Tuesday, February 3, 2015

የፓስተር ተከስተ ጌትነት የወሲብ ቅሌት በቪኦኤ

የዝሙትና የአፍቅሮ ንዋይ አንበሳ ያልሰበረውን መንፈሳዊ ሰው ማግኘት ከባድ እየሆነ ነው። በመጨረሻው ዘመን ላይ ሰይጣን እንደሚያገሳ አንበሳ እየዞረ ሰዎችን የሚሰብርበት ትልቁ መንጋጋው ትዕቢት፤ ዝሙትና ገንዘብን መውደድ ናቸው።
በየቤተ እምነቶቹ ትላልቅ የሚባሉት ሁሉ መንፈሳዊ አከርካሪያቸው የተሰበረው በነዚህ ወጥመዶች ነው። ጳውሎስም አለ፤ «ስመጣ፥ እንደምወደው ሳትሆኑ አገኛችሁ ይሆናል እኔም እንደምትወዱት ሳልሆን ታገኙኝ ይሆናል ብዬ እፈራለሁና፤ ምናልባት ክርክር ቅንዓትም ቁጣም አድመኝነትም ሐሜትም ማሾክሾክም ኩራትም ሁከትም ይሆናሉ፤
እንደ ገና ስመጣ በእናንተ ዘንድ አምላኬ እንዲያዋርደኝ፥ አስቀድመውም ኃጢአት ከሠሩትና ስላደረጉት ርኵሰትና ዝሙት መዳራትም ንስሐ ካልገቡት ወገን ስለ ብዙዎች ምናልባት አዝናለሁ ብዬ እፈራለሁ»
2ኛ ቆሮ 12፤20-21

Thursday, January 29, 2015

ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የካይሮ ጉብኝት በከፊል


የኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የሆኑት አቡነ ታዋድሮስ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ባደረጉላቸው ጥሪ ይፋዊ ጉብኝት አድርገው መመለሳቸው ይታወሳል። ፓትርያርክ ማትያስ በቆይታቸውም ከግብጽ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ተገናኝተው በብዙ ጉዳዮች ላይ የተነጋገሩ ሲሆን የኮፕቲክ ገዳማትንም ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። ከጎበኝታቸው በኋላ በግብጽ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር በሆኑትና ምድረ ግብጽን እስኪለቁ ከጎናቸው ባልተለዩት በአቶ ሙሐመድ ድሪር ቱርጁማንነት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በከፊል የተወሰደው ይህ ትዕይንተ ምስል የተገኘው ከራዲዮ ምስር 88.7 FM ነው።

Wednesday, January 14, 2015

«ሳይኖረኝ አኖርከኝ»

አሌክስ ሎዶቅያ፤ ኦስሎ/ ኖርዌይ ( 6/5/ 2007 )

   የሰው አስጨናቂ አገዛዝ ክብደት፣ የመከራ ስጋት፣ የኑሮ ውድነት ጭንቀትና የወዳጅ ክዳት ለሚያስጨንቁን መፍትሔው የሚያኖረንን ማወቅ ነው፡፡ በዘላለም ክንዶቹ ደግፎ፣ አእምሮን ሁሉ በሚያልፍ ሰላሙ አሳርፎ፣ ሳይዘነጋ አስቦ፣ ቸል ሳይል እንደ ዐይኑ ብሌን ጠብቆ፣ ሳይሰስት ሰጥቶ እና ሳይደክም ተሸክሞ የሚያኖረን እግዚአብሔር ነው፡፡ ለሚታየው ኑሮአችን መሰረቱ የማይታየው እምነታችን ነውና በእግዚአብሔር እንመን፤ በእግዚአብሔርም እንተማመን፡፡

