Wednesday, December 31, 2014

በመንበረ ፓትርያርኩ ቅ/ማርያም ገዳም በሚሊዮኖች የሚገመት ገንዘብ መመዝበሩ ተገለጸ

  
 (አዲስ አድማስ፤ ታህሣሥ 29/2007)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የፓትርያርኮች መንበር (መንበረ ፕትርክና) በኾነችው ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብና ንብረት በአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች መመዝበሩን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ጥቆማው የቀረበው፣ የገዳሟ ማኅበረ ካህናትና የልማት ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብና የንብረት አሰባሰብ በተመለከተ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲዘረጋ የገዳሟ ልማት ኮሚቴ የበላይ ጠባቂ ለኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ባቀረቡት ማመልከቻና ሪፖርት ነው፡፡

   የቤተ ክርስቲያኒቱ መተዳደርያ ቃለ ዐዋዲና ደንቡን መሠረት አድርጎ በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ መመሪያ የካህናቱን፣ የምእመናኑንና የእያንዳንዱን ሠራተኛ የሥራ ድርሻና ተጠያቂነት በግልጽ ማስቀመጡን የጠቀሱት ማኅበረ ካህናቱ÷ የገዳሟን ገንዘብና ንብረት የመቆጣጠርና የመከታተል መብታቸው በአስተዳደሩ ሓላፊዎች ተነፍጓቸው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና የንብረት ቁጥጥር ለማድረግ ሳይችሉ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ገዳሚቷ በየዕለቱና በየበዓላቱ ከምእመናን በስጦታና በስእለት የምታገኘው ሀብትና ንብረት ከራስዋ አልፎ ለተቸገሩ ገዳማትና አድባራት የሚተርፍ ቢኾንም ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው የአስተዳደሩ አሠራርና በሰበካ ጉባኤው የቁጥጥር ማነስ ሳቢያ የገቢ አቅሟን ለማጎልበት ከዓመታት በፊት የወጠነችው ኹለ ገብ ሕንፃ ግንባታ ከመጓተቱም በላይ ለሀገረ ስብከቱ መከፈል ለሚገባው ውዝፍ ዕዳ መዳረጓን ካህናቱ አስታውቀዋል፡፡ 

  በገንዘብ አያያዝና በንብረት አሰባሰብ ረገድ በአስተዳደሩ እየተባባሰ የመጣው ሙስና እንዲወገድና ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የተስተጓጎለው የልማት ሥራ እንዲቀላጠፍ በኅዳር ወር አጋማሽ ፓትርያርኩን መጠየቃቸውንም አመልክተዋል፡፡

ከገዳሚቷ የልማት ኮሚቴ ጋራ በመቀናጀት የቀረበውን የማኅበረ ካህናቱን ማመልከቻ መነሻ በማድረግ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በሰጡትና በረዳት ሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጻሚ በኾነው መመሪያ፤ የገዳሟን የገንዘብና ንብረት አሰባሰብ የሚከታተል አምስት ካህናት ያሉት የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ ኮሚቴ ኅዳር 18 ቀን መቋቋሙ ታውቋል፡፡ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ማግሥት አንሥቶ ኅዳር 19 እና 22 ቀናት ባካሔደው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ የተገኘውን ከብር 826‚000 በላይ ገቢ ጨምሮ ከንብረት ሽያጭና በሞዴል 30 የተሰበሰበውን በማካተት ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ አጠቃላይ ገቢ በአንድ ወር ብቻ መመዝገቡ ተገልጧል፡፡ 

በካህናቱ አስፈጻሚነት በአንድ ወር የተወሰነ ቆጠራ ብቻ ይህን ያኽል ገቢ መመዝገቡ፣ የገዳሟ ገቢ ‹‹የግለሰቦች መደራጃ ኾኖ መኖሩን የሚያሳይ ነው፤›› ብለዋል - ማኅበረ ካህናቱ፡፡ አያይዘውም ለሀገረ ስብከቱ መከፈል የሚገባው የኻያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ ሳይፈጸም አኹን በካዝና ያለው ብር 129‚000 ብቻ እንደኾነ በመጥቀስ ገዳሟ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ስትመዘበር እንደኖረችና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ኾነ ሀገረ ስብከቱ በየደረጃው ማግኘት የነበረባቸውን የፐርሰንት ፈሰስ ማጣታቸውን ስለሚያረጋግጥ ‹‹የአስተዳደር ሠራተኞቹን ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡  

    እንደ ማኅበረ ካህናቱ እምነት፣ የገዳሟ ገቢ ለአስተዳደር ሠራተኞቹ ምዝበራ የተጋለጠው የተጠናከረ ሰበካ ጉባኤ ባለመኖሩ ነው፡፡ አኹን ያለው የገዳሙ ሰበካ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው መሠረት፣ የገዳሙን የሥራ ክፍሎች አገልግሎት አፈጻጸም በወቅታዊ የክንውን መግለጫዎች የመከታተል፣ የሒሳብ አያያዙንና የንብረት እንቅስቃሴውን ጊዜውን ጠብቀውና እንዳስፈላጊነቱ በሚቀርቡ ሪፖርቶች የመቆጣጠር ሓላፊነቱን ካለመወጣቱም በላይ ‹‹ገዳሚቷ ችግር ላይ ስትወድቅ ዝም ብሎ የኖረ ተባባሪ›› በመኾኑና የሥራ ጊዜውም በማለፉ ጠንካራና ሓላፊነት በሚሰማው ሰበካ ጉባኤ እንዲተካ መመሪያ እንዲሰጥላቸው፣ ተጀምሮ የቆመው ልማት እንዲቀጥል፣ የገዳሟ ገቢና ወጪም በውጭ ኦዲተሮች እንዲጣራ ማኅበረ ካህናቱ ፓትርያርኩን ጠይቀዋል፡፡ ያለማኅበረ ካህናቱና ማኅበረ ምእመናኑ ፈቃድ ጊዜው በሀ/ስብከቱ ውሳኔ ተራዝሟል የተባለው ሰበካ ጉባኤ፣ በቆጠራ ኮሚቴው የተሰበሰበውን ከብር 440‚000 በላይ የገዳሚቷን ከፍተኛ ገንዘብ ያለተቆጣጣሪ ወጪ ማድረጉን ካህናቱ ገልጸው፣ ሕጋዊ ሰበካ ጉባኤ ሳይቋቋም ቀጣይ ቆጠራ እንደማይካሔድ አስጠንቅቀዋል፡፡

  በገዳሚቷ አስተዳደር ውስጥ ሙስናዊ ጥቅማቸው የተነካባቸው ናቸው ያሏቸው ግለሰቦች፣ የቆጠራ ኮሚቴውን ለማፍረስ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንና ግንቦት ሰባት ናችኹ፤ ምርጫውን ለማወክ ትንቀሳቀሳላችኁ፤ ወደ ሌላ ደብር እናዘዋውራችኋለን›› በሚል ከሚያደርሱባቸው ዛቻና ማስፈራራት እንዲቆጠቡ አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡የማኅበረ ካህናቱንና የልማት ኮሚቴውን ጥያቄ ተከትሎ ፓትርያርኩ በሰጡት መመሪያ÷ ሰበካ ጉባኤው የሥራ ክንውን ሪፖርት ካቀረበ በኋላ የአዲስ ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሔድ፣ የገዳሚቷ ገቢና ወጪ ሒሳብ በአስቸኳይ በውጭ ኦዲተር ተከናውኖ እንዲቀርብ፣ የቆጠራ ኮሚቴው የአስተዳደሩን ዕውቅና አግኝቶ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በ48 ሚልዮን ብር ወጪ በኹለት ምዕራፎች የተጀመረውና የተጓተተው የባለስድስት ፎቅ የአገልግሎትና ኹለገብ ሕንፃ ግንባታ የብቃት ማረጋገጫ ባለው አካል ክትትል እንዲፋጠን ማዘዛቸው ታውቋል፡፡

Tuesday, December 30, 2014

አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋዩ ማነው?



     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ስንት ጠንቅዋይ እንዳለ ሰፊ ጥናት ተደርጎ ነበር። በተገኘው ጥናት የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ቁጥሩ እጅግ አስደንጋጭ ነው። ጥንቆላን መደበኛ ሥራቸው አድርገው ባለጉዳይ አዲስ አበቤዎችን በማስተናገድ ላይ የተሰማሩ 4000 /አራት ሺህ/ ገደማ ጠንቅዋዮች መኖራቸውን የተደረገው የዳሰሳ ጥናት ያረጋግጣል። 4000 ሺህ ገደማ ጠንቅዋይ በአዲስ አበባ ብቻ መገኘቱ እግዚኦ መሐረነ! የሚያሰኝ ነው። በመላ ሀገሪቱ በአጠቃላይ ቢጠናማ ሚሊዮን ጠንቅዋዮች ይኖራሉ ማለት ነው።
  አንዳንዶች «ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ናት» ሲሉ አያፍሩም። ቀላል ቁጥር የማይባለውን ጠንቅዋይ ስንመለከት ለጠንቋዮቹስ ደሴት የማትሆንበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ደግሞም በተደረገው ጥናት እንደተመለከተው አብዛኛዎቹ ጠንቋዮች ክርስቲያን ነን ባዮች ናቸው። ስለዚህ «የክርስቲያን ደሴት ናት» ባዮች ጠንቋይ ክርስቲያኖችንም ጨምረው ከሆነ አባባላቸው እውነትነት ሊኖረው ይችላል። ነገር ግን ክርስቲያን መሆን ማለት ምን ማለት ነው? በሚለው ጉዳይ ላይ ጥያቄን ያስነሳል።  ጠንቅዋይ ክርስቲያኖች በሞሉባትና ክርስቲያን ነን የሚሉ የጠንቅዋይ አገልግሎት ተጠቃሚዎች በበዙባት ኢትዮጵያክርስትናና የክርስትና ደሴት ማለት ከስም ባለፈ ትርጉም የለውም ማለት ነው። በአጭር ቃል ክርስትና ተነገረባት እንጂ አልተኖረባትም ማለት ነው።
ያልተኖረበት ክርስትና ደግሞ ሙት ነው።

«በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው» ኤፌ 2፤1-2

ሐዋርያው ጳውሎስና በርናባስ በቆጵሮስ ደሴት ጫፍ ላይ ወደምትገኝ ጳፉ/ ፓፎስ/ ከተማ በገቡ ጊዜ በርያሱስ የሚባል አንድ አይሁዳዊ ጠንቅዋይና ሐሰተኛ ነብይ አግኝተው ነበር። /የሐዋ 13፤6 / ይህ በርያሱስ /1/  የተባለው ሰው በሃይማኖት አይሁዳዊ በተግባሩ ግን ጠንቅዋይ ነው።  ይህ ሰው የሚያሳስተው የአገሩን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የሚመራ አገረ ገዢውን ጭምር ነበር።  በጠንቅዋይ የጥንቆላ ጥበብ የምትመራ አገር ምን ልትመስል እንደምትችል ለመገመት አይከብድም።  በሌላ ስምም «ኤልማስ» /2/ የተባለው ይህ ጠንቅዋይ አገረ ገዡን መቆጣጠር ማለት አገሪቱን በራሱ የመንፈስ ግዛት ስር ማስተዳደር ማለት በመሆኑ  የጳውሎስንና የበርናባስን የወንጌል ስብከት እንዳይሰማ አጥብቆ ሲቃወም እናያለን።  መንፈሱ እንዳይገለጥና እውነት እንዳይታወቅ አጥብቆ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ ሕዝቡን በመንፈሱ ባርነት ስር ከማስገባት ባሻገር መሪዎችንም አጥምዶ መያዝ ዋና ሥራው ነው። መሪዎች የያዙት ወንበር በሥራቸው ባለው ሕዝብ ላይ የሚፈልገውን ተጽዕኖ ለማሳረፍ እንደሚጠቅመው አሳምሮ ያውቃል። ልክ ማኅበረ ቅዱሳን የሲኖዶስ አባላት የሆኑ ጳጳሳትን በራሱ ፈቃድ ስር መቆጣጠር ማለት የሲኖዶስን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት እንደሆነ ገብቶት እንደሚሰራው ማለት ነው። የሲኖዶሱን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መቆጣጠር ማለት ነው።

 ይህ በርያሱስ በተባለው ሰው ላይ ያደረው የጥንቆላ መንፈስ  አገረ ገዢው ወደነጳውሎስ የእውነት ቃል ልቡን እንዳይመልስ አጥብቆ በተቃወመ ጊዜ «ጳውሎስ የተባለው ሳውል ግን በመንፈስ ቅዱስ ትኩር ብሎ ተመለከተውና አንተ ተንኰል ሁሉ ክፋትም ሁሉ የሞላብህ፥ የዲያብሎስ ልጅ፥ የጽድቅም ሁሉ ጠላት፥ የቀናውን የጌታን መንገድ ከማጣመም አታርፍምን?» ሲለው እንመለከታለን።( የሐዋ 13፤10 )

    ስለሆነም ጠንቅ ዋዮችና አሰተኛ ነብያት ሁሉ ተንኰልና ክፋት የሞላባቸው፤ የዲያብሎስም ልጆች፤ የጽድቅ ሁሉ ጠላት፤ ቀናውን የጌታን መንገድ የሚያጣምሙ ናቸው እንጂ ክርስቲያን በመሆናቸው ወይም በመሰኘታቸው ወይም ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች በግልጥም በስውርም የእነሱን አገልግሎት ተጠቃሚዎች ሁሉ የሚባሉት ክርስቲያን ሳይሆን የክፋቱ መንፈስ ተካፋዮች ነው።  እንዲያውም ከአሳቹና ከተቃዋሚው መንፈስ አገልግሎት ማግኘት አይደለም! ሰላም የሚላቸው ቢኖር ከክፉ ሥራቸው ተካፋይ የመሆን ያህል ነውና ሁሉም በመንፈሱ ተይዘዋል ማለት ይቻላል። 

   በዚህ መልኩ ከ4000 የአዲስ አበባ ከተማ ጠንቅዋዮች አገልግሎት የጠየቁ ተራ ሕዝብና ትላልቅ ሹማምንት ስንት ይሆኑ ይሆን? በቀላል ስሌት እያንዳንዱ ጠንቅዋይ በቀን ዐሥር ሰው ቢያስተናግድ 4000 ሲባዛ በ10= 40,000 /አርባ ሺህ/ ሰዎች በየቀኑ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ሆነዋል ማለት ነው። በወራትና በዓመታት ስናሰላው በተደጋጋሚ ሊሄዱ የሚችሉትን የስሌት ግምት ቀንሰን ሚሊዮን ተጠቃሚዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ በቀላል ሎጂክ ማወቅ ይቻላል። ይህ እንግዲህ እንደነታምራት ገለታ ያሉትን በቀን ውስጥ በሺህ ሰው የሚያንጋጉትን ከፍተኛ ቁጥር ሳይጨምር መሆኑን ልብ ይበሉ። እያንዳንዱ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ በሕይወት ዘመኑ ቢያንስ አንድ ጊዜ ከጠንቅዋይ፤ ከቅጠል በጣሽ ደብተራ፤ ከአስማትና ከክታብ ፀሐፊ ዘንድ ሊሄድ እንደሚችል አመላካች መረጃ ነው። እናስ? አገሪቱን የተቆጣጠረው ይህ መንፈስ እግር ተወርች አስሮ የግዛቱ ምርኮኛ በማድረግ የእግዚአብሔር ክብር እንዳይገለጽ ተግቶ እየሰራ አይደለምን?  
   የቀናው የጌታ መንገድ እየተጣመመ እውነት የማይገለጠው ወይም የተገለጠው የሚዳፈነው በዚህ የክፋት መንፈስ የታሰረ ሕዝብ በመኖሩ ምክንያት መሆኑን መካድ አይቻልም።  የክፋት ሠራዊት ራሱ፤ አራዊት ማኅበር ያቋቋመው ቀናው መንገድ እንዳይገለጥ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ መሆኑንም ልብ ማለቱ ጠቃሚ ነገር ነው።

   ሰርግዮስ ጳውሎስ የተባለው አገረ ገዢ ሳይቀር ከጠንቅዋይ መንፈስ ጋር ኅብረት ያደርግ እንደነበር ማሳየቱ የሚጠቁመን ነገር ሹማምንትም የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች መሆናቸውንና ከዚህ መንፈስ ምሪት በሚያገኙት ምክር የሚሰሩት ሥራ ምን ሊሆን እንደሚችል ያሳየናል።  ከዚያም ባሻገር ጠንቅዋዮች የባለሥልጣን ከለላ እንዲያገኙና በአገሪቱ ውስጥ ያለሥጋት የመንፈስ ሥራቸውን እንዲፈጽሙ እድል የሚሰጣቸው  እንደሆነ ለመገመት  ይቻላል።  በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የዚህን ያህል ቁጥር ያላቸው ጠንቅዋዮች የመብዛታቸው ምክንያትም ይኸው ነው።  የአዲስ አበባ ጠንቅዋዮች እንዲስፋፉ እድልና ጊዜን የሰጣቸው የመንፈሱ አገልጋዮች መኖራቸው እንጂ እግዚአብሔር ደስ ስለተሰኘና ሰለፈቀደላቸው አይደለም። የቤተ ክህነቱ ጠንቅ-ዋይ ማኅበርም ቢሆን የመቆየት እድል ያገኘው እሱ እንደሚለው እግዚአብሔር ስላቆመው ሳይሆን የጠንቅ-ዋይ ሰላባ የሆኑ የቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አመራሮች አብረው ለመንፈሱ አሰራር ስለተሰለፉ ብቻ ነው። እግዚአብሔር ለክፉው መንፈስ አሠራር ፈቃደኛ የሆኑትን ሰዎች ለፈቃዳቸው አሳልፎ በመስጠት የሚተዋቸው ሰዎች ማድረግ ለሚፈልጉት ነገር ነጻ ፈቃድ ያላቸው ፍጥረቶች ስለሆኑ ብቻ ነው።

   የዚህን ያህል ቁጥር ባለው ጠንቅዋይና አስማተኛ ደብተራ ተገልጋዩ ማነው? ብለን ብንጠይቅ በአብዛኛው እምነት አለን በሚሉ ክርስቲያኖችና ሌሎች ሰዎች መሆናቸውም በተደረገው ጥናት ላይ ተመልክቷል። ከዚህም ውስጥ ሰፊውን ቁጥር የያዙት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ናቸው። የዚህ ታሪክ ፀሐፊ ከአንድ የጥንቁልና አገልግሎት ተጠቃሚ ከነበረ ሀብታም ሰው ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው አዋቂ ከተባለ ባለዑቃቢ የተሰጠው ትእዛዝ « የልደታን ታቦት በደባልነት ከዚህ ቤተ ክርስቲያን አስገብተህ፤ ካህናቱን እየደገስህ አብላ፤ በየዓመቱም ዝክር ዘክር ተብለኻል» በማለት ቃል ያስገባው ሲሆን ይህንኑ ተግባር እስካሁን ሳያቋርጥ እየፈጸመው የመገኘቱ ጉዳይ ነው። ለዚህ ሰው ደባል ታቦት ፈቃጅነት፤ በአገልግሎት ሰጪነት የሚያገለግል ካህን፤ በንግሥ በዓል ላይ የሚሰማራው ሰጋጅና አንጋሽ ሕዝብ  እግዚአብሔርን እያከበረ ቢመስለውም የመንፈሱ አሠራር በሃይማኖት ከለላ ምን ያህል የነፍስ ወረራ እንደሚፈጽም ከሚያሳይ በስተቀር ከእግዚአብሔር ሃሳብ ጋር አንዳችም ግንኙነት የለውም። በተለይም በአዲስ አበባ ሀብታም የሆኑ አፍቃሬ ደብተራ ሰዎች የእገሌን ታቦት እያሉ በስማቸው ደባል አድርገው በማስገባትና በመትከል ላይ ተጠምደዋል።

 ከዚህም በላይ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ የሚፈልጉትን ነገር በሚፈልጉበት ደብር እያስነገሱ ሕዝቡን ለስውሩ መንፈስ አገዛዝ አሳልፈው መስጠታቸው ሳያንስ ከሰይጣን ጋር የተዋርሶ ኪዳን የፈጸሙ፤ ከጠላት መከላከያ የሚሆን ዐቃቤ ርዕስ የሚል አስማትና ድግምት ጭምር እንደሚይዙ ይነገራል። የጠላት መንፈስ ባለበት ሁሉ አድማ፤ ሁከት፤ ብጥብጥ፤ ክርክር፤ ጥል፤ ጭቅጭቅ፤ ቡድንተኝነት፤ ዝሙት፤ ሙስና መኖሩ በራሱ የክፉው መንፈስ ብርታት ምን ያህል አካባቢውን እንደወረረ ማሳያ ነው።  የመንፈስ ፍሬ የሆኑቱ ምልክቶች የማይታይባቸውም ለዚህ ነው።  እነዚህን ምልክቶችን አይቼባቸዋለሁ ብሎ ምስክርነት ሊሰጥ የሚችል ከተገኘ በእውነት ድንቅ ነው።   
                          
«የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው» ገላ5፤22

 በግልጥ የሚታወቁና ጥንቆላን የሚጠቀሙ ጳጳሳት እንዳሉ በመረጃ አስደግፎ ሥራቸውንና ቦታቸውን ጠቅሶ መናገር ይቻላል። ከብዙዎቹም አንዱ በናይሮቢ ከተማ የሚኖሩ አንዕስት ኢትዮጵያውያትን በስመ «አውቅልሻለሁ፤ አጠምቅሻለሁ» ሰበብ የአስማትና የቅጠላ ቅጠል ጭማቂ እየነከረ የሚያደነዝዛቸውና ኀፍረተ ሥጋቸውን ሳይቀር የሚዳብስ ጠንቅዋይ ጳጳስ የክፉው መንፈስ ተካፋይ ካልሆነ የቅዱስ መንፈስ ማደሪያ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው? ከዚያም በዘለለ ሁኔታ ውስጥ የድርጊቱ ሰለባ  ስለመኖራቸው በሀዘን የሚናገሩም ተገኝተዋል። የአገራችን ሰው ጉዳዩን ማውጣት ሲከብደው «ውስጡን ለቄስ ይላል» እኛም ውስጡን «ወኅቡረ ዐለወ» ለሚባለው ለሲኖዶስ ትተነዋል።

    ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደተቋም በአዋጅ የምትቃወመውና የምታወግዘው ብትሆንም በየትኛውም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጥንቆላ፣ ለአስማት፤ ለምትሃት፤ ለድግምት፤ ለመርበብት፤ ለተዋርሶና ለተመሳሳይ የመናፍስት አሠራር ያልተጋለጠ ሰው ማግኘት እጅግ አዳጋች ነው። ወይ ሰርቷል፤ አለያም አሰርቷል ወይም አይቷል፤ አለያም ከብጥስጣሽ ክታባት ጋር በሆነ አጋጣሚ ተገናኝቷል። ይህ በሕይወት ገጠመኝ ያየነው የማይታበል እውነት ነው። ይህ ልምምድ ሠርጎ ከገባ በኋላ ውስጥ ለውስጥ ነግሶ እንደቆየ ዘመናትን አሳልፏል። በአጠቃላይ ሲታይ አዲስ አበባ ትሁን መላ አገሪቱ በአንድም፤ በሌላ መንገድም የክፉ መንፈስ እስረኛ ሆናለች። «ለሞት መድኃኒት አለን» ከሚለው ማስታወቂያ በስተቀር ለቡዳ፤ ለመጋኛ፤ ለዛር፤ ለውቃቤ/ዐቃቤ/፤ ለሚያስቃዥ፤ ለሟርት፤ ለገበያ፤ ለመስተፋቅር፤ ለእጀ ሰብእ በደፈናው ለሌሎችም ችግሮች ፍቱን መፍትሄ እንሰጣለን» የሚሉ ማስታወቂያዎች ከተማውን ያጠለቀለቁት የክፉው መንፈስ አሠራር ተንሰራፍቶ በአገሪቱ የመንገሱ ምልክት ነው።  

