በባህል፤ በትውፊት ገመድ ተጠፍንጎ ከወንጌል እውነት ሳይታረቅና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በልቡናው ሰሌዳ ላይ ሳይጽፍ ነገር ግን አንገቱ ላይ የመስቀልና ምስል አንጠልጥሎ የሚሳደብ፤ የሚዋሽ፤ የሚሰክር፤ የሚያጨስ፤የሚያመነዝር፤ የሚሰርቅ፤ እምነት የማይጣልበት የባህል እምነት ተከታይ ሆኖ የሚታየው የእውነትን ወንጌል በመጋት አሳድጎ የቃሉን አጥንት መጋጥ ወደሚያስችል ሰውነት ማድረስ ስላልተቻለ ነው። በእምነት ሳይሆን በሃይማኖት የኖረውም በልምድ እንጂ እውነት ስለገባው አይደለም።  «እውነት ባለበት በዚያ አርነት አለ» የተባለው አንገት ላይ መስቀል አንጠልጥሎ ነገር ግን ነጻ እንዳልወጣ ሰው የሥጋ ሥራ የሚሰራ ሰው ማለት አይደለም። ስለዚህ ትውልዱ በወንጌል ነጻ የመሆን የእውነት ቃል ተኮትኩቶና በቀደምት አባቶቹ አስተምህሮ ታንጾ ባለመኖሩ አርነት ያልወጣ ሰው የሚያደርገውን የሥጋ ሥራ እየፈጸመ  በስም ክርስቲያን እየተሰኘ የባህልና የልምድ ተከታይ ሆኖ እንዲኖር ተፈርዶበታል።  ከልምድና ከባህል መንፈስ ነጻ መውጣት አለበት።
2ኛ ቆሮንቶስ 3፥17  «ጌታ ግን መንፈስ ነው፤ የጌታም መንፈስ ባለበት በዚያ አርነት አለ»

ማጠቃለያ፤

አንድ ሰው ጤናማ የሚባለው አእምሮው፤ ኅብለ ሰረሰሩ፤ የውስጥ አካላቶቹ፤ ደም፤ ስጋ፤ አጥንትና ጅማቱ ተዋሕደው በጤንነት ሲገኙ ነው። ምሉዕ ሰው ሆኖ ሕይወት ያለው መንፈሳዊ ጤንነቱ የሚጠበቀው ደግሞ የነፍስያው ራስ የሆነው ፈጣሪውን ሲያውቅና በተገቢው መንገድ ሲያመልክ ብቻ ነው። ከእነዚህ ባንዱ ጉድለት ቢገኝ አደጋ ውስጥ መሆኑ እርግጥ ነው። ከዚህ ተነስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንን የሕይወት ኅልውና ስንመለከት ጤናማ ሁኔታ ውስጥ እንዳይደለች ከላይ ያነሳናቸው ነጥቦች ያስረዱናል። የተከታዮቿ ቁጥር ወደታች የማሽቆልቆሉ ምክንያት የበሽታውን ደረጃ ያሳየናል። የአስተዳደር ሰላም አለመኖር፤ የነበራት ክብርና ተደማጭነት ማነሱም የገጠማት የህመም ደረጃ አደገኛ መሆኑን ያስረዳናል። የመከፈፋሏ መነሻ፤ የመከባበር ድቀት፤ የነውር ገመና ማደግ፤ ዋልጌነት፤ የብክነትና የዝርፊያው የትየሌለነት የበሽታዋ ደረጃ ምን ያህል እንደገዘፈ ለማወቅ ምርምር አይጠይቀንም። ቤተ ክርስቲያኒቱ ያልጠፋችውም ከእግዚአብሔር ታጋሽነትና ለንስሐ የሚሆን እድሜ ከመስጠት አምላካዊ ባሕርይው የተነሳ ይመስለናል። እንደሚገባን ሆነን መልካም ፍሬ ካላፈራን ግን መቆረጣችን አይቀርም።
የፈለገውን ያህል ተኩራርተን የቀደመችቱ መንገድ እያልን ብንደሰኩር ከእግዚአብሔር አስቀድሞ የተቀበልነውንና የሰማውን ዛሬ ይዘን በተግባር ካልተገኘን ከያዝነው የቁልቁለት መንገድ አያድነንም።  በአንድ ወቅት በትንሹ እስያ ለነበረችውና በተመሳሳይ የቁልቁሊት መንገድ ላይ ለነበረችው ለሰርዴስ ቤተ ክርስቲያን በዮሐንስ በኩል መልእክት ደርሷት ነበር።  ነገር ግን መስማት ስላልቻለች እየወረደች ካለበት የቁልቁሊት መንገድ ወጥታ፤ ስህተቶቿን አርማ፤ በእውነት የጌታዋ መንገድ ላይ ለመጓዝ የሚያስችላትን የንስሐ እድሜ ባለመጠቀሟ ከ500 ዓመት በኋላ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመጥፋት በቅታለች። በፍርስራሾቿ ላይም የእስልምና አዛን የሚያስተጋባባት የታሪክ ቤተ ክርስቲያን ሆናለች። ከመሆኗ በፊት የተነገራት ቃል ይህ ነበር።
«እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም» ዮሐ 3፤3
( በቀጣይ ጽሁፋችን  ዝርዝር ነገሮችን ለማየት እንሞክራለን)