Friday, May 31, 2013

የግብጽ ኮፕቲክ ፓትርያርክ ታዋድሮስ 2ኛ በዓባይ ግድብ ጉዳይ ላይ ቤተክርስቲያናቸው የሽምግልና ሚና እንድትጫወት በመሐመድ ሞርሲ አልተጠየኩም አሉ»

 የኮፕቲክ ቤተክርስቲያን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር የነበራትን የብዙ ዘመናት የበላይነትና የጠነከረ ቅርርብ መሠረት አድርገው በፖፕ ታዋድሮስ 2ኛ በኩል የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ላይ ግፊት ለማድረግና የግጭት መነሻ እንዳይሆን ጫና እንዲያሳድሩ በመሐመድ ሙርሲ በኩል ጥያቄ ቀርቦላቸዋል የሚል ሰፊ ዘገባ ይዘው የወጡትን የግብጽ ጋዜጦች መነሻ በማድረግ የፓትርያርኩ ጽ/ቤት መግለጫ ሰጥቷል። አናዶሉ የተባለው የዜና ወኪልም በቀጥታ ፖፕ ታዋድሮስ ጉዳዩን ያውቁት እንደሆነ በስልክ አነጋግሮአቸው በሰጡት ምላሽ  እንደገለጹት «የግብጽ ጋዜጦች ይህንን ዜና ከየት እንዳገኙት አላውቅም፤ ለእኔ በግሌ ከፕሬዚዳንት ሞርሲ በኩል  የኢትዮጵያን ግድብ በተመለከተ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ጋር የሽምግልና ድርድር እንዳደርግ የጠየቁኝ ምንም ዓይነት ነገር የለም» በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል።

  የፓትርያርኩ ጽ/ቤት ለዜና ወኪሉ በተጨማሪ እንደገለጸው ጥያቄው ቢቀርብላቸው የኮፕት ቤተ ክርስቲያን በጉዳዩ ላይ ለመሥራት ምንም ቅሬታ የሌላት ቢሆንም መታወቅ ያለበት ነገር ግን፤  የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን በሀገሪቱ መንግሥት የውሳኔ ሰጪነት ሥልጣን ውስጥ ምንም ድርሻ የሌላት መሆኑን መረዳት እንደሚያስፈልግ በመግለጫው ተመልክቷል። ለግብጽና ለኢትዮጵያ ሕዝቦች የጋራ ጥቅምና ሰላም በሚበጅ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር ዝግጁ ነን፤ ይህንን በተመለከተም የኢትዮጵያው ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ሐምሌ 19/2013 ግብጽ በሚመጡበት ወቅት ስለግድቡ ጉዳይ እናነሳላቸዋለን በማለት ጽ/ቤቱ ያለውን ሃሳብ በተጨማሪ አስረድቷል። የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ቀድሞ በነበራት ተደማጭነት በመንግሥት ላይ የምታሳድረው ተጽእኖ ባለመኖሩ በግድቡ ጉዳይ ላይ የጎላ ሚና ይኖራታል ተብሎ አይጠበቅም ሲል በዜና ዘገባው ላይ «አናዶሉ» የዜና ወኪል ያገኘውን ማብራሪያ መነሻ አድርጎ የራሱን ትንታኔ በመስጠት ስለኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የወቅቱ አቅም እስከየት ድረስ እንደሆነ በግልጽ አስቀምጧል።
     ከዚሁ ጋር ተያይዞ የደርግን የውድቀት ቀን ተጠግቶ ግንቦት 20 የመፍሰሻ አቅጣጫው መለወጡ ስለተነገረው ታላቁ ኅዳሴ ግድብ የግብጽ ሚዲያዎች የጩኸትና የጦርነት ዜማ በማቅረብ ላይ ይገኛሉ። የጃማአ አል ኢስላሚያ ሙፍቲ የሆኑት ሼክ አብደል አክሄር ሐማድ ለተከታዮቻቸው ባሰሙት ንግግር እንደተጠቆሙት «ኢትዮጵያ የዓባይን ወንዝ አቅጣጫ መቀየሯ በግብጽ ሕዝብ ላይ ጦርነት እንዳወጀች ያህል ይቆጠራል» በማለት ጠጣር መልዕክት አስተላልፈዋል። «አል አረቢያ» ለተሰኘው ቴሌቪዥን ጣቢያም በቀጥታ ስርጭት ባደረጉት ንግግር «የኢትዮጵያን ድርጊት የግብጽ መንግሥት በትዕግስትና በዝምታ ሊመለከተው አይገባም፤ የኢትዮጵያ ድርጊት በግብጽ ላይ የተፈጸመ የጦርነት አዋጅ ነው፤ ይህንን ድርጊት በፍጹም አንታገስም፤ በሽምግልና  ብቻ የሚፈታ ጉዳይ ስላልሆነ መብታችንን በኃይል እስከማስከበር መሄዳችን የግድ ወደሚል ሁኔታ ውስጥ እየገባን ነው» በማለት አቋማቸውን ለአድማጭ፤ ተመልካቹ በግልጽ ተናግረዋል። ግብጾች የሚጠብቀንን ግዴታ ሳንዘነጋ የዲፕሎማሲውን ጉዳይ ጎን ለጎን በማካሄድ ትኩረት መስጠት ይገባናል ማለታቸውም ተወስቷል።
    በሌላ በኩልም በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ወቅት የግብጽ ጦር አዛዥ የነበሩት ጀነራል ሞሐመድ አሊ ቢላል እንዳስገነዘቡት ግብጽ በዓባይ ግድብ ላይ የጥቃት እርምጃ ብትወሰድ  ቀጣናውን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ የሚቀይረው ሲሆን በኢትዮጵያ ውስጥ ሰፊ የጋራ ጥቅም ያላት ቻይናና የግብጽ ባላንጣ የሆነችው እስራኤልን ወደጉዳዩ እንዲገቡ ሊያደርጋቸው ስለሚችል ግብጽ በምትወስደው  የጥቃት እርምጃ ምንም ትርፍ አታገኝም ሲሉ ለአል አረቢያ ሳተላይት ቴሌቪዥን ጣቢያ የረቡዕ 30/ 5/2013 ዕለት ስርጭት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
      የሰሞኑ የግብጽ ሚዲያዎች እያራገቡ የሚገኙበትን ዘገባ ስንቃኝ  ጦር፤ ጦር የሚሸት መንፈስን ባዘለ መልኩ መሆኑ  ምናልባትም አንዳንዶቹ ለኢትዮጵያ ባላቸው ዝቅተኛ ግምትና  ለራሳቸው ጥቅም አብልጦ የማሰብ ራስ ወዳድነት ሲሆን አንዳንዶቹም በከፍተኛ ፖለቲከኞች በኩል ሆን ተብሎ በማስፈራሪያ ሰበብ  የሚሰራጭና የግብጽ እርምጃ የት ድረስ ሊሄድ እንደሚችል ለኢትዮጵያ መንግሥት መልዕክት ለማስተላለፍ ተፈልጎ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። 
በዚህም ተባለ በዚያ «አስቀድሞ ነበር መጥኖ መደቆስ፤ አሁን ምን ያደርጋል ድስትን ጥዶ ማልቀስ» እንዳይሆን  አንዴ የገቡበትን ሥራ ቀድሞ ባልጀመርነው ኖሮ ከማለት የኢትዮጵያ መንግሥት ከዲፕሎማሲው ጎን ለጎን ራሱን ማዘጋጀት ይገባዋል እንላለን። መንግሥት ልቡን ሰፊና እጁን ረጅም አድርጎ በፖለቲካ ያኮረፉትን በመጥራት በሀገር የጋራ ጉዳይ ላይ ማግባባት ወደሚችል የግል ሁኔታ ለመግባት የመድብለ ፓርቲውን ሥርዓት በር ከፈት ማድረግ አለበት።  እንደኢትዮጵያ ባለና ውጥንቅጡ በወጣ አመለካከት ውስጥ ልማት ብቻውን ሀገር አይገነባም። አሸባሪ የተባለ ማንም ተነስቶ የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው ቢል አያስገርምም። ባራቅነውና በረገምነው ቁጥር መራቁ ባህሪያዊ ነውና። አሁን በኢትዮጵያ የሚታየው ሕገ መንግሥታዊ መብቶችን በልማት ዜማ የማዳፈን ጉዳይ አኩራፊ ማበራከቱና ለጠላት በር መክፈቱ አይቀሬ ይሆናል። ግብጾች ራሳቸው መሥራት ያልቻሉትን የውጪ ሥራ በሌሎች እጅ ከማሰራት ይመለሳሉ ማለት የዋህነት ነው። 
ዓለማችን በአየር ለውጥ የተነሳ ሙቀቷ እየጨመረና በረሃማነትም እየተስፋፋ እንደመሄዱ መጠን አንድ ዓባይን ብቻ በተስፋ የምትጠብቅ ግብጽ በሆነ አጋጣሚ አንድ ክረምት ዝናብ በበቂ ባይጥልና ወንዙ ጎድሎ በትነት መጠኑን ከቀድሞው ቢቀንስባት ወደአጥፍቶ መጥፋት አትገባም ማለት አይቻልም። ረጅም እሳቤ ያለው እቅድ ለዓባይ የዛሬው ግድብ አስፈላጊው ነው እንላለን። 
እንዲያውም ስለዓባይ የተነገረው  የግብጽ ሸክም የሚራገፍበት ዘመን ደርሶም ይሆን? የሚል የትንቢት ጥያቄም እናነሳለን።
«ግብጻውያንንም በጨካኝ ጌታ እጅ አሳልፌ እሰጣለሁ ጨካኝ ንጉሥም ይገዛቸዋል ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፦ ውኆችም ከባሕር ይደርቃሉ፥ ወንዙም ያንሳል ደረቅም ይሆናል። ወንዞቹም ይገማሉ፥ የግብጽም መስኖች ያንሳሉ ይደርቃሉም ደንገልና ቄጤማ ይጠወልጋሉ።  በዓባይ ወንዝ ዳር ያለው መስክ በዓባይም ወንዝ አጠገብ የተዘራ እርሻ ሁሉ ይደርቃል፥ ይበተንማል፥ አይገኝምም። ዓሣ አጥማጆቹ ያዝናሉ፥ በዓባይም ወንዝ መቃጥን የሚጥሉት ሁሉ ያለቅሳሉ፥ በውኆችም ላይ መረብ የሚዘረጉት ይዝላሉ» 
ኢሳ 19፤ 4-8

Thursday, May 30, 2013

በሰማንያ ወአሀዱ መጽሐፍ ሽፋን የተፈጸመው የጠላት ሴራ ሲገለጥ


(ክፍል ፩ )