  በአንድ ወቅት ጌታቸው ዶኒ የተባለ ሰው ቡዳ የበላውን መኪና ከቤተ ክርስቲያን ግቢ አስቁሞ ጸበል ሲረጨው ታይቶ ነበር። አሁን መኪናን ቡዳ የሚባለው እንዴት ነው? ድሮ ሰው ነበር ተበላ የሚባለው በዚህ ዘመን ደግሞ መኪናውንም ሳይቀር የሚቀረጥፍ ጥርስ ያለው ቡዳ ተፈጥሯል። ኢትዮጵያ የመኪና አደጋ የተበራከተባት ቡዳ እየበላባት ይሆናል። የትራፊክ መሥሪያ ቤትም የመኪና አደጋውን ለመቀነስ ጸበል እየገዛ መኪኖችን መርጨት አለበት ማለት ነው። የጌታቸው የግብር ታናሽ ወንድም የሆነው ግርማ ወንድሙ ደግሞ የሀገር ቤቱን ቡዳ ገድሎ የጨረሰ ያህል አበሾችን ብቻ የሚከተለውን ቡዳና እጀ ሰብእ ለመግደል ባህር ማዶ ሄዶ የማርከሻ ጸበል እየረጨሁ ነው ይለናል።  የነ ግርማ ወንድሙ ክህነት ሰጪ፤ ሻሚ ሸላሚዎች ደግሞ የመንፈሱ ደጋፊዎች እነዚያው ጳጳሳት መሆናቸውን ስንመለከት የክፉው መንፈስ ኃይል ምን ያህል ስር እንደሰደደ ያሳያል።

ጥንቆላና ቀጠል በጣሽ ደብተራ በአዲስ አበባ ምን እየሰራ እንዳለ የሚያሳይ «ፔሌማ» በሚል ርዕስ የተሠራ ፊልም የድርጊቱን ስፋት በሰፊው ያትታልና ቢመለከቱ ጥሩ ግንዛቤ ሊያገኙ እንደሚችሉ ይገመታል።

እግዚአብሔር አምላክ «አስማተኛም፥ መተተኛም፥ በድግምት የሚጠነቍልም፥ መናፍስትንም የሚጠራ፥ ጠንቋይም፥ ሙታን ሳቢም በአንተ ዘንድ አይገኝ» በዘዳ 18፤11 ላይ ቢናገርም በዚህ ዘመን ከመገኘት ባለፈ መደበኛ ሥራ ሆኗል። ስለዚህም የእግዚአብሔር ረድዔትና በረከት ርቆናል።

እርስዎ አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋይ ማነው ይላሉ? እንቅፋት መታኝ ፤ ጥቁር ውሻ አቋረጠኝ፤ እብድ ለከፈኝ፤ ሲቀዳ ያልሞላ አልጠጣም፤ በቀኝ አውለኝ፤ ኮከቤ አይወደውም፤ ሴጣኔን አታምጣብኝ፤ ዓይነ ጥላ አለበት፤ ገፊ፤ ከማያቁት መልዓከ የሚያውቁት ሴጣን ይሻላል ወዘተ ብሂሎች እርስዎ ብለው ወይም ያለ ሰው ሰምተው ያውቃሉ? እነዚህ አባባሎች ምንን ያመለክታሉ? እስኪ ይመርምሯቸው!
-----------------------------
/1/ በርያሱስ ማለት በአረማይክ ቋንቋ የኢያሱ ልጅ ማለት ነው።
/2/ ኤልማስ ማለት ጥበብ ማለት ነው።

Saturday, December 20, 2014

“ ቅ/ ሲኖዶሱ በአድባራት ሓላፊዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ነው ” /ፓትርያርኩ/


  (  አዲስ አድማስ ) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ‹‹የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና በሰጠችው ማኅበር ላይ ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ባላቸው አንዳንድ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራት አስተዳዳሪዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አፈጻጸም ‹‹ሕገ መንግሥቱንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር ነው›› በሚል ፓትርያርኩ ማገዳቸው ተገለጸ፡፡
ፓትርያርኩ ባለፈው ኅዳር 30 ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ ‹‹አፈጻጸሙ እንዲቆይ›› በማለት ያገዱት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት በተካሔዱ ጉባኤዎች÷ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል፤ ይህም አነጋገር ጉባኤውን ቅር አሰኝቷል፤›› ያላቸው የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ በመንበረ ፓትርያርክና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሾች በተካሔዱት ስብሰባዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም አስተዳደርና ወቅታዊ ችግሮች የተመለከቱ የጉባኤተኞች አስተያየቶችና ሐሳቦች መቅረባቸውን በደብዳቤያቸው ያስታወሱት ፓትርያርኩ፤ ተሰብሳቢዎቹ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ መናገራቸውና አሉ የተባሉ ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ መጠየቃቸው ‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃም ኾነ በሀገራችን ለሕዝብ የተፈቀደ ዴሞክራሲያዊ መብት መኾኑ አያጠያይቅም›› ብለዋል፡፡ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ ያቀረቡ ሰዎችን መገሠጽና መውቀስም ሕገ መንግሥቱን እንደሚፃረር ጠቁመዋል፡፡
ጉባኤዎቹ በቤተ ክርስቲያን ጠሪነት የተካሔዱ እንደነበሩና ተሰብሳቢዎቹም የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት፣ አገልጋዮችና ሠራተኞች መኾናቸውን ፓትርያርኩ ጠቅሰው÷ የጎደለው እንዲሟላ የጠመመው እንዲቃና ያላቸውን አስተያየት በማቅረባቸው ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹የስብሰባ ነፃነትንና መብትን ነፍጎ ሐቁ እንዳይነገር›› የሚከለክልና ውጤቱም ‹‹ጊዜ ያለፈበትን አፈና በማንገሥ ችግሮች ተባብሰው እንዲቀጥሉ የሚያደርግ ነው›› ብለዋል፡፡ “በውይይቱ ወቅት ‹‹የዳኅፀ ልሳን ወለምታ›› አጋጥሞም ከኾነ በወቅቱ ማብራሪያና ማስተካከያ ይሰጥበታል እንጂ እንደ ከባድ ጥፋት ተቆጥሮ ሰዎች ሊገሠጹበትና ሊወቀሱበት አይገባም፤ ሕግም አይፈቅድም፡፡” ሲሉ ገልጸዋል - በደብዳቤያቸው፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ያላቸው አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ቀርበው ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹ሕግንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር›› ብቻ ሳይኾን ‹‹ትልቁን ጉባኤ በታሪክና በሕግ ዐዋቂዎች ዘንድ ግምት ውስጥ የሚጥለው እንዳይኾን አቡነ ማትያስ አስጠንቅቀው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ጉዳዩን እንደገና በጥልቀትና ከሕግ አንጻር ፈትሾ እንዲያጤነው በማለት አፈጻጸሙ እንዲቆይ አስታውቀዋል፡፡
በሕገ ቤተክርስትያን ት/ሲኖዶሱ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈውን ውሳኔ ፓትርያርኩ የማገድ ሥልጣን እንደሌላቸው ያመለክታል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ከተጠቀሰበት አግባብ አኳያም፣ “ቤተ ክርስቲያናችን በቂ ሕግጋት አሏት፤ እነዚህ ሕግጋት ማዕከሉ ተጠብቆ ሊሠራባቸው ይገባል፤” ሲልም ቅ/ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡
ባለፈው መስከረም መጨረሻ “የቤተ ክርስቲንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ” በሚል መርሕ በተካሔደው ስብሰባ አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ ‹‹ፈጣሪ የለም ይላል፤ አሸባሪና አክራሪ ነው፤›› በማለት ቤተ ክርስቲያኗ ዕውቅና የሰጠችውን ማኅበረ ቅዱሳንን ከዓለም አቀፍ ጽንፈኞች ጋራ እያመሳሰሉ መወንጀላቸው ተገቢ እንዳልኾነና የማኅበሩ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን አስፈላጊ እንደኾነ ቅዱስ ሲኖዶሱ አረጋግጧል፡፡
‹‹ቆራጣ ደብዳቤ ይበቃዋል፤ ከመንግሥት ጋራ በመተባበር እስከ ጫፍ አድርሱልን፤ በቶሎ ቁረጡት›› እያሉ መጠየቅ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱንም “ከፈለጉ ቆባቸውን አስቀምጠው ወደዚያው ይግቡ” እያሉ መዝለፋቸውስ በምን መመዘኛ ነው ዴሞክራሲያዊና ሕገ መንግሥታዊ የሚኾነው በማለት የሚገልጹ የስብሰባው ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ ፓትርያርኩ የውሳኔውን አፈጻጸም ማገዳቸው፣ አድሏዊ እንደሚያደርጋቸውና በካህናቱና በምእመናኑ ዘንድ መንፈሳዊ አባትነታቸውንና ታማኝነታቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባው እንደሚኾን ጠቁመዋል፡፡

Saturday, December 13, 2014

በማኅበረ ቅዱሳን ተቃውሞ ባቀረቡ ካህናት ላይ እርምጃ እንዲወሰድ የተደረገው ተጋድሎ ከሸፈ!

   ( 4/4/ 2007 )
 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የጥምቅት ወርን መባቻ ተከትሎ የአጠቃላይ ሰበካ ጉባዔ ዓመታዊ ስብሰባና የሲኖዶስ ጠቅላላ ጉባዔ እንደሚደረግ ይታወቃል። በዚህ ዓመት የተለየ የሚያደርገው ከሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ ቀደም ብሎ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የስብሰባ አዳራሽ በቅዱስ ፓትርያርኩ የተደረገ የሀ/ስብከቱ አድባራትና ገዳማት ልዩ ልዩ ኃላፊዎች በተጠራ ጉባዔ ላይ የተካሄደው ውይይት ዋነኛው ጉዳይ ሆኖ አልፏል። በወቅቱ ከተደረገው ውይይትና ከተሰብሳቢዎቹ ድምጽ ለማወቅ እንደተቻለው በአጭር ቃል «ማኅበረ ቅዱሳን» ስለተባለው ማኅበር እንቅስቃሴ ላይ ያጠነጠነ ውይይት መሆኑ የተለየ አድርጎታል።

  ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ድርጅት እንቅስቃሴ፤ በቤተ ክህነቱ ዙሪያ ያለው የሥራ ድርሻ፤ የአባላት ምልመላ፤ የገንዘብ አሰባሰብና ውጪን ስለማሳወቅ፤ ሊኖረው ሲለሚገባው ገደብና ሌሎች  አሳቦች ተነስተው ሰፊ ውይይት የተደረገባቸው እንደነበር ይታወሳል። በማኅበሩ ዙሪያ በተነሱት የማኅበረ ካህናቱና የፓትርያርኩ ውይይት ደስተኛ አለመሆን ከማኅበሩ ዘንድ የሚጠበቅ ቢሆንም በአስገራሚነቱ የተመዘገበው ተቃውሞ የተነሳው ቤተ ክርስቲያኒቱን ይመራሉ ተብለው በከፍተኛ ስልጣን ላይ በተቀመጡት በዋና ሥራ አስኪያጁና ከዋና ፀሐፊው በኩል መሆኑ ነው። የማኅበሩ አባል የመሆን መብታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ማኅበሩን በተመለከተ ፓትርያርኩ ማኅበረ ካህናቱን የማወያየት አቅምና ሥልጣን የሌላቸው በማስመሰል መቃወም ግን በምንም መመዘኛ ተቀባይነት ያለው አይደለም። ማኅበሩ ምን እየሰራ ነው? እንቅስቃሴው ምን ይመስላል? ቤተ ክርስቲያን የምትቆጣጠረው እንዴት ነው? ለሚሉ ጥያቄዎች የማኅበረ ካህናቱን ድምጽ የመስማትና የማወያየት አቅም ፓትርያርኩ የላቸውም ከተባለ ዋና ሥራ አስኪያጁ ስለማኅበሩ የመጮህ ሥልጣንን ከየት አገኙ? የሚል አንጻራዊ ጥያቄን ማስነሳቱ የግድ ነው ።

  ሌላው ስለማኅበሩ የጦፈ ክርክር ተደርጎ የነበረው ከአዲስ አበባው ሀ/ስብከት ጉባዔ በኋላ በተፈጸመው የሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ ላይ በድጋሜ መነሳቱ ነበር። በዚህ ጉባዔ ላይ ስለማኅበረ ቅዱሳን ያልተነገረና የቀረ አንዳች ነገር አልነበረም። የተናገሩትን ሰዎች ማንነት ለጊዜው ወደጎን ትተን በተነገረው ጉዳይ ላይ ስናተኩር ከተነገረው እውነት የቀረ ነገር ካልሆነ በስተቀር የተጨመረ አዲስ ነገር ምንም አልነበረም ማለት ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ጣልቃ ይገባል? ያልተፈቀደ ጉባዔ ይጠራል? የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት ለራሱ አባልነት ይመለምላል? ቤተ ክርስቲያኒቱ የማታውቀውን ገቢ ይሰበስባል?  የቤተ ክርስቲያኒቱን የኦዲት ምርመራ አልቀበልም ይላል?  ለሁሉም አንድ መልስ «አዎን» ነው። በነዚህ አንኳር ነጥቦች ላይ የካህናቱና የፓትርያርኩ መነጋገር የሚያንገበግበው ቢኖር ማኅበሩና ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ ለማኅበሩ ጥብቅና የሚቆሙ ወገኖች ብቻ ናቸው። ካልሆነ ስለማኅበረ ቅዱሳን ተግባር መነጋገር ለምን ያናድዳቸዋል?

   ማኅበሩ የተሳሳተውን መንገድ አውቆ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ ማሳሰብና የማኅበሩ ቅን አባላት ለተሻለ መንፈሳዊ ተግባር ትኩረት እንዲሰጡ የሚያስችል ውይይት ማድረግ ተገቢና ተቀባይነት ያለው መሆኑን የሚክድ ያለ አይመስለንም። ቅዱስ ፓትርያርኩ ያደረጉትም ይህንኑ ነው። በጠራ ቃል «ማኅበሩን ይፈረስ ያለ ማንም የለም» ብለዋል። ከዚህ ውጪ እነዚህ ቡድኖች ምን እንዲሆን  ይፈልጋሉ? በዚህ ዙሪያ የሚታመም ሊቀ ጳጳስ ወይም ተመሳሳይ ሰው ቢኖር ራሱን መመርመር ያለበት ራሱን ነው። ህመሙ የጤንነት ምልክት አይደለም። ዘረኝነት፤ ጥቅምና ጭፍን ደጋፊነት ብቻውን ማንነትን ከሚያጋልጥ በስተቀር የትም አያደርስም። ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አባ ማቴዎስ ለቅዱስ ፓትርያርኩ የተናገሩት « ማኅበረ ቅዱሳንን ከነኩ እርስዎም እንደአባ ጳውሎስ ይሞታሉ» ማለታቸውን ሰምተን ጤንነታቸውን ተጠራጥረን ነበር። ቅዱስ ፓትርያርኩ ከእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ጋር እንዴት አብረው ሊሰሩ እንደሚችሉ ስናስብ እጅግ ያስገርመናል። ዓይን ያወጣ ጥላቻና አንድን ቡድን መደገፍ አሳዛኝም አስገራሚም ነው። በዚህ ዓይነት ጉዞ ቤተ ክርስቲያን ወዴት እየሄደች እንዳለ ለማወቅ አስቸጋሪ አይደለም። ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ ለራስ ክብርና ለማኅበር መቆም ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ውድቀት እየገፏት መሆኑን ለማወቅ ምርምር አይጠይቅም። ባለፉት 23 ዓመታትም ከቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት መካከል ከ16 ሚሊየን በላይ ልጆቿ ወጥተው የቀሩትም በዚህ ዓይነት ቡድናዊ አስተዳደርና ደካማ አስተምህሮ የተነሳ ነው።

 የሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ እንደተፈጸመ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ቀጥሎ ነበር። በዚህ የሲኖዶስ ጉባዔ ላይም በግንባር ቀደምትነት የተነሳው ጉዳይ ቢኖር ማኅበሩ ለምን ተነክቶ? የሚሉ የጳጳሳት ቡድን በአንድ በኩል፤ ቅዱስ ፓትርያርኩ ብቻቸውን በሌላ በኩል ሆነው የጦፈና የከረረ ውይይት ማድረጋቸውን ከውስጥ አዋቂ ምንጮች ሰምተን ነበር።  ማኅበሩን የሚያወግዙና የሚወቅሱ የማኅበረ ካህናት አባላት እኛንም ከማኅበሩ ጋር ቀላቅለው ስለዘለፉን ቀኖና እንዲሰጣቸውና እንዲቀጡ ይደረግ የሚሉ አፍቃሬ ማኅበረ ቅዱሳን ጳጳሳት የጉባዔውን አቅጣጫ ለማሳት ሙከራ አድርገው ነበር። ፓትርያርኩ ምንም እንኳን ለጉዳዩ መልስ በመስጠት ዝም ለማሰኘት ሞክረው የነበረ ቢሆንም «ወደ ገዳማችን እንሄድልዎታለን፤ ሲኖዶሱን ሊያከብሩ ይገባል፣ እርስዎ በአቡነ ጳውሎስ ዘመን ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን አለው፤ ሲሉ የነበር  ዛሬ እርስዎ ለምን ይሽሩታል?» ወዘተ መከራከሪያ ነጥብ ለማንሳት ተሞክሮም ነበር። ይህ ሁሉ የሆነው የሲኖዶስ ውሳኔ ስለተሻረ ሳይሆን በሲኖዶሱ ሉዓላዊ ስልጣን ከለላ በማኅበረ ካህናቱ ዘለፋና ውግዘት የደረሰበትን ማኅበር ለመካስ ሲባል በማኅበሩ ላይ የተናገሩት ካህናት ሁሉ እንዲቀጡና ቀኖና እንዲሰጣቸው ለማስቻል ነበር።

  ማኅበሩን አጋልጠው ለአጋላጭ ሰጥተዋል የተባሉት በዋናነት አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል፤ ሊቀትጉኃን ዘካርያስ ሐዲስ፤ መልዓከ መንክራት ኃይሌ አብርሃ፤ ዲያቆን አበበ፤ ዲያቆን ዘመንፈስ አብርሃ፤ አባ ነዓኩቶ ለአብ የመሳሰሉት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያና ቀኖና እንዲሰጣቸው እንዲሁም ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ በተለይ ከፓትርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት እንዲባረሩ ይደረግ የሚል ውሳኔ ለማሳለፍ ተሞክሮ ነበር። በተካፈሉበት ጉባዔ ላይ ሁሉም አሳብ ሰጪዎች የተናገሩት በማኅበሩ ዙሪያ ብቻ ሆኖ ሳለ ከእስከዛሬው በተለየ ሁኔታ በእነዚህ ካህናት ላይ የበቀል እርምጃ እንዲተላለፍ የተፈለገው ለምንድነው? ዋና የስም ማጥፊያ ማጠንጠንጠኛው ሙሰኞችና አማሳኞች ናቸው የሚል ቢሆንም ማን ምን ሰረቀ? ስንት ሰረቀ? መቼ ሰረቀ? የት ሰረቀ? ለሚለው የጥያቄ ጭብጥ መልስ የሚሰጥ አካል የለም። በወሬ ደረጃ የምናየውንና የምንሰማውን ይዞ ካልሆነ በስተቀር ማስረጃውን በነጥብ የሚያስረዳ አካል የለም። የተጠቀሱት ግለሰቦች በሥራቸው ያልተመሰረከላቸው መሆኑ ወይም የሙስና ተሳታፊ ስለመሆናቸው መጠርጠራቸው ብቻውን ስለማኅበረ ቅዱሳን መናገራቸውን ስህተት ሊያደርገው አይችልም። ታዲያ ቅዱስ ሲኖዶስ በነዚህ ሰዎች ላይ እርምጃ ይወሰድ! የሚለው በምን መነሻ ነው? ሲኖዶስ ሊያደርግ የተገባው ሀቅ ቢኖር ማኅበሩንም ይሁን በማኅበሩ ዙሪያ ተቃውሞ ያነሱ ሰዎች ያጠፉት ነገር ካለ መርምሮ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም የእርምት እርምጃ መውሰድ ነበር። ነገር ግን አንዱን አጥፊ ደግፎ ሌላው አጥፊ ላይ ጣትን መቀሰር ቅንም፤ መንፈሳዊም አካሄድ አይደለም።

 ይህንን ዘገባ እስካወጣንበት ጊዜ ድረስ ከላይ በጠቅስናቸውና በሌሎች ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ማኅበሩ ከኋላ እየገፋ ብዙ ተጽዕኖ ሲያደርግ ቆይቷል። በአባ ማቴዎስና በአባ ሉቃስ አሳሳቢነት ቋሚ ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ ጉዳዩን እያነሱ የሲኖዶስ ጠቅላላ ጉባዔ ካሳለፋቸው ውሳኔዎች እንደአንዱ ተቆጥሮ በተጠቀሱት ሰዎች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ላለፈው አንድ ወር ሙሉ ጽኑ ክርክር ሲያደርጉ መቆየታቸው ተሰምቷል። ከተወሰኑ ጉባዔዎች በስተቀር ያልተነሳበት ስብሰባ አልነበረም። በተለይም አባ ሉቃስ «ሊቃነ ጳጳሳት ተዘልፈዋል፤ የቤተ ክርስቲያን ክብር ሲነካ ዝም ማለት አይቻልም፤ ማኅበሩም ቢሆን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ እየሰራ ነው» በሚል መከራከሪያ በተቃዋሚ ካህናት ላይ እርምጃ ለማስወሰድ ብዙ ተጉዘው ነበር። ነገር ግን በፓትርያርኩ በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ውድቅ ተደርጓል።
    የፓትርያርኩ አቋም ማኅበረ ካህናቱን ሰብስቦ ለማናገር የማንንም ፈቃድ አልጠይቅም። ቅዱስ ፓትርያርክ የሚመራቸውን ካህናት የማናገር መብቱን የሚያገኘው ሥልጣኑን  ከተቀበለት ሰዓት ጀምሮ ነው። ካህናቱንም የተሰማቸውንና የታያቸውን ጉዳይ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ ማቅረባቸው ትክክልና ተገቢ ነው። አያስወቅሳቸውም። ከዚያ በተረፈ የሊቃነ ጳጳሳቱን ስም አንስቶ ጸያፍ ቃል የተናገረ ካለ በቦታና በስም ተለይቶ ይነገረንና ምክርና ተግሳጽ እንሰጠዋለን እንጂ የመናገር መብቱን ተጠቅሞ የመሰለውን ሃሳብ ያንጸባረቀ ሁሉ ጥፋተኛ አይባልም» በማለት የማኅበሩን ደጋፊ ጳጳሳት ኩም አድርገዋቸዋል። በተለይም ባለፈው አንድ ሳምንት በማኅበሩ በኩል ከኋላ ይገፉ የነበሩትና አሳባቸው ውድቅ የሆነባቸው አባ ማቴዎስንና አባ ሉቃስን ያየ መጨረሻቸውን ለማየት ናፍቆ ነበር።
ሁልጊዜም የሚሸሸጉበት ስነ ሞገት «የሲኖዶሱ ውሳኔ ይከበር» የሚል ሲሆን ሲኖዶስ የማንን የመናገር መብት እንደከለከለ የሚገልጽ ማስረጃ ግን ማቅረብ አልቻሉም። ወደፊትም አይችሉም።

 ከዚሁ ጋር ተያይዞ የደረሰን መረጃ እንደሚያስረዳው ማኅበሩን በመቃወም ድምጻቸውን ያሰሙ ካህናት መብታቸው በመሆኑ የትኛውም አካል ይህንን መብታችሁን ለምን ገለጻችሁ?ብሎ እርምጃ የሚወስድ አካል ቢኖር የሕግ ጥበቃ እንዲደደረግላቸው ለመንግሥት አካላት ባቀረቡት አቤቱታ መሠረት ቃል የተገባላቸው መሆኑ ታውቋል።

Wednesday, December 3, 2014

ሰበር ዜና፤ አባ እንባቆም ኢየሩሳሌም ገቡ፤ አባ ዳንኤል ደግሞ ሚኒያፖሊስ ከተሙ!