   ከኮሌጅ ተመርቄ እንደወጣሁ በሲኦል ፊት የተጣልኩ ያህል እጅግ ከፍቶኝ ነበር፡፡ ተስፋ ያደረኳቸው ሁሉ አነሱብኝ፡፡ የያዝኩት ዲግሪ ሰርተፊኬት የሌላቸው ሰዎች የሚበሉትን እንጀራ እንኳ ሊሰጠኝ አልቻለም፡፡ በቤቴ እንደ እንግዳ በእናቴ ጓዳ እንደ ባእድ በመሆኔ ልቤን ሀዘን ወጋው፡፡ አንድ ወዳጄ ጋር ሻይ ቡና እያልን የወዳጄ ወዳጅ ድንገት ተቀላቀለን፡፡ “ሕይወት ከምርቃት በኋላ እንዴት ነው?” አለኝ “እንዳሰብኩት መኖር አልቻልኩም” አልኩት፡፡ እርሱም የፍቅር መንፈስ በለበሰ ተግሳጽ “ወዳጄ እንደተፈቀደልህ እንጂ እንዳሰብከው አትኖርም” አለኝ፡፡ ይህ ቃል በልቤ ቀረ፡፡ እንዳሰብነው ለመኖር ብዙ ደክመን ይሆናል፤ መኖር የምንችለው ግን የሚያኖረን አምላክ እንደፈቀደልን ነው፡፡
   ተስፋ ካደረኳቸው ሁሉ አይኔን አንስቼ የሁሉ ዐይን ተስፋ ወደሚያደርገው የዘላለም አምላክ አንጋጠጥኩ፡፡ ያላሰብኩት በረከት ከበበኝ፡፡ ከምኞቴ በላይ በሆነ ከፍታ እግዚአብሔር አኖረኝ፡፡ ከወራት በኋላ በእልፍኜ ብቻዬን ሳለሁ የምድረበዳውን ጉዞ ከጀመርኩ በኋላ የሆነውን አሰብኩ ዐይኖቼ በእንባ ተሞሉ አንደበቴም ለምስጋና ተከፈተ “ሳይኖረኝ አኖርከኝ አምላኬ ተመስገንልኝ” አልኩት፡፡ ዲያሪዬም ላይ የሆነውን ሁሉ መዘገብኩት፡፡ እግዚአብሔር የሚኖር የሚያኖር አምላክ ነው፡፡ ምንም ሳይኖረን እግዚአብሔር እንደሚያኖር የእስራኤል ታሪክ ማሳያ ነው፤ ማንም በማይቀመጥበትና በማያልፍበት ምድረበዳ መርቷቸዋልና፡፡
 ዘዳ. 32፡11፣ ኤር. 2፡5፡፡
   የአንዲት እህት የሰላምታ ቃል “ኖሮ ያኖረኛል” በሚል ምስክርነት የተቃኘ እንደሆነ ሰምቼ ራሴን በሚያኖረኝ ውስጥ ስላገኘሁት ልቤ ሀሴት አደረገ፡፡ እግዚአብሔር ኖሮ የሚያኖር አምላክ ነው፡፡ መኖሩ የሚያኖረን ህልውናው ያቆመን ከእንግዲህ አንታወክም፡፡ ሕይወታችን ለምን በስጋት ታጠረ? የሚያኖረን እግዚአብሔር አይሞትም፤ አይሻርም፤ አያረጅም፤ አይደክምም፤ አይሰለችም፡፡ በአስፈሪ ሁኔታዎች ብንከበብም መኖር እንደምንችል የሚገባን እግዚአብሔር እንደሚያኖረን ስናውቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር እንደሚያኖራት የገባት ነፍስ የአራዊት መንጋጋ፤ የክፉዎች መንጋ አይነካትም፡፡
ዳዊት “በክንፎችህ ጥላ ደስ ይለኛል፡፡ ነፍሴ በኋላህ ተከታተለች፡፡ እኔንም ቀኝህ ተቀበለችኝ፡፡” አለ መዝ. 62፡9፡፡ እረኛችንን በደስታ እንከተል በሚያስተማምን እረፍት፣ በማይነጠቅ ደስታና አይምሮን ሁሉን በሚያልፍ ሰላም እንኖራለን፤ በለምለም መስክ እንሰማራለን፤ በእረፍት ውሃ በፍቅሩም ጥላ እናድራለን፤ በጥበቃው አጥር እንከበባለን፤ እረኛችን ሆኗልና የሚያሳጣን የለም፡፡ መዝ. 22፡1
ሙሴ ምድረ ርስትን በናባው ተራራ በሩቅ ከተሳለመ በኋላ ስለማይወርሳት አዘነ፡፡ እግዚአብሔር ግን መኖሪያህ እኔ ነኝ አለው፡፡ ሙሴም ለሕዝቡ “ይሹሩን ሆይ መኖሪያህ የዘላለም አምላክ ነው፡፡ የዘላለም ክንዶች ከአንተ በታች ናቸው፡፡” አለ፡፡ ዘዳ. 33፡26-29፡፡ የዘላለም አምላክ እግዚአብሔር የዘላለም መኖሪያችን ነው፡፡ እኛም የእርሱ መኖሪያ ዐለማት ነን፡፡
ለመኖር ከመሠረታዊ ጥያቄዎች ባሻገር ለዛሬ ጥበቃ ለነገም ተስፋ ያስፈልገናል፡፡ እግዚአብሔር ለዘላለም መግባትና መውጣታችንን ሳያንቀላፋ የሚጠብቅ መልካም እረኛ ነው፡፡ የትውልድ መጠጊያ የሁላችን ተስፋ እርሱ ነው፡፡ ችግረኛና ምስኪኑን ይረዳዋል፡፡ መዝ. 71፡12፤ 120፡1-8፤ 144፡15፡፡
ስለዚህ ልቤ ከዘማሪው ጋር አብሮ ዘመረ “የሚያኖረኝ ጌታ ነው፤ ምን ያስጨንቀኛል፡፡ የሚያስፈልገኝንም ያዘጋጅልኛል፡፡ አይሻግትም አይጎልም ሞሰቤ፤ ከሰማይ ነው ቀን በቀን ቀለቤ” እንደ እኔ ምንም ሳይኖራችሁ የሚኖረው እግዚአብሔር የሚያኖራችሁ፤ ሀብት፣ እውቀትና ስልጣን ያላስመካችሁ ኖሮ የሚያኖረንን ባርኩ፡፡ ከፍ ስንል ከፍ ያደረገንን አምላክ በምስጋና ቃል ከፍ ማድረግን አንርሳ፡፡
// ካነበብኩት//