መግቢያ፤

ሰይጣን የሰውን ልጅ ከሚያሳስትበት  አንዱ መንገድ የእግዚአብሔርን ቃል በማጣመም መተርጎም ነው። እግዚአብሔር አዳምን ከገነት ዛፎች መካከል አንዱን ሲከለክለው እንዲህ ብሎት ነበር። «ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና» ዘፍ 2፤17  ሰይጣን  ደግሞ ለዚህ ትዕዛዝ በመጀመሪያ የጥርጣሬ መንፈሱን በመርጨት «ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን?» ዘፍ 3፣1 ብሎ ከጠየቀ በኋላ ስለማይበላው የዕጽ ፍሬ አስፈላጊነት ራሱ መልሱን ሲሰጥ እናገኘዋለን። የምንጊዜም ምላሹ ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል በተቃረነ መልኩ መሆኑ ነው። «እባብም ለሴቲቱ አላት። ሞትን አትሞቱም» ዘፍ 3፤4 እግዚአብሔር አምላክ ሞትን ትሞታላችሁ ሲል ሰይጣን ደግሞ ሞትን አትሞቱም ማለቱ የሀሰት አባት ያሰኘዋል። ከራሱ አመንጭቶ የሚናገር፤ ያመነጨውንም እውነት አስመስሎ የሚያቀርብ የክፋት ሁሉ ስር በመሆኑም ጭምር ነው። ሰይጣን እሱ ያመነጨውን ሀሰት አስቀድሞ ልበ ድኩም ፈልጎ  ይጭንና ሥራው ሁሉ በዚያ ሰው በኩል እየተላለፈ ለዓለሙ ሁሉ እንዲዳረስ ያደፋፍራል። ልክ የዘመኑ ትሮጃን ፈረስ የተባለው አንዱ ቫይረስ እየተራባ ኮምፒውተሮችን ሁሉ እንደሚያጠቃው ሰይጣን እውነተኛ ቃል አጣምሞ ሰዎችን ሁሉ ያጠቃል። ልዩነቱ የሰይጣን የጥቃት መሠረት የሰው ልጆችን ከእግዚአብሔር መንግሥት መለየት መቻሉ ስለሆነ ጥቃቱን የከፋ ያደርገዋል። ሰይጣን የጥርጣሬና የሞትን አትሞቱም መርዙን በቅድሚያ የረጨው በሔዋን ልቦና ውስጥ ሲሆን ስራው በትክክል ተቀባይነት ማግኘቱን ሲያረጋግጥ ትቷቸው ሄዷል። አዳምም የሞትን [ትሮጃን ሆርስ] ሃሳብ ከሚስቱ ተቀብሎ ተግባር ላይ ካዋለ በኋላ ውድቀቱን በማየቱ ረዳት የሰጠው እግዚአብሔርን በመክሰስ ለዚህ ሁሉ ውድቀቴ ምክንያቱ አንተ የሰጠኸኝ ሴት ናት በሚል ወቀሳ ሲያቀርብ እንመለከታለን።
« አዳምም አለ፦ ከእኔ ጋር እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት እርስዋ ከዛፉ ሰጠችኝና በላሁ» ዘፍ 3፤12  ሔዋንም በተራዋ ጣቷን ወደእባብ ስታመለክት ማየታችን(ዘፍ 3፤13) የሰው ልጅ የራሱን ስህተት ባለመመልከት ሌላውን ስሁት አድርጎ የማቅረብ የዳበረ ልምድ እንዳለው ያረጋግጥልናል። ሰይጣን እስካለ ድረስ ድረስ ውጤታማ የሆነበትን ይህንን የማሳሳት ልምዱን ወደጥልቁ እስኪወረወር ድረስ ገቢራዊ ከማድረግ ለአፍታም እንደማያርፍ የቀደመ ሥራው ለዚህ ዘመንም አረጋጋጭ ነው። ሰይጣን ራሱ ሲጠየቅ በዓለሙ ሁሉ ለማሳሳት ያለዕረፍት እንደሚዞር መናገሩ በቂ ማስረጃ ነው።
«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ» ኢዮብ 1፤7
ሰይጣን ምድርን ሁሉ የሚዞረው ስለአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ጥናት ለማካሄድ አለያም የተፈጥሮ ሀብት ክብካቤ ወይም የሰላምና ጸጥታ ሁኔታን መርምሮ ለማረጋጋት እንዳልሆነ እርግጥ ነው። መልካምነት ባህርይው ስላልሆነ ሰይጣን ዙረቱ ሁሉ ማጥፋት፤ ማሳሳት፤ መፈተንና መግደል ብቻ ነውና አሁን ድረስ እንደዞረ ነው። በዚህም ዘመን የሰው ልጆችን ዋና የሚያጠቃበት መሣሪያው ሰዎች እግዚአብሔርን ወደማወቅ እንዳይደርሱ፤ እውነቱን አውቀው ንስሐ እንዳይገቡ፤ የእግዚአብሔርን ቃል በመጋረድና በመከለል የስህተት መንገድ እንዲፈጠር በማድረግ ነው። ምክንያቱም ይህ ትውልድ የያዕቆብን አምላክ የሚፈልግ ነውና። «ይህች ትውልድ እርሱን የምትፈልግ ናት፥ የያዕቆብን አምላክ ፊት የምትፈልግ» መዝ 24፤6  በመጨረሻው ዘመን የመንግሥትም ወንጌል በዓለሙ ሁሉ እንደሚሰበክ አስቀድሞ ተነግሮ ነበርና። (ማቴ 24፤14) የቀረለት  ጊዜ  ጥቂት እንደሆነ ስለሚያውቅ እየዞረ ቃሉን በማጣመም እግዚአብሔር እንዳይመለክ ይጋርዳል፤ እውነት የሚመስል የስህተት ቃል እየፈጠረ ይከራከራል።
«ስለዚህ፥ ሰማይና በውስጡ የምታድሩ ሆይ፥ ደስ ይበላችሁ፤ ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፥ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና» ራእይ 12፣12
ልክ እንደተወርዋሪ ኮከብ በዘመናት ውስጥ ብቅ ብለው (በቀደሙት ዘመናት፤ እንደአባ እስጢፋኖስ ፤በኋላም እንደአለቃ ታዬና አቡነ ፊልጶስ ጳጳስ ዘኢየሩሳሌም ወዘተ) ዓይነቶቹ ብርሃናቸውን አብርተው ሳይጨርሱ እልም ብለው የጠፉት ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ጠላት ባስቀመጠው እንቅፋት እንደነበር ታሪክ ይነግረናል። ለዚህም ዋናው ነጥብ ጠላት ቤተክርስቲያኒቱ ጥንት ከምትቀበለውና በሐዋርያት መሰረት ላይ ከታነጸችበት አለት ላይ እያንሸራተተ በመከራ ወጀብ እንድትናጥ የሚያደርጋት የክፉ መንፈስ አሰራር በመንገሱ ነው። ወደዋናው የሰማንያ አሀዱ ገመና ከመግባታችን በፊት እስኪ አንዱንና  ፈጣሪን  ከፍጡራን ጋር አዳብሎ  በአምሳለ አምላክ የማስመለክ የጠላትን አሰራር አስቀድመን እንመልከት። ይህንን ቃል የማቅ አገልጋይ ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ ከዚህ ቀደም እርሱ ከሚፈልገው መንገድ በመተርጎም የበለሱን ውበት እንዲያስጎመጅ አድርጎ አቅርቦት ነበር። ብዙዎችም ይህንን በለስ እየተቀባበሉ በማማሩ ተስበው ሲመገቡት ቆይተዋል። እስኪ ከዚያ እንጀምር።
1/ ፍጡርና ፈጣሪ አንድ ምስጋና ይገባቸዋልን?
«"ለእሉ ክሌቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ»  «ለእነዚህ ሁለት ፍጡራን/ለማርያምና ለመስቀል/ የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል፤ በክብራቸው ተካክለውታልና» የሚለውን ትርጉም ዲ/ን ኅብረት የሺጥላ እንዲህ ሲል በመተርጎም ዓይናችሁን  ግለጡና የበለሱን ውበት ተመልክቱ በማለት ያባብለናል።
«ይህ መጽሐፍ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጸሎት መጽሐፍ ነው፡፡ ለበርካታ መቶ አመታት አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ በተሐድሶ መናፍቃን ጠንካራ ትችትና ነቀፋ ቢደርስበትም አሁንም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ስለቅዱስ መስቀል በተጓዳኝ አንሥቶ ይናገራል፡፡ ካለ በኋላ ዲ/ኑ በመቀጠል ፤በመስተብቁዕ ዘመስቀል ላይ የሚገኘው ‹‹እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ›› የሚለው የግዕዝ ዐረፍተ ነገር ወደ አማርኛ ‹‹በክብር ተመሳስለዋልና›› ተብሎ መተርጎም ሲኖርበት ወደ አማርኛ የመለሰው ክፍል ‹‹በክብር ተካክለዋልና›› ብሎ ስለተረጎመው አንባቢን የሚያሳስት ሊሆን ችሏል፡፡ ስለዚህ ዋናው ችግር የመጽሐፉ ሳይሆን ከግዕዝ ወደ አማርኛ የመለሰው ሰው ነው፡፡በዚህ ዐረፍተ ነገር ውስጥ ወሳኝ ሚና የሚጫወተው ቃል ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግሥ ነው፡፡ ‹‹ዐረየ›› ሁለት ፍቺ አለው፡፡ አንደኛው ‹‹ተካከለ›› ማለት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ‹‹ተመሳሰለ›› የሚል ነው፡፡ «ዐረየ» በመለኮት «ተካከለ» እንደሚባል ነግሮን «ዐረየ« የሚለው «ተመሳሰለ» ተብሎ የሚተረጎምበትን ምክንያታዊ ጭብጥ ሳይነግረን ዝም ብሎ አልፎታል። «ማርያምና መስቀል፤ ከፈጣሪ ጋር ተመሳስለዋል » ተብሎ ቢፈታ ትንሽ የላላ መስሎት ከሆነ ፍጡርና ፈጣሪ በምን ሊመሳሰሉ እንደሚችሉ ሊነግረን የግድ ይሆናል። ያለበለዚያ «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል» በማለት የስህተት ቃል በቀደመችው ቤተክርስቲያን ውስጥ ጠላት የተከለውን ስህተት ዲያቆኑ ደግሞ  የዘርዓ ያዕቆብን  ሌጋሲ ለማስቀጠል ካለው ፍላጎት የመነጨ ከመሆን አይዘልም።
እንግዲህ ይህ ሰው መስተብቁዕን አይቶ አያውቅም ወይም ግሱን ከመጻሕፍት አላገላበጠም። ካልሆነም ደግሞ እባብ ያሳየውን የበለሱን መልክና ውበት ተቀብሎ እያገለገለ ነው ማለት ነው። «ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለዋልና የሚለውን ቃል «በክብር ተመሳስለዋል እንጂ ተካክለዋል ማለት አይደለም በማለት ሊያዘነጋን ይሞክራል። ስሁት መንገዱን ከፍቶ ኑ በዚህ ሂዱ እያለ የሞትን በለስ ጎዳና ያመላክተናል። ትርጉሙን ስንመለከት «ዐርይ» ማለት በገቢር መምሰል፤ መተካከል፤ ትክክል መሆን ሲሆን በተገብሮ ደግሞ ተካከለ፤ ተመሳሰለ ማለት ነው።  በፈጣሪነት ባህርይ፤ በሥራው ካልተስተካከለው ወይም ካልመሰለው፤ አከለው፤ መሰለው ማለት አንችልም። አለበለዚያም መመሳሰልን ወደምድራዊ የሰዎች ሚዛን በማውረድ «መስቀልን፤ማርያምንና ክርስቶስን» ወደመለካት ክህደት ውስጥ የባሰ መውረድ ይሆናል። ዲያቆኑ በዚያ መንገድ ተመልከቱ እያለ መገኘቱ ከማይወጣው ድቅድቅ ውስጥ እየገባ ነውና የምታውቁት እባካችሁ ምከሩት። ንስሐም ይግባ!
ስለመለኮት  ዕሪና ስንናገር አንዱ ከሌላው ጋር የተካከለ/እኩል የሆነ/፤ የተስተካከለ/ከፍታና ዝቅታ የሌለው/፤ ምንም ያልተለየ ፤ፍጹም አንድ የሆነ ማለት ነው። አምላክ፤ ወልደ አምላክ ኢየሱስን ከማርያምና ከመስቀል ጋር ማመሳሰልም ሆነ ማስተካከል አይቻልም። «ለእሉ ክልዔቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ» ለእነዚህ ሁለቱ ፍጡራን የአምላክ ምስጋና ይገባቸዋል» ማለት የአምላክነት ባህርይን ይጋራሉ ማለት ሲሆን ምክንያታዊ ንጽጽሩን ሲያቀርብ ደግሞ «እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ» በክብር ተካክለውታልና በማለት ያመጣዋል። የፈጣሪነት ክብር ከፍጡርነት ክብር ጋር ሊተካከልም ሆነ ሊመሳሰል በፍጹም አይችልም። ቅድስት ማርያም ኢየሱስን በመውለዷ ወደአምላክነት አልተቀየረችም። መስቀሉም ኢየሱስ ስለሞተበት አምላክ ወደመሆን አልተለወጠም። ፍጡር በፈጣሪ ይከብራል እንጂ ከማንም የማይቀበልና ማንም ሊወስድበት የማይችል ክብር ያለውን አምላክ ከፈጣሪ ጋር ተመሳሳይ ምስጋና ይገባቸዋል ማለት ትልቅ ክህደት ነው። ጸጋ ተቀባይ ቢከብር ከሰጪው ቸርነት እንጂ  ራሱ ባለው አምላካዊ የመሆን ብቃት አይደለም።
«ጸጋን የተመላሽ ክብርት ሆይ ደስ ይበልሽ» ብለን ማርያምን ስናመሰግናት ጸጋውን የመላት አንድያ ልጇ መሆኑን እንረዳለን። ብጽእት ማርያም እያለ ትውልድ ማመስገኑ ከአምላክ ጋር ስለተካከለች ወይም ስለተመሳሰለች ሳይሆን ከሴቶች ሁሉ ተመርጣ የአብ አንድያ ልጅ ኢየሱስን በሥጋ ስለወለደችው ነው።  ማርያም መውደድና ማክበር ወደአምላክነት እስክንቀይራት ድረስ እንድንሄድ  ሊያደርገን አይገባም። « ነፍስየሰ ትትሐሰይ፤ በአምላኪየ ወበመድኃኒትየ» ነፍሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ሀሴት ታደርጋለች ማለቷን ስንመለከት ድንግል ማርያም የትህትናና የእውነት እናት መሆኗን ነው። እኛ እውነቱን ስንናገር ማርያምን አትወዷትም በማሰኘት ሰይጣን በሌሎች አፍ ሊከሰን ይፈልጋል። ዝም ስንል ደግሞ በሌሎች አፍ አድሮ  እሷ እኮ ለአምላክ የሚሰጠው ምስጋናና አምልኮ ይገባታል እያለ ያታልላል። «ይህንን ዕፅ ብትበሉ ዓይናችሁ ይከፈታል» በማለት ለሔዋን ሹክ እንዳለው ዛሬም  ቅን በምትመስል ቃለ እግዚአብሔር ስር ተከልሎ አምላክ ብቻውን እንዳይመሰገን ለማስቀናት ሥራውን ይሰራል። እግዚአብሔር ራሱ ሁሉን የሰራ፤ ሁሉን የተሸከመና ከማንም ጋር እንደማይመሳሰል በቃሉ እንዲህ ሲል ይነግረናል።
«እስከ ሽምግልና ድረስ እኔ ነኝ፥ እስከ ሽበትም ድረስ እሸከማችኋለሁ እኔ ሠርቻለሁ እኔም አነሣለሁ እኔ እሸከማለሁ እኔም አድናለሁ።በማን ትመስሉኛላችሁ? ከማንስ ጋር ታስተካክሉኛላችሁ? እንመሳሰል ዘንድ ከማን ጋር ታስተያዩኛላችሁ?» ኢሳ 46፤5
ይቀጥላል…………….

Monday, May 27, 2013

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ለምን ተሐድሶ ያስፈልጋታል?