(ደጀ ብርሃን፤ሕዳር 24/2007 )

 አባ እንባቆም እስራኤል በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀጳጳስ ሆነው በጥቅምቱ የሲኖዶስ ጉባዔ መመደባቸው ይታወሳል። በዚሁ መሠረት ቀደም ሲል የገዳማቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩትና ባለመግባባት ከቦታው እንዲነሱ በተደረጉት በአባ ዳንኤል ምትክ የተመደቡት አዲሱ ሊቀ ጳጳስ አባ እንባቆም ትናንት በ23/3/ 2007 ዓ/ም ኢየሩሳሌም መግባታቸውና ደማቅ አቀባበል እንደተደረገላቸው ተያይዞ የደረሰን ዜና ያስረዳል።

    አባ እንባቆም ቀደም ሲል በድሬዳዋ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ይሰሩ እንደነበር ሲታወቅ በቆይታቸውም ከሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች ጋር ከፍተኛ አለመግባባት ላይ ደርሰውና ከቦታው እንዲነሱ የሕዝብ ግፊት አይሎ በነበረበት አጋጣሚ ወደኢየሩሳሌም መመደባቸው ለጊዜውም ቢሆን ትንፋሽ የመግዢያ ጊዜ ሊሆናቸው እንደሚችል ተገምቷል።

 በተመሳሳይ መልኩ ሊቀጳጳሱ በደብረ ሊባኖስ ገዳም ከፍተኛ ጥላቻና ተቃውሞ ሲደርስባቸው የቆየ ሲሆን የጉዳዩን ዝርዝር ምክንያት ለመግለጽ የተቆጠቡት ምንጮቻችን ሊቀጳጳሱ ከኢየሩሳሌም መነኮሳት ጋር ተግባብተው መስራት ይችላሉ ወይ? የሚለው ጉዳይ እንደሚያሳስባቸውና በሂደት ምን ሊፈጠር እንደሚችል ወደፊት የሚታይ ይሆናል ሲሉ አክለው ገለጸውልናል።
በሌላ በኩል ከገዳሙ አባቶች ጋር ባለመግባባት የተነሱት አባ ዳንኤል የተመደቡበትን ሀገረ ስብከት ሳይረከቡ እስካሁን አሜሪካ በሚኒሶታ ስቴት ሚኒያፖሊስ ውስጥ በምትገኘው የግላቸው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከትመው የሚገኙ ሲሆን  ታቦተ ኪዳነ ምህረትን ከአዲስ አበባ ተሸክመው እንዲሄዱና ከመድኃኔዓለም ታቦት ጋር በደባልነት እንዳስገቡ ለመረዳት ችለናል። ሀገረ ስብከቱ በአቡነ ዘካርያስ የሚመራ ቢሆንም የሲኖዶሱን ህግ በመጻረር አንዱ በሌላው ሊቀ ጳጳስ ሀ/ስብከት ውስጥ ጣልቃ ገብቶ የፈለገውን መሥራት የለመደ አሰራር ሆኗል። በተለይም በአሜሪካ የመኖሪያ ፈቃድ ያለው ሊቀ ጳጳስ ጡረታውንና ድጎማውን እየተቀበለ በስሙ ያቋቋማትን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በግሉ ያለከልካይ ያስተዳድራል።



Sunday, November 30, 2014

በምድር ላይ በክፉው መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ አሰተኛ ክርስቶሶች (ክፍል 4 )

ላዝሎ ቶት(1938-2012) 

በትውልዱ ሀንጋሪ፤ በዜግነት አውስትራሊያዊ የሆነ ሰው ነው። በትውልድ ሀገሩ በጂኦሎጂ ትምህርት ዲፕሎማ የነበረው ቢሆንም የእንግሊዝኛ ቋንቋው ደካማ ስለነበርና የሙያ ክህሎቱም ተቀባይነት ባለማግኘቱ አውስትራሊያ እንደገባ ሀንጋሪ በተማረው ሙያ መስራት አልቻለም። በኋላም በአንድ ሳሙና ፋብሪካ በቀን ሰራተኝነት ተቀጥሮ ጥቂት ከቆየ በኋላ በ1971 ዓ/ም ወደኢጣሊያ አቅንቷል።  ጣልያን እንደደረሰም እኔ «ኢየሱስ» ነኝ እያለ ለመስበክ ቢሞክርም ጣሊያንኛ ባለመቻሉ ስብከቱን ያዳመጠው አልነበረም። ከሮማው ካቶሊክ ፖፕ ጳውሎስ 6ኛ ለመገናኘትና የራሱን ማንነት ሊገልጽላቸው እንደሚፈልግ ደብዳቤ ጽፎላቸው ደብዳቤው ከፖፑ ሳይደርስ መንገድ ላይ ቢቀርበትም በሌላ መንገድ ለመገናኘት ያልተሳካ ሙከራም አድርጓል። ይሁን እንጂ በዚህ ሁሉ ተስፋ ያልቆረጠው «ቶት» የመጨረሻ ሙከራውን ለማድረግ በ33ኛው ዓመት ዕድሜው ግንቦት 21 ቀን 1972 ዓ/ም ጂኦሎጂስቶች በተለይ የሚጠቀሙበትን ትንሽ መዶሻ ከፍ አድርጎ በመያዝና በአደባባይ እየጮኸ «እኔ ኢየሱስ ነኝ፤ ሞቼም ነበር፤ ሕያው ነኝ» እያለ ይረብሽ ጀመር። ከዚያም ወደ ቫቲካን ሲቲ በመግባት በሚካኤል አንጄሎ የተሰራውን ቅርጽ ማለትም ኢየሱስ ከመስቀል ላይ ወርዶ በእናቱ በማርያም እቅፍ ላይ ሆኖ ከአንገቱ ዘንበል ብሎ የሚታየውን ምስል በያዘው መዶሻ መደብደብ ጀመረ። በድብደባውም የማርያምን ምስል ቀኝ ክንድ፤ የአንድ ዓይን ክፍሏንና አፍንጫዋን ሰብሮ ጥሏል።


 በቦታው ከነበሩ ጎብኚዎች አንዱ የሆነው ቦብ ካሲሊ የተባለ ሰው ቶት ላይ ተጠምጥሞ በመያዝ ሊያስጥለው ችሏል። ቶት በቁጥጥር ስር ውሎ ህክምና ሲደረግለት የአእምሮ በሽተኛ መሆኑ በመረጋገጡ ከጣሊያን ወደአውስትራሊያ በአስቸኳይ እንዲባረር ተደርጓል። አውስትራሊያም እንደደረሰ በተመሳሳይ ድርጊት ላይ በመገኘቱ ከህሙማን ክብካቤ ማዕከል እንዲገባ ተደርጎ ህይወቱ እስካለፈችበት 2012 ዓ/ም ድረስ በዚያው ሲረዳ ቆይቷል።

===============================================================================

ዌይን ቤንት ወይም ማይክል ትራቬሰር (ከ1941- እስካሁን በሕይወት ያለ)

 በ1941 ዓ/ም የተወለደ ሲሆን  በአይዳሆ ሴንትፖይንት ከተማ በምትገኝ «ጌታ የኛ ቅድስና ቤተ ክርስቲያን» መሪ የነበረ ሰው ነው። ቤንት የዚህች ቤተክርስቲያን መሪ ከመሆኑ በፊት «በሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን» ፓስተር ሆኖ ያገለግል ነበር። በ1987 ዓ/ም ቤተ ክርስቲያኒቱን በይፋ ለቆ ሲወጣ «ሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን የታላቂቱ ጋለሞታ ሴት ልጅ ናት» ብሎ በአደባባይ ተናግሮ ነበር። ይህንን ለማለት ያበቃውን ምክንያት ግን በወቅቱ አልተናገረም።  ከዚያም ወደ አይዳሆ በማምራት ጥቂት ጊዜ በአባልነት ከቆየ በኋላ በ2000 ዓ/ም «ጌታ የኛ ቅድስና» በተባለችውና አነስተኛ ቁጥር በያዘችው ቤተ ክርስቲያን መሪ  ለመሆን ቻለ። በዚያው ዓመት «እግዚአብሔር፤ አንተ ኢየሱስ ነህ ብሎ ተገልጾ ነገረኝ» በማለት ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት አወጀ። ጥቂት ቆይቶም ከሰባት ደናግላን ጋራ ለወሲብ እንድትተኛ የሚል ትዕዛዝ ስለመጣልኝ ደናግል ልጆቻችሁን እንድትሰጡኝ በማለት ጥያቄውን አቀረበ። ገሚሶቹ የቡድኑ አባላት ሃሳቡን ውድቅ ያደረጉበት ቢሆንም በግላጭ ሴት ልጁን አሳልፎ የሰጠው ማን እንደሆነ ሳይታወቅ በምስጢር ከደናግላን ጋር ወሲብ መፈጸሙ በኋላ ላይ በፖሊስ በተደረገበት ምርመራ ሊረጋገጥ ችሏል። ቻናል 4 የተባለው የዩኬ ቴሌቪዥን ጣቢያ በ2007 ዓ/ም ከዌይን ቤንት ጋር ባደረገው ቃል ምልልስ ስለደናግላኑ ወሲብና ከእግዚአብሔር ስለሚመጣለት ትዕዛዛት ተከታታይ ፕሮግራም አስተላልፎ ነበር።(ከቪዲዮዎቹ አንዱን ለማየት እዚህ ይጫኑ)
  የዓለምም መጨረሻ ጥቅምት 31/2007 ዓ/ም እንደሚሆንና ተከታዮቹም ለመነጠቅ እንዲዘጋጁ የተናገረ ቢሆንም ቀኑ ሲደርስ እንዳለው የሆነ ነገር ምንም አልነበረም።  ይልቁንም ቤንት ከልጁ ሚስት፤ ከደናግላን ጋር እንዲሁም ለአቅመ ሄዋን ካልደረሱ ታዳጊዎች ጋር ወሲብ በመፈጸም ወንጀል ተከሶ በ2008 ዓ/ም የ18 ዓመታትን እስራት ተከናንቦ ከርቸሌ ወርዷል። ዌይን ቤንት ከርቸሌ ከወረደ በ2014 ዓ/ም ገና 6ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን ቢያንስ በአመክሮ ለመፈታት ከእንግዲህ 3 ዓመት ገደማ በዚያው መቆየት ይጠበቅበታል። 

==============================================================================

አሪፊን ሙሐመድ ( 1943- እስካሁን ያለ)

 አሪፊን ሙሐመድ በ1943 ዓ/ም ከሙስሊም ቤተሰብ በማሌዢያ ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ህውከት እንደደረሰ በ1980ቹ አጋማሽ  በማላያን ቋንቋ «ካራጃአን ላንጊት» ወይም በእንግሊዝኛው «የሰማይ መንግሥት» የተሰኘ ድርጅት አቋቋመ። በአክራሪ ሙስሊሞች በምትታወቀው ማሌዢያ ውስጥ አሪፊን ሙሐመድ «እኔ አልመሲህ ዒሳ፤ ቡድሃ፤ ሙሐመድ ሺቫ ነኝ» እያለ በመስበክ ተከታዮችን ለማፍራት ጊዜ አልፈጀበትም። በዚህ አድራጎቱ ብርቱ ተቃውሞ ገጠመው። በተደጋጋሚ ሲታሰር፤ ሲፈታ ቆይቶ መንግሥታዊ ስርዓቱን በዓመጽ ለመገልበጥ በመሞከርና ሃይማኖታዊ ብጥብጥን በመፍጠር ወንጀል ተከሶ ድርጅቱ እንዲዘጋ፤ በአባልነት የተሳተፉትም እንዲታሰሩ ሲወሰን አሪፊን ሙሐመድ ሾልኮ አመለጠ። ከአራቱ ሚስቶቹ ሦስቱና ከተከታዮቹም 58 ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ።

 እያንዳንዳቸውም 3000 የማሌዢያን ገንዘብ እንዲከፍሉና ሁለት ዓመት እንዲታሰሩ ፍርድ ቤት ወሰነባቸው።  የድርጅታቸውም ህንጻና ማንኛውም ንብረት እንዲፈርስ ተደረገ። አሪፊን ሙሐመድ አንዴ ኢየሱስ ነኝ፤ አንዴ ማህዲ ነኝ እያለ ተከታዮቹን ቢያጭበረብርም በማሌዢያ መንግሥት በወንጀል ከሚፈለጉ ሰዎች ቀንደኛው ሲሆን ማሌዢያን ለቆ ከጠፋ በኋላ በታይላንድ ውስጥ ተሸሽጎ እንደሚገኝ ይገመታል።
==================================================================================

ማታዮሺ ሚትሱኣ (1944- እስካሁን በሕይወት ያለ) 

በጃፓን፤ ኦኪናዋ ከተማ በጥር 5/ 1944 ዓ/ም ተወለደ። ከዚያም ለአቅመ ትምህርት እንደደረሰ በመጀመሪያ በተወለደት ቦታ በኋላም በቶኪዮ ቹዋ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ድግሪውን አግኝቷል። በ1997 ዓ/ም «ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚያዊ ኅብረት ፓርቲ» የተባለውን ሃይማኖትንና ፖለቲካን በጥምር የሚያንቀሳቅስ ፓርቲ መሰረተ። እንደሃይማኖት ሥርዓት ዓለም በኔ እንዲገዛ «እኔ ኢየሱስ ነኝ» አለ። እንደፖለቲካ አስተዳደር ደግሞ ዓለም በኔ እንዲመራ «የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ መሆን ያለብኝ እኔ ነኝ አለ»። የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ለመሆን ባለው ከፍተኛ ጉጉት የርሱ ፓርቲ በተደጋጋሚ በምርጫ ቢወዳደርም  እንኳን ከትልቅ ስልጣን ሊደርስ ቀርቶ የመንደር ምርጫም ማሸነፍ ሳይችል ቀርቷል። በምርጫ የተፎካከሩትን ሰዎች ለዚህ ድርጊታችሁ የምሰጣችሁ ምክር «ራሳችሁን አጥፉ»  ያላቸው ሲሆን ስልጣን ብይዝ ደግሞ ሁሉንም ሰብስቤ እሳት ውስጥ እጨምራቸው ነበር እያለ ሲለፍፍ ተሰምቷል።

== ==============================================================



ጆሴ ሉዊስ ደ ጂሰስ ሚራንዳ ( 1946- 2013) 

 ፖርቶሪኮ ውስጥ ፖንሴ በተባለች ከተማ በ1946 ዓ/ም ተወለደ። ወላጆቹ በጣም ድሃ ስለነበሩ የሴቶችን ቦርሳ መመንተፍ የተለማመደው በልጅነት ዕድሜው ነበር። ገና የ14 ዓመት ዕድሜ ሳለም የሔሮይን አደገኛ ተጠቃሚ እስከመሆን ደርሷል።  ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ በፖንሴ ከተማ በነበረችው መጥምቃውያን ቤተ ክርስቲያን ተቀላቀለ። እግዚአብሔር ባደረገልኝ ጥሪና እገዛ ከነበረብኝ ደባል ሱስ ሁሉ ተላቅቄአለሁ አለ።  ጆሴ ሚራንዳ በ1973 ዓ/ም  ሁለት መላዕክት መጥተው በነገሩኝ መሠረት «እኔ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ሆኜ በምድር ላይ መገለጤን ነግረውኛል» ብሎ መለፈፉን «ሀ»ብሎ ጀመረ። በማያሚ፤ ፍሎሪዳ የስደት ኑሮውን የቀጠለው ሚራንዳ የ15 ደቂቃ የሬዲዮ ፕሮግራም በማሰራጨት የሱን ኢየሱስነት ይሰብክ ገባ። በስብከት መርሐ ግብሩ «ሚኒስትሮ ግሬሴንዴ  ኤን ግራሲያ» ወይም « በጸጋው የማደግ አገልግሎት» የተሰኘ ድርጅት ከመሰረተ በኋላ በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች ማስፋፋቱን ቀጠለ። በ35 ስቴቶች በከፈተው ተቋም 287 የሬዲዮ ጣቢያዎችና በእንግሊዝኛና ስፓኒሽ ቋንቋ የሚተላለፍ የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን ስርጭትም እስከማስተላለፍም ደርሷል።
ጆሴ ሚራንዳ አንድ ጊዜ ሐዋርያው ጳውሎስ ነኝ፤ አንድ ጊዜ ደግሞ ኢየሱስ ነኝ እያለ ከቆየ በኋላ በ2006 ዓ/ም ክህደቱን በማጠናከር ከዛሬ ጀምሮ «እኔ የኢየሱስ ተቃዋሚ ነኝ» ሲል አወጀ።  «Anti Christ» ወይም ተቃዋሚው ስለሆንኩኝ መለያ ምልክቴ በራእይ 13 ላይ የተጠቀሰው«666» ቁጥር ነው በማለቱ  ተከታዮቹ ሁሉ በሰውነታቸው ላይ እንዲነቀሱ ትዕዛዝ አስተላለፈ። ተከታዮቹም «666» ቁጥርን በሰውነታቸው ላይ በሰልፍ ተነቀሱት።
የሚራንዳ ወርሃዊ ደመወዝም ልዩ ልዩ ክፍያና አበልን ሳይጨምር 228,000 ዶላር ገደማ ነበር። ሚራንዳ ባደረበት የጉበት ህመም በተወለደ በ67 ዓመቱ በ2013 ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል። ከ2 ሚሊዮን በላይ በሚገመቱ ተከታዮቹም ዘንድ «እንደመልከ ጼዴቅ ለዘለዓለም የሚኖር» ተብሎለታል።
በአንድ ወቅት CNN ካቀረበው የጆሴ 666 ታሪክ የተወሰደ ቪዲዮ ይመልከቱ።





Monday, November 24, 2014

ኡጋንዳዊቷ የቤት ሠራተኛ ሕይወት ለማጥፋት በመሞከር ወንጀል ተከሠሠች!

( ዕድሜአቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ እንዲመለከቱ አይመከርም ) The film is not suitable for viewing by anyone under 18 years of age

ባለፉት ቅርብ ቀናት በኢትዮጵያ ውስጥ ሐና በተባለች ታዳጊ ወጣት ላይ አስነዋሪና እጅግ አሳሳቢ ድርጊት ተፈጽሞ የብዙዎችን ልብ እንደሰበረ ይታወቃል። ማኅበራዊ አኗኗራችን ከመተሳሰብ እያፈነገጠ፤ ሥነ ምግባራዊ አስተሳሰባችን እያደፈ የመሄዱ ምልክት ነው። ዓለም አንድ መንደር እየሆነች ነው ሲባል በመሰልጠኑ ብቻ ሳይሆን በመሰይጠኑም ጭምር በመሆኑ ስግብግብነት፤ ራስ ወዳድነት፤ ብልግናና ዐመፃንም ዓለማዊ መንደርተኝነት እያካፈለው ይገኛል። ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጸመው አስነዋሪ ድርጊት ትኩሳቱ ሳይበርድ አንድ መንደር የሆነችው ዓለም ከወደዑጋንዳ ሌላ ዜና ብቅ አለች። በአንዱ ጫፍ የተፈጸመው ወሬ ወደሌላ ጫፍ ለመድረስ ደቂቃ የማይፈጅባት ዓለማችን ካስተናገደቻቸው ብዙ ዜናዎች መካከል አንዱን አሳዛኝ ድርጊት አሰማችን። ጉዳዩ እንዲህ ነው።

  ድርጊቱ የተፈጸመው በዑጋንዳ፤ ኪዋቱሌ በተሰኘች አነሰተኛ ከተማ ነው። ድርጊቱን የፈጸመችው የ22 ዓመቷ ጆሊ ቱሙሂርዌ የተባለች የቤት ሠራተኛ ስትሆን በተቀጠረችበት ቤት ውስጥ እንድትንከባከብ ከአሰሪዎቿ አደራ የተሰጣትን ሕጻን በዘግናኝ ሁኔታ ስትደበድብ በቤት ውስጥ ስውር ካሜራ የተቀረጸ ቪዲዮ ያሳያል። በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተሠራጨው ይህ ቪዲዮ ብዙዎቹን አሳዝኗል። በጣም የሚረብሸው ይህ ምስል ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ እንደዋለ ዓለም ዐቀፍ ትኩረት ስቧል።  የሕጻኗ ወላጅ አባት የሆነው ኤሪክ ካማንዚ ቪዲዮውን እንደተመለከተ ለኪዋቱሌ  ፖሊስ ጣቢያ በማመልከቱ ፖሊስ ደብዳቢዋን የቤት ሠራተኛ በቁጥጥር ስር አውሎ «በማሰቃየትና ለመግደል ሙከራ በማድረግ» ወንጀል የክስ ፋይል ከፍቶ ለፍርድ ቤት እንዳቀረባት የተገኘው ዜና ያስረዳል።  የቤት ሰራተኛዋ ከተቀጠረች 26 ቀናት ብቻ ያስቆጠረች ቢሆንም የፈጸመችው ድርጊት በተመሳሳይ ሁኔታ የቆየች እንደሚመስል ፖሊስ ግምቱን የሰጠ ሲሆን  ስለሰራተኛዋ ማንነትና የቀደመ ተግባር ምርመራ ለማድረግ የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ለፍርድ ቤቱ በማመልከቱ ለታህሳስ 8/2014 እንዲያቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል። ሕጻኗ በደረሰባት ጭካኔ የተሞላበት ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባት ቢሆንም እስካሁን ህክምና እየተደረገላት በሕይወት እንደምትገኝ ታውቋል።
ሕጻናት የተለየ ክብካቤና ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው ቢሆንም ዓለም በምታስተናግደው የሥነ ልቡና ማኅበራዊ ቀውስ የተነሳ ለጥቃት እየተጋለጡ ይገኛሉ። ፍሪሃ እግዚአብሔር የሌለው ትውልድ ከሥነ ምግባር ውጪ በመሆን ለማኅበራዊ ኑሮ የአስተሳሰብ ቀውስ መጋለጡ አይቀሬ ነው። አሳዛኝና አስነዋሪ ድርጊት የመፈጸሙ ምክንያትም ይህ ነው።  በየቤታችን ለሕጻናት፤ በየአካባቢው ለሴቶችና ለታዳጊ ወጣቶች፤ ለአረጋውያንና ረዳት ለሌላቸው የምናደርገውን ክትትልና ቀና ድጋፍ በማጎልበት «የአባቴ ብሩካን» ተብሎ የተነገረውን የሕይወት ዋጋ ለማግኘት ዛሬውኑ እንነሳ!!

«ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደ ሆነ፥ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ» 1ኛ ጴጥ 2፤2



Friday, November 21, 2014

ፍሪማሰንሪ /freemasonry/ ምንድነው?




ከዚህ በፊት በአንድ ጽሁፍ «ስለኤርያ 51» አጭር ምስጢራዊ ጽሁፍ ማስነበባችን ይታወሳል። አሜሪካና ዲሞክራሲ፤ ሥልጣኔና አሜሪካ መሳ ለመሳ ናቸው። እንደዚሁ ሁሉ ሌላው ዓለም ይቅርና የሀገሪቱ ዜጋ የማያውቃቸው ብዙ ምሥጢሮችም ያሉባት ሀገር ናት። ላይ ላዩን በዲሞክራሲው ዕድገት ጫፍ ረግጫለሁ በማለቷና በሥልጣኔውም መጥቄአለሁ እያለች ከመለፈፏ ጀርባ ብዙ ጉድ እንዳዘለች ብዙው ሰው አያውቅም፤ ቢያውቅም ትኩረት አይሰጠውም።  በነገረ መለኮት የበሰሉና የትንቢቱ ፍጻሜ ሰዓት መድረሱን በደንብ ያጠኑ ምሁራን ግን አሜሪካንን «ታላቂቱ ባቢሎን» ይሏታል። ምክንያቱም በአደባባይ ከሚታወቅላት የዲሞክራሲውና የሥልጣኔው እርከን ባሻገር የተሸከመችው ጉድ የት የለሌ ነውና። ሁሉም ነገር ከብረት በጠነከረ ምስጢርና ከምስጢሩ አጠባበቅ ጋር ሕይወት በሚያስከፍል ዋጋ፤ የረቀቀ መዋቅር በተዘረጋበት ሥርዓት የምትመራ ሀገር በመሆኗ እያወቁ ወይም ሳያውቁ ታደነዝዛለች።  በህጋዊ ደረጃ ከ«Church of Satan” አንስቶ እስከመጨረሻው ክሂዶተ እግዚአብሔር  «Atheism” ድረስ በነጻ የሚንቀሳቀሱባትና ለዓለሙ ሁሉ ማዕከል ሆና የምታገለግለዋ አሜሪካ ጾታን በመቀየር እንዲሁም የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻንም በመፍቀድ መሪ በመሆን ታገለግላለች።

      ሌላው ቀርቶ በየዓመቱ የሚከበረውን የሀለዊን /Halloween/ በዓል ጥቅምት/31 ቀን ከጫፍ ጫፍ በማክበር አሜሪካንን የሚቀድማት የለም። ለነገሩ «ሀለዊን» የሞቱ ቅዱሳንን ለማሰብ በሚል ይጀመር እንጂ ድርጊቱ የሙት መንፈስ የሆነውን ሰይጣንን ለማሰብ የተሰራ ለመሆኑ የድርጊቱ ክንዋኔ ያስረዳል። የሚያስፈራ ምስልና ቅርጽ፤ ጥርሱ ያገጠጠ፤ ዓይኑ ያፈጠጠ፤ አጽሙ  የተቆጠረ ማስጠሎ ነገር ለብሶ ወይም አጥልቆ  ሰውን በማስደንገጥና በማስፈራራት ቅዱሳንን ማክበር ነው ቢባል እንዴት ሊሆን ይችላል? ለነገሩ ቅዱሳንን ተጠግቶ ይህንን ማድረጉ ራሱን የቻለ ሌላ ምስጢር ስላለው እንጂ ቅዱሳንን ስለሚወክል አይደለም። (የዚህን ምስጢር ፍቺ በዚህ ጽሁፍ ቀጣይ ክፍሎች ለመዳሰስ ይሞከራል) አሜሪካ ለመጨረሻው ዘመን የተዘጋጀችና ለጥፋት ነጋሪት የምትጎስም ሀገር በመሆንዋ ነገሩ ሁሉ እየተበላሸ ሄዷል። ባለፈው ጥቅምት 31/ 2014 ዓ/ም በሚዙሪ፤ ሴንት ሉዊስ ከተማ ዓለም አቀፍ የ«ሀሎዊን» በዓል እንደሚደረግ የተላለፈው የጥሪ ምስል እንደሚያሳየን የጨለማውን ኃይል ካልሆነ በስተቀር ሌላ ማንን ሊሆን ይችላል? እስኪ ምስሉን አይተው ግምትዎን ይስጡ!!
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነን አሜሪካ ከምታስተናግዳቸው እንግዳ ነገሮች አንዱ ክፍል ስለሆነው ስለ«ፍሪማሰንሪ»/freemasonry/ ውቅያኖስ ታሪክ ጥቂቱን በጭልፋ ልናካችላችሁ ፈልገን ነው። ምክንያቱም የአንድ ዓለም አገዛዝ /One World Order/ እንዴት እየሰራ እንዳለ በማወቅ ከሚመጣው የስህተት መንፈስ እንድንጠበቅ አበክረን ለማስገንዘብ ነው። በዚህ ዙሪያ ምሁራኑ በሀገርኛ ቋንቋ ጽፈው በሰፊው እስኪያስነብቡን ድረስ ለጥንቃቄ እንዲበጅ በጥቂቱ እንዲህ አቅርበነዋል። መልካም ንባብ!

ፍሪማሰንሪ ምንድነው?

     «ማሰን» የሚለው ቃል ከላቲኑ / machio/ ከሚለው ቃል የተወረሰ ነው።  ትርጉሙም «ድንጋይ ጠራቢ ፈላጭ ወይም ግንበኛ  ማለት ነው።  ቃሉም ከ1155 እ,ኤ,አ ጀምሮ አገልግሎት ላይ ውሏል። freestone-mason ማለት «ነጻ ድንጋይ ጠራቢ፤ ግንበኛ ሰው ማለት ሲሆን ይህም ስያሜ በዚህ ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች «free mason» ፍሪማሰን በሚል አኅጽሮት አገልግሎት ላይ እንደዋለ በ1908 ዓ/ም የታተመው የፍሪማሰን ዜና መዋዕል መጽሐፍ ያስረዳል።  የላቲኑን ውርስ ቃል ተከትሎ “free” እና “mason” ከሚለው የእንግሊዝኛ ጥምር ቃላት የተገኘው ይህ ስያሜ ድንጋይ የመጥረብ፤ የመቁረጥና የመገንባትን ድርጊት ሲያመለክት «ፍሪማሰንሪ» /freemasonry/ ይባላል።  ይህም በነጻ ፈቃድ፤ በራስ ውሳኔ ዓለቱን ጠርቦ የማይነቃነቅና የማይናወጥ መሠረት ያለው ግንብ የመገንባት ዓላማ ነው ማለት ነው።  

«ፍሪማሰን» የተባለው ስያሜ በግንበኝነት ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች በተናጠል ሲጠሩበት የቆየ ቢሆንም ከ14ኛው ክ/ዘመን መጨረሻ ጀምሮ በአውሮፓ የህንጻ ምህንድስና ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች በጥቂት ሰዎች ተደራጅተው ራሳቸውን የመጥራት እንቅስቃሴ ጀምረው ነበር። ይሁን እንጂ የማሰን የተናጠል እንቅስቃሴ ቀደም ሲል እንደነበረ ቢሆንም ድርጅታዊ ሕግና ፒራሚዳዊ የብቃት የእርከን ደረጃ ወጥቶለት የተመሰረተው በ1717 ዓ/ም በለንደን ከተማ ነው።። በ1731 በአሜሪካ ፤ በ1736 በስኮትላንድ መሰረቱን አስፋፋ። ከዚያም በ1725 በአየር ላንድ እንደተጀመረ ይነገራል።  አሜሪካ ውስጥ የተቋቋመው በጣም ደርጅቶና ጎልብቶ ዓለም ዐቀፍ ቅርጽ ለመያዝ በቅቷል። 

      ይህ የፍሪማሰን ማኅበር የአውሮፓን የኢንዱስትሪ አብዮት ተጠግቶ የተመሰረተው የህንጻና የምህንድስና ባለሙያዎችን የያዘው እንቅስቃሴ ቅርጹንና መልኩን ለውጦ በሰው አእምሮና አስተሳሰብ ላይ እንደህንጻ የሚያድግ ግብረገብነትን፤ በጎ አድራጎትንና  መልካም ስብእና ያለው ሕብረተሰብን የመፍጠር ዓላማ ባለው መመሪያ ላይ ራሱን በማቆም ሕግና ደንብ አውጥቶ መሥራት መጀመሩን የተጻፈ ታሪኩ ያስረዳል። 

  ምንም እንኳን የፍሪማሰንሪ ማኅበር በኦፊሴል ከአምልኮና ከፖለቲካ አስተሳሰብ ነጻ ነኝ ቢልም በ1723 እና በ1738 ዓም ተሻሽሎ በወጣው የፍሪማሰንሪ ሕገ መንግሥት ላይ እንደተመለከተው የሁሉም ነገር ንድፍ / architect/ ባለቤት «እግዚአብሔር ነው ስለሚል እንቅስቃሴው ሃይማኖት ለበስ እንደሆነ ፍንጭ ከመስጠቱም በላይ ድርጅቱ የራሱ የሆነ ዶግማና መመሪያ ስላለው የእምነት ድርጅት አይደለሁም የሚለው አባባሉ ተቀባይነት እንዳይኖረው አድርጓል።  ድርጅቱ የአንድ ወጥ የሃይማኖት ተቋም ላለመሆኑ እንደመከራከሪያ የሚያቀርበው ጭብጥ የፍሪማሰንሪ አባል ለመሆን  የየትኛውንም ሃይማኖት ተከታይ ወይም የሃይማኖት መጽሐፍ ተቀባይ ወይም የትኛውንም የፖለቲካ መስመር የያዘ ሰው በአባልነት መቀበል መቻሉን በማስረጃነት ያቀርባል።  ድርጅቱ ይህንን ይበል እንጂ አባል የሚሆን ሰው ቀድሞ የነበረውን እምነቱን ይሁን አመለካከቱን እንዲጥል ሳይገደድ የፍሪማሰንን አስተምህሮና ሕግ በተከታታይ ተምሮ በድርጅቱ የረቀቀ አስተሳሰብ ውስጥ እንዲሰጥም ማድረግ በራሱ ቀድሞ የነበረውን የማስቀየር ዘዴ እንደሆነ በተሞክሮ ያዩት ሰዎች በተግባር ያረጋገጡት ሀቅ ነው።

    እንደፍሪማሰንሪ አባባል የጥበቦች ሁሉ /Architect/ የንድፍ ባለቤት እግዚአብሔር ሲሆን ያገኙትን ጥበብ ወደተግባር የሚለውጡት ደግሞ የፍሪማሰንሪ እውቀት የተሰጣቸው ሰዎች ናቸው ይላሉ። ለምሳሌም የኖኅ መርከብ የተሰራቸው በኖኅ የፍሪማሰን እውቀት ነው። የባቢሎን ግንብ ይሁን የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ያለፍሪማሰን እውቀት ፍጻሜ አያገኝም ነበር ባዮች ናቸው። የግብጽ ፒራሚዶች የፍሪማሰን ጥበብ ውጤት ነው። የኖስቲኮች እውቀት፤ የግሪክ ፍልስፍና፤ የፓይታጎረስ ስሌት፤ የዞሮአስተር ትምህርት፤ የቻይና ጥበብ፤ የአልኬሚስቶች ፈጠራ ሁሉ በፍሪማሰን እውቀት ጎልምሶ ወደተግባር የተለወጠ መሆኑን ያምናሉ። 

   ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ሲመለመል የትኛውንም ሃይማኖት የሚከተል ወይም የትኛውንም የሃይማኖት መጽሐፍ የሚቀበል ሰው መሆኑ ችግር የለውም። እንዲተውም አይጠበቅም። ቁምነገሩ አንድ ጊዜ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ከሆኑ በኋላ ድርጅቱን መልቀቅ እንደማይቻል ወይም በምክንያት ከለቀቁ ደግሞ የቆዩበትን የድርጅቱን ምስጢር ማውጣት የሞት ዋጋ እንደሚያስከፍል አስቀድሞ ቃለመሃላ ይፈጽማል። ፍሪማሰንሪ በስብከትና በድለላ የአባልነት ምልመላ አያደርግም። አብዛኛው የዚህ ድርጅት አባላት ፕሬዚዳንቶች፤ ጠቅላይ ሚኒስትሮች፤ ዶክተሮች፤ ፕሮፌሰሮች፤ ጀነራሎች፤ ዳኞች፤ የሴኔትና የምክር ቤት አባላት፤ ቢሊየነሮች፤ ታዋቂ ሰዎችና ከፍተኛ ነጋዴዎች ናቸው። ከአሜሪካ 44 ፕሬዚዳንቶች ውስጥ 14ቱ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባላት እንደነበሩ በግልጽ ሲታወቅ  ከተቀሩትም ውስጥ በምስጢራዊ አባልነት የነበሩ እንዳሉ ይነገራል።

ፍሪማሰንሪ ካሉት 330 (ሠላሳ ሦስት ድግሪ) ማእርጋት አንዱ በሆነው የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ የተወሰኑ ትምህርቶችን አስቀድሞ ከወሰደ በኋላ ወደድግሪ ትምህርቱ ሲገባ ይህንን መሃላ ይፈጽማል።

« ዛሬ የፍሪማሰንሪ አባል ከሆንኩ በኋላ አባል ለሆንኩበት ድርጅት ካልታመንኩ ወይም ብከዳ ወይም ምስጢር ባወጣ በጎሮሮዬ ላይ ስለት ይረፍ፤ ምሳሴ ከስሩ ተነቅሎ ይጣል፤ አጽሜ አመድ ሆኖ ከውቅያኖስ የጥልቁ አሸዋ ውስጥ የተሰወረ ይሁን» ይላል። ለምን?

የፍሪማሰንሪ ዓርማና ሌሎች ምልክቶች ምንድናቸው? ከኢሉሚናቲ ጋር ያላቸው ግንኙነት ምንድነው? ይህንንና ሌሎች ምስጢሮችን በቀጣይ ክፍል ለማቅረብ እንሞክራለን።

Monday, November 17, 2014

«ጌታ ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን» (ዮሐ. 12፥21)

“ንፈቅድ ንርአዮ ለእግዚእ ኢየሱስ - ጌታ ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን”
 (ዮሐ. 12፥21)
( ከጮራ ድረ ገጽ የተወሰደ)
ከግሪክ ወደ ኢየሩሳሌም ለፋሲካ በዓል መጥተው የነበሩ የግሪክ ሰዎች ለሐዋርያው ፊልጶስ ያቀረቡት ሐሳብ ነው። ፊልጶስም ለእንድርያስ ነግሮት ኹለቱም ለኢየሱስ መጥተው የሰዎቹን መሻት አወሩለት። ጌታም፥ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች” አለ። በዚህ መስተጋብር ውስጥ በተለይ ኢየሱስን ማየት የሚፈልጉ ሰዎችንና ለእነርሱ ኢየሱስን ማሳየት የቻሉ አገልጋዮችን መመልከት እንችላለን።
ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ኢየሱስን የሚፈልጉና ኢየሱስን ከፈላጊዎቹ ጋር የሚያገናኙ ምን ያኽል ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ማንሣት ይኖርብናል። በዚህ ዘመን በቤተ ክርስቲያን እየታየ ያለው አንዱ ችግር፥ ጌታ ኢየሱስን የሚፈልግ ምእመንና እርሱን የሚያሳይ አገልጋይ ቍጥር እየተመናመነ መምጣቱ ነው። ርግጥ የምእመናን የልባቸው መሻትና የነፍሳቸው ጥያቄ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ብዙዎቹ አገልጋዮች ግን ዕረፍተ ነፍስ ወደ ኾነው ጌታ ምእመናኑን ማድረስ ሲገባቸው ወደ ራሳቸው ይስቧቸዋል። በዚህ ምክንያት ምእመናን የክርስቶስ ተከታዮች ሳይኾኑ የእነርሱ ተከታይና አድናቂ እንዲኾኑ፥ ክርስቶስን ሳይኾን እነርሱን እንዲመለከቱ፥ የሕይወታቸው ዋና ምሳሌም ክርስቶስ ሳይኾን አገልጋዮቹ እንዲኾኑ በማድረግ፥ ኢየሱስን ፈልገው የመጡትን ምእመናን ወደ ኢየሱስ ሳያደርሷቸው እነርሱ ዘንድ በማስቀረት የእነርሱ ሎሌ ያደረጓቸው አገልጋዮች ጥቂቶች አይደሉም። 

እንጠብቀዋልን ብለው ከጌታ በዐደራ የተቀበሉትን መንጋ የራሳቸው የግል ንብረት በማድረግ በተሳሳተ መንገድ ስለ መሩት፥ ብዙው ምእመን ወደ ቤተ ክርስቲያንም ኾነ ወደ መንፈሳውያን ጉባኤዎች የሚኼደው ክርስቶስን ለማየት ሳይኾን ተከታዮቻቸው ያደረጓቸውን አገልጋዮች ለማየትና ለእነርሱ ለመገበር ይመስላል። ይህ ለምእመናን ትልቅ ኪሳራ ለአገልጋዮቹም ከባድ ቅጣትን የሚያስከትል ዐደራ በልነት ነው።
ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ብቻ ሙሽራ ናት። ዘወትር ልትፈልግና ልትሻ የሚገባት ውዷን ኢየሱስን ብቻ መኾን አለበት። ጌታ ለሙሽራው ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችን የሰጠው ለቤተ ክርስቲያኑ እንጂ ለአገልጋዮቹ ጥቅም እንዳልኾነም ሊታወቅ ይገባል። አገልጋዮቹ በቤተ ክርስቲያን ላይ እንዲሠለጥኑባት፥ ትልቅ ስምና ዝናን እንዲያገኙ፥ እንዲበለጽጉና የመሳሰለውን ምድራዊ ትርፍ እንዲያተርፉ አይደለም። ቃሉ እንደሚመሰክረው፥ ጌታ አገልጋዮችን ለቤተ ክርስቲያን የሰጠው፥ “ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት፥ ሙሉ ሰውም ወደ መኾን፥ የክርስቶስም ሙላቱ ወደሚኾን ወደ ሙላቱ ልክ እስክንደርስ ድረስ፥ ቅዱሳን አገልግሎትን ለመሥራትና ለክርስቶስ አካል ሕንጻ ፍጹማን ይኾኑ ዘንድ” ነው (ኤፌ. 4፥12-13)። ስለዚህ አገልጋዮች ይህን ተረድተው ለተሰጣቸው ተልእኮ መፋጠንና ኀላፊነታቸውን በሚገባ መወጣት አለባቸው።
ምእመናንም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የእነርሱ መጋቢዎች እንጂ አምላኮቻቸው እንዳልሆኑ ዐውቀው እንደ እግዚአብሔር ቃል የሆነውን ትምህርታቸውን ሊቀበሉ፥ የሕይወታቸውን መልካም ምሳሌነት ሊከተሉ፥ የኑሯቸውንም ፍሬ እየተመለከቱ በእምነታቸው ሊመስሏቸው ይገባል። ከዚህ ዐልፈው እነርሱን በማክበር ስም ከማምለክ ያልተናነሰ ተግባር በመፈጸም የመጥፎ ሥራቸው ተባባሪ መኾን የለባቸውም። ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ኢየሱስን የሚሹ ምእመናን ኢየሱስን የሚያሳዩ አገልጋዮች በእጅጉ ያስፈልጋሉ።

ዐዲሱ ዓመት ጌታን የምንፈልግበት ጌታን የምናሳይበት ዓመት ይሁንልን
(በጮራ ቍጥር 46 ላይ የቀረበ)

Wednesday, November 12, 2014

ግብረ ሰዶማዊነትና የእኛ ዘመን አገልጋዮች

( ከአቤኔዘር ተክሉ )

    ስለግብረ ሰዶማዊነት በሁለት የተለያዩ ክፍሎች መጻፌና በሁለቱ ክፍሎችም ለጊዜው የነበረኝን ሃሳብ ማጠቃለሌን አልዘነጋውም፡፡ ነገር ግን አሁንም ግብረ ሰዶማዊነት የቤተ ክርስቲያንን ቅድስና ከማርከስ፤ ምድራችንን ለከፋ ጉስቁልናና ርኩሰት አሳልፎ ከመስጠት ያላቆመ ፍጹም ወደመስፋፋት የሄደ ክፉ ርኩሰት ነውና ዳግም ይህንን ርዕስ ማንሳት አስፈልጎኛል፡፡ ለዚህ እውነታ ብዙ የቅርብ ጊዜ ማሳያ ብቻ ማንሳቱ በቂ ይመስለኛል፡፡

    ድርጊቱ የተፈጸመው በምስራቁ የሃገራችን ክፍል ነው፡፡ የሠላሳ ሁለት አመት አጐት የአራት አመት የወንድም ልጁን በእረኝነት ሥፍራ በመሄድ ጫት እንዲቅም ያግባባዋል፡፡ ህጻኑ እንቢ ቢልም ያስገድደዋል፡፡ ጫት እንዲቅም ካስገደደው በኋላ ልጁ ራሱን መቆጣጠር ሲያቅተው ልጁን የግብረ ሰዶም ጥቃት ይፈጽምበታል፡፡ የልጁ የሰገራ ማውጫ ሙሉ ለሙሉ ይቀዳዳል፡፡ ከሆዱ የወጣው የውስጠኛው የሰገራው ክፍል ሙሉ ለሙሉ የልጁን ጠረን ይለውጠዋል፡፡ ልጁ ፍጹም ራሱን ስቶ ሲወድቅ ከወደቀበት ቦታ ተሸክሞት ከወላጆቹ ጓሮ አምጥቶ ጥሎት ይሰወራል፡፡ ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ የልጁ ህይወት ያልፋል፡፡

    ሌላም ብንጨምር፦ አንድ “ስመ ገናና” አገልጋይ እንዲህ ያለ ነውር እንደሚፈጽም በምስክር ይረጋገጥና ብዙዎች ተረባርበው ሊመክሩት ይፈልጋሉ፡፡ ነገር ግን ከማስመሰልና የሽንገላ እሺታ ከማሳየት በቀር ከነገሩ ሳይታቀብ ይቀራል፡፡ በኋላ ይባስ ብሎ በአቋም፤ የሠራው ትክክል እንደሆነና ይቅርታ መጠየቅ እንደማያስፈልግ ከብዙ ደጋፊዎቹ ጋር በግልጥ በአቋሙ ይጸናል፡፡ ወንድሞቹን ይቅርታ ሳይጠይቅ በግልጥ ለሠራውና ሌሎችን ላሰናከለበት ኃጢአቱ ንስሐ ሳይገባ እንደዋዛ ዛሬም አለ፡፡ በድርጊቱ የተጠቁት ወንድሞች ግን “እንዲህ ያለ ነገር እያደረገ በአንድ የኃይማኖት ጥላ ሥር አንቀመጥም” በማለት ወደሌላ የእምነት ተቋም ራሳቸውን አገለሉ፡፡ (ርቀው ወደሌላ የኃይማኖት ተቋም እንዳይሄዱ ብዙ ርብርብ ቢደረግም አልተሳካም፡፡)

    በመንግስትም ደረጃ በዘንድሮው የይቅርታ መመሪያ ውስጥ ይቅርታ ከሚያሰጡ ወንጀሎች መካከል ግብረ ሰዶማዊነትም እንዲካተት ጥረቶች “መደረጋቸውና መሳካቱንም” ጭምጭምታዎች ይሰማሉ፡፡ ጉዟችን ወዴት ይሆን? እንዲህስ እስከምን ድረስ ነው የምንጓዘው?