ምንጭ፡-http://www.tehadeso.com/
ቤተ ክርስቲያን በእግዚአብሔር እና በክርስቶስ ደም የታደሱና የተቀደሱ የምእመናን ጉባኤ ናት፡፡ ይህቺን አማናዊት ቤተ ክርስቲያን ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ ታሪኳን ስናጠና በእግዚአብሔር ሐሳብ ውስጥ የሰው ሐሳብ እየተቀላቀለ እና ጤናማውንና ርቱዕ የሆነውን አስተምህሮ የሚያደፈርሱ ሰብኣዊ፣ አጋንንታዊና ዓለማዊ ሐሳቦች በተለያየ ሁኔታና መንገድ ወደ አማናዊቷ ቤተ ክርስቲያን ዘልቀው እየገቡ እውነተኛ የሆነውን መንፈሳዊ ትምህርትም ሲያደፈርሱ እናያለን፡፡ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ያሉ ለእውነተኛው የእግዚአብሔር ሐሳብ ቀናዕያን የሆኑ ቅዱሳን የእግዚአብሔርን ሐሳብ በሚያደፈርሱ አስተሳሰቦች እና ግለሶቦች ላይ ጠንከር ያለ ተግሣጽ ሲሰጡና አስፈላጊውን የእርምት እርምጃ ሲወስዱ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እናነባለን፡፡ ምክንያቱም ተሐድሶ አዲስን ነገር አፍልቆ ማምጣትና በነበረ እውነት ላይ መጨመር ሳይሆን ከጌታችንና ከሐዋርያት የተቀበልነውን የሚያድነውን መለኮታዊ መገለጥ (አስተርእዮ) የሚጋርድ ትምህርትና ድርጊት ሲከሠት መጽሐፍ ቅዱሳዊውን ትምህርት ለመጠበቅ የሚወሰድ የእርምት እርምጃ ስለሆነ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያናችንም ሐዋርያዊት በመሆኗ የተመሠረተችበት የእምነት መሠረት አማናዊ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ነገር ግን በየጊዜው ምንጫቸው የማይታወቅ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ዲያብሎስንና ሰብእን ከእውነት ይልቅ ሐሰትን የሚያገለግሉ አስተሳሰቦች እና አስተምህሮዎች በመስኮት እውነተኛው የእግዚአብሔር ሐሳብ ወደ ጎን ተትቶ መንፈሳዊ ሕይወታችን ታውኮ በእውነተኛው ትምህርት ላይ ሐሰት ተቀላቅሎበት መንፈሳዊ ቁመናዋ ተበላሽቶ እንመለከታለን፡፡
ይህንን መንፈሳዊ ዝቅጠት የተመለከቱ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና መምህራን በየዘመናቱ እርምት እንዲወሰድበት ሲታገሉና ሲያስተምሩ ቢኖሩም ከእግዚአብሔር ያልሆነው ከቅዱሳት መጻሕፍት (ከአሥራው መጽሐፍት) የሚቃረነው አዲስ ትምህርት እንዳይታረም በነገሥታቱ ተደግፎና ታግለውለት ሲቆይና ሌላ ጊዜ ደግሞ ጨዋው ከአባቶቼ የተቀበልኩት ትምህርት ስለሆነ በማለት በእውነተኛ የክርስትና ትምህርት ላይ እንደ እራፊ የተለጠፈውን ባዕድ ትምህርት ለማስጠበቅ ሊቃውንቱንና መምህራኑን አፉን ሞልቶ “መናፍቃን ናችሁ” ብሎ መከራና ስደት እንዲነሣባቸው በማድረጉ በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ብዙዎች ስለቤተ ክርስቲያንና ስለእግዚአብሔር እውነት በብዙ መከራ ሕይወታቸውን መሥዋዕት አድርገዋል፡፡ ሌሎችም ተሰድደዋል፤ ተደብድበዋል፤ ታስረዋል፤ ተራቁተዋል፡፡
ይህ በመሆኑና ዛሬም በወንጌል ትምህርት ላይ የተጨመረ አሳሳች ትምህርትን እንደ ዶግማ የሚቆጥሩ የተደራጁ የእውነት ጠላቶች በመኖራቸው ብዙ የማስፈራሪያ ድምፅ ስለሚያሰሙ መምህራኑ አፋቸው ተለጉሞ በመከራ አሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ይህ አደጋ ክፉውን መንፈስ ሊያገለግሉ በቆረጡ ደጋፊዎቹ ታጅቦ ሙሉ በሙሉ የመንፈስ ቅዱስን ሐሳብ የሚዋጋ የዲያብሎስ ጦር ሆኖ ይታያል፡፡ እንዲህ ያለውን አደጋ ገልጦ ማሳየት እና ቤተ ክርስቲያን ወደ አማናዊው የክርስቶስ ሐሳብ እንድትመለስ ማድረግ የማንኛውም ጤናማ አእምሮ ያለው ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ከዚህም በመነሣት ለሰው ሳይሆን ለእግዚአብሔር ሐሳብ በመቅናት፣ ሰውን ሳይሆን እግዚአብሔርን በመስማት ቤተ ክርስቲያናችን ለምን ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት አስረጅ የሆኑ ምክንያቶችን እናቀርባለን፡፡
1.    በቤተ ክርስቲያኒቱ እንግዳ ትምህርቶች ስለበዙ
ክርስትናን በተመለከተ ከመሥራቹ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና ከእርሱም ቀጥሎ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩ ሐዋርያት ትምህርት የበለጠና የተሻለ ትምህርት አይገኝም፡፡ እነዚህ ትምህርቶች ለክርስትናችን ቋሚ መሠረት ሆነው የሚታዩና በምንም ሌላ እንግዳ ትምህርት ሊተኩ የማይችሉ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “እኛም ብንሆን ወይም የሰማይ መልአክ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን” ብሎ በጻፈልን አምላካዊ ቃል ሙሉ በሙሉ መስማማት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው (ገላ. 1÷8)፡፡ ወደ ፊት በስፋት እና ነጥብ በነጥብ የምንተችበት ቢሆንም በአንዳንድ ገድላት፣ ድርሳናት እና ተአምራት ላይ ተጽፈው የሚገኙ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በቀጥታ የሚጋጩ እንግዳ ትምህርቶችን ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ራስዋ ተመልክታ ልታስተካክላቸው ስለሚገባ ወደ እውነተኛውና ከአምላኳ ወደተቀበችው ትምህርት እንድትመለስ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፡፡
እንግዳ ትምህርቶቹ መወገድ የሚገባቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህች ምድር ወርዶ የሰው ልጆችን ለማዳን በመስቀል ላይ የሠራውን ሥራ ስለሚያቃልሉ እና እነዚህን ትምህርቶች እውነት ናቸው ብለው የተቀበሉት ሰዎች ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ባለመቻላቸው አንዳንዶች እነዚህን እንግዳ ትምህርቶች የኢትዮጵያዊነት መለያ አድርገው ቢወስዱዋቸውም፣ እንደ እውነት ቢከራከሩላቸውም፣ የሰው ልጆችን ከኀጢአት እስር ፈትቶ የዘላለም ርስታቸውን መንግሥተ ሰማያትን እንዲወርሱ ያደረገው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው እንጂ ሌላ ምንም ነገር ስላይደለ ከሲኦል እስር ከዲያብሎስ ቁራኛነት ለመላቀቅ ከቃሉ ውጭ የሆኑ ሐሳቦችን ሽረን ለወንጌሉ እንግዳ የሆኑ ትምህርቶችን ትተን በጠራው የመስቀል መንገድ ላይ በእምነት መጓዝ በዚህ ዘመን ለቤተ ክርስቲያን ወሳኝ ጊዜ ስለሆነ ይህን ውድቀቷን በቃለ እግዚአብሔርና በመንፈስ ቅዱስ ምርመራ ከእንግዳ ትምህርቶች ልትለይ ይገባልና ተሐድሶ ያስፈልጋታል፡፡
2.    የእግዚአብሔር ቃል ተገቢውን ስፍራ ስላጣ
ሌላው ቤተ ክርስቲኒቱ ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት አስረጅ የሆነው እውነት ቅዱስ ወንጌል በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ተገቢውን ስፍራ ማጣቱ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉን መጽሐፍ ይመረምራል፣ ይመዝናል፤ እርሱ ግን  በየትኛውም መጽሐፍ አይመረመርም፤ አይመዘንም፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት የተለየ ሐሳብ ያለው ማንኛውም በቤተ ክርስቲያን የምንገለገልበት  መጽሐፍ ሌላ ምንም አይነት አንድምታ ሳያስፈልገው ከስህተት ትምህርት ጎራ ሊካተት ይገባዋል፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ የሁሉ ዳኛ በሆነው በእግዚአብሔር መንፈስ በመጻፉና የእግዚአብሔርን እውነት በመያዙ ነው፡፡ አሁን  ግን ምንጫቸው የማይታወቅ እና በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስን የሚቃረኑ መጻሕፍት ከመጽሐፍ ቅዱስ እኩል መሳ ለመሳ በመቀመጣቸው እና መጽሐፍ ቅዱስን በመገዳደራቸው በእውርነት ልምራችሁ የሚሉንን መጽሐፎች ተገቢውን ስፍራቸውን ማሳወቁ አግባብ ስለሆነ ተሐድሶ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስፈላጊ ነው፡፡
ሌላው ቀርቶ በስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር ወቅት ንጹሑን ወንጌል መስበክ እንደ መናፍቅነት እየተቆጠረ ስለመጣ አገልጋዮች የግድ የእግዚአብሔርን እውነት የሚጋፉ መጻሕፍትን እየጠቀሱ እነርሱም አገልግሎታቸውም የእግዚአብሔርን መንግሥት እውነተኛ ሐሳብ የሚቃረኑ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ የእውነተኛ ኦርቶዶክሳዊነት መሠረቱ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እና በሐዋርያት አባቶች የተሰበከውን ቃል በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ማብራራት መሆኑ እየቀረ ድርሳነ ባልቴትን መተረክ እየሆነ ይገኛል፡፡
እንዲህ ያለው አስተሳሰብ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ትክክለኛውን ተሐድሶ ካላገኘ እና ቤተ ክርስቲያኒቱ ሙሉ በሙሉ መመሪያዋ እንዲሆናት ወደ እግዚአብሔር ቃል ካልተመለሰች አሁንም ቢሆን በየዕለቱ እየጨመረ የመጣውን የምእመናን ፍልሰት ማስቆም ይቸግራታል፡፡ ሰውን በስፍራው ለማጽናት የተሻለው እና እግዚአብሔርም የሚደሰትበት ትክክለኛው መንገድ የእውነትን ቃል በእውነት ሳያፍሩ እና ሳይሸሽጉ እንደ ጥንት አባቶቻችን ለሕዝቡ መግለጥ ነው፡፡ ለዚህም ቤተ ክርስቲያን ጤነኛ በሆነ የተሐድሶ ኣስተሳሰብ ልትቃኝ ያስፈልጋታል፡፡
3. የመዳንን እውነት የሚገዳደሩ ትምህርቶችን ማስተናገድ ስለጀመረች
የልጅ ቡኮ ዕለቱን ነው
ቢጋግሩት ነቀፋ ነው
ቢቀምሱትም የከረፋ
ቢጨብጡት ወዮ አበሳ
እንደተባለው መንፈስ ቅዱስን ሳያማክሩ ለአሸናፊው የእግዚአብሔር ሐሳብ ብቻ መገዛትን ትተው የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምሮ በማያውቁ እና ለስሜታቸው ባሪያ በሆኑ ሰዎች እየተፈጠሩ ያሉት አዳዲስ አስተምህሮዎች ሀይ ባይ ከልካይ አጥተው የክርስቶስን መስቀል እየወጉ ይገኛሉ፡፡ እኛም እንደ ቤሪያ ምእመናን “ነገሩ እውነት ይሆንን?” በማለት ለመመርመር ከመሞከር ይልቅ “ከኛ ወገን ያለ ሁሉ የሚለው ሁልጊዜ እውነት ነው” በሚል በጨዋ ምእመን አመክንዮ ተይዘን ለስህተት ትምህርቶች ተገዝተን እንገኛለን፡፡ እነዚህ የስህተት ትምህርቶች የመዳንን እውነት ቀስ በቀስ እየሸረሸሩ አሁን ፊት ለፊት መዋጋት ጀምረዋል፡፡ “ያለ ድንግል ማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም” የሚለውና እርሱን የመሰሉ ጥንተ ተፈጥሮዋቸው አጋንንታዊ የሆኑ እና “መዳን በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና” (የሐዋ.ሥራ 4÷12) የሚለውን የመንፈስ ቅዱስ አዋጅ የሚሽሩ እንግዳ ትምህርቶች በመጽሐፍ ደረጃ ታትመው እስከ መሰራጨት ደርሰዋል፡፡
በእግዚአብሔር ቃል የተገለጸውን “መዳን በሌላ በማንም የለም” ተብሎ የተዘጋውን የጽድቅ ማኅተም የሚከፍቱ በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው እውነት ውጭ  ሌላ አማራጭ አለ ብለው የሚያስተምሩ ሁሉ ለሰው መዳን ሳይሆን መጥፋት በአጋዥነት የሚሠሩ ናቸው፡፡ ከዚህ ጋር የተያያዙ እና በዝክር፣ ወንዝ በማቋረጥ፣ ገዳማት በመሳለም፣ በቀብር ቦታ እና በሌሎችም ብዙ መንገዶች ሰው ሊድን ይችላል፡፡ ብለው የሚያስተምሩ ደፋር ብዕር የገለበጣቸው አጋንንታዊ ሐሳቦች ያሉባቸው ገድላት እና ተአምራት በመኖራቸው ሕዝቡ ያዳነውን ጌታ በእውነተኛ ማንነቱ ሳይረዳ በዋል ፈሰስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡
መዳን የህልውና ጉዳይ ስለሆነ በቀላሉ ሊታይ የሚችል አይደለም፡፡ እናቶቻችን እንደሚሉት “እስቲ ይሁና!! ምን ይታወቃል የአንድዬ ሥራ” በማለትም በቀላሉ ሊታለፍ የሚችል ነገርም አይደለም፡፡ የአንድዬ ሥራ የሚታወቅ እና በአደባባይ በመስቀል ላይ የተከናወነ ነው፡፡ አንድዬ ለመዳናችን ከደሙ የተሻለ አማራጭ አልሰጠንም፡፡ በመስቀል ላይ የፈሰሰውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ደም ለኔ ስለኃጢአቴ የተከፈለ ቤዛነት ነው ብሎ አምኖ መቀበል ለመዳን ዋነኛውም ብቸኛውም አማራጭ ነው፡፡
ነገር ግን ህዝቡ ይህንን እውነት አምኖ እንዳይቀበል የሚከለክሉ ሌላም አማራጭ አለህ ብለው የሚያስተምሩ በክርስቶስ የተሰጠንን መዳን ቀብረው ማሳሳቻ የሚሰብኩ ስለበዙ ቤተክርስቲያናችን ወደ ሐዋርያት ትምህርት እንድትመለስ መታደስ አለባት፡፡ መዳን በክርስቶስና በመስዋዕታዊ ሞቱ በማመን መሆኑን መቀበልና ማስተማር አዲስ ትምህርት የሚመስላቸው አሉ ግን አይደለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ እና በተደጋጋሚ የተቀመጠ፣ ሐዋርያት የሰበኩት እስከ ዘመናችን ድረስ እውነተኛውን መንገድ የተከተሉ እንደ እነ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ያሉ አባቶቻችን መዳን በእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ የሆነ እና በክርስቶስ በማመን ብቻ የምንቀበለው ነው፡፡ ብለው ያስተማሩት ትምህርት ነው፡፡(ትምህርተ ሀይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት )
ስለዚህ በእነዚህ እና በሌሎች ተጨማሪ ምክንያቶች ተሐድሶ ለቤተክርስቲያኒቱ ያስፈልጋታል ብለን እናምናለን፡፡ ለእናት ቤተክርስቲያናችን መታደስም የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማድረግ እናገለግላለን፡፡
ይቀጥላል

Sunday, May 26, 2013

የክርስቲያኖች ሰንበት የሚል ሕግ አለ?