      ግብረ ሰዶማዊነት እግዚአብሔር የፈጠረውን ፍጥረት ሙሉ ለሙሉ በመቃረን የሚፈጸም ርኩሰት ነው፡፡ ቃሉም “ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵስነት አሳልፎ ሰጣቸው”(ሮሜ.1፥24) እንዲል ቅዱሱን የእግዚአብሔር ፍጥረት በመቃረናችን ምክንያት የገዛ ኃጢአታችን “ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ እንደሰጠን” ትልቅ ምስክር ነው፡፡(ሮሜ.1፥26)

   ጥቂት የማይባሉ አገልጋዮች “ለአገልግሎት” ወደክፍለ አገር ወይም ወደውጪ አገር ሲወጡና ጨርሰው ሲመለሱ ጥንድ ጥንድ እየሆኑ ሹልክ ብለው ለሴሰኝነትና ለዝሙት እንደሚገባበዙ ፀሐይ የሞቀው እውነት ሆኗል፡፡   በአቶ አስማማው ኃይሉ በተጻፈውና “ኢህአሠ” በተባለው ቅጽ አንድ መጽሐፍ ላይ ከትግል መልስ ደራሲው አንድ ታጋይ ነገረኝ ብሎ ሲጽፍ ፤ ታጋዩ ማደሪያ አገኘሁ ብሎ ወደ አንድ ቤተ ክርስቲያን ሊጠለል ጎራ ባለበት ወቅት ሌሊቱን ሙሉ  የገጠመው ሌላ ትግል ይኸው ከግብረ ሰዶማውያን ጋር ያደረገው ያለመደፈር ትግል እንደነበር በግልጥ አስቀምጦታል፡፡ በእርግጥ ዛሬ በገዳም ካሉት ጥቂት የማይባሉ መነኰሳትና መነኰሳይያት፤ እንዲሁም  በወንዶችም ሆነ በሴቶችም ዘማሪዎቻችን መንደርም የምንሰማው ነገር ጆሮን ጭው የሚያደርግ ነው፡፡ (እንደአገር ስናስብ ደግሞ በካርዲናሎቹና በፓስተሮቹም መካከል አጸያፊ የርኩሰት ነገር ጆሯችን ከመስማት አልታከተም!!)   

     ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ያሉ ኃጢአተኞችን በግልጥ ከመቃወም እየደከመች የመጣች ይመስላል፡፡ ምክንያቱም የግብረ ሰዶማውያን “አገልጋዮችን” የጨለማ ሥራን ከመግለጥ (ኤፌ.5፥11)፤ ሌሎች ሰዎችም ከክፋታቸው እንዳይተባበሩ ከማስጠንቀቅና መክራ እንዲመለሱ ከማድረግ ድምጿን አሰልላለች፡፡ ስለዚህም ሌሎች ብዙዎች ግብረ ሰዶማውያኑን  “በርቱ፤ እኛም ከጎናችሁ ነን” ከማለት አልፈው ለግብረ ሰዶማውያኑ ድጋፍ ሲሰጡና ሲሟገቱላቸው በአይናችን እያየን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ኩልልና ጥርት ያለ የተቃውሞ ድምጿን ልታሰማ ግድ የሚላት ጊዜ አሁንና አሁን ነው፡፡ ከረፈደ በኋላ መሯሯጥ ድካም እንጂ ሚዛን የሚደፋ ትውልድ የማዳን ሥራ አይሠራም፡፡

    የሰዶም ሰዎች ያደርጉት የነበረው የክፋት ድርጊታቸውን እንደመልካም ከመቁጠር አልፈው እነርሱ የሚያደርጉትን ነውር የማያደርጉትን ሰዎች ይቃወሙ፤ የእነርሱን ነውር እንዲቀበሉ ያደርጉም ነበር፡፡ በአገሪቱ ካሉት ሰዎች ሁሉ ጋር ነውራቸውን ከፈጸሙ በኋላ  እንግዳ ሰዎች በመካከላቸው በተገኙ ጊዜ ከእንግዶቹ ጋር ሊፈጽሙ (በሎጥ ቤት የመጡትን መላዕክት ሲያዩ ወደአዲስ መጎምጀት መጥተዋልና!) የኃይልን መንገድ እንደተጠቀሙ፤ ጻድቁንም ሎጥ እንደተጋፉትና በሩን ሊሰብሩ እንደተገዳደሩ ታላቁ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡(ዘፍ.19፥5-9) ሰው ለእግዚአብሔር ባህርይና ለተፈጥሮ እውነት መገዛት ሲሳነው የኃጢአት መሻቱ ድንበር አልባ ይሆናል፡፡ ሁሉንም ርኩሰት ከመፈጸም የሚያግደውም የለም፡፡

   ዛሬ ላይ ድሆች ሃገራትን ለመርዳት የሚዘረጉ ብዙ የእርዳታ እጆች ስውር አጀንዳቸው ግብረ ሰዶምና ሰዶማዊነት ለመሆኑ ብዙ ማስተንተኛ ማቅረብ አያስፈልግም፡፡ ግብረ ሰዶምን በግልጥ የተቃወመች ብቸኛይቱ አፍሪካዊት ሃገር ይህንን በግልጥ አይታዋለችና፡፡ እኛ “ከቃል ባልዘለለ” ክርስትናችን በከንቱ ስንመካ ከአገራችን ቀድማ ግብረ ሰዶማዊነትን በግልጥ አለም አቀፍ በሆነ ዕይታ ህግን አስደግፋ ተቃውሞ ያሰማችው አፍሪካዊት አገር ኡጋንዳ ናት፡፡ በእርግጥ የእኛ ወንጀል ህግ “ግብረ ሰዶማዊነት ወንጀል ነው” ይላል፤ ግን የአገሪቱን ትልልቅ ከተሞች ጎዳና እያጥለቀለቁ ያሉትና ቁጥራቸው የማይናቅ አገልጋዮችን እንደወረርሽኝ በሽታ እየወረሱት ያሉት “ሴት እንተኛ አዳሪዎች” ብቻ ሳይሆኑ ግብረ ሰዶማውያኑም ጭምር ናቸው፡፡ ህጉ ቢኖርም ለነዚህ ምድርን ለሚያረክሱ “ወገኖች” ግን ጥርስ የሌለው አንበሳ ሆኖ ተቀምጧል፡፡

   የኡጋንዳ መሪዎች ያንን የመሰለ ቁርጥ ያለ አቋማቸውን በግብረ ሰዶማዊነት ላይ ሲያሰሙ፤ ሰለጠን ያሉቱ ምዕራባውያን የኡጋንዳን ድርጊት “የሰይጣን ድርጊት” አድርገው ለማቅረብ ጊዜ አልወሰደባቸውም፡፡ (እግዚአብሔርስ ይቅር ሰይጣን እንኳ እንዴት ታዝቦን ይሆን?!)  የእኛ አገልጋዮች ግን ዛሬም ግብረ ሰዶማዊነትን በመካከላችን ያሽሞነሙኑታል፡፡ ከዓመታት በፊት ግብረ ሰዶማውያኑም አለም አቀፍ ስብሰባ አፍንጫችን ስር ባለችው አዲስ አበባ አድርገው አባላታቸውን መልምለው ሲሄዱ እንኳ ዝም ጭጭ ሆኗል ክርስትናችን፡፡ እንኪያስ ወርቁ ለምን ይሆን የደበሰው?
   ግብረ ሰዶማውያንን ለመቃወም የአገልጋዮች “ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ” ማለት ከበለጠብን እንኪያ እኛስ ከእነርሱ በምን እንሻላለን? መንፈሳዊነት መለኪያው የአገልግሎት ስኬት ሳይሆን የህይወት ጥራት ነው፡፡ ጌታ ጥራት ከሌለው ሸንጋይ መንጋ ጋር ህብረት እንደሌለውና ጥራት ካለው ጥቂት አማኝ ጋር ብቻ ህብረት እንዳለው በጌዴዎንና በሐዋርያት ህይወት አይተናል፡፡ ምክራችን፣ ጩኸታችን፣ ተግሳጻችን፣  ቁጣችን … “ምክር ለምኔ” ያሉ ግብረ ሰዶማውያን አገልጋዮች በንስሐ ተመልሰው የበደሏቸውንና ያሰናከሏቸውን ወንድሞች ይቅርታ በመጠየቅ እንዲመለሱ ነው እንጂ በመካከላችን ተቀምጠው ሌሎችን ለማጥቃት እንዲያደቡ አይደለም፡፡

    የእግዚአብሔርን ምህረት የሚያሸንፍ ወይም የሚበልጥ ኃጢአት የለም፡፡  እንዲህ የምንለው ግን በንስሐ ለሚመለሱ እንጂ ልብን ለሚያደነድኑ አመጸኞች አይደለም፡፡ ጌታ ለምድሪቱ ምህረትና የንስሐን ልብ ያውርድላት፡፡ አሜን፡፡

Wednesday, November 5, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን መድኅን? ዋስትና? ጠባቂ? ወይስ ምንድነው?



1/ ማኅበረ ቅዱሳን ማነው? 

ከማኅበረ ቅዱሳን መሥራቾች አንዱ እንደሆነ የሚናገረው የሜሪላንዱ ኤፍሬም እሼቴ  ስለማቅ ጥንስስ እንደተረከው ብላቴ ጦር ካምፕ ውስጥ ተቀፍቅፈን፤ ዝዋይ ላይ በመፈልፈልና አዲስ አበባ ላይ ኅልውና አግኝተን ሕይወት ዘራን ሲል ይተርክልናል። የኅልውናቸውም መስራቾችና ፈልፋዮች ማንነት ኤፍሬም ዘለግ አድርጎ ሲናገር በኅብረተሰባዊት ኢትዮጵያ በመንደር ምሥረታ ታሪክ ውስጥ ብዙ ድርሻ የነበራቸው ሰዎች ባሉበት ሁኔታ የዳቦ ስም ወጥቶላቸው «ማኅበረ ቅዱሳን» እንደተባሉ «አደባባይ» በተሰኘው መካነ ጦማሩ እንዲህ እያለ ያወጋናል።
«ተማሪው በጋምቤላ፣ በመተከል፣ በወለጋ … ጎጆ ቤት ሲሠራ፣ ተፈናቃዩን ሲያቋቁም ቆይቶ ተመለሰ። በደህና ወጥቶ ለመመለስ ያልቀናውም ነበር። እነዚያ መንደር ሊመሠርቱ የወጡት ታላላቅ ወንድሞቻችን በየዛፉ ሥር፣ በየመንገዳቸው ጸሎተ ማርያም ማድረሳቸውን፣ ሲችሉም ተገናኝተው ቃለ እግዚአብሔር መስማታቸውን እንዳላስታጎሉ ሲናገሩ ሰምቻለሁ። እኛን ቃለ እግዚአብሔር ያስተማሩን የዚያ “መንደር መሥራች ትውልድአካላት የሆኑ ወንድሞች ናቸው። ወደ ዝዋይም የላኩን እነርሱ ናቸው። እኛ እና እነርሱ በአንድ ላይ ስንሆን ጊዜ በጋራ “ማ/ቅዱሳን” ተባልን።»
በእርግጥ የዚያን ዘመን መንደር መሥራች ትላልቅ ወንድሞች የተባሉት ማኅበሩን የመሠረቱበት ዓላማ ግልጽ ባይሆንም ኤፍሬምን ጨምሮ አብዛኛው የማኅበሩ አባላትን ግን ያሰባሰባቸው እምነታቸው ስለመሆኑ ከጥርጣሬ የሚወድቅ አይደለም። ያሳደጋቸውም የቤተ ክርስቲያን ቅናት ብቻ ነበር። ሲመሰረትም የወንድሞች ማኅበር «ማኅበረ ቅዱሳን» ከዚያ ከትንሹ ጅምር ተነስቶ ይህንን ያህል በመግዘፍ ሀገራዊ ማኅበርና የሲኖዶስ ጉባዔ የየዓመቱ የመነጋገሪያ አጀንዳ ይሆናል ብሎ የገመተ አይኖርም ይሆናል። ምናልባት ትላልቅ ወንድሞች የተባሉት እግር በእግር እየተከታተሉና እየኮተኮቱ ያሳደጉበትን  ኅቡእ አጀንዳ ራሳቸው ያውቁ እንደሆን እንጂ ዛሬም ድረስ ከጥቂቶች በስተቀር አብዛኛው የማኅበሩ አባላት እያገለገሉ ያሉት ቤተ ክርስቲያናቸውን እንደሆነ መገመት ይቻላል።
 ነገር ግን ግዝፈቱ እውን እየሆነ ሲሄድ ወደ ረጅም ህልምና ራእይ የመድረስ ስንቅ ሳይቋጥር አልቀረም። ኅልውናውን የሚያስጠብቅበትን የሕግ ማዕቀፍ መጎናጸፍ፤ የድርጅት ኃይል ማሳደግ፤ የገንዘብ አቅም ማጎልበት፤ የዓላማና ግብ ስትራቴጂ መቅረጽ ወዘተ ራሱን የሚያስጠብቅበት ቅርጽና መዋቅር እየያዘ እንደመጣ እርምጃዎቹ ዋቢዎቻችን ናቸው። ዓላማና ግብ ሳይኖረው ኅልውናውን ማስጠበቅ እንደማያስፈልገው ይታወቃል።  እዚህ ይደረሳል ብለው ያልገመቱ ቢገኙም ሂደት ራሱ በሚፈጥረው ስኬት ከተነሳበት ሃሳብ ወጣ ባለ መልኩ ወደሚፈልጉበት አዲስ ግብ ለመድረስ  ስትራቴጂ ቢኖራቸው አያስገርምም።  ትንሹ ትንሣዔው ስኬትን ሲያጎናጽፈው መድረስ የሚፈልገው ዓላማ ሊኖረው የግድ ስለሆነ ለዚህ ደግሞ ሁሉን መስዋዕትነት እንደሚከፍል አይጠረጠርም።
ማኅበረ ቅዱሳን በጥቂቶች አስተሳሰብ በእቅድ የተመሠረተ፤ በተራው አባል ግን በአጋጣሚ እግዚአብሔር ፈቅዶ የተቋቋመ ያህል የሚታሰብ ድርጅት ነው። መቋቋሙ በቀና ዓይን ቢታይ ባያስከፋም በተግባር ግን እየታየ የቆየው የተገላቢጦሽ መሆኑ እርግጥ ነው።

2/ ማኅበረ ቅዱሳን ለማኅበረ ካህናቱ ምንድነው?

ዛሬ ላይ ማኅበሩ ያለው ስትራቴጂ  የተነሳበት ነበር ወይ? ብለን ብንጠይቅ መልሳችን አይደለም ነው።  ከላይ እንደተመለከትነው ማኅበሩ ሲነሳ አብሮ ለመዘመርና ለማማር የተሰባሰበ እንጂ የዚህን ያህል ስፋት ያለው ርቀት እሄዳለሁ ብሎ አልነበረም። ይህ ሲባል ግን የሚሄድበትን ርቀት እየለኩ የሚመሩት ሰዎች አልነበሩትም ማለት አይደለም። በዚህም የተነሳ ጉዞውን ለማሳካት የሚሄድበት ርቀት ከተነሳበት ዓላማ ጋር በእጅጉ የሚጣረስ ሆኖ ይታያል።  ተወዳጅነት ያገኘውን ያህል የተቀባይነት ማጣት ግጭትና ዓላማን ለማሳካት የሚደረገው ስልት ከፊት ለፊት ተቃውሞ መፍጠሩ አልቀረም። ለዚህም ነው ማኅበሩን ባልተቀበለው የቤተ ክህነቱ አባላት ዘንድ እርቅ ወደሌለው ቅራኔ እየከተተው የሚገኘው። ማኅበሩ አብዛኛውን በሚል ደረጃ በአባልነት የያዛቸው የየአጥቢያውን ሰንበት ተማሪዎች፤ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች እንዲሁም በራሳቸው ተነሳሽነት ተሰባስበው በዓመታዊው የጥምቀት በዓል ላይ ታቦታት ሲወጡና ሲገቡ ቄጠማ በመጎዝጎዝ ይሳተፉ የነበሩትን ወጣቶች ማኅበሩ መልክና ቅርጽ በመስጠት ወደራሱ ዓላማ በመሳብ «የጥምቀት ተመላሾች ማኅበር» በሚል ያደራጃቸው ናቸው። ማኅበሩ የፖለቲካ ድርጅት የሆነ ያህል አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት በሚጠሉ ፖለቲከኞች ሁሉ እንደ አንድ አስፈላጊ አካል መቆጠሩ ሳይዘነጋ መሆኑንም ያስተውሏል። የዚህ አብሮነት ያገናኛቸው የእምነት ስምምነት ውል መኖሩ ሳይሆን ፖለቲካዊ ስልት መሆኑን ለማወቅ ብዙም ምርምር አይጠይቅም።
 ከዚያ በተረፈ ማኅበረ ቅዱሳንን ከጥቂት የጥቅም ተጋሪዎችና በፍርሃት ቆፈን ከተያዙት በስተቀር አብዛኛው የቤተ ክህነቱ ሰው ግን «ዓይንህን ላፈር» እንዳለው ይገኛል። የማኅበረ ቅዱሳን ኅልውና እንደሪፈረንደም በቤተ ክህነቱ አባላት ድምጽ የሚወሰን ቢሆን ኖሮ አንድም ቀን ኅልው ሆኖ ሊኖር እንደማይችል በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል።  ምንም እንኳን ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክህነቱን ኃይል ማሳኝና አማሳኝ እያለ በደፈናው ንቆ ቢጨፈልቅም ማኅበሩ እንደሚገምተው በቀላሉ እጁን የሚጠመዘዝ ኃይል አይደለም። የቤተ ክህነቱ ሰው  በክህነት አገልግሎት ላይ ስለሚገኝ  ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ ያለው በመንፈሳዊው የክህነት አገልግሎት ስር ነው።  ስለሆነም የማኅበረ ካህናቱን ኃይል ከህዝበ ክርስቲያኑ መነጠል አይቻልም። ስለዚህ የዚህ ኃይል ማኅበረ ቅዱሳንን መቃወም መቻሉ የማኅበሩን የወደፊት ኅልውና የመወሰን አቅም አለው። ማኅበሩ ደግሞ ከዚህ ከክህነት አገልግሎቱ ኃይል ጋር ዓይንና ናጫ ሆኗል። በማኅበሩ የሚደረገው የስለላ፤ የመረጃ፤ የስም ማጥፋት፤ የአድማ፤ ከስራ የማስባረር፤ ዋስትና የማሳጣት፤ መተማመንን የማዳከም ተግባራቱ በክህነት አገልጋዩ ዘንድ በሰፊው ስለታወቀ መቼም ቢሆን መተማመን እንዳይኖር አድርጎታል።

 በማኅበረ ቅዱሳንና በማኅበረ ካህናቱ መካከል ያለው የዓላማ ቅራኔ የሚፈጥረው ሽኩቻ ቤተ ክርስቲያኒቱን ከማዳከም በዘለለ አንዳችም ትርፍ አላስገኘም። ማኅበረ ቅዱሳን ዓላማው አጠቃላይ ማኅበረ ካህናቱን በራሱ ፖሊሲና ስትራቴጂ ማጥመቅ ሲሆን ማኅበረ ካህናቱ ደግሞ ይህ ማኅበር ከቤተ ክርስቲያን ተወግዶ ማየት በመሆኑ ልዩነቱን የማይታረቅ አድርጎታል።
ማኅበረ ቅዱሳን በካህናቱ በኩል የሚታየው እንደፍልስጣ ኃጢአትን መዝግቦ እንደሚከስ ባላንጣ እንጂ እንደቅዱሳን ስብስብ አይደለም። ማኅበረ ቅዱሳን ለማኅበረ ካህናቱ የፈየደው አንዳችም ነገር አለ ተብሎ አይታሰብም። ምክንያቱም ማኅበሩ በክህነት አገልግሎት አያግዝም። በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ከማኅበረ ካህናቱ የተሻለ ዕውቀት የለውም። ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ከካህናቱ በተሻለ ሁኔታ በዕለት ዕለት ቅርርብ አይመሰከርለትም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ማለት ለካህናቱ ምንም ማለት ነው።

ይህ ባለበት ሁኔታ ሳለ መልካም ግንኙነት መመሥረት የሚችልበትን ዕድል በማበላሸት የካህናቱን ሥነ ምግባር በማጉደፍ፤ አደባባይ ላይ በማዋልና ስም በማጥፋት ላይ በመሰማራቱ ከካህናቱ ጋር ለመተሳሰር ምንም ድርሻ የሌለው ማኅበር ሆኖ ቀርቷል።  ሁሉም ሰው «ነግ በኔ» በሚል ፍርሃት በአንድነት በተቃርኖ የቆመበት ማኅበር ነው። ይህ  የቅራኔ ግንኙነት መቼ ይሻሻላል? ቢባል መቼም የሚታረቅ አይደለም እንላለን። የማኅበሩ ዓላማና ግብ በራሱ ጳጳሳት የሚመራ ሲኖዶስ አቋቁሞ፤ በራሱ ጳጳሳት የሚሾሙ ማኅበረ ካህናትን መስርቶ አሁን ያለውንና የማይቀበለውን የማኅበረ ካህናት አስወግዶ የራሱን መዋቅር መዘርጋት በመሆኑ አሁን ካለውና ከሚቃወመው ጋር መቼም ቢሆን እርቅ ይኖረዋል ተብሎ አይጠበቅም።ስለሆነም ማኅበሩ ከአጠቃላይ ማኅበረ ካህናት ጋር ሰላም ሊመሰርት አይችልም ብሎ መደምደም ይቻላል። ማኅበሩም ራሱ ዓላማውን ለማሳካት የሚሄድበት መንገድ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናት ጋር ለመስማማት የሚያስችል ተፈጥሮ ላይ የተመሠረተ አይደለም። 

3/ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ምዕመናን ያበረከተው ምንድነው?

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ መቅደሱ የክህነት አገልግሎት ላይ የተሰማራ ባለመሆኑ ለምዕመናኑ ከካህናቱ በተሻለ የሚሰጠው አገልግሎት ይኖራል ተብሎ አይታሰብም።
 በየአድባራቱ ወይም በየገዳማቱ ከምዕመናን አባላቱና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶች ጋር ያለውን ቅርርብ በመጠቀም ዓላማና ግቡን ለማስረጽ በሚያደርገው ትግል ውስጥ ከካህናቱ በኩል ያለውን  ተቃውሞ ለመከላከል ሲል ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆር በመምሰል ስም በማጥፋት፤ በአድማና በህውከት ከቦታቸው እንዲነሱ፤ እንዲጠሉ በማስደረግ ወይም ዝም ጭጭ ብለው፤ አንገታቸውን ደፍተው እንዲኖሩ በሚያደርገው ተግባሩ ያተረፈው ነገር ቢኖር የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ወደሌሎች ቤተ እምነቶች መኮብለል ብቻ ነው። በሐረር፤ በድሬዳዋ፤ በደቡብ፤ በምዕራብና በምሥራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት እንደጎርፍ ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው የኮበሉለት ማኅበረ ቅዱሳን በየቦታው በፈጠው ሁከትና ብጥብጥ የተነሳ ነው።

   በእርግጥ አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ባሉበት መርጋት ትልቅ ሚና ተጫውቷል ቢሉም ተረትና እንቆቅልሽ ለማስተማር ካልሆነ በስተቀር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን የመተካት አንዳችም አቅም የሌለው ድርጅት ነው።
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከ1960 ዓ/ም በፊት ከ1% በታች የነበሩት የፕሮቴስታንት ቤተ እምነቶች እስከ 1984 ዓ/ም ድረስ 5.5% ሲደርሱ እስከ 1994 ዓ/ም ድረስ በዐሥር ዓመት ውስጥ ብቻ 10.2% ለመድረስ በቅተዋል። አሁን ባለው ስታስትስቲክ የፕሮቴስታንቱ ቁጥር ከሀገሪቱ ሕዝብ ውስጥ 18.6% ፐርሰንት መድረሱን ያሳያል። በተቃራኒው ደግሞ ከሀገሪቱ ሕዝብ 60% ገደማ የኦርቶዶክስ ቤተ እምነት ተከታይ የነበረው ቁጥር በአስደንጋጭ መጠን ወደ 43.5% ያሽቆለቆለው ባለፉት ዐሥርተ አመታት ውስጥ መሆኑ የሚያሳየን ነገር የማኅበረ ቅዱሳንን የስብከትና እንቅስቃሴ ምዕመናኑን ከመበተን ይልቅ በቤታቸው የማቆየት አቅም እንዳልነበረው አረጋጋጭ ነው። 
ወደፕሮቴስታንቱ ጎራ ከኮበለለው 17% ገደማ የሚሆነው ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የወጣ መሆኑ እርግጥ ነው። ማቅ እንኳን ከሌላ ቤተ እምነት ሰብኮና አሳምኖ ሊያመጣ ይቅርና ያሉት ተረጋግተው እንዳይኖሩ ሲሰራ የቆየ መሆኑ አይታበልም። የማኅበረ ቅዱሳን የተረትና እንቆቅልሽ አስተምህሮ ማንንም ሰብኮ መመለስ እንደማይችል ይታወቃል።

  የሁሉም ነገሮች ችግር መነሻው ማኅበረ ቅዱሳን ነው ባይባልም ምዕመናን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ሲሳሳቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት በኩል አስተምሮና ናዝዞ ከመመለስ ይልቅ ተሐድሶ፤ጴንጤ፤ መናፍቅ፤ ሌባ፤ ዘማ፤ ነፍሰ ገዳይ እያለ በመፈረጅ በፍርሃት እንዲኮበልሉና እንዲሰደዱ በማድረግ በኩል የማኅበረ ቅዱሳን ድርሻ ወደር የለውም። ማኅበረ ቅዱሳን ኖሮ ቤተ ክርስቲያን ከተጠቀመችው ይልቅ ማኅበሩ በየቦታው በሚፈጥረው ሁከትና ግርግር የተጎዳችበት ይልቃል።

4/ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ያበረከተው አገልግሎት እውነት እንደሚወራው ነው?

ሲጀመር ጀምሮ ማኅበረ ቅዱሳን የካዝና ቋቱንና ኪሱን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አያሳይም። በሞዴላ ሞዴል ተጠቀም! ሂሳብህን አስመርምር! በምትሰራው ነገር ሁሉ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ ጠይቅ! መባሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥር የመሆኑ ማረጋገጫ  ካልሆነ በስተቀር ሀብትና ንብረቱን ስለመውረስ የሚያውጅ ድርጊት አልነበረም።  ከአባ ሠረቀ ብርሃን ጋር ያጋጫቸው ይኸው ዘራፍ ባይነቱ እንጂ አባ ሠረቀ ብርሃን ማኅበሩን የማፍረስ ዓላማ ስላላቸው አይደለም። ማኅበሩ የትኛውንም የቤተ ክርስቲያኒቱን ቁጥጥር መቀበል አይፈልግም። ለምን?

   ማኅበሩ ፈቃደኛ አለመሆኑ የሚያመለክተው ቢኖር አንድም ራሱ ብቻ አዋቂ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያኒቱን አሠራር ይንቃል፤ አለያም ምን እየሰራ እንዳለ እንዲታወቅበት አይፈልግም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳንለቤተ ክርስቲያን  አበረከትኩት የሚለው አገልግሎት የስም፤ የዝናና ራስን ለማሳበጥ የሚጠቅምበት ስልታዊ እንቅስቃሴ ከመሆን የዘለለ አልነበረም ማለት ነው። 
ለምሳሌ ጣሊያን ኢትዮጵያን ከወረረች በኋላ በመንገድ ሥራ፤ በውሃ ቧንቧ ግንባታ፤ በመብራት ዝርጋታ ላይ ተሰማርታ ነበር። ኢጣሊያ ያንን ማድረጓ ወረራዋን ፍትሃዊ ሊያሰኘው እንደማይችለው ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን ፈጸምኳቸው የሚላቸው አንዳንድ እንቅስቃሴዎች  የማኅበሩን ኢፍትሃዊ እርምጃዎችን ፍትሃዊ ሊያሰኙት በጭራሽ አይችሉም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ተመስርቶ ከተከናወኑት ሥራዎች ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ የደረሰባት ወከባና ሁከት ዐሥር እጅ ይልቃል። ደግሞስ በ22 ዓመት ዓመት እድሜው «ጧፍና ሻማ ረዳሁ» ከሚል በስተቀር የጧፍና ሻማ ማምረቻ ሲገነባ አልቆየም። ይልቁንም ቤተ ክርስቲያኒቱን መስሎና አክሎ የሚንቀሳቀስበትን የግሉን ሕንጻና ሀብት ሲገናባ ኖሯል።  ሠራሁ የሚለውም ቢሆን በአካፋ ከዛቀው በማንኪያ እያካፈለ ላለመሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱ ባደረገችው ምርመራ አልመሰከረችለትም።  ያለውን የካዝና አቅም ከቤተ ክህነቱ መሸሸጉ የሚያስረዳን ነገር ቢኖር በአካፋ የዛቀውን በማንኪያ መስጠቱን እንጂ ሐቀኛነቱን አይደለም። አመራሮቹ እስከ 500 ሺህ ብር እየተበደሩ ሳይከፍሉ የውሃ ሽታ የሆነውን የገንዘብ ወጪ መረጃ በምን ሂሳብ ሊያወራርዱት? ተብሎ ለሚቀርበው መጠይቅ ሕጋዊ መልስ የለውም።  ስለዚህ ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያኒቱ ጋሻዬ፤ መከታዬ ልትለው የምትችልበት ምንም ምክንያት የላትም።

5/ ለማኅበረ ቅዱሳን አሠራር ሁሉ ዋና ተጠያቂዎች ደጋፊ ጳጳሳቱ ናቸው!

ጳጳስ አይጠየቅም የሚል ልምድ አለ። መታወቅ ያለበት ነገር ጳጳስ ሰው መሆኑን ነው። እንደማንኛውም ሰው መሰናክል የሚገጥመውና ሰውኛ ድክመት ሊታይበት የሚችል ፍጡር መሆኑን መረዳት አለብን። እንዲያውም ቤተ ክርስቲያኒቱ በቀየረችው የጵጵስና ትርጉም የተነሳ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳደር እየተበላሸ ሄደ እንጂ ጳጳስ መሆን የሚችለው በቤተሰብእ አስተዳደር ልምድ ያለውና የአንዲት ሴት ባል የሆነ ሰው መሆኑን ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በጻፈው መልዕክቱ በግልጽ ተቀምጧል። ጳውሎስ «ቤተ ሰብኡን በመልካም በማስተዳደር ያልተመሠከረለት፤ ቤተ ክርስቲያንን እንዴት ይመራታል?» በማለት መጠየቁ ጳጳሳት ስለተባሉት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንጂ ዛሬ እንደሚነገረው በተናጠል ስለቀሳውስት አይደለም። በዚህ ዘመን ቀሳውስቱ መቼ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሆኑ? መነኮሳቱ መሪነቱን ተረክበው ይዘውት አይደለም እንዴ ያሉት?
ወደርዕሰ አሳባችን ስንመለስ ጳጳሳት እንደማንኛውም ሰው ሊሳሳቱ ይችላሉ። በኃጢአትም ሊወድቁ ይችላሉ። እንኳን በዚህች ምድረ ፋይድ ያለው የሰው ልጅ ቀርቶ በገነት የኖረው አዳምም ተሳስቷል። ስለዚህ ጵጵስና ማዕርግ እንጂ ከኃጢአት የመንጻት ማረጋገጫ አይደለም። ሁለት ፓስፖርት ይዘው የሚኖሩ፤ በሚሊዮኖች ብር የሚገመት ቤት የሚገነቡ፤ እንደውሃ የሚፈስ መኪና በሚነዱበት ሀገርና ገንዘባቸው ባንክን ማጨናነቁ በሚነገርበት ዓለም ስለብቃት መናገር አይቻልም። የዘር ቆጠራውና የወንዜ ልጅ ዜማው የሚገነው በነዚሁ በጳጳሳቱ ላይ ነው። የሚነገረውና የሚወራው ሁሉ እውነት ባይሆንም ስለሥጋ ድክመትና ስለኃጢአት መኖር ግን ማንም ሊያስተባብል አይችልም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳንን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በማሳደግ፤ በማግነን አሁን ላለበት ደረጃ በማድረስ በኩል ጳጳሳቱ ኃላፊነት አለባቸው። የትውልድም፤ የታሪክም ተጠያቂነት እንዲሁም በሆነውና በሚሆነው ነገር ሁሉ በእግአብሔር ፊት ተጠያቂዎች ናቸው።
ጳጳሳቱ በተቀመጡበት የቤተ ክርስቲያን አመራር ወንበር ላይ መንፈሳዊ ይሁን ቁሳዊ ልማት የማምጣት፤ ሕዝቡን ወደ እድገትና ራስን ወደመቻል የሥራ አቅም የማሳደግ ኃላፊነት የተጣለባቸው ቢሆንም ይህንን ሲያደርጉ አይታዩም። ከዚህ ይልቅ በማኅበረ ቅዱሳን ባላ እየተደገፉ ስሙን ጳጳሳቱ ተሸክመው ሥራውን ለማኅበሩ በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱ ከነበረችበት ፈቀቅ እንዳትል አድርገዋታል። ቤተ ክርስቲያኒቱ ካሏት ሁለት ኮሌጆች በስተቀር በሀገረ ስብከት ደረጃ አንድም ጳጳስ ኮሌጅ ወይም ሴሚናሪ ት/ቤት ከፍቶ አልታየም። የጧፍ ወይም የሻማ ማምረቻ ሠርቷል የሚል ዜና አልሰማንም። 
ምናልባት ወደፊት ቤተ ክርስቲያኒቱ የጳጳሳትን ሹመት ይሁን ያሉትን የማዘዋወር ሁኔታ ማከናወን ያለበት ከፈጸሙት ልማትና የሥራ ብቃት አንጻር መሆን እንዳለበት ሊሰመርበት ይገባል። ጵጵስናን በተመለከተ ከማዕርጉ የሚያስሽሩ ሁኔታዎችም ትኩረት ተሰጥቶባቸው የሕግ ማዕቀፎች ካልተሰራባቸው ቤተ ክርስቲያኒቱ የበለጠ ፈታኝ ሁኔታ እንደሚገጥማት ለማወቅ ነብይ መሆንን አይጠይቅም። ከካህናቱና ከሕዝቡ ዓይን የተሰወረ አንዳችም ነገር አይኖርም።
 ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሁለት የተከፈለችውም ይሁን ክፍፍሉ ባለበት ቦታ ሁሉ ውስጧ የሚታወከው በጳጳሳቱ በራሳቸው መሆኑን ያየናቸው ተሞክሮዎች ያስረዱናል።

6/ ማኅበረ ቅዱሳንና የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ አይገናኙም!

ቤተክርስቲያን በመዋቅር የሊቃውንት ጉባዔ እንዳላት ይታወቃል። ይሁን እንጂ ይህ የሊቃውንት ጉባዔ የቤተ ክርስቲያኒቱን በዘመኑ ያሉ አስተምህሮዎች እየመረመረ ስህተቶችን እየለየ፤ በሐዋርያት መሠረት ላይ ያሉትን እያጸና እውነታኛውንና የቀደምት አበውን ትምህርት ሕዝቡን መመገብ ሲገባው እስከመኖሩ በማይታወቅበት ደረጃ ላይ መገኘቱ ያሳዝናል። ዛሬ ላይ የሊቃውንት ጉባዔውን ጉባዔ በአጅ አዙር በመረከብ በመመርመር ለስደትና ለውግዘት ተሰልፎ የሚገኘው ይህ ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ያልተማረው ሊቃውንት ጉባዔ ነው። በዚህ ማኅበር የተነሳ እውነት ተደፍቆ ተቀብሯል። ሊቃውንት ተሰደዋል። እነ ሆድ አምላኩና እነልጆቼን ላሳድግበት ብቻ ወንበር ይዘው ቀርተዋል። ይሁን እንጂ ይህ ድርጊት መቀጠሉ መልስ ያልተገኘላቸውን ጥያቄዎች ማስቀረት አልቻለም።ወደፊትም አይችልም። የተለመደው ባህላዊ እምነት ሳይነካ ባለበት ተሸፍኖ እንዲቀመጥ ማድረጉ ኩብለላውን አላቆመም።  ሊያቆምም አይችልም። ትውልዱ የሚነገረውን ብቻ እየሰማ የሚነዳ ሳይሆን የሚጠይቅም በመሆኑ ከፊት እየሄደ የሚመራ ሊቃውንት ጉባዔ ያስፈልግ ነበር። እንዳለመታደል ሆኖ ይህ አልሆነም። አሁን በሚታየው ሁኔታም መቼም ይሆናል ተብሎ አይጠበቅም። በዚህ ላይ የተረት አባትና የአፄው ዘውግ አንጋች ማኅበረ ቅዱሳንና ጳጳሳቱ እያሉ የወንጌል እውነት ተገልጦ፤ የአበው አስተምህሮ አደባባይ ላይ ይነገራል ማለት ዘበት ነው። ተረትና እንቆቅልሽ፤ ባህልና ወግ እምነት መሆናቸው ያበቃል ተብሎ አይታሰብም። ተኃድሶ የባህሪው የሆነው እግዚአብሔር ነገሮችን በሆነ መንገድ ይለውጥ እንደሆነ ወደሰማይ ማንጋገጥ የወቅቱ አማራጭ ሆኗል። በአጠቃላይ ሲታይ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይፈለግ የተገኘ፤ ሳይወደድ የቆየ፤ እየተጠላ ለመኖር የሚታገል በጥቂት አንጃ ጳጳሳት የሚደገፍና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሸክም የሆነ ድርጅት ነው።
ኤር 29፥12
እናንተም ትጠሩኛለችሁ፥ ሄዳችሁም ወደ እኔ ትጸልያላችሁ፥ እኔም እሰማችኋለሁ።ኤር 29፥12 «እናንተም ትጠሩኛለችሁ፥ ሄዳችሁም ወደ እኔ ትጸልያላችሁ፥ እኔም እሰማችኋለሁ» ያለ እግዚአብሔር ሁሉን እስኪለውጥ በትዕግስት መጠበቅ ብልኅነት ይመስለናል።

Thursday, October 30, 2014

«የሚያስፈራሩን ከሆነ ወደየገዳማችን እንሄድልዎታለን!» አባ አብርሃም፤ «ወደየትኛው ገዳምዎ? ለመሆኑ ገዳም ያውቃሉ?» ፓትርያርክ ማትያስ


ቅዱስ ፓትርያርኩ ስለማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውን የፈረጠመ ጡንቻ ሲገልጹ «የፈርዖን አገዛዝ» ነበር ያሉት። ማኅበረ ቅዱሳን የደርግ መንግሥት መውደቅ የወለደውና በዓለት ስንጥቅ መካከል የበቀለ ዛፍ ነው። ዓለቱን አንቆ ይዞ በላዩ ላይ የለመለመ ነገር ግን ከአለቱ መካከል ከወጣ ኅልውና የሌለው ሥር አልባ መሆኑም እርግጥ ነው።  ይህን ሽብልቅ ገብቶ የፈረጠመውን ዛፍ ከማነቃነቅ ባለፈ ከሥሩ ነግሎ ለመጣል ጊዜና ሰው የተገናኙት ዘንድሮ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ዘመነ ፕትርክና ነው። ዋና ዓላማውም ከመሠሪና ስውር የቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወረራ ብቸኛዋን ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያንን መታደግ መሆኑን ቅዱስ ፓትርያርኩ በግልጽ ደጋግመው ተናግረዋል።

 «ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር» እንዲል መጽሐፉ ዘንድሮ ቀኑ ደርሶ ማኅበረ ቅዱሳንም ሆነ በማኅበረ ቅዱሳን እስትንፋስ የሚንቀሳቀሱ ተላላኪ ጳጳሳቱ የቤተ ክርስቲያኒቱን እጅ ጠምዝዘው ለማስረከብ ደፋ ቀና የሚሉበት ዘመን ግብዓተ መሬቱ እየተፈጸመ ይገኛል። ከትናንት በስቲያ በነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ የጉድ ሙዳይ የሚባለው ሊቀጳጳስ አባ አብርሃም በአቡነ ጳውሎስ ላይ የለመደ አፉን በአቡነ ማትያስ ላይ በመክፈት «የመንግሥትን ኃይል ተማምነው አያስፈራሩን፤ የሚያስፈራሩን ከሆነ ሲኖዶሱን ለቀንልዎ ወደየገዳማችን እንሄድልዎታለን» ብሎ እስከመናገር የደረሰ ሲሆን ቅዱስ ፓትርያርኩም ለሱም ይሁን ለቢጤ ወንድሞቹ ራስ ምታት የሆነ ምላሽ በመስጠት ዝም ጭጭ እንዲል አድርገውታል።

«ኧረ ለመሆኑ የእርስዎ ገዳም የት ነው? እስኪ ንገሩኝ የትኛው ገዳም ነው ያገለገሉት?  ደግሞስ እኔ አባ ማትያስ ለእርስዎ አንሼ ነው የመንግሥትን እርዳታ የምጠይቀው? ምነው! ቤተ ክርስቲያን እንደተሸከመችዎ አውቀው አርፈው ቢቀመጡ?!» በማለት የጳጳሱን ጉድ ጫፍ ጫፉን በመናገር አፉን እንዳስያዙት የውስጥ ምንጮች ገልጸዋል።

ተመሳሳይ በሽታ የነበረባቸው የማኅበሩ ጳጳሳት የጓደኛቸው ጉድ ፊታቸው ሲነገር በመስማታቸው የተሸማቀቁ ሲሆን አንዳንዶቹ በብስጭት ጉባዔውን ለመረበሽና ለምን ተነካን? የማለት ያህል ሲቁነጠነጡ ታይተዋል። ይሁን እንጂ ከቅዱስ ፓትርያርኩ የተሰጣቸው ምላሽ «ምን አለፋችሁ? ዘንድሮ ማኅበረ ቅዱሳንን በሕግና በሥርዓት ሳላስገባው አልተወውም!» በማለት ቁርጡን እንደነገሯቸው ተያይዞ የደረሰው ዜና ያስረዳል።
ቀደም ሲል የማኅበሩ ደጋፊ የነበሩ አንዳንድ ጳጳሳት ግን የፓትርያርኩን የጠነከረ አቋም ያጤኑ በሚመስል መልኩ ተዐቅቦን መርጠዋል። እነአባ ኤልያስ፤አባ ሉቃስ፤ አባ ቀውስጦስና በእድሜ ገፋ ያሉት ጳጳሳት ጥቂት የታገሉ ቢሆንም ከአባ ገብርኤል በስተቀር ወሎዬዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ግን ዝምታን መምረጣቸው ተዘግቧል። ምናልባትም «እነዚህ እኮ መንግሥትን ከአንድ ክፍለ ሀገር፤ ወደ ሌላ ክ/ሀገር ማዛወር የቻሉ ናቸው፤ ዛሬ አቤሲዲ ቆጥረውማ ማን ይችላቸዋል?» የተባለው ኃይለ ቃል ሳይከነክናቸው የቀረ አይመስልም።

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የተደረሰበት ውሳኔ እንደሚያሳየው ማኅበረ ቅዱሳን አፈንግጦ ከወጣበት የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ተመልሶ በሥሩ እንዲተዳደር፤ በቤተ ክህነቱ ሞዴላ ሞዴሎች እንዲጠቀም፤ እስከዛሬ የፈጸመው የገቢና ወጪው አጠቃላይ ሂሳብ በቤተ ክህነት ባለሙያዎች እንዲመረመር፤ አዲስ በሚረቀቀውና ፀድቆ በሚሰጠው የመተዳደሪያ ደንብ በቤተ ክህነቱ ቁጥጥር እንዲንቀሳቀስ፤ ማንኛውንም ሥራ ቤተ ክህነቱን እያስፈቀደ እንዲፈጽም የሚያስገድደው ውሳኔ የተላለፈበት መሆኑም ተዘግቧል። ድንቅ ውሳኔና ተገቢነቱም ትክክለኛ እንደሆነ አስምረንበታል።

 ድሮም በዚህ ዓይነቱ ልክና ገደብ ባለው አካሄድ ይስራ ከመባሉ ውጪ ይፍረስ፤ ይውደም ያለው  ማንም አልነበረም። ነገር ግን ማኅበሩ ያለውን ዓላማ ከግብ ለማድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግና ሥርዓት ዘለለ መልኩ በአባላት ጳጳሶቹ በኩል እንደሚመቸው አጣሞ በማስቀረጽ መንቀሳቀሱ እንዲገደብ ካለመፈለጉ የተነሳ ወደመላተም አድርሶታል።

የሚደርስበትን ጥላቻና ተቃውሞ ለመሸፈንና በቅዱስ ሲኖዶስ ሥር ለመሸሸግ በመፈለግ «ሲኖዶሱ ቀርጾ ከሰጠኝ መተዳደሪያ ደንብ ውጪ አልንቀሳቀስም» እያለ መደዴ አካሄዱን ሕጋዊ ለማስመሰል ይፈልጋል። እንደነአባ የጉድ ሙዳይ አባላቱ የሰጡትን ገደብ አልባ መተዳደሪያ ደንብ በማሞካሸት በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ የተጻፈ ለማስመሰል መሞከሩ ራሱን ከሚያታልልበት በስተቀር ማንንም ማሞኘት አይችልም። «የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው» በሚል ስልት የሚያጨበጭቡለት ጥቂቶች ባይታጡም አብዛኛው የቤተ ክህነት ሰው ዓይንህን ላፈር ካለው ውሎ አድሯል።
ጳጳሳቱ በማኅበረ ቅዱሳን አዚም ነፍዘው ቤተ ክርስቲያኒቱን አጨብጭበው ለማስረከብ በደረሱበት ሰዓት ፓትርያርክ አባ ማትያስ ደርሰው ልጓም አልባ ሩጫውን ገደብ ሰጥተውታል። ምናልባትም በማኅበሩ ግፍና መከራ የወረደባቸው ማኅበረ ካህናት፤ በኃጢአት ገመናቸውን እየገለበ የሚያሳድዳቸው ማኅበረ መነኮሳትና በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ያለቀሱት ልቅሶና ያፈሰሱት እንባ ከመንበረ ጸባዖት ደርሶ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ የመጣ ፍርድ ይሆን ይሆናል።
ወደፊትም ማኅበሩ ጊዜ በመግዛት የራሱን ሌላ አማራጭ ለመፍጠር እስትንፋሱን ያሰባስብ ይሆናል እንጂ አሁን በሚሰጠው ሕግና ሥርዓት ይተዳደራል ተብሎ አይጠበቅም። ለሁሉም አሁን የተያዘው የፓትርያርኩ እርምጃ በቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ዘንድ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት ያለው ነው።
 ሁላችንም ይበል ብለናል!