 ታሪክ፤
እሁድን እንደመንፈሳዊ የእረፍት ቀን መቁጠር ከመጀመሩ በፊት ቀደምት ሕዝቦች የፀሐይ ቀን አድርገው ያከብሩት ነበር። በእንግሊዝኛው/ Sun- day / የሚለው ቃል ትርጉም የሚያመለክተው ያንን ሲሆን መነሻ ስርወ ቃሉም  የአንግሎ ሳክሶን ቃል ከሆነው / sunnandei/ ከሚለው የመጣ ቃል ነው። ትርጉሙም የፀሀይ ቀን ነው።  እሁድ ወይም /ዮም ርሾን יום ראשון/ ማለት የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን ማለት ነው። ዮም ርሾን እንደአንድ ቁጥር/ 1/  ሆኖም ያገልግላል። የአይሁድ ሰንበት፤ ሰባተኛው ቀን እንደመሆኑ መጠን የእሁድን የመጀመሪያ ቀን መሆንን ከአንድ ተነስተን ብንቆጥር ያረጋግጥልናል። ይህ የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን/ እሁድ/ በጥንት ሮማውያን ዘንድ ከሥራ ሁሉ የእረፍት ቀን ሆኖም አገልግሏል። ቆስጠንጢኖስ ንጉሥ መጋቢት 10/ 313 ዓ/ም ይህንን ቀን የሮማውያን ግዛት እረፍት ቀን ይሆን ዘንድ በአዋጅ አጽድቆታል።  ስለእሁድ የመጀመሪያ ቀን መሆንና በጥንታዊው ስያሜ ዙሪያ ታሪካዊ ዳራውን በአጭሩ ካመላከትን መንፈሳዊ አመጣጡን ደግሞ በጥቂቱ እንመልከት።
1/ ሰባተኛ ቀን፤
ሰንበት የሚለው ቃል ከእብራይስጡ Shabbat (שַׁבָּת) ከሚለው ቃል የመጣ ሲሆን ቀጥተኛ ትርጉሙም ከድካም ማረፍ ወይም ሥራን ማቆም (to cease or to desist from exertion) ማለት ነው። ሰንበት እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ለእስራኤል ከሰጠው አሥርቱ ትእዛዛት ውስጥ አንዱ ነው።
 ኦሪት ዘጸአት 20:8-11  የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ።ስድስት ቀን ሥራ ተግባርህንም ሁሉ አድርግ:: ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክህ ሰንበት ነው አንተ፥ ወንድ ልጅህም፥ ሴት ልጅህም፥ ሎሌህም፥ ገረድህም፥ ከብትህም፥ በደጆችህም ውስጥ ያለ እንግዳ በእርሱ ምንም ሥራ አትሥሩ:: እግዚአብሔር በስድስት ቀን ሰማይንና ምድርን፥ ባሕርንም፥ ያለባቸውንም ሁሉ ፈጥሮ በሰባተኛው ቀን ዐርፎአልና ስለዚህ እግዚአብሔር የሰንበትን ቀን ባርኮታል ቀድሶታልም።
የቃሉ ትርጉምና እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ሰንበት ከድካምና ከሥራ ሰዎችና እንስሳት የሚያርፉበት የእረፍት ቀን ነው። በተለይ ከሰንበት ጋር ተያይዞ የተጠቀሱት ሎሌዎች፣ የቤት ሠራተኞች፣ ባሪያዎችና ከብቶች በዚያን ጊዜ እጅግ አድካሚ ሥራ ይሠሩና ይለፉ የነበሩ ናቸው። ሰለዚህ ሰንበት በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ከሠራው ሥራ በሰባተኛው ቀን እንዳረፈ ሁሉ ከሥራና ከድካም ማረፍ ጋር የተያያዘ ነው። ለዚህ ነው ሰውን ብቻ ሳይሆን የአምልኮ ፕሮግራም ማድረግ የማይችሉትን ከብቶችንም የሰንበት ትእዛዝ የሚያጠቃልለው።
ከዚህ በተጨማሪ ሰንበት በእግዚአብሔርና በእስራኤል ሕዝብ መካከል የተደረገ የምልክት ቃል ኪዳን ነው። እንደማናቸውም የብሉይ ኪዳን ሕግ ሰንበትም በማያከብሩት ላይ መርገምና ፍርድ የሚያመጣም ትእዛዝ ነው።
ኦሪት ዘጸአት 31:12-17 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው። ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብለህ ንገራቸው። እኔ የምቀድሳችሁ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቁ ዘንድ በእኔና በእናንተ ዘንድ ለልጅ ልጃችሁ ምልክት ነውና ሰንበቶቼን ፈጽሞ ጠብቁ። ስለዚህ ለእናንተ ቅዱስ ነውና ሰንበትን ጠብቁ የሚያረክሰውም ሰው ሁሉ ፈጽሞ ይገደል፥ ሥራንም በእርሱ የሠራ ሰው ሁሉ ከሕዝቡ መካከል ተለይቶ ይጥፋ። ስድስት ቀን ሥራን ሥራ ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር የተቀደሰ የዕረፍት ሰንበት ነው በሰንበት ቀን የሚሠራ ሁሉ ፈጽሞ ይገደል። የእስራኤልም ልጆች ለልጅ ልጃቸው ለዘላለም ቃል ኪዳን በሰንበት ያርፉ ዘንድ ሰንበትን ይጠብቁ። እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን በስድስት ቀን ስለ ፈጠረ፥ በሰባተኛውም ቀን ከሥራው ስላረፈና ስለ ተነፈሰ፥ በእኔና በእስራኤል ልጆች ዘንድ የዘላለም ምልክት ነው።
ብዙ ጊዜ ሰንበት ተብሎ በልማድ የሚታወቀው ሥራ የማይሠራበትንና የአምልኮ ፕሮግራሞች የሚካሄዱበትን ቀን ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ግን ሰንበት የሚባለው በእስራኤልና በእግዚአብሔር ብቻ የተገባን ቃል ኪዳን ነው። በዚያ ቀን "የአምልኮ ፕሮግራም የማይካፈል ይሙት" ሳይሆን ትእዛዙ የሚለው "በሰንበት ቀን የሚሠራ ሁሉ ፈጽሞ ይገደል" የሚል ፍርድና ቅጣት ያለው ነው። በብሉይ ኪዳንም ይሁን በአሁኑ ዘመን እስራኤላውያን ሰንበትን የሚጠብቁት ቅዳሜ ነው፡፡
2/ የመጀመሪያው ቀን
ክርስቲያኖች የአይሁድ ሰንበትን ይጠብቁ ዘንድ አልታዘዙም። በእርግጥ እስራኤላዊ ሆነው ወደ ጌታ እምነት የሚመጡ ሰንበትን መጠበቅ ይችላሉ አልተከለከሉም። ነገር ግን ሰንበት ለክርስቲያኖች የተሰጠ ትእዛዝ አይደለም። እስራኤላዊ ባልሆኑ አህዛብ ክርስቲያኖችም ዘንድ በአዲስ ኪዳን ሰንበት ሲጠበቅ ይሁን ሰንበትን እንዲጠብቁ ሲታዘዙ አናነብብም። ይህ ብቻ አይደለም፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ክርስቲያኖች ይጠብቁትና ያከብሩት ዘንድ የተሰጠ ምንም ዓይነት ቀን ወይም በዓል የለም። ክርስትና የቀኖችና የበዓላቶች አክብሮ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ የሆነ ሕይወት ነውና።
ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2:16-17 እንግዲህ በመብል ወይም በመጠጥ ወይም ስለ በዓል ወይም ስለ ወር መባቻ ወይም ስለ ሰንበት ማንም አይፍረድባችሁ። እነዚህ ሊመጡ ያሉት ነገሮች ጥላ ናቸውና፥ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው።
በአዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች በዚያን ዘመን የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን በሆነው እሁድ እሁድ ይሰበሰቡና ጌታን እያመለኩ የጌታን እራት ይካፈሉ እንደነበር ተጽፎአል፦
የሐዋርያት ሥራ 20፥7 ከሳምንቱም በመጀመሪያ ቀን እንጀራ ለመቁረስ ተሰብስበን ሳለን፥ ጳውሎስ በነገው ሊሄድ ስላሰበ ከእነርሱ ጋር ይነጋገር ነበር፥ እስከ መንፈቀ ሌሊትም ነገሩን አስረዘመ።
ይህ የሳምንቱ መጀመሪያ የሆነው እሁድ ቀን ጌታ ኢየሱስ ከሙታን የተነሳበትም ቀን ሰለ ነበር አንዳንዴም የጌታ ቀን ተብሎ ይጠራል፦
የሉቃስ ወንጌል 24:1-5 ነገር ግን ከሳምንቱ በመጀመሪያው ቀን ያዘጋጁትን ሽቱ ይዘው ከእነርሱም ጋር አንዳንዶቹ ወደ መቃብሩ እጅግ ማልደው መጡ። ድንጋዩንም ከመቃብሩ ተንከባሎ አገኙት፥ ገብተውም የጌታን የኢየሱስን ሥጋ አላገኙም። እነርሱም በዚህ ሲያመነቱ፥ እነሆ፥ ሁለት ሰዎች የሚያንጸባርቅ ልብስ ለብሰው ወደ እነርሱ ቀረቡ፤ ፈርተውም ፊታቸውን ወደ ምድር አቀርቅረው ሳሉ፥ እንዲህ አሉአቸው። ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቶአል እንጂ በዚህ የለም።
የዮሐንስ ራእይ 1፥10 በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፥ በኋላዬም የመለከትን ድምፅ የሚመስል ትላቅ ድምፅ ሰማሁ፥
አዲስ ኪዳን የሚሰጠው ፍንጭ ክርስቲያኖች ጌታ ኢየሱስ በተነሳበት ቀን እሁድ እግዚአብሔርን እንደሚያመልኩና የጌታን እራት እየቆረሱ ሕብረት እንደሚያደርጉ ያመለክታል። ይሄንን ሲያደርጉ ግን ሰንበትን እያከበሩ አይደለም፡፡ ሰራተኞቻቸውንና ከብቶቻቸውን ወዘተ ቀኑን ሙሉ ከድካማቸው እያሳረፉና ሰው ቢተላለፈው ፍርድ ያለበትን በሕግ የተደነገገውን ሰንበትን እያከበሩ አይደለም። በአዲስ ኪዳን የቀንና የምግብ እርኩስና ቅዱስ የለም! የምግብና የበዓላት ትእዛዛት ሁሉ በሕግ ውስጥ ካለ የሥርዓት ሸክምና ለጽድቅ የሚደረግ ልፋት ሊያሳርፈንና ወደ እረፍቱ ሊያስገባን የመጣው የክርስቶስ ጥላዎችና ምሳሌዎች ብቻ ናቸው። የክርስቶስ የሆኑትስ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ እነርሱም ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብና እርሱን ለማግኘት ከሚደረግ የሥርዓት ጥረትና ድካም እርሱን አግኝተው አርፈዋል። ወደ እግዚአብሔር ሰንበትም ገብተዋል።
ወደ ዕብራውያን 4:9-10 እንግዲያስ የሰንበት ዕረፍት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ቀርቶላቸዋል። ወደ ዕረፍቱ የገባ፥ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ፥ እርሱ ደግሞ ከሥራው አርፎአልና።
ስለዚህ ክርስቲያኖች ምንም እንኳን ታሪካዊ አመጣጡ ለብዙ የታሪክ ተመራማሪዎችም እንኳን ግልጽ ባልሆነ እሁድ እሁድ የመሰብሰብና እግዚአብሔርን የማምለክ ልምድ ቢኖራቸውም፤ ይሄን ግን እንደ ሰንበት መውሰድ ወይም ይባስ ብሎ ሰንበት ከቅዳሜ ወደ እሁድ እንደተቀየረ ማሰብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የለውም። እሁድ የክርስቲያኖች ሰንበት አይደለም። የብሉይ ኪዳኑን ሰንበትን የመጠበቅ ትእዛዝ ለአዲስ ኪዳን አማኞች አልተሰጠም። ማንም ግን ሰንበትን ማክበር ቢፈልግ፤ ሰንበት ሕግ ነውና ሕጉ ደግሞ ያለ መርገም አልመጣምና በሰንበት ምንም አይነት ሥራ ቢሠራ ራሱን ከሕግና ከእርግማን በታች እያደረገ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግና ከእርግማን በታች ሳንሆን ከጸጋ በታች ሆነን በነጻነት እንድንኖር ከሕግ እርግማን ሊያመጣን መጣ እንጂ እንደገና ለሥርዓትና ለበዓላት ባርነት አልጠራንም።
ወደ ገላትያ ሰዎች 3፦11-13  ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸውና፤ በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና።ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎአልና ማንም በእግዚአብሔር ፊት በሕግ እንዳይጸድቅ ግልጥ ነው። ሕግም ከእምነት አይደለም ነገር ግን፤ የሚያደርገው ይኖርበታል ተብሎአል። በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን፤
3/ ማጠቃለያ፣
የአይሁድ ሰንበት በእግዚአብሔር በራሱ ከፍጥረት ሥራው በማረፍ ለአይሁዳውያን የተሰጠ የተለየ ቀን ነው። በኋለኛው አዲስ ዘመን ደግሞ ዓለሙን ሁሉ በልጁ ደም ካዳነ በኋላ የመጀመሪያውን ቀን ወይም የጌታ ቀን የተባለውን ዕለት በአይሁዳውያን ሰንበት መልኩ በማረፍ፤ እናንተም ዕረፉ በማለት ሕግን አልሰጠም። ስለዚህም የክርስቲያን ሰንበት የሚባል ቀን የለም። ትንሣዔውን፤ ዕርገቱን፤ ቅዱሳን በጌታ ቀን ሲጸልዩ መታየታቸው በራሱ የዕረፍት ቀን የመሆንን ሕግ ሳይሆን የሚያመለክተው መንፈሳዊ ተግባራትን በማድረግ፤ ቃሉን በማሰብና በመጸለይ ብናሳልፍ መልካም እንዲሆንልን የሚያመለክት ነው። ለጸሎት፤ ለቅዳሴ፣ ለጾምና ጸሎት መፋጠን የተለየ ድንጋጌ መሰጠቱን አያመለክትም። ቅጠል በመበጠስ፤ ከአንድ ምዕራፍ በላይ መንገድ በመሄድ ወይም ሥራ በመስራታችን ለቀኑ ከተሰጠ ድንጋጌና የውግዘት እርግማን ለመጠበቅ ተብሎ አይደለም። እንደአይሁድ ሰንበት የሚያከብሩ ሰዎች  አልፈው ተርፈው፤ የእመቤታችንን 33 በዓላተ ቀኖቿን እንደእሁድ ሰንበት ያላከበረ ፈጽሞ የተወገዘ ይሁን በማለት ብዙ ሰንበታት ፈጥረውልን ይገኛሉ። /መቅድመ ተአምር/ ከዚያም  ባለፈ ሰንበተ ክርስቲያን ተብላ በሰዎች የተሰየመችው ይህች ቀን በሰው አምሳል ከመጥራት ተጀምሮ መልሷን እስከመፈለግም ተደርሷል።«ሰዓሊ ለነ ሰንበተ ክርስቲያን ቅድስት፣ለውሉደ ሰብእ መድኃኒት፣ ወእስከ ለዓለም ሰፋኒት» ትርጉም--ለሰው ልጆች መድኃኒትና እስከዘለዓለም ገዢ የሆንሽ፣ ቅድስት የክርስቲያን ሰንበት ሆይ ለምኝልን ማለት ነው። ሰንበት የተባለው ክርስቶስ ራሱ ነው የሚሉ ደካማዎች ቢኖሩም ክርስቶስን « ለምኝልን» ሊሉ ቢመኙ እንዴትና ከማን? በሚል ጥያቄ ማጣደፋችን አይቀርም። ይልቁንም ይህ የክርስቲያን ሰንበት እንዳለ ከሚያስብ አእምሮ የመነጨ ትምህርት ነው። አንዲቱን ቀን በሰው አንደበት እያናገሩ፤ ከሷ ምላሽ መጠበቅ ክርስቲያናዊ ትምህርት አይደለም።
ብዙ አይሁዶች ከይሁዲነት ወደክርስትና ሲመለሱ ቀዳሚት ሰንበትን በነበራቸው ልምድ ዓይነት የክርስቲያን ሰንበት አድርገው ያከብሩ ነበር። የቀዳሚት ሰንበትን የማክበር ባህል በሀገራችን እስካሁን ድረስ በብዙ ቦታዎች አልተቀየረም። ቀዳሚት ሰንበት የአይሁድ በዓል እንጂ የክርስቲያኖች እንዳልሆነ በ363 ዓ/ም የላኦዲቂያ ጉባዔ አንቀጽ 29 ላይ ተደንግጎ ነበር።  የክርስቶስ ሞትና ትንሣዔ የተለየች ቀንን ለመባረክና የእረፍት ቀን ለማድረግ ሳይሆን ክርስቲያኖች ከነበረን የሕግ ሸክም ሊያሳርፈን መሆኑን ልንረዳ ይገባል። እሁድን በጸሎት፤ በምሥጋናና በቅዳሴ ብናከብር ለክርስቲያን የተሰጠ ልዩ ቀንና ሰንበት ስለሆነ አይደለም። ምክንያቱም በእግዚአብሔር ቀናት ውስጥ ርጉምና ቅዱስ የሚባል የለም።

Wednesday, May 22, 2013

የጤና መረጃ ( በሰውነታችን ከመጠን ያለፈ ስኳር መከማቸት ችግር )

ጣፊያ የተባለው የሰውነታችን ክፍል ለደም ዝውውር የሚያገለግለውን ኢንሱሊን የተባለውን ንጥረ ነገር ማምረት ሳይችል ሲቀር ወደ ደም ሴል መሄድ የሚገባው ስኳር ክምችት ይፈጠራል። ከመጠን በላይ የስኳር መገኘት ችግርም «የስኳር በሽታ» ወይም /Diabetes/ ይባላል። ቁጥር 1 ተብሎ የሚጠራው የስኳር በሽታ በዘር ሊወረስ እንደሚችል ሲነገር፤ ቁጥር 2 ተብሎ የሚጠራው የስኳር ህመም ግን በአብዛኛው ከኑሮ ምቹነትና ከሰውነት እንቅስቃሴ ጉድለት የሚመጣ ነው። ሰዎች በተፈጥሮአችን በመንቀሳቀስ፤ በመውጣት፤ በመውረድ፤ ላብና ወዛችንን አንጠፍጥፈን በመስራት እንድንኖር ተደርገን ወደዚህ ምድር የመጣን ቢሆንም ኑሮአችን ምቹና ድካም በማይጠይቅ ሁኔታ ውስጥ እንድንኖር በሚያደርግ ቅንጦት ውስጥ በዕለታዊ ምግባችን ውስጥ በስብና ቅባት ክምችት የተነሳ የደም ዝውውራችንን እንዲዛነፍ እናደርገዋለን። ስለሆነም ለሰውነታችን ሥርዓተ ዑደት /metabolism/ በስራ ወይም በአካል እንቅስቃሴ እናስተካክል። ከመጠን በላይ በሆነ የሰውነት ግዝፈትና ድሎት ራሳችንን ከምንጎዳ በማጣት ሰው ለተራቡ ያለንን እናካፍል።

Tuesday, May 21, 2013

«እግዚአብሔርን ወደማወቅ መድረስ


የሥነ አእምሮ፤ የፍልስፍናና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ሪቻርድ ፕራት ሃይማኖትን ሰዎች የሚጠቀሙት ከሚመጣባቸው ቁጣና ቅጣት በማምለጥ ሰላምና ዘላለማዊ ዋስትና አገኝበታለሁ ብለው ለመጠለያነት ነው ይላሉ። ከዚያ ተቋም ውጪ ዋስትና አለ ብለው አያስቡም። ሰላምና ዋስትና መፈለግ በራሱ ጥሩ ቢሆንም ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት በራሳቸው መንገድ የተገለጸውን ሰላምና ዋስትና መስጠት ወይም ማሰጠት አለመቻላቸው እውነት ነው። እንደሃይማኖቶቹ ልዩነት የተለያየ የደኅንነት መንገድ የለም። ምክንያቱም ዋስትናና ሰላም በተቋም ደረጃ ለተከታዮች የሚከፋፈል ስጦታ ሳይሆን  መስጠት ከሚችልና ዋስትና ካለው የሰላም ባለቤት ከራሱ ከእግዚአብሔር ለጠየቁትና ለለመኑት በቀጥታ የሚሰጥ እንጂ እግዚአብሔር ለሃይማኖት ተቋማት በተለይ አድሎ፤ እነርሱ ደግሞ በተናጠል ወደእነሱ ለመጣ እንዲያድሉ የተደረገበት መንገድ በፍጹም የለም። እግዚአብሔርን አባት ብለው ለሚጠሩት አማኞች ሁሉ አባት  የሚሆነው ልጅ የመባልን ጸጋ በነጻ ማግኘታቸውን አምነው ለተቀበሉ ብቻ ነው ይላሉ ዶ/ር ፕራት።
« በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና» ገላ 3፤26
በማመን የሚገኘውን ጸጋና ልጅነትን በሃይማኖት ተቋም በኩል መቀበል አይቻልም። ዛሬ በዚህ ዓለም ላይ የሃይማኖት ተቋማት መብዛት ዋናው ምክንያት ከሌላው የተሻለ ሰላምና ዋስትናን ለተከተለን ሁሉ እናድላለን ብለው ስለሚሰብኩ ብቻ ነው። በየድርጅቶቹ ውስጥ ያሉ ተከታዮችም በዚያ ተቋም በኩል ሰላምና ዋስትና ያገኙ ስለሚመስላቸው እኔ ኦርቶዶክስ ነኝ፤ እኔ ካቶሊክ ነኝ፤ እኔ ይሁዲ፤ እኔ እስላም፤ እኔ ፕሮቴስታንት ነኝ፤  ጴንጤ ነኝ፤ እኔ ደግሞ ሙሉ፤ ጎዶሎ፤ ቤዛ፤ መሠረት፤ሞርሞን፤ ወዘተ ነኝ እያሉ መታመኛና ዋስትና ያለበት የራሳቸውን ተቋም ትክክለኛነት ይናገራሉ። ሁሉም ራሱን ከሌላው የተሻለ የዋስትናና የሰላም ምንጭ የሆነውን ፈጣሪ ለመስጠት ብቃቱና ውክልናው አለኝ ብሎ ለራሱ ይመሰክራል።  እንዲያውም አንዱ ሃይማኖት የሌላውን ጉድለት በራሱ መንገድ እየዘረዘረ ራሱን ከማንም የተሻለ የእግዚአብሔርን ጎዳና መሪ አድርጎ በመደስኮር ወደእሱ ለመምጣት እንዲሽቀዳደሙ ሲሰብክ ይታያል። እግዚአብሔር ሰዎችን የሚመዝነው ባሉበት የእምነት ተቋም ያለውን ህግና ደንብ ማክበራቸውን በማየት ሳይሆን እግዚአብሔርን አውቀው ከእርሱ ጋር ያደረጉትን እምነትና ኅብረት በመመዘን ብቻ መሆኑ እውነት ነው። አማኞች ያሉበት ሃይማኖት የሰራላቸውን አጥር አልፈው እግዚአብሔርን ለማወቅና ለማግኘት፤ ከእኔነት አዙሪት ወጥተው ለአንዱ እግዚአብሔር መገዛት ቢችሉ ኖሮ የሃይማኖት ተቋማት ባልኖሩም ነበር።  የመጀመሪያይቱ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። ዛሬም ከድርጅትነት የተለየች የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት። የየሃይማኖቶች ጥምቀት፤ ጌታና አባት የለም። ሃይማኖቶች ግን የየራሳቸውን ጌታ፤ አባትና ጥምቀት ሲሰጡ ይታያሉ። ይህም የመጽሐፉ ተቃራኒ ነው።
«አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ»  ኤፌ 4፤5-6
 ይሁን እንጂ ያለው እውነት አንድ ብቻ በመሆኑ እኔ፤ እኔ ያለው ሁሉ እውነተኛ ሊሆን አይችልም። በዚህም ይሁን በዚያ የማይናወጥና የማያጠራጥር እውነት፤ ሰላምና ዋስትና ያለው ከምንጩ ባለቤት ከኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ክርስቶስም  ሰላምና ዋስትናን በውክልና እንዲሰጥ ያቋቋመው አንድም ተቋም እና ድርጅት በዚህ ምድር ካለመኖሩም በላይ ክርስቶስ በአማኞች ልቦና ላይ ሰላምና ዋስትናን ሊመሰርት መጣ እንጂ ድርጅት ሊያቋቁም አይደለም። ክርስቶስ ያቋቋመው እኔን ነው ማለት የሚቻለው  ባለሰርቲፊኬት ተቋም ባለመኖሩ ሁሉም እኔ ከሌላው የተሻልኩ ለክርስቶስ ቅርብ ነኝ እያለ ራሱን አጽዳቂ ከመሆን ውጪ ሰላምና ዋስትናን በዚህ ምድር ማምጣት አይችልም።
ሳይካትሪስትና የነገረ መለኮት ምሁር የሆኑት ዶ/ር ሪዩበን ዴቪድ  ደግሞ እንዲህ ይላሉ። ሁሉም ሃይማኖቶች እግዚአብሔርን የሚገልጹበት የየራሳቸው ዶግማና አስተምህሮ፤ የእግዚአብሔር ወዳጅ ለመሆን የሚያስችልም የየራሳቸው ሕግና ደንብ አላቸው። ያንን ዶግማና አስተምህሮ፤ ሕግና ደንብ በመጠበቅ ብቻ ትክክለኛው እግዚአብሔር ይገኛል ስለሚሉ  እያንዳንዱ የሚያምነውና ከእርሱ ዘንድ ብቻ በትክክል እንዳለ የሚገልጽበት የራሱ እግዚአብሔር አለው  ሲሉ  ያብራራሉ።  ዶ/ር ሪዩበን ማብራሪያቸውን ሲቀጥሉ ትክክለኛው እውነት ግን እግዚአብሔር ራሱን የገለጸበትና የሚለካበት መንገድ እያንዳንዱ ሃይማኖት በጻፈው ዶግማ፤ አስተምህሮ፤ ሕግና ቀኖና መሠረት አለመሆኑ ነው።  የእስላሞች ፈጣሪ «አላህ» ይባላል። እስላሞች ራሳቸው የተረጎሙትን ያንን «አላህ» ሰው ማመን ካልቻለ አይድንም ይላሉ። አላህ የሚገኘውም ቁርአን በተባለ መጽሐፋቸው ውስጥ ነው። ከዚያ ውጪ አላህ የለም።ካቶሊኮች የራሳቸው የሆነና ካቶሊካዊ ትርጉም  የተሰጠው እግዚአብሔርን የማወቅ ዐለምዓለቀፋዊነት አስተምህሮ፤ ዶግማና ቀኖና አላቸው። ሰዎች ትክክለኛውን እግዚአብሔርን ለማግኘት እነዚያ መጽሐፍቶች ውስጥ ገብተው በተተረጎመው ተቋማዊ እምነት ውስጥ መነከር አለባቸው። ካቶሊክ መሆን ካልቻሉ እግዚአብሔርን አያገኙትም፤ ወይም በተሳሳተ ጎዳና ላይ ናቸው ይላሉ።  ገሚሱም የቀደመችው መንገድ በዚህ አለች ይላሉ። አንዳንዶቹም ኢየሱስን ከእኛ ዘንድ ተቀበሉ፣ እንደግል አዳኝ ካልወሰድክ አትድንም ይላሉ። እርግጥ ነው፤ እምነት የግል ነው። የክርስቶስ የማዳን አገልግሎት የተሰጠው ግን ለግል አይደለም። ላመኑ ሁሉ እንዲያው የተሰጠ ጸጋ ነው። አንድ ሰው በግሉ ክርስቶስን ማመኑ ክርስቶስን የግል አዳኝ አያደርገውም። ማንም ለመዳን በዚህ የግል አዳኝነቱ መስመር ውስጥ የግድ ማለፍ የሚሉ እንደብቸኛ ወኪልነት ራሳቸውን  የሚቆጥሩ ናቸው።  ዶ/ር ሪዩበን፤ በእርግጥ ማንም ሰው ስለክርስትና መሠረታዊ የመዳን ትምህርትና ሕይወት የሚገኝበትን የመንፈስ ቅዱስ ምሪት እውቀት ያስፈልጉታል። «ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል» 2ኛ ጢሞ 3፤5   «እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው» ሮሜ 10፤17
ቅዱሱን መጽሐፍ መማርና ማንበብ ሕይወት የሚገኝበትን ቃል ለማግኘት እንጂ የድርጅት አባል በመሆን ለእግዚአብሔር ያሉበትን ተቋም እንደትክክለኛ ሥፍራ የማቅረብ ዓላማ አይደለም። ሐዋርያትም ወንጌልን እየተዘዋወሩ ሕዝቡን እያስተማሩና እያጠመቁ ወደ ሕይወት መንገድ መመለስ ቻሉ እንጂ  ድርጅትና የእምነት ተቋም በመመስረት ስለማገልገል አንድም ቦታ ወንጌል ላይ አልነገሩንም በማለት ያብራራሉ ዶ/ር ሪዩበን።  ሰው በመጠየቅ፤ በማንበብ፤ በመማር፤በመጸለይና በእግዚአብሔር ፈቃድ እውነቱን ወደማወቅ  ሊያደርስ ይችላል። በአንድ ድርጅት ውስጥ ተወትፎ መኖር ግን እውነት ምን እንደሆነ ከማወቅ ይከለከላል። ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ የአይሁድ እምነት ተከታይ እንደነበረ የኦሪቱን ሕግ ሊፈጽም ኢየሩሳሌም የመገኘቱ ታሪክ ይነግረናል። ወደሀገሩ ሲመለስ ያልገባውን በመጠየቅ በሐዋርያው ፊልጶስ የኢሳይያስ መጽሐፍ ትርጉም ሲነገረው  እውነቱን ወደማወቅ ደረሰ፤ አመነ ተጠመቀም። ከአይሁዳዊ የእምነት ተቋም ወደክርስትና የመዳን ሕይወት ወዲያው ተሸጋገረ። በሕይወቱ ላይ የመጣው አዲስ ለውጥ ከአይሁድ ሕግና መመሪያ ድርጅታዊ ትእዛዝ ነጻ በመሆን ክርስቲያን የመባል የሐዋርያት እምነትጋር ኅብረት አደረገ እንጂ ከድርጅት ወደድርጅት አልተዘዋወረም። ያለኝ ኦሪታዊ ሕግና ደንብ ይበቃኛል፤ መዳን በዚያ ነው ያለው ብሎ በተቋማዊ ሕግጋቱ ላይ በድርቅናው ጸንቶ ቢሆን ኖሮ እውነቱን ወደማወቅ ባልደረሰም ነበር።  ክርስትና ማለት በክርስቶስ የተገለጠውን እውነት ማወቅና በዚያ ሕይወት ውስጥ መኖር በመሆኑ ጃንደረባው ከዚህ አዲስ እምነት ጋር ለማወቅ ባለው ትጋት ልክ ሊገባ በቃ።  የሃይማኖት ተቋማት አባል ሆኖ መቅረት ማለት በተቋሙ ጣሪያ ስር ተደፍኖ መቅረት ማለት ነው። በጣሪው ከተዘጋ ልቡና ወጣ ብሎ እውነቱን ለማወቅ ሰው ቢፈልግ ኖሮ እንደጃንደረባው ወደእውነቱ መድረስ በቻለ ነበር። ዛሬ በዓለማችን ላይ ያሉ ሃይማኖቶች ሁሉ በተለይም በክርስትናው ስም የሚንቀሳቀሱት በየራሳቸው ጣሪያ ስር ሚሊዮኖችን ነፍሳት ደፍነው በመያዝ ከዚያ እንዳይወጡ በሕግ፤ በመመሪያ፤ በደንብና በትዕዛዝ አጥር  እውነቱን ወደማወቅ እንዳይደርሱ ከልክለው ይገኛሉ።  እስልምና የተባለው እምነት ተከታዮቹን በሃይማኖት መጽሐፉ ላይ ከየትኛውም  ሌላ እምነት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርጉና በእምነት ከማይመስሏቸው ሰዎችም ጓደኝነትን እንኳን እንዳይዙ በጥብቅ ያስጠነቅቃል።  (ሱረቱ አል ኢምራን 3፤28) ከዚህ ጥብቅ መመሪያ የተነሳ ከዚህ እስር ለመውጣት አይችሉም። ከዚህም የተነሳ እውነት ምን እንደሆነ ወደማወቅ ለመድረስ ሊደርሱ አይችሉም። ኢየሱስ ክርስቶስ  በትንሣኤ ዘለሙታን ዳግም ሲመጣ በእሱ ላይ የነበረንን እምነትና ምግባር ይመዝናል እንጂ በነበርንበት የሃይማኖት ተቋም ልክና ማንነት አይፈርድልንም ወይም አይፈርድብንም።  እኔ ቀጥተኛይቱ ስላልን ቀጥተኛ አንሆንም። ቀጥተኛው የት እንዳለ በቃሉ ስንመረምር ብቻ እውነቱን ማወቅ ይቻለናል። አስተዋይ ልብም  በእውቀት፤ ጠቢብም በመሆን ሰሚ ጆሮ ካለን መንገዳችንን ያሰፋዋል፤ በታላቅም ሥፍራ ያደርሰናል። 
«የአስተዋይ ልብ እውቀትን ያገኛል፥ የጠቢባንም ጆሮ እውቀትን ትፈልጋለች፣ የሰው ስጦታ መንገዱን ታሰፋለታለች፥ በታላላቆችም ፊት ታገባዋለች» ምሳሌ 18፤15-16
መንፈሳዊ ሰው መሆን ማለትም ያሉበትን ድርጅት ዓላማ መቀበልና መፈጸም ሳይሆን እግዚአብሔርን ማወቅ፤ እንደትእዛዙና ፈቃዱ መኖር ማለት ነው። ስለዚህ ከድርጅት በላይ እግዚአብሔርን ወደማወቅ አዲስ ሕይወት ልንሻገር ይገባል ።
1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2፥3-4
ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው።

Friday, May 17, 2013

ሰምና ወርቅ ! geezonline.com

 (The best ever Gold & Wax of the year ) dejebirhan
ጥጃዋ የሞተባትን ጥገት፤ አላቢዎች የቋንቋ ዕድርተኞች የጥጃውን ቆዳ ከጅራቱ እስከ አፉ ፈልቅቀው ሥጋውን አውጥተው በምትኩ 800 ቅርጫት ጭድ 500 ያኽሉን በጥጃው ቆዳ ጎስረው ጠቅጥቀው፤ የጥጃ ጎፍላ ወይም እንቡጣ (እንቦሣ) አስመስለው ሠርተው፤ ጸጕር ይብዛው እንጂ መንፈሰ ሕይወት በተለየው ቆዳ ገላው ላይ ጥቁር ጨው ነስንሰው፤ ለሷ ያንን እያላሱ፤ ለራሳቸው ወተቷን እያለቡ "ቴሌቫንጀሊዝም" እሚባል ቅላቸው ውስጥ ሲያንቆረቁሩባት፤ ላሚት እንዲህ አለች አሉ፦

ያለ እየመሰለኝ! ልጄ ሙቶ ሳለ
እንቦሣውን ባየው ልቤ ተታለለ!!

አላቢዎቹም ታዲያ እንዲህ ሲሉ መለሱላት ይባላል፦

ስንኳን አንቺ! ቤተ እስራኤል
ትታለል ነበረች በጥጃ ምስል!!

ሰሙ ጥጃዋ የሞተባትን ጊደር ኑሮ ለሚያውቅ ኹሉ ግልጥ ነው፤ ወርቁም ቢኾን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ የምትገኝበትን ኹኔታ ለሚያውቅ የተሰወረ አይደለም። እንዲያውም ዕድሜ ለቴክኖሎጂ በዓይነ ኅሊና ብቻ ሳይኾን እነሆ በዓይነ ሥጋም ጭምር ወለል ብሎ ይታያል።
http://www.eotc.tv/?q=node/65 ( ሊንኩን ከግዕዝ ኦን ላይን ይመልከቱ )
አዬ ቤተ ተዋሕዶ፤ አንቺም እንዲህ በትንሣኤው ምድር ልብሽ ሙቶ አእምሮሽ ደንዝዞ የለየልሽ ሞኝ ተላላ ላም ኾነሽ ታርፊው!!! "ከመ ዘንቃሕ እምንዋም" ትንሣኤውን ያሳየን አምላክ ያንችንስ ትንሣኤ የሚያሳየን መቼ ይኾን?!

Thursday, May 16, 2013

የማኅበረ ቅዱሳን ተላላኪና ሙሰኛው አባ ኅሩይ ወንድይፍራው ከሥራ አስኪያጅነታቸው ታገዱ።

አባ ኅሩይ ወንድይፍራው የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊነቱን ከአባ ሠረቀ ብርሃን ወ/ሳሙኤል እጅ ተረክበው ማኅበረ ቅዱሳን በሚሰጣቸው መመሪያና ምክር መሠረት ለቤተ ክህነቱ ሸክም፤ ለማኅበሩ ግን ታማኝ አገልጋይ ሆነው መቆየታቸው ይታወሳል። በሥራው ላይ እያሉም በአንድ ወቅት አምነው የፈረሙበትን ደብዳቤ በጨለማ ተታልዬ ነው፤ አሳስተውኝ ነው፤ መዝገብ ቤቷ አሞኝታኝ ነው…………. ወዘተ፤ በሚል ማጭበርበሪያ ምክንያት የፈረሙትን ደብዳቤ መልሰው በመካድ የሰውዬው አቋመ ቢስና እምነት የማይጣልባቸው፤ እንደተልባ ስፍር የሚንሸራተቱ መሆናቸውን አይተን ከዚህ በፊት መዘገባችንም አይዘነጋም። ሰውዬው ማኅበረ ቅዱሳንን የሚያገለግሉት ስለሚወዱት ሳይሆን ስለሚፈሩት እንደሆነ በቅርብ የሚያውቋቸው ሰዎች ሲናገሩ ተሰምተዋል። ለምን እንደሚፈሩት የሚያውቁት እሳቸውና የኃጢአት መዝገብ ጸሐፊው ማኅበር ብቻ ናቸው። እንደክርስቲያን መፍራት የሚገባቸው የፈጠራቸውን እግዚአብሔርን ብቻ መሆን እንደሚገባው  ብናምንም እንደሥጋዊ ሰው ድካማቸውን አይተን ማኅበሩ እዳ በደላቸውን አደባባይ እንዳያውለው ቢፈሩ በእርግጥም ሊታዘንላቸው ይገባል እንላለን።
ይሁን እንጂ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አራት ቦታ ተበታትኖ ልዩ ልዩ ያልጠረቁ ጅቦችን ለማዳረስ ቅርጫው በሲኖዶስ በተወሰነ ጊዜ አባ ኅሩይም አንዱ እግር ደርሷቸው በምዕራብ ክፍለ ከተማ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅነት ተመድበው ነበር። አባ ኅሩይ ብዙዎች ከሚያዝኑባቸውና ከሚያማርሩባቸው ምክንያቶች ዋናውና ግንባር ቀደሙ ጉዳይ ፈርሃ እግዚአብሔር የተለየው ጉቦኝነታቸው ሲሆን እስከዛሬም ብዙዎች እንባቸውን እንደራሔል ወደሰማይ የረጩባቸው ርኅራኄ የለሽ መሆናቸው ነው። አባ ኅሩይ እንኳን ሥራ አስኪያጅ የመሆን ብቃት ምንም የሌላቸው ይሁኑ እንጂ  ጉቦ / ዘረፋ/ በተባለው በሽታ ግን ፈጣንና ጥሩ የገፈፋ ልምድ ያካበቱ እንደሆኑ ገንዘባቸውን የገበሩ ሰዎች በምሬት ሲናገሩ ይደመጣሉ። እሰራልሃለሁ ብለው ሳይሰሩላቸው ያጉላሏቸውና አቤቱታ አቅርበው ከተባባሪ ሌባ አስተዳዳሪዎች ጋር ውስጥ ለውስጥ እየተገናኙ ባለጉዳዩን ያለሥራ ያንሳፈፈፉ፤ ማስጠንቀቂያ እንዲጻፍበት ያስደረጉ፤ የቤተ ክህነቱ ሸክምና የካህናቱ የልቅሶ ምንጭ መሆናቸው ሲነገር የቆየ ጉዳይ ነው።
ይህ ግፍና መከራው የበዛባቸውና ሸክሙ የከበዳቸው ካህናት በአንድ ድምጽ ሆ ብለው ጩኸት በማሰማታቸው፤ ጉዳዩ እስከ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ድረስ ቀርቦ ማስረጃዎች በመገኘታቸው የመጨረሻ ውሳኔ እስኪሰጥባቸው ድረስ የማኅበረ ቅዱሳኑ ተላላኪና የሙሰኞች አባት አባ ኅሩይ ወንድይፍራው በሊቀጳጳሱ ደብዳቤ ከሥራቸው ታግደዋል።
ከዚህ በፊት «ደጀሰላም» ብሎግ እኒህን ሙሰኛ መነኩሴ ሲያንቆለጳጵሳቸውና ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ተስማምተው ለመስራት ተነሳሽነቱ ያላቸው እያለ ለመካብ የሞከረ ቢሆንም በወቅቱ እንደዘገብነው ጊዜውን ጠብቆ ማንነታቸው ገሃድ ወጥቶ እነሆ በሙስና ተግባራቸው ከስራቸው እስከመታገድ ደርሰው የተሸፈነው ሲገለጥ ለማየት ችለናል። ጊዜው ቢረዝምም «ጉድና ጅራት ከወደኋላ ነው» እንዲሉ ከብዙ ጥፋት በኋላ ስራቸው  ማንነታቸውን ገልጦ ሰዓቱ ሲደርስ በመናገሩ፤ ማኅበረ ቅዱሳንን ሲሸማቀቅባቸው፤ እውነታውን ሲለፈልፉ ያልተሰሙት ደግሞ ተግባሩ ራሱ ምስክርነቱን ሰጥቶላቸዋል።  እነማን የማኅበሩ አባላት እንደሆኑ እንደአንድ ማሳያ  ሆኖም ይቆጠራል።
በሌላ መልኩ በእነአሉላ ጥላሁን፤  በእነ መረዋ ዱከሌ በዘመናዊ ስሙ/ ጳውሎስ መልክአ ሥላሴ/ እና በመሰሎቹ የሚዘወረው ከደጀ ሰላም ብሎግ ሞት በኋላ አዲስ የመጣው የማኅበሩ አገልጋይና የደብረ ብርሃን ወታደር የሆነው/ ሐራ ዘተዋሕዶ/ ብሎግ በአዲሱ ፓትርያርክ ምርጫ ወቅት የምርጫው ሂደት ፍትሃዊ አይደለም ሲል እንዳልቆየ ሁሉ የፈለገው አለመሳካቱን ሲያረጋግጥ ፓትርያርኩ ከሰማይ የወረዱ መልአክ ናቸው ወደሚል ውዳሴ መሸጋገሩ ፍቅር ስለጸናበት ሳይሆን »ጅብን ሲወጉ……» እንዲሉ ሆኖ በፓትርያርኩ ሙገሳ ተተግኖ «የማኅበሩ መንገድ ይጠረግ፤ ስርጓጉጡም ይቅና» ለማለት ካልሆነ በስተቀር የንግድ ማኅበሩን ነጋዴነትና የሙሰኞች ወዳጅነቱን ሊሸፍነው አይችልም። ለቤተ ክርስቲያን ከማሰብ የመነጨ እንዳይደለም አሳምረን እናውቃለን። ሌላው ጉዳይ ደግሞ የሙስና አለቃና የቤተክህነቱ ሸክም እንደሆነ የሚነገርለት ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃና  በዙሪያው ያሉ ሙሰኞች የስራ መሰናክል መሆናቸው ባይካድም ማኅበሩ ደግሞ ይህንን ግልጥ ጉድለት በሐራ ተዋሕዶ በኩል ፓትርያርኩን ተጠግቶ እየጮኸ፤  መንገዱን በመዝጋት ማኅበሩ ሰርጎ እንዳይገባ እንቅፋት የሆነባቸውን ሰው በስመ ሙስና አስወግደው  የራሳቸውን የቀን ጅቦች በቦታው ለመተካት ብሎጉ ሲዳክር ይታያል። ነገሩ «ከዝንጀሮ ቆንጆ ማን ይመራርጡ» ስለሆነ የእነ ንቡረ እድ ኤልያስ ቡድንም ይሁን የደብረ ብርሃኑ ወታደር ቡድን ሁላቸውም በቤተክህነቱ ውስጥ የራሳቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚደክሙና የፍትህና ርትዕ ዜማ እየጮሁ ቀበሮነታቸውን ለመሸፈን የሚጥሩ አስመሳይ በላተኞች እንጂ ቤተክህነት የምትሄድበትን የቁልቁሊት መንገድ ለማቃናት ተፈጥሮም ዓላማም የላቸውም። ምክንያቱም  እነንቡረ እድ የሚታሙበትን ሙሰኝነት በተቃራኒው በማኅበሩ አባልና ደጋፊ በአባ ኅሩይም በኩልም እየተገለጸ ይገኛልና። ሁሉም ሙሰኞችና ነጋዴዎች ስለሆኑ ከቤተክህነት ዐውድ መገኘታቸው አንዱ አንዱን ለመጣል በሚደረገው የባለሥልጣናት ጥገኛ የመሆን አባዜ ውስጥ ቤተ ክህነቱን የመንፈሳዊነት ሳይሆን የጥቅም ጦር ዐውድማ አድርገዋታል።
ለፓትርያርኩ የምናሳስበውና የምንጠይቀው ዐብይ ነጥብ ማንም የቤተ ክህነቱ አዛኝ መስሎ የሚጮኸውን ሁሉ በግ ብለው እንዳይቆጥሩና እንዳይታለሉ ሲሆን የመዋቅር ለውጥ፤ የአስተዳደር ሪፎርም፤ የሥራና ሠራተኛ ግንኙነትን ማሻሻል፤ ሕግና ደንብ ገዢ ማዕከል እንዲሆን በማስቻል አዲስ የሥራ መንፈስን በመፍጠር እንጂ በጥገናዊ ለውጥ አንዱን በማቅረብ ሌላውን በማራቅ ላይ አይጠመዱ ድምጻችን ነው። የአባ ኅሩይን የእግድ ደብዳቤ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