Wednesday, October 29, 2014

«የነብር ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም!»

በጥያቄ እንጀምር! ማኅበረ ቅዱሳን ይፍረስ፤ ይበተን አልተባለም። ወደሕግና ሥርዓት ይገባ ነው እየተባለ ያለው። ማኅበሩ ይሁን ማፈሪያ ሊቃነ ጳጳሳቱ በዚህ አባባል የሚናደዱት ለምንድነው? «ደረጃ፤ ቦታና መጠን ተበጅቶለት መቀጠል ይገባዋል» የሚለውን የማኅበረ ካህናቱን ድምጽ ለመስማት ያለመፈለግ ምክንያት ከምን የመነጨ ነው? እኮ አሳማኝ ምክንያት አቅርቡ!!
 አለበለዚያ «እኛ ሊቃነ ጳጳሳት ስለሆንና ጉባዔው በድምጽ ብልጫ ስለሚመራ የአድማ እጃችንን ቀስረን ማኅበረ ቅዱሳን የሚደሰትበትን እንወስናለን» የሚለው ፈሊጥ የተበላ ዕቁብ ነውና ዘንድሮ አይሠራም።  በትክክል ዘንድሮ አልሠራም፤ አይሠራምም።

 ሊቃነ ጳጳሳቱ በየአህጉረ ስብከታቸው የካህናት ማሰልጠኛ ኮሌጆችን በመክፈት፤ የሴሚናሪ ትምህርት ቤቶችን በማስፋፋት የመንፈሣዊና ሳይንሳዊ እውቀት ባለቤት እንዲሆን ለቤተ ክርስቲያን እድገት እንዲሁም ፤ ለህብረተሰቡ ደግሞ በአካባቢ ልማት ተሣትፎ፤ በመንገድ ሥራ፤ በጤና ጣቢያና በንጹህ ውሃ አቅርቦት ተግባር ላይ በመትጋት ያንን ድሃ ምእመን ሕዝባቸውን መርዳት፤ መደገፍና በሥራ ማሳየት ሲገባቸው ተሸፋፍነው በመቀመጥ ሠራተኛ ሲቀጥሩ፤ ሲያባርሩ፤ ደመወዝ ሲቀንሱና ከቦታ ቦታ ሲያዘዋውሩ እድሜአቸውን ይፈጃሉ። ንቡረ እድ አባ ገ/ማርያም የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ በነበሩበት ጊዜ ሊቀ ጳጳስ አባ ቀውስጦስ ከራሳቸው ብሔርና ጎጥ ብቻ የመጣውን እየለዩ ለመቅጠር ሲታገሉ በተነሳ አለመስማማት የሙስና አፍ የዘጉትን ሥራ አስኪያጅ አይታዘዘኝም በሚል ውንጀላ ከስሰው እንዲቀየሩ ማስደረጋቸው አይዘነጋም። አሁን ደግሞ አባ ቀውስጦስ «ሞቴን ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ያድርገው» እያሉ ለያዥ ለገራዥ እያስቸገሩ እንዳሉ ይሰማል። ለምእመናን ልጆቹ በእኩል ዓይን አባት ይሆን ዘንድ ቃል የገባ ሊቀ ጳጳስ በዘረኝነትና በጎጠኝነት ሲታወር ሥጋውያኑማ እንዴት ይሆኑ?
የጎጃሙ ለጎጃም፤ የወሎው ለወሎ፤የጎንደሩ ለጎንደር፤ የሸዋው ለሸዋ የዘረኝነትን ገመድ የሚጎትት ሊቀ ጳጳስ ቤተ ክርስቲያንን እያወካት እንደሚገኝ ፀሀይ የሞቀው፤ አገር ያወቀው ጉዳይ ነው። እነማን? እንዴትና የት? ለሚለው በማስረጃ የተደገፈ ዝርዝር ማቅረብ ይቻላል።
ከብዙ መልካምና ጥሩ ነገሮቻቸው መካከል ሙት ወቃሽ አያድርገንና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የፈጸሟቸው ስህተቶች ለጵጵስና ማዕረግ ቀርቶ ለአንዲት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪነት የማይበቁ ሰዎችን የመሾማቸው ጉዳይ ትልቁ ስህተታቸው ነበር። እሳቸውም በሕይወት ሳሉ ሊሾሙ የማይገባቸውን ሰዎች በመሾማቸው ይጸጸቱ እንደነበር እናውቃለን። ዛሬም የዚያ ስህተት ውጤት የሆኑ ሊቃነ ጳጳሳት ስንት ሥራና አገልግሎት ባለባት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለአንድ ማኅበር ጥብቅና ቆመው «ሞታችንን ከማኅበረ ቅዱሳን ጓሮ ያድርገው» ሲሉ ይታያሉ። ከተመቻቸውና ከሞቃቸው ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ሞታችንን ያድርገው ያሉት ይሁንላቸው። ነገር ግን ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ወደሕግና ሥርዓት ካልገባ መሞቱ አይቀርም። ያን ጊዜ ምን ሊውጣቸው ይሆን?

ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የማኅበረ ካህናቱ ሙሉ ድጋፍ እንዳላቸው ይታወቃል። ማኅበሩን ሥርዓተ አልበኛ የሚያሰኙ ተግባራቱ የማኅበሩን የመጨረሻ እድል ይወስናሉ። የጳጳሳቱ ጩኸት መነሻውና መድረሻው ከጎጥ፤ ከጥቅምና ከፍርሃት የመነጨ እንጂ ለቤተ ክርስቲያን ከማሰብ አይደለም። ምክንያቱም ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖር ቤተክርስቲያን ነበረችና። ማኅበረ ቅዱሳንም ባይኖር ትኖራለች።  ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በሊቀ ጳጳሳቱ አድማ እንዳይፈቱ አደራችን ጥብቅ ነው። ከሕግና ከኃይል በላይ የሚሆን ማንም የለምና በበሉበት ለሚጮኹት ቦታ ሳይሰጡ ሥርዓትና ደንብ የማስገባት እርምጃዎትን ይቀጥሉ ዘንድ አበክረን እናሳስባለን። ዘንድሮን ነካክተው ከተዉት ይሄ የተደራጀ አውሬ እስከመጪው ዓመት ይበላዎታል። አቡነ ጳውሎስንም የበላው እንደዚሁ ነው። ዕድሜአቸውን በዐሥር ዓመት አሳጠርነው እያሉ የሚፎክሩት እስከየት የመጓዝ እልክ እንዳላቸው ማሳያ ነውና ይጠንቀቁ። ክፉ ሥራቸውን የሚጸየፍ እግዚአብሔር ይረዳዎታል።

«የነብር ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም!»






Friday, October 24, 2014

የቅዱስ ፓትርያርኩ የሲኖዶስ ጉባዔ መክፈቻ ንግግር (እዚህ ይጫኑ)



ሐራ ተዋሕዶ የተባለው የማኅበረ ቅዱሳን ቀኝ ክንፍ መካነ ጦማር ቅዱስ ፓትርያርኩ በሲኖዶሱ መክፈቻ ላይ ባቀረቡት ንግግር ተወገዙ፤ ውሳኔም ተላለፈባቸው ሲል ከብራዘር ሁድ ጳጳሳቱ ጋር ያለውን የምስጢር ትስስር በሚያሳብቅ መልኩ ዘገባውን አቅርቧል። ማኅበሩ የሲኖዶስ አባል ሆኖ በጉባዔው ላይ በመገኘት የጉባዔው ተካፋይ መሆን አይጠበቅበትም። በሱ ምትክ የጉባዔውን እስትንፋስ እየለኩ ምስጢር የሚያካፍሉ አባላት የሆኑ ጳጳሳት እንዳሉት ይታወቃል። ማኅበሩን ያናደደውና ደረጃውን ያልጠበቀ የፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር ያሰኘው ነገር ቅዱስ ፓትርያርኩ ከመቼውም ጊዜ በላይ ስለማኅበሩ ቀጥተኛ አቋም ይዘው በመክፈቻ ንግግራቸው ላይ አበክረው ስላሳሰቡ ከደረሰበት ጭንቀት የተነሳ መሆኑ ይገባናል። የፓትርያርኩን ንግግር ደረጃ የሚያወጣና ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ እሱ ማነው? አባ ሉቃስ? አባ ማቴዎስ?
በዚህ ዓመት ስለማኅበረ ቅዱሳን አቅምና ጡንቻ የመጨረሻ ገደብ ካልተደረገበት የነብርን ጅራት ይዞ እንደመልቀቅ ይቆጠራል። ጳጳሳቱም ቢሆን ክብራቸውን ካልጠበቁና ለማኅበሩ በአድማ ተሰልፈው ከቆሙ በተመዘገበ ግለ ታሪካቸው ቦታ ቦታቸውን እንዲይዙ ሊደረግ ይገባል። በአጭር ቃል ባለትዳሮቹና የልጅ አባቶቹ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ማዕረግ ወርደው ከምዕመናን አንድነት ሊቀላቀሉ የሚገባው ዓመትም ይህ ዓመት ነው። ሳይገባቸው ከፍታ ላይ የተቀመጡ ሰዎች ባለበት አስተዳደር ምን ጊዜም ሁከት፤ ክፍፍልና እርስ በእርስ መለያየት መኖሩ እርግጥ ነው።
ይህ ዓመት ቤተ ክርስቲያንን የሚያምሱ፤ በአድማ የሚወስኑ ሰዎች ሰልፍ የሚሰበርበት እንዲሆን እንመኛለን።

Wednesday, October 22, 2014

ማኅበረ ቅዱሳንን ክርስቲያናዊ ብራዘር ሁድ የሚያሰኙ ማስረጃዎችና መመሳሰሎች!

ሙስሊም ብራዘር ሁድ ወይም የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር የተባለው ድርጅት በ1928 ዓ/ም በግብጽ ተመሠረተ። ከሰማንያ ዐመታት በኋላ በጄኔራል አልሲሲ መንግሥት በአሸባሪነት ተፈርጆ ድምጥማጡ እስኪጠፋ ድረስ በ70 ሀገሮች ውስጥ ቅርንጫፎቹን ከፍቶ በዘመናዊና ሃይማኖታዊ ትምህርት ቤቶች፤ በገበያ ማዕከላት፤ በንግድ ሱቆች፤ በማከፋፈያ ድርጅቶች፤ በሚዲያ ተቋማት ወዘተ የሀብት ማግበስበሻ መንገዶች እየተሳተፈ ክንዱን በማፈርጠም ለእንቅስቃሴው የሚጠቅመውን የገንዘብ ምንጭ ሲፈጥር ቆይቷል። ይህ የግብጹ ሙስሊም ብራዘር ሁድ በዐረብ ሀገራት ውስጥ ተመሳሳይ የሙስሊም ወንድማማች ማኅበራትን በማደራጀትና በማሰልጠን መንግሥታቱን ሲያስጨንቅ የቆየ ሲሆን አሁንም እያስጨነቀ ይገኛል።

የሙስሊም ብራዘር ሁድ ለተባለው ሃይማኖታዊ-ፖለቲካዊ ድርጅት ዋነኛ ተቀባይነት ማግኘት ዋናው ምክንያት የሆነው በእስላሙ ሕብረተሰብ ውስጥ ቶሎ ሰርጾ እንዲገባ የሚያካሂደው ሃይማኖታዊ አስተምህሮቱና  ለዚህ እምነት መክፈል የሚገባውን ዋጋ ሁሉ በመክፈል ከአላህ ዘንድ የሚከፈለውን ምንዳ ለመቀበል ቶሎ መሽቀዳደም ተገቢ መሆኑን አበክሮ በመስበኩ የተነሳ ነው።

1/ የሙስሊም ብራዘር ሁድ መዋቅራዊ እንቅስቃሴ 

 ሙስሊም ብራዘር ሁድ መዋቅሩ በሀገሪቱ የመንግሥት ሲቪላዊ መዋቅር ደረጃ የተዘረጋ ነው። ይህም ከማዕከላዊ ቢሮው ተነስቶ አባል በሆኑ በእያንዳንዱ ቤተሰብ ውስጥ በሰንሰለት የተያያዘ ነው። ቤተሰባዊውን የአባልነት ማኅበር «ኡስራ» ይሉታል። አንድ «ኡስራ» አምስት አባላት ሲኖሩት ከአምስት በላይ ከሆነ በሁለተኛ የኡስራ ስያሜ ደረጃ ይዋቀራል። በቤተሰቡ ያሉትን ኡስራዎች የሚመራ ደግሞ የቤተሰቡ አባል የሆነ በእስልምና ሃይማኖቱ የበሰለና የብራዘር ሁድ አስተምህሮት በደንብ የገባውን ሰው የቤተሰቡ ጉባዔ ይመርጠውና «ናቂብ» ተብሎ ይሰየማል። ይህ «ናቂብ» የተባለው ሰው የቤተሰቡ አባላት በእስልምናው ደንብ ዘወትር ስለመንቀሳቀሱ ይቆጣጠረዋል፤ ያስተምረዋል፤ ይነግረዋል። ያልተመለሰውን በማኅበረሰቡ ደረጃ ለተቀመጠውና ከፍ ላለው ሃይማኖታዊ መሪ ያቀርበዋል። ይህ ሁሉ ሲሆን ስለእስልምናው የሚደረግ እርምጃ በመሆኑ በደስታ ከሚቀበል በስተቀር ማንም በተቃውሞ አያንገራግርም፤ ሊያንገራግርም አይችልም። ምክንያቱም ጸረ እስልምና እንደሆኑ ራሳቸውን አስገዝተዋልና። በዚህ ዓይነት አደረጃጀት የሙስሊም ወንድማማቾች ማኅበር ከላይ ወደታችና ከታች ወደላይ የተሳሰረ መዋቅር አለው።

2/   የገንዘብ ምንጮቹን ማሳደግ

ገንዘብ የዚህ ዓለም እንቅስቃሴ የደም ሥር ነው። አባላት ለመመልመል፤ እንቅስቃሴውን ለማስፋፋት፤ የሽብር ተግባሩን ለመፈጸም፤ ለመደለል፤ ለመሰለል፤ ሃይማኖታዊ ዶክትሪኑን ለማስተማር  እጅግ ጠቃሚ ነገር መሆኑን ጠንቅቆ የተረዳው ብራዘር ሁድ የገንዘብ አቅሙን ለሀገር ውስጥና ድንበር ዘለል ተግባሩ ያውለው ዘንድ ተግቶ ይሰራል።

የእስላም ወንድማማቾች ማኅበር ሁለት ዓይነት የገንዘብ ምንጮች አሉት። አንዱ በውጪ ሀገራት ካሉ አባላቱ በመዋጮ የሚሰበሰብ እንዲሁም ብዙ ሃብት ካላቸው የድርጅቱ ደጋፊ ሚሊየነሮች  የሚደረግለት የገንዘብ ፈሰስና በእስላማዊ መንግሥታት ስር ከተሸሸጉ ባለስልጣናት የሚዋጣለት ገንዘብ ነው።  ሁለተኛው ደግሞ በተራድዖ ስም ከውጭ የሚያሰባስበውን ገንዘብ ወደልማት ካዝና በመቀየር በአካባቢ ልማት፤ በትምህርት ቤቶችና መድራሳ ማቋቋም፤ ሥራ አጥ ህብረተሰብን በማደራጀት፤ የራስ አገዝ እንቅስቃሴን በመመሥረት የሚሳተፍ ሲሆን ለዚህም ሀገር በቀል የእርዳታ ስልት በመቀየስ መዋጮውን ቅርጹን ለውጦ ያግበሰብሳል። ይህም፤

ሀ/ ከአባልነት መዋጮ
ለ/ ከንግድ ድርጅቶቹና ከሚዲያ ተቋማቱ የሚገኝ ገቢ ነው።


ይህንን ገንዘብ በተለያየ የገንዘብ ማስቀመጫ ስልቶችና በብዙ የሂሳብ አካውንቶች ቋት ውስጥ በተለያየ ስም በማስቀመጥ ለሚፈልገው ዓላማ በፈለገበት ሰዓት ማንም ሳያውቅበት ያውለው ነበር። በተለይም የእስልምና ባንኮች ተመራጭ መንገዶቹ ነበሩ።

3/ በመንግስታዊ ተቋማት ውስጥ ሰርጎ መግባት

ብራዘር ሁድ አባላቱን ሲመለምል ነጻና ገለልተኛ የሆኑትን ብቻ አይደለም። ከሚኒስትሮች እስከፍርድ ቤቶች፤ ከመከላከያ እስከ ፖሊስ መምሪያዎች፤ ከድርጅት ሥራ አስኪያጆች እስከ አስተዳደር ኃላፊዎች ድረስ በአባልነት መልምሎ፤ አሰልጥኖና ሃይማኖታዊ ትጥቅ አስታጥቆ የሚንቀሳቀስ ድርጅት ነበር። እነዚህ የመንግሥታዊ አካላት ክፍሎች ድርጅታቸው ለሚነሳበት ተቃውሞና ኅልውናውን ፈታኝ ለሆኑ ችግሮች የግብዓት ምንጭ ሆነው ያገለግላሉ። አስፈላጊ በሆነ የመረጃ፤ የፋይናንስና የአፈና ሥራው በትጋት ይሰራሉ።
ይህ ድርጅት እንደሃይማኖታዊ ተቋም አራማጅነት ተነስቶ ወደፖለቲካዊ ሥልጣን መቆናጠጥ እርምጃው ለማደግ መሠረት አድርጎ የሚነሳው የእስልምና ሃይማኖትን ነው። ይህም ብራዘር ሁድን መቃወም እስልምናን እንደመቃወም እንዲቆጠር በሕብረተሰቡ ዘንድ የኅልውናውን ስዕል በማስቀመጥ እንዳይነካ ወይም እንዳይጠፋ ረድቶታል። የእስልምናውን አስተምህሮ መነሻ በማድረጉ የማይነቃነቅ ፖለቲካዊ ግብ ለማስረጽ ያገዘው ሲሆን የዚህም መገለጫው በአልሲሲ መንግሥት ላይ በአንድ ጊዜ እስከ 33 ሚሊዮን ተቃዋሚ ሰልፈኞችን በመላ ሀገሪቱ ማንቀሳቀስ የሚችል ድርጅት አድርጎታል።
 ይሁን እንጂ የጀነራል አልሲሲ መንግሥት እርምጃ ስልታዊ በመሆኑ በአንድ ቀን ብቻ ከሁለት ሺህ በላይ ከፍተኛና ዝቅተኛ አመራሩንና የሃይማኖታዊ ተፍሲር መምህራኖቹን ለቃቅሞ ወደማጎሪያ ካምፕ በመክተቱ ድርጅቱ በ85 ዓመት እድሜው አይቶት የማያውቀውን ውድቀት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያስተናግድ አድርጎታል። በአልሲሲ መንግሥት የተተገበረው «ወፎቹ እንዲበተኑ ቅርንጫፉን መቁረጥ» የሚለው አባባል ብቻ ሳይሆን ግንዱን መንቀል በመሆኑ የብራዘር ሁድ ዋና መሪ መሐመድ ሙርሲን ጨምሮ ከፍተኛውን የሹራ ካውንስል ሳይቀር ከስር ገርስሶታል። በሺዎች የሚቆጠሩ አባላቱም የሞትና የእስራት ፍርድ ተከናንበዋል። አልሲሲ በቲቪ ቀርበው "ብራዘር ሁድን ከስረ መሠረቱ ነቅለን ካላጠፋን ሰላም የለንም" በማለት ድራሹን አጥተውታል። ዛሬም ድረስ የተቃውሞ ሰልፎች ያሉ ቢሆንም በሃይማኖት ካባ ስር በተሸፈነው ድርጅት በኩል የአእምሮ አጠባ ተደርጎ የተታለለው ሕብረተሰብ እንጂ ብራዘር ሁድ እንደተቋም በግብጽ ታሪክ ግብዓተ መሬቱ ተፈጽሟል። ያ ማለት ግን ብራዘር ሁድን የሚደግፍ፤ የሚጠባበቅና እንዲያንሰራራ የሚፈልግ የለም ማለት አይደለም።

4/ማኅበረ ቅዱሳን እንደክርስቲያን ብራዘር ሁድ ስንል ምን ማለታችን ነው?