Tuesday, May 14, 2013

ፓትርያርክ አቡነ ማቲያስና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በዓባይ ወንዝ ዙሪያ ትልቅ የቤት ሥራ ይጠብቃቸዋል … !!


ጸሐፊው በፍቅር ለይኩን (ምንጭ የረቡዕ ሪፖርተር ጋዜጣ)፤ለደጀ ብርሃን በተለይ የተላከ
በቅርቡ ሙስጠፋ አል ላባድ የተባለ ሊባኖሳዊ ፖለቲከኛና ጸሐፊ Egypt is Battling Ethiopia over the Nile Water በሚል ርዕስ አንድ መጽሐፍ አሳትሞ አውጥቷል፡፡ ይህን የአል ላባድን መጽሐፍ ‹‹አስ ሳፊር›› የተባለ የሊባኖስ ዕለታዊውና ተነባቢ የዐረብኛ ጋዜጣ የመጽሐፉን አጭር ዳሰሳ በፊት ለፊት ገጹ ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡ ራኒ ጌሃ የተባለ ጋዜጠኛም የሊባኖሱን ‹‹አስ ሳፊር›› ጋዜጣ ዳሰሳ Egypt and Ethiopia Heading Toward a War Over Water በሚል ርዕስ በእንግሊዘኛ አሳትሞ ወሬውን ለዓለም መገናኛ ብዙኃን አድርሶታል፡፡
   ሊባኖሳዊው ጸሐፊ በመጽሐፉ ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ ያላትን ጥንታዊና ሺሕ ዘመናትን ያስቆጠር፣ ታሪካዊና ሕጋዊ የሆነ ልዑላዊ መብቷን በመጋፋት ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ በአፍሪካ ተወዳዳሪ የሌለው ግዙፍ የሆነ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ እየገነባች ነው በማለት የተለመደውን ውግዘትና ማስፈራራት የተንጸባረቀበት የሚመስል እሳቤውን በመጽሐፉ በሰፊው አካቶታል፡፡
    ጸሐፊው ይህ ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ ያለችው ግዙፍ ግድብ ‹‹በግብፃውያን ጉሮሮ ላይ የመቆም ያህል ነው፡፡›› ሲል በቁጣና በእልኽ ስሜት ውስጥ የገባ በሚመስል ሁናቴ ነው የገለጸው፡፡ ይኽም ይላል ሙስጠፋ አል ላባድ 97.5 በመቶ በረሃማ ለሆነችው ግብፅ፣ ዓለምን እጹብ ድንቅ ላሰኘው ለግዙፍ ሥልጣኔዋ፣ ወርቃማ ለሆነው ታሪኳ፣ ክብርና ኩራቷ እንዲሁም 90 ሚሊዮን የሚሆነው የግብፅ ሕዝብ ሁለተናዊ ሕይወት ቁልፍ በሆነው በዚህ ታሪካዊ ወንዝ ላይ ኢትዮጵያ የጀመረችው የኃይል ግንባታ ለግብፃውያን አስጊ መሆኑን ነው የገለጸው ላባድ በመጽሐፉ ውስጥ፡፡
  ይኸው ጸሐፊ ግብፅ፣ ሱዳንና ብሪታኒያ የተዋዋሉትን የ1950 ስምምነት በማንሣት ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ ያላትን መብት ማንም ሊጋፋው የማይችል ታሪካዊና ሕጋዊ መብቷን መሆኑን አስረግጦ ሊያስረዳንም ሞክሯል፡፡
   ላባድ በተጨማሪም የታችኛዎቹ የተፋሰሱ አገራት የሆኑት ግብፅና ሱዳን በተናጠል ከእንግሊዝ ጋር ያደረጉትን ስምምነት ሕጋዊ እውቅና በመስጠት ይደግፋል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ በላይኛዎቹ ተፋሰስ አገራት በኢትዮጵያ አስተባባሪነት በናይል ወንዝ ላይ ፍትሐዊ የሆነ የውኃ አጠቃቀም እንዲኖር ያደረጉትን የኢንተቤውን ስምምነት በማንሣት ኢትዮጵያ በላይኛዎቹ ተፋሰስ አገራት መካከል ያደረገችውን ስምምነት በተመለከተ ሲናገር ‹‹ኢትዮጵያ ግብፅን በጉልበት ለማስፈረም አትችልም፤›› ሲል ይደመድማል፡፡
  ይህ ስምምነትና ይላል ላባድ ግብፅ እስከሌለችበትና እስካልተስማማች ድረስ ዋጋ የሌለው ወረቀት ላይ ብቻ ፉከራ ነው የሚል አንድምታ የተንጸበራቀበት አቋሙን ለመግለፅ ሞክሯል በዚሁ መጽሐፉ፡፡
    ሙስጠፋ አል ላባድ ግብፅ ወይም ግብፃውያን ዘወትር የማያንቀላፉ፣ ንቁ የሆነና በተጠንቀቅ የቆሙ ሁለት ዓይኖች አሏት፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ትልቁና ዋንኛው ዓይኗ ሁሌም በዓባይና በዓባይ ዙሪ ላይ እንደተተከለ ነው፡፡ ሌላኛው ዓይኗ ደግሞ በመካከለኛው ምስራቅና በባሕረ ሰላጤው እንደሚያማትር ጽንፈኝነት የተጫነው በሚመስል አገላለጽ ሊያስረዳን ይዳደዋል፡፡
   እናም ሙስጠፋ ግብፅና ግብፃውያን በዓባይ ዙሪያ ላይ ምን ያህል ስሱና ቀልድ የማያውቁ መሆናቸውንም ሊነግረን ይሞክራል፡፡ ይኸው ሊባኖሳዊ ጸሐፊ ኢትዮጵያ ይህን ያህል ግዙፍ የሆነና በአፍሪካ ተወዳዳሪ የሌለው የኤሌክትሪክ ማመንጫ ኃይል ለመገንባት ያነሳሳት ምክንያቶች በማለት ስድስት ዐበይት ምክንያቶቹን በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ይተነትናል፡፡ ወደእነዛ የሙስጠፋ አል ላባድ ትንታኔዎች ለመግባት አልሻም፡፡
        ግን ሊባኖሳዊው ጸሐፊ ሙስጠፋ አል ላባድ በዚህ መጽሐፉ ውስጥ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የጀመረችውን ግዙፍ ግንባታና ይኽን ተከትሎም ከናይል ተፋሰስ አገራት በዋነኝነት ደግሞ ከግብፅ ጋር የገባችበትን ፍጥጫና የጀመረችውን ውይይት/ድርድር ፈር ለማስያዝ ግብፅ ምን ዓይነት ውሳኔ ልትወስድ እንደምትችል የሚያውቀው እግዚአብሔር ብቻ ነው ይለናል፡፡
     ነገር ግን ይላል ሙስጠፋ ማብራሪያውን ሲቀጥል ግብፅ ለወደፊቱ የምትወስደውን እርምጃ ምንም ይሁን ምን የምናየው ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ግን ግብፅ ይህን ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የጀመረችውን ግዙፋ ግንባታ ለማስቆም መውሰድ ካለባት እርምጃ መከካል ብሎ በግንባር ቀደምትነት ከጠቀሳቸው ምክንያቶቹ መካከል ሲጠቅስም፡-
   ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ ያላትን ‹‹የማይለወጥና የማይሻር›› ታሪካዊ፣ ሕጋዊና ሉዓላዊ የሆነ ጥቅሟን ለማስከበር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሺሕ ዘመናት እናት በሆነችው በግብፅ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን በኩል ከፍተኛ የሆነ ጫና ማሳደር የምትችልበትን አማራጭ ማየት ይገባታል በማለት አበክሮ ይገልጻል፡፡
      ሙስጠፋ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የጀመረችውን ልማት በግብፃውያን ሕልውና ላይ የመፍረድ ያህል ነው ብሎ ለሚሟገትላት ግብፅ ለዚህ የሞት ሽረት ጥያቄ ያለ ምንም ልዩነት ሁሉም ግብፃዊ ሊነሣ እንደሚገባው ይወተውታል፡፡ እናም በዚህ የሞት ሽረት ዲፕሎማሲያዊ ትግል ግብፅና ግብፃውያን ያላቸው ተስፋ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በኩል ብቻ እንደሆነ ለግብፅና ለግብፃውያኑ አበክሮና አስረግጦ ገልጧል፡፡

በእርግጥ ግብፃውያን በሃይማኖት ወዳጃቸው በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በኩል የተቻላቸውን ያህል ጥረት ሊያደርጉ እንደሚችሉ እርግጥ ነው፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነን ባለፈው ወርኻ ክረምት የግብፅ ሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ አባልና አዲሱ የግብፅ ፕሬዝዳንት የሆኑት መሀመድ ሙርሲ ለአፍሪካ ኅብረት ስብሰባ ወደ መዲናችን አዲስ አበባ መጥተው በነበሩበት ጊዜ ከነፍሰ ሔር ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር ተገናኝተው መነጋገራቸውን በይፋ ከመገናኛ ብዙኃን አይተናል፣ አድምጠናል፡፡
   ይህ የመሀመድ ሙርሲ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያደረጉት ጉብኝትና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር ያደረጉትን አጭር ቆይታ እንደ አንዳንድ ተንታኞች ሁለት ዐበይት ምክንያቶች ሊኖረው እንደሚችል ተገልጾ ነበር በወቅቱ፡፡
   የመጀመሪያው በሁለቱ አገራት ማለትም በግብጽ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያንና በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በኩል ለሺሕ ዘመናት ለዘለቀው ታሪካዊ ግንኙነት ክብርና እውቅና መስጠት ሲሆን፡፡
     በሌላ በኩል ደግሞ ይህን ጥንታዊና ታሪካዊ የሆነ የሁለቱ አገራትና አብያተ ክርስቲያናትን ግንኙነት አስታኮ በጥንታውያኑ ኢትዮጵያውያን ነገሥታት ዘመን በኢትዮጵያ በኩል በእናት ቤተ ክርስቲያናቸው በግብጽ ኮፕቲክ ክርስቲያን ወንድሞቻቸው ላይ ይደረስ ለነበረው በደልና ግፍ እንደማስፈራሪያ ሆኖ በቆየውና ለግብፃውያን ሕልውና መሠረት በሆነው በዓባይ ወንዝ ላይ የተንጠለጠለ እንደሆነ ነው፡፡
     ምናልባትም ሌላኛው ምክንያት በዘመነ ሆስኒ ሙባረክ አንፃራዊ በሆነ መልኩ የተረጋጋ ሕይወት አላቸው የሚሉት ግብፃውያኑ ክርስቲያኖች የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ ባልተጠበቀ ሁናቴ ወደ ግብፅ ፖለቲካ ማማ ላይ መውጣቱ በግብፃውያኑ ክርስቲያኖች ላይ ምንም ዓይነት የተለየ ጫና፣ ግፍና መከራ እንደማይደርስባቸው ዋስትና ወይም ማረጋገጫ የመስጠት ዓይነት እንደሆነ ትርጉም ተሰጥቶታል፡፡
      ይሁን እንጂ የመሀመድ ሙርሲ ጉብኝትና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር ያደረጉት ውይይት ዐቢይ አጀንዳ ግን የዓባይ ውኃ ጉዳይ መሆኑን ለመናገር ነቢይ ወይም ወልይ መሆን የሚያስፈልገው ነገር አይመስለኝም፡፡ እናም መሀመድ ሙርሲ ወደ ስልጣን በመጡ ማግሥት በአፍሪካ ኅብረት ስብሰባ ሰበብ ይህን የግብፅንና የግብፃውያንን ቁልፍ አጀንዳ፣ የዓባይን ጉዳይ ከግብፅ ጋር ቆየና ታሪካዊ ግንኙነት ባላት በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጠረጴዛ ላይ ማስቀመጣቸው፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የአደራ መልእክትና ትልቅ የቤት ሥራ መስጠታቸው እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡
   ይህን ከላይ በአጭሩ ለመግለጽ በሞከርኩት የሙስጠፋ አል ላባድ መጽሐፍ ውስጥ ግብፅና ግብፃውያን በዓባይ ውኃ ላይ ለመደራደር ያላቸው ተስፋ ‹‹በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲየን በኩል ብቻ ነው፡፡›› የሚል አንድምታ ያለው ምክሩና ከሰሞኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባትና መንፈሳዊ መሪ የሆኑት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ባስተላለፉት ቃለ ቡራኬ ስለ ዓባይ ውኃ ጉዳይ ያነሡት ቁም ነገር ለዚህ አጭር መጣጥፍ መነሻ ሆነኝ፡፡
      በመላው በክርስትና ሃይማኖት አማኞች ዘንድ ባለፈው ሳምንት የተከበረውን የኢየሱስ ክርስቶስን የትንሣኤ በዓል አስመልክተው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የሆኑት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ በአገር ውስጥና በውጭ አገር ለሚገኙ መንፈሳዊ ልጆቻቸው ቡራኬና ቃለ በረከት አስተላልፈው ነበር፡፡
      ቅዱስ ፓትርያርኩ ባስተላለፉት በዚህ በቃለ በረከታቸውና በቡራኬያቸውም፡- ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ የዘመናት እንቆቅልሽ ሆኖ በቆየ በአንድ ወቅታዊ፣ አንገብጋቢና እጅግ ወሳኝ በሆነ አገራዊ አጀንዳ ላይ ፍጹም አዎንታዊነት፣ የድልና በእግዚአብሔር አምላካችን ኃይል ሁሉ ይቻለናል የሚል እምነትና ጽናት በተንጸባረቀበት በሚመስል፣ በትንሣኤው በዓል ‹‹የእንኳን አደረሳችሁ!›› የመልካም ምኞት መግለጫቸው ለኢትዮጵያውያን ሁሉ አንድ ዐቢይ የሆነ መልእክትን አስተላልፈዋል፡፡
    ይኸውም ኢትዮጵያ አገራችን በእግዚአብሔር ከአምላኳ በተቸራት በጥንታዊውና በታሪካዊ ወንዟ በዓባይ ላይ የጀመረችው ታላቁ የሕዳሴው ግድብ ያለ ምንም ጥርጥር በድል ተጠናቆ፣ ለፍሬ በቅቶ፣ ‹‹ከዓባይን ልጅ ውኃ ጠማው›› ተረት ወጥተን ከዓባይ በረከት ጠጥተን የምንረካበት መልካምና ብሩኅ ዘመንን ኢትዮጵያውያን ሁሉ በዓይናቸው እንደሚያዩት ቅዱስነታቸው ያላቸውን ጽኑና የማያወላውል ተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡
     ቅዱስነታቸው በዚህ መልእክታቸውም ለሕዳሴው ግድብ መጠናቀቅ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ባለበትና በተሰማራበት የሥራ መስክ ሁሉ በአገር ፍቅር ስሜት፣ በአንድነትና ጠንካራ የሥራ መንፈስ የበኩሉን እገዛና ርብርብም እንዲያደረግም ነው ያሳሰቡት፡፡
      የቅዱስ ፓትርያርኩ ይሄ መልእክታቸው በአንዳንዶች ዘንድ እምብዛም የተወደደላቸው አይመስልም፡፡ እንደውም እነዚሁ ይህ የፓትርያርኩ መልእክት ያላስደሰታቸው በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚኖሩ አንዳንድ ኢትዮጵያውን ወገኖቻችን ይህች በመንግሥት ተቀንብባ ለፓትርያርኩ አንደበት ለሕዝብ ይደርስ ዘንድ የተላላፈች ‹‹ኢህአዴጋዊ›› መልእክት ናት በማለት የሰላ ትችታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

እርሳቸው የሃይማኖት አባት ናቸው እንጂ የመንግሥት አፈ ቀላጤ አይደሉም፡፡ እናም በዚህ በትንሣኤው በዓል ላይ ማስተላለፍ የሚገባቸው መልእክት እኛ የሰው ልጆች ሁሉ በክርስቶስ ኢየሱስ ሞትና ትንሥኤ ስለተጎናጸፍነው ነጻነት፣ ድል፣ በረከትና የዘላለም ሕይወት እንጂ ስለ መንግሥት የፖለቲካ አጀንዳ መሆን አልነበረበትም በማለት ቅሬታቸውን በጓዳም በይፋም ሲገልጹ ተሰምተዋል፡፡
      በበኩሌ ግን ከትንሣኤው ኃይልና ተስፋ፣ መንፈሳዊነት ተቀዳሚና ዋና አጀንዳነት ባሻገር ይህ በዓባይ ወንዝ ላይ የተጀመረውን የታላቁን የኢትዮጵያ የሕዳሴ ግድብ በማስመልከት ቅዱስ ፓትርያርኩ 40 ሚሊዮን ለሚጠጉ ኢትዮጵያውያን ምእመኖቻቸው ያስተላለፉት መልእክት የመንግሥት ፖለቲካዊ አጀንዳ ነው የሚያስብለው ምክንያት ብዙም አይዋጥልኝም፡፡
        አገራችን ከድህነት፣ ከልመና፣ ከራብ፣ ከስደት፣ ከተመጽዋችነት ወዘተ የምትወጣበትና እኛም ሕዝቦቿም ለጥ ብለን ከተኛንበት የስንፍና ፍራሽ ላይ አቅንቶ የሚቀሰቅሰን ሁለተናዊ የሆነ የትንሣኤው አዋጅ መለከት በብርቱ እንደሚያስፈልገን ጥያቄ የለውም፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ ዕለት ለአገራችንም ሆነ ለሕዝባችን ሁለተናዊ የሆነ ትንሣኤ እንደሚያሰፈልገው ማወጅ የአንድ መንፈሳዊ አባት ተግባርና ኃላፊነት እንደሆነ ነው አጥብቄ የማምነው፡፡
     ብሔራዊ ጥቅማችን፣ የአገራችንን ነፃነት፣ ልዑላዊነትና አንድነት በተመለከተ ቤተ ክርስቲያናችን እንደ ትላንትናው ሁሉ በቃልም በተግባርም የነበራትን ወሳኝ ሚናና ተሣትፎ በተመለከተ ዛሬም ድምፅዋን ከፍ አድርጋ ማሰማቷ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ትላንትና ያደረገችው፣ ዛሬም ልታደርገው የሚገባና ወደፊትም አጽንታ ልትቀጥልበት የሚገባው መልካም የሆነ ክርስቲያናዊ ባህል ነው የሚመስለኝ፡፡
      ስለሆነም የዓባይ ጉዳይ በማንም ይነሳ በማንም አንድ የማምንበት እውነት ግን አለ፡፡ ይኸውም የዓባይ ጉዳይ ብሔራዊ አጀንዳችን፣ የሁላችንም ጉዳይ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ፡፡ በአንድ የታሪክ ወቅት ታይተው የሚያልፉ የአንድ መንግሥት ወይም የአንድ ፓርቲ ጉዳይ አይደለም፡፡ ሊሆንም አይችልም፡፡ ዓባይና የዓባይ ጉዳይ ዘርን፣ ጎሳን፣ ሃይማኖትን ሳይለይ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ አንገብጋቢ ጉዳይ እንጂ፡፡

በዓባይ ጉዳይ ላይ ንጉሡ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ፣ በርካታ ኢትዮጵውያን ምሁራንና ዲፕሎማቶች ያደረጉት በርካታ የሆኑ ጥረቶችና ልፋቶች ነበሩ፡፡ የደርግ መንግሥት እንዲሁ የበኩሉን ያላሰለሰ ጥረት አድርጓል፣ ለፍቷል፡፡ ዛሬ እነዚህ መንግሥታት አልፈው ታሪክ ሆነዋል፡፡ ኢትዮጵያችን ግን ዛሬም አለች፣ ወደፊትም ትኖራለች፡፡ ዓባይ ወንዛችንም ትላንትና ነበር፣ ዛሬም አለ፣ ወደፊትም ይኖራል፡፡
      የኢህአዴግ መንግሥትም በለስ ቀንቶት ይህ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውያን ሁሉ የዘመናት እንቆቅልሽ የሆነውን ዓባይን ጉዳይ ከወረቀት አጀንዳነት ወደ መሬት በማውረድ በታሪካችን በአፍሪካ ትልቅ የሆነውን ሕዳሴውን ግድብ እውን ለማድረግ የበኩሉን ተግባራዊ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ ኢህአዴግም እንደ ትላንትናዎቹ የኃ/ሥላሴና የደርግ መንግሥታት ያልፋል፣ አንድ ቀን እንደ ሸማም ተጠቅልሎ በታሪክ ማኅፀን ውስጥ በተራው ይገባል፡፡ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውን ግን ዛሬም፣ ሁሌም ይኖራሉ!!
       ከጥንት ዘመን ጀምሮ ኢትዮጵያ ነበረች፣ ዓባይም ነበር፡፡ ኢህአዴግ ገና ሳይታሰብ፣ ሳይጸነስና ሳይኖርም በፊት ዓባይ ይፈስ ነበር፣ ዛሬም በፊታችን እየፈሰሰ አለ፣ ወደፊትም ሲፈስ ይኖራል፡፡ መንግሥት ዓባይን በየትኛውም መልኩ ቢሆን የራሱን ፖለቲካዊ አጀንዳ ማስፈጸሚያ፣ ዕድሜ ማራዘሚያና ጊዜያዊ የፖለቲካዊ ትርፍ ማጋበሻ አደረገውም አላደረገውም ዓባይን በማልማት ረገድ ግን ከአሁን ወዲያ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ወደኋላ የምንመለስበት ጉዳይ ይኖራል ብዬ አላስብም፡፡ ለምን ቢባል የዓባይ ጉዳይ በእኛ ዘመን የህልውናችን፣ የመኖርና ያለ መኖር ጥያቄ ሆኖ ከፊታችን ተድቅኗልና፡፡

ስለሆነም በዓባይ ወንዝ ላይ የሚካሄድ ማንኛውንም ዓይነት ልማትን በተመለከተ የሃይማኖት አባቶቻችንም ሆኑ ባለ ሥልጣኖቻችን ከሚነግሩን በላይ በተግባር አንደበት፣ በፍቅርና በአንድነት መንፈስ እጅ ለእጅ ተያይዘን ልንወጣው የሚገባን ታላቅ የሆነ የቤት ሥራ ገና ከፊታችን እንዳለን ነው የሚሰማኝ፡፡
 በዚህ ረገድ ደግሞ ከዓባይ ወንዝ ጋር በተያያዘ ታላቅ የሆነ ታሪካዊ ሚና የነበራትና ያላት ጥንታዊቷና ሐዋርያዊቷ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን፣ መንፈሳዊ አባቶችቻንና መሪዎቻችን እንዲሁም እኛ ክርስቲያኖች ሌላውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለ ምንም ልዩነት በማስተባበር ገና በተግባር ልንወጣው የሚገባ ትልቅ የቤት ሥራ በፊታቸው ተደቅኖ እንዳለ ይሰማኛል፡፡
ይህ አጭር መጣጥፍም ቤተ ክርስቲያናችን፣ መንፈሳዊ አባቶቻችንና መሪዎቻችን እንዲሁም እኛንም ጨምሮ ዓባይ ወንዛችንን በተመለከተ ከቃል ባለፈ በተግባር ልንወጣው የሚገባ ትልቅ የቤት ሥራ ከፊታችን ተዘርግቶ እንዳለ በቅንነት መንፈስ ለማሳሰብ ነው፡፡ በተጨማሪም ቤተ ክርስቲያናችን በቀደመ ታሪክ ዘመኗ የዓባይ ወንዝን በተመለከተ የነበራትን ወሳኝ ሚና ከታሪክ ማሕደር በመፈተሸና አሁን ካለው ወቅታዊ ሁኔታ ጋር በማያያዝ የበኩሌንና የተሰማኝና ጥቂት ነገር ለማለት ነው ብዕሬን ያነሳሁት፡፡
      ግብፃውያኑ በመንፈሳዊነት ስም ባቀነባበሩት፣ የፈጠራ ተረት ተረት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለ1600 ዘመናት በግብፃውያኑ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን የባርነት ቀንበር ውስጥ ወድቃ ስትማቅቅ እንደነበር የታሪክ መዛግብቶቻችን ይጠቁማሉ፡፡ ይህ ሐቅም የቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ አጥኚዎችና የሥነ መለኮት ምሁራኖቿም ሳይቀሩ የሚመስክሩት ነው፡፡  
     እነዚህ በአፍሪካና በመላው ዓለም ባለፉት ሺሕ ዓመታቶች ባስመዘገቡት ድንቅና ኃያል ሥልጣኔያቸው የተነሣ በዓለም መድረክ እንደ ብርቅ የሚታዩ ጥንታዊ የሆኑ ሁለቱ አገራት፣ ኢትዮጵያና ግብፅ ለዘመናት የሰው ዘር ታሪክ፣ ቅርስና ታላቅ ሥልጣኔ አሻራ ማሳያ የሆኑ ታላላቅ አገራት መሆናቸው በሰፊው ሲጠቀስ ቆይቷል፣ አሁንም ይጠቀሳሉ፡፡
        ለእነዚህ አገራት ታሪክ፣ ታላቅ ሥልጣኔና ዕድገት መነሻና እምብርት ደግሞ የዓባይ ወንዝ እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ይጠቁማሉ፡፡ ታላቁ ቅዱስ መጽሐፍም፡- ‹‹ስለ ዔደን ገነት ሲያትት የዔደን ገነትን ከከበቡትና ከሚያጠጡት ወንዞች መካከል አንዱ የዓባይ ወይም የግዮን ወንዝ መሆኑን በግልጽ አስቀምጦታል፡፡ የዘፍጥረት ጸሐፊ የሆነው እስራኤላዊው ነቢይ ሙሴ ይኽው የዓባይ ወንዝም ኢትዮጵያን መሬት ሁሉ እንደሚከብ ይናገራል፡፡››
        በክርስቲያኖች ቅዱስ መጽሐፍ ዘንድም ሆነ በእስልምና ሃይማኖት ቅዱሳን መጻሕፍት የከበረ ስምና ዝና ያላት ኢትዮጵያ ገና ከፍጥረት ማግሥት ጀምሮ የራሷን መንግስት አቋቁማ የምትኖር፣ ኃያላ፣ ባለ ታሪክና ልዑላዊት አገር እንደነበረች ይመሰክራሉ፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያ የዓለማችን ታላቅ የሆኑ የአይሁድ፣ የክርስትና እና የእስልምና ሃይማኖቶች ማእከል እንደሆነችም ይታወቃል፡፡
         ኢትዮጵያ የታሪክ፣ የሃይማኖትና የሥልጣኔ ማእከል መሆኗ ብቻ ሣይሆን ከኢትዮጵያ ምድር ፈልቆ ሱዳንና ግብፅን አቋርጦ ወደ ሜድትራኒያን ባሕር የሚገባው የዓባይ ወንዝ አያሌ ዘመናትን ላስቆጠረው ለግብፃውያኑ አፍሪካዊው ሥልጣኔ፣ መነሻና መሠረት እንደነበር የታሪክና የአንትሮፖሎጂ ምሁራን አስረግጠው ጽፈዋል፡፡
        ከእነዚህም ምሁራን መካከል አፍሪካውያኑ ስመ ጥር፣ እውቅ ምሁራንና የታሪክ ተመራማሪዎች የሆኑት ሼክ አንታዲዮፕና ኢቫን ኢቫን ሰርቲማ በጥናታቸው፡- ‹‹ግብፅ የኢትዮጵያ ሥልጣኔ የመንፈስ ልጅ›› እንደሆነች ባሳተሙት በዳጎስ ጥናታቸው በግልጽ ጽፈዋል፡፡
         ኢትዮጵያንና ግብፅን ከሚያስተሳስሩ ዋና ጉዳዮች በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው ታሪካዊው የዓባይ ወንዝ ነው፡፡ ዛሬ ዓለም ጉድ የሚሰኝበት የግብፃውያኑ ታሪክ፣ ቅርስና ታላቅ ሥልጣኔ መሠረቱ የዓባይ ወንዝ ነው፡፡ እነዛ ዓለምን ጉድ ያሰኙና በየቀኑ በብዙ ሺህ የሚቆጠር ቱሪስቶችን ቀልብና ዓይን የሚቆጣጠሩ የግብፅ ፒራሚዶች የተገነቡት የዓባይ ወንዝ ዳርቻን ተከትለው ነው፡፡
        ግብፅና ግብፃውያን ከዓባይ ውጪ የሚኖሩት ሕይወት፣ የሚተርኩት ታሪክ፣ ዓለም ሁሉ የሚያየው፣ የሚያደነቅውና ጉድ ጉድ የሚሉለት አንዳንችም ሥልጣኔም ሆነ ቅርስ የላቸውም፡፡ ዓባይ ለግብፅና ለግብፃውያን ሁሉን በሁሉ ነው ብንል ብዙም ከእውነታው የራቅን አይመስለኝም፡፡ ለዚህም ይመስለኛል በተለምዶ ‹‹ታሪክ አባት›› ተብሎ የሚጠራው ጥንታዊው ታሪክ ጸሐፊ ግሪካዊው ሄሮዱተስ Egypt is the gift of Nile ሲል በአጭር ቃል ግብፅን የገለጻት፡፡
          እናም ኢትዮጵያና ግብፅ ለዘመናት ተሳሰረው የቆዩበት እትብት የዓባይ ወንዝ መሆኑን ማንኛችንም ብንሆን እንስተዋለን ብዬ አልገምትም፡፡ ይህ በዓባይ ወንዝ አማካኝነት የተፈጠው የሁለቱ አገራት ታሪካዊ ትስስር የክርስትና ሃይማኖት ወደ ኢትዮጵያ መግባት በኋላ ደግሞ ሌላ የሃይማኖትና የታሪክ የቃል ኪዳን ውልን ፈጠረ፡፡ ከ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በኋላ የኢትዮጵያ የስልጣኔ ልጅ ናት ተብላ የተጠቀሰችው ግብፅ ዳግም ለኢትዮጵያውያን የመንፈስ እናት ሆና በታሪክ መድረክ ብቅ አለች፡፡
       ይህ ግብፃውያን በሃይማኖት ስም ከኢትዮጵያ ጋር የተሳሰሩበት የእናትነትና የልጅነት መንፈስ የፈጠረውን ወይም ያመጣውን መንፈሳዊ ፋይዳና ጥቅም፣ እንዲሁም ያሰከተለውን መንፈሳዊና አሥተዳደራዊ ቀውስና ውጥንቅጥ ለመተንተን የዚህ ጽሑፍ ዓላማ አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ እዚህ ጋር ሳይነሳ ሊታለፍ የማይገባው ነጥብ ቢኖር፡- ግብፃውያን በሃይማኖት ስም በኢትዮጵያ ላይ የጫኑት ከባድ ቀንበርና ብርቱ ክንድ ከጊዜ በኋላ መልኩን ቀይሮ ወደ ፍፁም አምባገናነዊነትና ቅኝ ግዛትነት ተቀይሮ እንደነበር ሁላችንም ቢሆን ልንዘነጋው አይገባንም፡፡
     በወርቅ፣ በእንቁ፣ በከበሩ ስጦታዎች ጋጋታ ወደ ኢትዮጵያ ይመጡ የነበሩት በጣት ከሚቆጠሩት ግብፃውያን ጳጳሳት በስተቀር የሚበዙት ከስምና ከምልክትነት ባለፈ (Puppet Fathers) ይሄ ነው የሚባል ሥራ እንዳልነበራቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ አጥኚዎች በግልጽ ይናገራሉ፡፡
        በተለይም ደግሞ ግብፅ ሙሉ በሙሉ በሙስሊም ወራሪዎች እጅ ከወደቀችበት ዘመን ጀምሮ ግብፃውያኑ ገዢዎች በጳጳሳቱ በኩል ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ የሆነ አጀንዳቸውን ለማስፈጸም በተቀነባበረና በረቀቀ ሴራ እንዲያም ሲል በኋላኛው ዘመን በጦር ኃይል አጀንዳቸውን ለማስፈጸም ወደኋላ እንዳላሉ የታሪክ ድርሳናቶቻችን በሚገባ ያስረዳሉ፡፡
          ግብፃውያኑ ኢትዮጵያ አንድ ቀን የዓባይን ወንዝ ልትገድብ ትችላለች የሚለው ስጋታቸው ቀን ከሌሊት እረፍት ስለማይሰጣቸው ዓባይን በዓይነ ቁራኛ ነበር የሚከታተሉት፡፡ እናም ኢትዮጵውያኑ በዓባይ ወንዝ ላይ ያላቸውን ማንኛውንም እንቅስቃሴ ይቃኙ ዘንድ ሁለት ሼኼዎችን ጳጳስ አድርገው በተለያዩት ጊዜያት በቃፊርነት ወደ ኢትዮጵያ ምድር ልከው እንደነበር የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ይህን የግብፃውያኑን አሣፋሪ ቅሌት በታሪክ ድርሳናት ውስጥ አስፍረውታል፡፡