1/ ተቋማዊ አደረጃጀቱ ከመንግሥትም፤ ከቤተ ክህነትም ቁጥጥር ነጻ መሆኑ
2/ የራሱን አባላት የሚመለምልና የሚያደራጅ መሆኑ
3/ የራሱ የሆነ የገቢ ምንጭ ያለውና የንግድ ተቋማትን የሚያንቀሳቅስ መሆኑ
4/ ከአባላቱ ልዩ ልዩ መዋጮዎችና የስጦታ ገቢዎችን በመሰብሰብ በልማት ውስጥ እየተንቀሳቀሰ እንዳለ የማሳየት ብልሃት ያለው መሆኑ
5/ በመንግሥት ተቋማትና መሥሪያ ቤቶች፤ ፍርድ ቤቶች፤ ፖሊስ መምሪያዎች፤ በኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች ስውር መዋቅር ያለው መሆኑ
6/ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላዕላይ መዋቅርና እስከ አጥቢያ ድረስ በተዘረጋው አስተዳደር የራሱ አደረጃጀት የዘረጋ መሆኑ
7/ በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ውስጥ የራሱን ጳጳሳት በመመልመል ማስሾም የቻለ መሆኑ
9/ ከሀገር ውጭ ዓለም አቀፍ ቢሮዎችን ከፍቶ የሚንቀሳቀስና አባላት ያሉት መሆኑ
10/ ከዓለም አቀፍ የገቢ ፈጠራው ውስጥ በልማት ሰበብ የሚያጋብስ መሆኑ
11/ የመረጃ፡ የስለላና የትንተና መዋቅር ያለው መሆኑ
12/ የቤተ ክርስቲያኒቱን አደረጃጀቶች ለራሱ ዓላማ የመጠቀም አቅም ያለው መሆኑ
( ሰንበት ት/ቤቶችን፤ የጥምቀት ተመላሽና የጽዋ ማኅበራትን)
14/ የግለሰቦችን ስም በማጥፋት ወይም ራሳቸውን በማጥፋት፡በማባረር፡በመደብደብ ወይም ግለታሪካቸውን ለራሱ ዓላማ ጠምዝዞ በማዋል እርምጃ መውሰድና ማስወሰድ የቻለ መሆኑ
15/ ስሙን ለማግነን፤ ክብሩን ለማስጠበቅ የሚያስችል በራሱ የሚመራ እንዲሁም በፖለቲካ የተቃውሞው ጎራ የተሰለፉ ደጋፊዎችና በስውር መረብ የሚንቀሳቀስ የሚዲያ ተቋም ያለው መሆኑ፤
ማኅበረ ቅዱሳንን ክርስቲያናዊ ብራዘር ሁድ እንድንለው ያስችለናል።

እስካሁንም ማንም ምላሽ ሊሰጥበት ያልቻለው ዋናው ነጥብ ማኅበረ ቅዱሳን ከመንግሥት እይታ ውጪ መሆን ባይችልም ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ የሆነ ክርስቲያናዊ ማኅበር መሆኑ ሲሆን እንደክርስቲያናዊ ተቋምነቱ  ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ ላይ ቁጥጥርና ክትትል የማድረግ ችሎታ አንዳችም አቅም የሌላት በመሆኑ ያሳዝናል:: በመንግሥትም፤ በቤተ ክህነቱም ማንም ጠያቂ የሌለው ሆኖ መቆየቱን ለማመን ያለመፈልግ ዝንባሌ መኖሩም ያስገርማል::  ማኅበሩ እንደምክንያት ሁልጊዜ የሚያቀርበው ሲኖዶስ በሰጠኝ ደንብ እመራለሁ ቢልም እውነታው ግን ብራዘር ሁድ በሆኑ ጳጳሳት አባላቱ በኩል የሚመቸውን ደንብ አስጸድቆ ያለጠያቂ በነጻነት ከሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የገቢ አቅሙን እያሳደገ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት ለራሱ አባላት እየመለመለ፤በቤተ ክርስቲያኒቱ ቁመናና መልክ የራሱን አደረጃጀት፤ መዋቅርና እንቅስቃሴ እያከናወነ ያለ ማኅበር መሆኑ የማይካድ እውነታ ነው። ለምሳሌ የማኅበሩ ብራዘር ሁድ አባላት ጳጳሳቱ አባ ማቴዎስ፡አባ ቀውስጦስ፡ አባ ቄርሎስ፡ አባ ያሬድ፡አባ አብርሃም፡አባ ሳሙኤል፡ በአባ ማቴዎስ አደራዳሪነት የትግሬን መንግስት በጋራ መዋጋት በሚል ፈሊጥ ከማኅበሩ እግር ላይ ወድቀው የታረቁት አባ ፋኑኤል ተጠቃሾች ናቸው:: አባ ገብርኤል ግን ከአቶ ኢያሱነታቸው ጀምሮ የተጠጋቸው የውግዘት በሽታ  መቼም አይለቃቸውም::

5/ ለመሆኑ አሁን ያለው ማኅበረ ቅዱሳን አደረጃጀት፤   

የሰንበት ት/ቤት ስብስብ ነው? እርዳታ ድርጅት ነው? የልማት ተቋም ነው? የበጎ አድራጎት ማኅበር ነው? ራሱን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ውጪ አስደርጓል። በዋና ሥራ አስኪያጅ ሥር የሚተዳደር ነገር ግን የቤተ ክህነቱ መምሪያ ያልሆነ መምሪያ ነው?
በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሥፍራው ከየት ነው? በምንስ እንመድበው? ማኅበሩ በምን ሂሳብ እንደተቋቋመና በምን አደረጃጀት ኅልውና እንዳገኘ አይታወቅም::

እስከሚገባን ድረስ እንቅስቃሴውንና ያለውን አደረጃጀት ተመልክተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳናዊ ብራዘር ሁድ ብንለው ተግባሩ ያረጋግጣል።
በሌላ መልኩ መንግሥት በኢትዮጵያ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ እንዲህ ዓይነት ማኅበር ከእስልምና ምክር ቤቱ ውጪ እንዲቋቋም ይፈቅዳል ወይ ብለን እንጠይቃለን? መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው።

Saturday, October 18, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የሚፈርሰው በራሱ ተግባር ነው፤ ኢሕአዴግ ላለፉት 22 ዓመታት መቼ ነካው?

ይህን ጽሑፍ በመጋቢት ወር 2006 ዓ/ም በመካነ ጦማራችን ላይ አውጥተነው ነበር።። ዳግመኛ ማውጣት ያስፈለገን ጉዳይ ሰሞኑን በፓትርያርክ አቡነ ማትያስና በማኅበረ ካህናቱ በኩል ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን በቅኝ ገዢነት የመቆጣጠር ስልቱና ይህንን ስለማስቆም በአንድ ድምጽ የተናገሩትን አቋም በመጻረር የማኅበረ ቅዱሳን ቀኝ ክንፍ የሆኑት አባ ማቴዎስ የሰጡትን  ማስጠንቀቂያ መነሻ በማድረግ ለማስታወስ የምንፈልገው ቁም ነገር ስላለ ነው።
 ዛሬ አባ ማቴዎስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስን « እንደአቡነ ጳውሎስ በሞት ይወገዳሉ» በማለት የተናገሩትን ቃል ከስምንት ወራት በፊት ማኅበሩ ራሱ በአሉላ ጥላሁን መካነ ጦማር በኩል ተናግሮት ነበር። ያንኑ የእናስወግዳለን ዛቻ አባ ማቴዎስ ሲደግሙት በቤተ ክህነቱ ውስጥ በተቃርኖ የቆሙ አካሎች ስውር መጠፋፋት እንደሚፈጽሙ ማሳያ ምስክር ነው።  በሌላ መልኩም ማኅበሩ ሊታረም የሚችል አካል ስላይደለ እየታየ ባለው የምድራዊ ሥልጣን ግብግብ ውስጥ ማኅበሩ በያዘው መንገድ ከቀጠለ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር መጥፋቱ የማይቀር መሆኑንም አስረግጠን ገልጸን ነበር። መቅኖ አጥቶና ባክኖ እንዲቀር ባንፈልግም አንዴ «ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ነው፤አንዴ አቡነ ማትያስ ሊበሉኝ ነው» የሚለው ጩኸት የራሱን ሥፍራ ቆም ብሎ እንዳያይ እያደረገው ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ቢጠፋ፤ መጥፋቱ በሌላ በማንም ሳይሆን በራሱ ተግባር መሆኑን ጠቁመን ነበር።
 መልካም ንባብ ይሁንላችሁ!!

ይህ ሕንጻ የማነው? የቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን? የመንበረ ፓትርያርክ? የአስመጪና ላኪ? የበጎ አድራጊ ድርጅት?

 የሀገሬ ሰው «ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል» ይላል። ይህ አባባል ለሰሞነኛው የማኅበረ ቅዱሳን የጅቡ በላኝ ጩኸት ይስማማል። ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ነው ሲል በየግል ጋዜጣው ማስወራቱ 22 ዓመታት ኢህአዴግ በሚመራት ሀገር ውስጥ ያልነበረ ይመስላል። ሲነግድ፤ ሲያስነግድ፤ ሲሸጥ ሲለውጥ፤ከግብርና ታክስ ተከልሎ በሚሊዮኖች ብር ህንጻ ሲገነባ በሀገሪቱ ኢህአዴግ ያላየው ወይም የማያውቀው ይመስላል። ኢህአዴግ ማኅበረ ቅዱሳንን በአስማት ይሁን በምትሃት እስከዛሬ ሳያየው ቆይቶ አሁን ለማየት ዓይኑን ሲከፍት ማኅበረ ቅዱሳንን አገኘውና ሊበላው ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ኢህአዴግ ሊያጠፋኝ ለምን ፈለገ ሲል ለመጠየቅ የተገደደ ይመስላል። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ያለው ተግባሬ ከማኅበረ ካህናቱ ጋር አጋጨኝ፤ በማያገባኝ አስተዳደር ውስጥ እጄን ሳስገባ ተገኘሁ እንዳይል ከመሬት ተነስቶ ኢህአዴግ ሊውጠኝ ነው ወደሚል ቅስቀሳ መግባቱን  ከመምረጡ በስተቀር በምድር ላይ ያለው እውነታ ግን የምርጫ ዘጠና ሰባት ውጤትና ተከትሎ የመጣው ፖለቲካዊ ቀውስ ስንቱን ፓርቲና የተቃዋሚ መሪዎች እየደፈጠጠ ሲያልፍ ማኅበረ ቅዱሳን ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ታዛ ተጠልሎ አልፏል።ኢህአዴግ ቢያጠፋው ኖሮ ያኔ ባጠፋው ነበር። 

ከዚህ በፊት ማኅበሩ እንደጥራጊ አውጥቶ የጣለው ዳንኤል ክብረት ይህን ኢህአዴግ ሊበላኝ ነው የሚለውን የማኅበረ ቅዱሳንን ዘፈን እንዲህ ሲል በደጀሰላም ብሎግ ላይ አውጥቶ ነበር።
«እኔ እንደምገምተው የማኅበሩ አባላት መንግሥትን እንዲፈሩ እና እንዲጠሉ የሚፈልጉ አካላት በአመራሩ ውስጥ ሳይኖሩ አይ ቀርም፡፡ ምንጊዜም አንዳች ከባድ ነገር ሲነሣ መንግሥት እንዲህ ብሎናል፣ በዚህ ስብሰባው እንዲህ ብሏል፣ ሊዘጋን ነው፣ ሊያስረን ነው፣ ሊጨርሰን ነው ከማለት ያለፈ አንድም ቀን በጎ ነገር ስለ መንግሥት የማያነሡ አካላት አሉ»
 ስለዚህ ከዚህ አባባል ተነስተን ልንል የምንችለው ነገር ይህ መንግሥት ሊበላን ነው የሚለው ዜማ እንደስልት የተያዘና መንግሥት በአባላቱ ዘንድ እንዲጠላ የተዘየደ መሆኑ ነው። ከዚያም ባሻገር መሰሪ ስራውን ለመደበቅ ራሱን ጻድቅ አድርጎ በሌሎች ሰዎች ዘንድ ለመሳል የታቀደ ጥበብ ሲሆን ጻድቁ ማኅበረ ቅዱሳንን ኢህአዴግ ሊያጠፋው ስለሆነ ኦርቶዶክሳውያን የሆናችሁ ሁሉ የዚህን መንግሥት መሠሪነት ተመልከቱ ብሎ ክፉ ስዕል ለመስጠት የተፈለገ ብልጠት ነው።
እውነቱ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ነጋዴ ድርጅት መሆኑ ማንም ያውቃል። የግል ይሁን የአክሲዮን ማኅበር መሆኑ ያልታወቀና የራሱን ሀብት የፈጠረ ተቋም ስለመሆኑም ስራው ምስክር ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ከንግድ ተቋማቱና ከልዩ ልዩ የገቢ ምንጮቹ ባሻገር የራሱ የሆኑ አባላት ያሉትና የአባልነት መዋጮ የሚሰበስብ ድርጅት ነው። ከዋናው ማዕከል ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ ቁመት የራሱ የሆነ መዋቅርና  ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ነገር ግን አደረጃጀቱ በየትኛው የሀገሪቱ  የአደረጃጀት ፈቃድ ላይ እንደቆመ ያልታወቀ መሆኑም እርግጥ ነው። ይህንን የራሱ ተቋማዊ ኅልውና ያለውን ማኅበር በሀብቱ፤ በንግድ ተቋማቱ፤ በመዋቅራዊ አካላቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመቆጣጠርና የማዘዝ ምንም ሥልጣን የላትም።  በአንጻሩም ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስር ተሸፋፍኖ እንደመጠለሉ መጠን ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ ላይ የመቆጣጠርና የማዘዝ ሥልጣን እንዳላት ግምት ያለው በመሆኑ መንግሥት ይህን ድርጅት ነክቶት አያውቅም። ስለዚህ ይህንን ማኅበር ቤተ ክርስቲያኒቱም፤ መንግሥትም ሳይመለከቱት ከሁለት ወገን ቁጥጥር ነጻ ሆኖ 22 ዓመት ዘልቋል። 
 «ለሁሉም ጊዜ አለው» እንዲሉ ሆኖ ማኅበሩን ማነህ? ምንድነህ? የት ነህ? ምን አለህ? ምን አገባህ? የሚሉ ካህናትና የአመራር አካላት ተባብረው በመነሳት መጠየቅ ሲጀምሩ ጥቂት ሟሳኞችና አሟሳኞች ወደሚል ሃሳብ ለመውረድ ተገዷል።  በምንም ደረጃ ያሉ ሰዎች ማኅበረ ቅዱሳንን መክሰስ መቻላቸው የማኅበሩን ማንነት ማሳያው ተግባሩ እንጂ ክሱ አይደለም።  እየተከሰሰ ያለው ማኅበር በተግባሩ ያልታወቀ ማኅበር ባለመሆኑ በሟሳኞችና አሟሳኞች የቃላት ጫወታ እየፈጸመ የቆየውን ሸፍጥ ሸፍኖ ማስቀረት አይቻልም።
ማኅበረ ቅዱሳን በተግባር በሌለው ሥልጣንና መብት መናፍቃን ናቸው ያላቸውን ኢትዮጵያውያንን በራሱ ጥቁር መዝገብ አስፍሮ አስደብድቧል፤ ሰልሏል፤ ስም አጥፍቷል፤ አስፈራርቷል፤ እንዲሰደዱ አድርጓል። ማኅበረ ቅዱሳን በቤተክርስቲያኒቱ ስም መጽሔትና መጻሕፍትን፤ ካሴትና ቪዲዮ፤ አልባሳትና ንዋየ ቅድሳትን ከታክስና ከቀረጥ ነጻ ሆኖ ነግዷል። የማኅበረ ቅዱሳን አቋም የሚቃወሙ ሁሉ ጠላቶቹ ናቸው። የሚደግፉት ደግሞ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ ወንጀል ቢኖርባቸው እንኳን የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ አገልጋይ ተደርገው ዜና ይሰራላቸዋል፤ ሙገሳ ይሰጣቸዋል። አባ እስጢፋኖስን ማንሳት ይቻላል። ጠላቶቼ ከሚላቸውና ስማቸውን ሌሊትና ቀን ሲያጠፋቸው ከቆዩት ጳጳሳት ውስጥ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ደግሞ የጥላቻ የአፍ መፍቻው ናቸው። ሌሎቹም ፈርተው አንገታቸውን ደፍተውለታል። የተገዳደረውን አንገት ያስደፋል፤ አለያም ቀና ካለ አንገቱን ይሰብራል።  ሌላው ቀርቶ ሲያመሰግናቸው የነበሩትን አዲሱን ፓትርያርክ ጠላቶቼ የሚላቸውን ሰዎች ሲቀጣ በቆየበት መልኩ በስም ማጥፋት ቅጣት ናዳውን እያወረደባቸው ይገኛል። ለራሱ ኅልውና ብቻ የሚጨነቅ፤ ካልመሰለው ደግሞ ሲያወድሳቸው ለነበሩት ሳይቀር ግድ የሌለው ማኅበር ስለመሆኑ ከድርጊቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።  ወትሮውንም ሸፋጭ ነጋዴ ገንዘቡን እንጂ ወዳጅና እውነት በእሱ ዘንድ ዋጋ የሌላቸው ስለሆኑ የሚያስበው ጊዜያዊ ትርፉን ብቻ ነው። በዚህ ዙሪያ ማኅበሩ አሸንቅጥሮ የጣለውና ለተቀበለው የእጅ መንሻ በውጪ እንዳለ የሚለፈልፈው ዳንኤል ክብረት ማኅበሩ ስለግለሰቦችና ስለቤተ ክርስቲያኒቱ ደንታ ቢስ እንደሆነ ያጋለጠው እንዲህ ሲል ነበር።
«ዲያቆን በጋሻው ማስተማር የጀመረው መቼ ነው? ማኅበሩ በነዲያቆን በጋሻው ላይ ሃሳብ ዛሬ መሠንዘር ለምን ጀመረ? በጋሻው ለቤተ ክርስቲያን አደጋ ነው ብሎ ስላሰበ አይደለም፡፡ በጋሻው ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ ስለ ተናገረ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ምንም ያልተናገረው ማኅበር ስሙ ሲነሣ ቤተ ክርስቲያን ተነካች ብሎ ተነሣ፡፡ ማኅበሩ አቡነ ጳውሎስን በተመለከተ የተለየ አቋም መያዝ የጀመረው መቼ ነው? «እርሳቸው ማኅበሩን ሊያፈርሱ ነው» ብሎ መሥጋት ከጀመረ በኋላ፡፡ አባ ሠረቀንም ቢሆንኮ ዛሬ ዛሬ በእምነት ችግር ይከሳቸዋል እንጂ፣ ከእርሳቸው ጋር ያለው ዋናው ችግሩ ማኅበሩ መነካቱ ነው፡፡ አባ ሠረቀ ማኅበረ ቅዱሳንን ሳይነኩ የፈለጉትን ቢሆኑ ኖሮ አይናገራቸውም ነበር፡፡ ባለፈው ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ ችግር ሲፈጠር፣ ዝምታን መርጦ የነበረው አመራር የመንግሥት አካላት ከቤተ ክህነቱ ባለሥልጣናት ጋር ሆነው ስለ ማኅበሩ ሲያወያዩት ግን አገር ይያዝልኝ አለ፡፡ የአዋሳ ምእመናንን ችግር በዝምታ ያለፈው አመራር አባ ሠረቀ አንዳች ነገር ተናገሩ ብሎ ድምፁን አሰምቶ ተናገረ፡፡ እነዚህ እና መሰል ሁኔታዎች አመራሩ የሚቆረቁረው ማኅበሩ ሲነካ እንጂ ቤተ ክርስቲያኒቱ ስትነካ አለመሆኑን ያመለክታሉ» ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ከራሱ በላይ ማንንም እንደማይወድ እርግጥ ነው። የራሱን ድክመት ቆም ብሎ በመገምገም ለመስተካከል ከመሞከር ይልቅ አንገቱን በማደንደን ወደ ስድብ፤ ዛቻ፤ ማስፈራራትና ስም ማጥፋት ይሮጣል። ይህም በመሆኑ ማኅበሩ የሚጠፋው በራሱ ተግባር እንጂ በቅንነቱ ወይም በቀናዒነቱ አይደለም። ይህም ማለት ግን ቀናዒና ቅን አባላት የሉትም ማለት እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። ቅን አባላቱ ጠማማውን አመራር ማስተካከል የሚችል አቅም የላቸውም። ማኅበሩ ራሱ የሚመራው በቡድናዊ ስልት ስለሆነ በቡድን ይመታሉ፤ በቡድን ይወገዳሉ። 
ማኅበረ ቅዱሳን በፖለቲካው ዙሪያ ከምርጫ 97 በፊትም ሆነ በኋላ ስላለው ሁኔታ መንግሥት በቂ መረጃ እንዳለው ይሰማል። በዚህ ዙሪያ መንግሥት ያለውን መረጃ እስኪያወጣ ድረስ የምንለው ነገር የለም። ነገር ግን ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያምሳት መቆየቱን፤ እጁን እያስገባ ሲኖዶሱን ሳይቀር እንደሚጠመዝዝ እናውቃለን። ማኅበሩ ደፋርና የልብ ልብ የተሰማው አንዳንድ የሲኖዶስ አባላት ተጠግቶ የጉባዔ ሃሳብ በራሱ መንገድ እስከመጠምዘዝ የመድረሱን አቅም እየለካ በመሄዱ ነው። ዛሬ ላይ ያ ነገር የለም። ፓትርያርክ ማትያስ ለዚህ የማኅበሩ ሃሳብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ገና አንድ ዓመት ሳይሞላቸው ከኢህአዴግ ጋር ተመሳጥረው ሊያጠፉኝ ነው እያለ ስም ወደማጥፋት ወርዷል። በተቃራኒው ደግሞ ማንም እንደማያጠፋው በሚገልጽ ጀብደኝነቱ ፓትርያርክ ጳውሎስም እንደዚሁ ሊያጠፉኝ ሞክረው እንደማያዋጣቸው አውቀው አጃቸውን ከእኔ ላይ ለማንሳት ተገደዋል በማለት ለፓትርያርክ ማትያስ የማስጠንቀቂያ ማስታወቂያ እየሰራ ይገኛል። እጅዎን ከእኔ ላይ የማንሳትን ጉዳይ ችላ ሳይሉ ከቀድሞው ፓትርያርክ ትምህርት ውሰዱ በማለት ማሳሰቢያ እየሰጠ መሆኑ ነው። 
የሚፈራው ከተገኘ ጥሩ ጀብደኝነት ነው፤ ነገር ግን ባለቀ ጊዜ ማላዘን ዋጋ የለውም። ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያኒቱ ስንት ችግር ባለባት ሰዓት ራሱ ችግር ፈጣሪ ሆኖ ካለቦታው የተገኘ ማኅበር ስለሆነ ተገቢ ቦታውን መያዝ ካለበት ሰዓቱ አሁን ነው። ማኅበረ ካህናቱና የቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር አባላት ጠንክሮ መታገል የሚገባችሁ ወቅት ቢኖር ዛሬ ነው። ማኅበሩ ቁጭ ብሎ አዋጭ የሆነውን መንገድ መቅረጽ ካለበት ቶሎ ብሎ ይህንኑ እንዲፈጽም ምክር እንለግሰዋለን። የአክሲዮን ማኅበር፤ የሃይማኖት ተቋም፤ በጎ አድራጊ ድርጅት ወይም የተሻለ ነው ብሎ የደረሰበትን ውሳኔ ወደተግባር መቀየር ካለበት ቀኑ ሳይመሽ በብርሃኑ ይሆን ዘንድ ልናሳስበው እንወዳለን። ሲሆን ዘንድሮ፤ ካልሆነም በቀጣዩ ዓመት፤ ቢረዝም፤ ቢረዝም አንድ ቀን ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጉያ እንደመዥገር የተጣበቀበት ቀን እንደሚያበቃ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ምክንያቱም ማኅበሩና ተግባሩ፤ ካህናቱና አስተዳደሩ መቼም ቢሆን አሁን ባለው መንገድ አብረው መጓዝ አይችሉምና ነው።  ከዚህ ሁሉ ፓትርያርኩም፤ ካህናቱም፤ አመራሮችም፤ መንግሥትም ይህንን ማኅበር ቦታ የማስያዙን ጉዳይ ችላ ሊሉት አይገባም። ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖር ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይኖርም ትኖራለች!!!  «ማኅበረ ቅዱሳን ከሌለ ቤተ ክርስቲያን ትጠፋለች» የሚለው ራሱ ማኅበረ ቅዱሳን ብቻ ነው።