በኢትዮጵያ በኩልም የዓባይ ወንዝ ለአናሳዎቹ ግብፃውያን ክርስቲያኖች የመደረደሪያና ለግብፃውያኑ ገዢዎች ማስፈራሪያ መሣሪያም በመሆን ያገለገለበት በርካታ ጊዜያቶች ነበሩ፤ በተለይም ደግሞ በዛግዌ ስርወ መንግሥትና በመካከለኛው ዘመን ታሪካችን፡፡
      በእነዚህ ሁለት ጥንታዊ እና የታላቅ ሥልጣኔ ባለቤቶች በሆኑ ሀገራት መካከል በየጊዜው ትልቅ አጀንዳ ሆኖ ይነሳ የነበረው የዓባይ ውኃ ጉዳይ ነበር፡፡ እናም በዛግዌ እና በመካከለኛው የኢትዮጵያ የታሪክ ዘመን ወደ ግብፅ የሚፈሰው የዓባይ ውኃ መጠን በቀነሰ ቁጥር ጉዳዩ አሳሳቢ እየሆነ መነሳቱን ከታሪካችን እንረዳለን፡፡
      የግብፅ ነገሥታት አልፎ አልፎ የዓባይ ወንዝ በምንጩ አካባቢ በሚደርስ ድርቅ ምክንያት የፍሳሹ መጠን የሚቀንስ መሆኑን ባለመጠርጠር፣ የኢትዮጵያውያን ውኃን የዘጉት ወይም ወደ ሌላ አቅጣጫ እንዲፈስ ያደረጉት እየመሰላቸው፣ ውኃውን ለማስለቀቅ ወደ ኢትዮጵያ ነገሥታት ዘንድ በየጊዜው መልእክተኛ ይልኩ ነበር፡፡
    ለምሳሌ ታሪክ ጸሐፊው የዓረብ ተወላጅ አል ማኪን ድርጊቱ ከሆነበት ከሁለት መቶ ዓመት በኋላ ሲጽፍ በፋቲሚድ ሥርወ መንግሥት በሡልጣን አቡ ታምሊን አል ሙስታንዚር የአገዛዝ ዘመን (1036-1094) ግብፅ የሚደርሰው የውኃ ብዛት በ1089-1090 አካባቢ ቀነሰ፡፡ በዚህ የተነሳ ሡልጣኑ ወዲያውኑ የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ አባ ሚካኤልን ከፍ ያለ ገጸ በረከት አስይዞ ኢትዮጵያውያን የተቋረጠውን የዓባይን ወንዝ እንዲለቁ ለመለመን ወደ ኢትዮጵያ እንደላካቸው አትቷል፡፡
     አል ማኪን ጉዞውም በ1092 እና በ1094 ዓ.ም ማሃል ባለው ጊዜ ውስጥ ነበር በማለት፤ የኢትዮጵያዊው ንጉሠ ነገሥት የነበረው ይምርሃነ ክርስቶስ አንድ ኮረብታ እንዲፈርስ ባዘዘ ጊዜ የውኃው መጠን በአንድ ሌሊት ሦስት ጫማ ከፍ ብሎ አደረ ሲል በመጽሐፉ በሰፊው ተርኮአል፡፡
      በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን የግብፅ ማምሉክ ሡልጣን አል ናሲር ሙሀመድ ኢብን ቃላኡን በርካታ አብያተ ክርስቲያናት የማፍረሱና ክርስቲያን የሆኑ ዜጎቹን በጽኑ የማሰቃየቱ ዜና ወደ ኢትዮጵያ ደርሶ ከፍ ያለ የኀዘን ስሜት መፍጠሩን አል ማቅሪዝ የተባለው የሞሮኮ ተወላጅ ታሪክ ጸሐፊ በወቅቱ ዘግቦአል፡፡
        በታሪኩ ውስጥ ስሙ ባይጠቀስም ከ1380-1409 ዓ.ም የነገሠው የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አፄ ዳዊት አንድ የልዑካን ቡድን ወደ ግብፅ ልኮ የዓባይን ወንዝ ፍሳሽ ወደ ሌላ አቅጣጫ በማዞር የግብፅን ሕዝብ በራብ ለመፍጀት እንደሚችል ለግብፁ መሪ በብርቱ ማስጠንቀቂያ ገልፆለት እንደነበር ጽፎአል፡፡

ኢብን ፋድል አል አልዑማሪ የተባለ አንድ የግብፅ ቤተ መንግሥት ባለሟልና ጸሐፊ ‹‹ማሳሊክ አል አብሳር ፊ ማምሊክ አል አምሳር›› ቀጥታ ትርጉሙ ‹‹የነገሥታት ምድር ቅኝት›› በሚል ርዕስ በዘመኑ ያስተዋለውን የተለያየ ነገር ጽፎ ነበር፡፡ በዚህ መጽሐፉ ሀበሾች (ኢትዮጵያውያን) ወደ ግብፅ የሚፈሰውን ዓባይን እንደሚቆጣጠሩና ለግብፅ ሡልጣን ከበሬታ ሲሉ ብቻ ውኃው እንደተለመደው ወደዚያ እንዲፈስ የሚፈቅዱ መሆናቸውን ይናገራሉ ሲልም ገልጾአል፡፡
         የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከግብፃውያኑ መንፈሳዊ ባርነትና ፖለቲካዊ ሴራ ትላቀቅ ዘንድ የኢትዮጵ መንፈሳዊ አባቶችና ንጉሡ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ባደረጉት ያላሰለሰ ጥረት ቤተ ክርስቲያኒቱ ከ1600 ዓመታት መራር የግብፃውያን ቀንበር ተላቃ የራሷን መንፈሳዊ መሪ ካገኘች አምሳ ዓመታት ያህል ተቆጥረዋል፡፡ ምንም እንኳን ቤተ ክርስቲያኒቱ ከግብፃውያን አገዛዝ ብትላቀቅም ሁለቱን አገራትን በሚያስተሳስራቸው በዓባይ ጉዳይ ላይ አሁንም ድረስ ግብፃውያኑ ክርትስቲያኖች ሆኑ ሙስሊሞች ያላቸው አቋም በዓባይ ላይ ለምን ሲባል ጥያቄ ታነሳላችሁ የሚል ዓይነት ጠንካራና ግትር ነው፡፡

ግብፃውያኑ ኢትዮጵያ በዓባይ ላይ ያላትን የመጠቀም መብት በተመለከተ ሲነሳ ሁሌም ዓይናቸው ደም ነው የሚለብሰው፣ ይህ ቅናታቸውና ቅንነት የጎደለው ጭፍንነታቸው ከዓባይ አልፎም ኢየሩሳሌም ድረስ ሣይቀር እንኳን ተሻግሮ በኢትዮጵያውኑ ጥንታዊ ይዞታ በሆነው በዴር ሱልጣን ገዳም ላይ ያሳረፈውን ብርቱ ጥላቻና ክንድ አይተናል፣ ታዝበናልም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ምናልባት በሌላ ጊዜ ሰፋ አድርጌ እጽፍ ይሆናል፡፡
    ግብፃውያኑ እንቀድሞው ዘመን በመንፈሳዊነት ስም ኢትዮጵያንም ሆነ የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ዳግም በቅኝ ገዢነት መንፈስ ይዘው ዓላማቸውን ለማስፈጸም ምንም ዓይነት ዕድል እንደሌላቸው ካወቁ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ የዓባይ ውኃን በተመለከተ ኢትዮጵያ ፍትሐዊ በሆነ መንገድ የመጠቀም መብቷ ሙሉ በሙሉ የተጠበቀ እንደሆነ ግብፅና ግብፃውያን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተረዱት መጥተዋል፡፡ እንደቀደመው ዘመን በማስፈራራትና በዲፕሎማሲያዊ ጫና የዓባይን ውኃ ከመጠቀም የሚከለክሉበት ምክንያት እንደሌላቸውም እርግጥ ሆኗል፡፡
     አሁን አሁን ከግብጽ እየወጡ ያሉ መረጃዎችና ዜናዎች እንደሚያሳዩትና በቅርቡ ፕሬዝዳንት ሙርሲም እንዳረጋገጡት፡- ‹‹ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የምታካሂደው ልማት ግብፅንና የተቀሩት የተፋሰሱን አገሮች እስካልጎዳ ድረስ ደስተኞች ነን፡፡ ከጎናችሁም እንቆማለን ሲሉ እየተደመጡ ነው፡፡›› ይህ ከልብና ከቅንነት የመነጨ ከሆነ መልካም የሚባል እርምጃ እንደሆነም የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብም እየገለጹ ናቸው፡፡

ሕዝባችን ለዘመናት ከተጣበው ድህነት፣ የመከራ፣ ሰቆቃና የስደት ሕይወት ተላቆ በአገሩና በሕዝቡ መካከል ተረጋግቶና እፎይ ብሎ መኖር እንዲችል ሰላም፣ ዲሞክራሲ፣ ፍትሕ፣ መልካም አስተዳር፣ ልማት ወዘተ በጣሙን አስፈላጊ ናቸው፡፡
       መንፈሳዊ ተቋማትና መሪዎቻቸው በአገራችን ሰላም፣ ዲሞክራሲ፣ ፍትሕ፣ መልካም አስተዳደር፣ ዕድገትና ብልጽግና እንዲሰፍን የራሳቸው የሆነ ከፍተኛ ድርሻና ተሣትፎ አላቸው፡፡ በቅርቡም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መሪ የሆኑት ፓትርያርክ አቡነ ማቲያስ በዓባይ ወንዝ ላይ ስለተጀመረው ልማት፣ በዴር ሱልጣን ገዳማት ጉዳይና እንዲሁም በቤተ ክርስቲያኒቱ የተንሰራፋውን ሙሰናና ሙሰኞችን በተመለከተ ያስተላለፉት መልእክት ብዙዎችን ደስ አሰኝቷል፡፡
       የቅዱስነታቸው ይህ ቃል ከቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ብፁዓን አባቶቻች ጋር በመተባበር ተግባራዊ ሆኖ የምናይበትን ጊዜ መንፈሳዊ ልጆቻቸው በታላቅ ጉጉት እንጠብቃለን፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስለተንሰራፋው ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ የሞራል ዝቅጠትና ውድቀት፣ እንዲሁም የመንፈሳዊነት ሕይወት መታጣት ብዙ የተባለለት ያረጀና ያፈጀ ጉዳይ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ችግሩን ከማውራት በስተቀር ይህን ነው ተብሎ ሊነሣ የሚችል ተግባራዊ እርምጃ እስካሁን አልተወሰደም፡፡
      እንዲሁም ቅዱስ ፓትርያርኩ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ያጣበቡትን ነጋዴዎችና ዘራፊዎች ያለ ምንም ቅደም ሁኔታ በማስወጣት መንፈሳዊና ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰዱና፣ በተጨማሪም የተሠጣቸውን መንፈሳዊ የሆነ ኃላፊነት ዘንግተው ፍጹም መንፈሳዊ ባልሆነ አካሄድ በሥጋዊና በዓለማዊ ምኞት ተጠልፈው፣ ያልደከሙበትንና ያለፉበትን ሀብትና ገንዘብ የማከማቸት ሥራ ውስጥ ተዘፈቁ የቤተ ክርስቲያኒቱን ኃላፊዎች ተገቢውን ሥርዓት እንዲይዙ እንደሚያደርጉ ያስተላለፉት መልእክት በእውነት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡
       ቅዱስ ፓትርያርኩ በመንፈሳዊ ቅንአትና ቆራጥነትና እንዲሁም ባላቸው ከፍተኛ መንፈሳዊ ኃላፊነትና እረኝነት በቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ አገልጋዮችና ተከታዮቿ መካከል ለአገርና ለወገን የሚቆረቆር፣ የተሠጠውን ግዴታውንና ኃላፊነቱን በታማኝነት የሚወጣ፣ በወንጌል የእውነት ቃል የታነጸ መልካም ዜጋና ትውልድ ለመፍጠር ከቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ አባቶች ጋር የበኩላቸውን ጥረት በማድረግ ተወዳጅና ተከባሪ አባት እንዲሆኑልን እመኝላችኋለሁ፡፡
      በተጨማሪም ቅዱስ ፓትርያርኩ የዓባይን ውኃ በፍትሐዊነት የመጠቀም መብታችንን በተመለከተ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከግብፅ ጋር የነበራትንና አሁንም ያላትን የረጅም ዘመን ግንኙነትና እንዲሁም ታሪካዊ ትስስር ከግምት ውስጥ በማስገባት የጀመሩትን እንቅስቃሴ ይቀጥሉበታል የሚል ጽኑ ተስፋ አለኝ፡፡
       ከግብፃውያን ጋር ለረጅም ጊዜያት አተካራ በገባንበትም በዴር ሱልጣን ገዳማችን ጉዳይን በተመለከተም ፓትርያርኩ በኢየሩሳሌም ለረጅም ዓመታት በመቆየታቸው ያለውን ሃይማኖታዊ ሆነ ፖለቲካዊ ችግሩን በሚገባ ያውቁታልና ቅዱስ ሲኖዶስንና መንፈሳዊ ልጆቻቸውን በማስተባበር ሰፊ የሆነ ሥራን ሊሠሩ እንደሚችሉ መንፈሳዊ ልጆቻቸው ተስፋ እናደርጋለን፡፡
     በቀጣይ ጽሑፌ በዴር ሱልጣን ገዳም ዙሪያ ያለውን ታሪክና የግብፃውያኑን ሴራ ከወቅታዊው የዴር ሱልጣን ገዳም ጉዳይ ጋር አያይዤ ለመጻፍ ከወዲሁ ቃል በመግባት ልሰናበት፡፡

ሰላም! ሻሎም!