ይድረስ ለወንድሜ ዳንኤል ክብረት!

( ምንጭ፤ አባ ሰላማ )
 እኔ ስሜ እገሌ እባላለሁ የተወለድሁት በጎጃም ክፍለ ሀገር ነው። እንደ ማነኛውም የቤተ ክርስቲያን ልጅ ገና የሰባት ዓመት ልጅ ሆኜ ነበር ቆሎ ት/ ቤት የገባሁት። በልጅነቴ የሀገሬ ቤተ ክርስቲያን መርጌታ ከሆኑት ከዬኔታ ሞገሴ ፍቅር እያገኘሁ አደግሁ። እናት እና አባቴ ጥሩ አሳዳጊዎች ነበሩ፣ ነገር ግን ባሀገሩ ባህል ትምህርት እንዲገባው በሚለው አስተሳሰብ ለምኜ እየበላሁ እንድማር ተገደድሁ። አባቴ በግ እንድጠብቅለት ነበር የሚፈልገው፣ እናቴም እንዲሁ። የኔታ ግን ቤተ ሰቦቼን እየመከሩ እንድማር አደረጉ። ቀን ፊደል አቡጊዳ፣ መልክተ ዮሐንስ ወንጌለ ዮሐንስ ከዚያም ዳዊት ጾመ ድጓ እየተማርሁ፣ ማታ ደግሞ የዘወትር ጸሎት፣ ውዳሴ ማርያም፣ አንቀጸ ብርሃን፣ መልክአ ማርያም መልክአ ኢየሱስ፣ ት/ኅቡአት፣ ውዳሴ ማርያም ዜማ፣ መስተጋብዕ፣ አርባዕት፣ አርያም፣ ክስተት፣ ሰለስት፣ ስብሐተ ነግሕ። ተማርሁ እነዚህ ሁሉ የቃል ትምህርት ናቸው ሌት ያለ መብራት ስለምንማራቸው በቃል የምንይዛቸው ናቸው።
 ይህ በእንዲህ እንዳለ እነዚህን ትምህርቶች አጠናቅቄ ገና ሳልጨርስ ከብፁእ አቡነ መቃርዮስ የምስራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ዲቁና ተቀበልሁ። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቴን ካጠናቀቅሁ በኋላ የኔታ መርቀዉኝ ጉልበት ስሜ ተሰናብቼ ቅኔ ቤት ገባሁ። ቅኔው ወዲያው ነበር የገባኝ። ሦስት ቦታዎች ላይ ከጉባኤ ቃና እስከ መወድስ ያሉትን ሞልቼ አራተኛው ቦታ ላይ አስነጋሪ ሆንሁ። በቅኔ አዋቂነቴ ባካባቢው ሊቃውንት ዘንድ አድናቆትን አትርፌ ነበር። የኔን ቅኔ ለመስማት የማያሰፈስፍ ሊቅ አልነበረም።

 ከቅኔ ቤት እንደተመልስሁ ወደ ዜማ ቤት ገብቼ አስቀድሜ የተማርኳቸውን የቃል ትምህርቶች እንደ ገና አጥንቼ ድጓ የተባለውን ረጅም ትምህርት ተማርሁ። አከታትየም ወደ አቋቋም ቤት ገባሁና መዝሙር፣ ክብረ በዓል፣ ወርኀ- በዓል፣ ጾም ቀለም፣ ለእመ ኮነ፣ አጠናቀቅሁ። ከዚያም ዝማሬ እና መዋስዕት ተምሬ መሪጌታ ሆኜ ተሾምኩ። በዚህ ጊዜ ጎርምሼ ነበር። እናትና አባቴ ሊድሩኝ እንደሆነ ስሰማ መጽሐፍ ሳልማር አልታሰርም ብዬ ወደ ሽዋ ተሻገርሁ። በአታ ገዳም አራት ኪሎ ገብቼ ብሉይ ኪዳንን ተማርሁ፣ ጎን ለጎንም ሐዲስ ኪዳንን አጠናሁ። የትምህርት ጥማቴ እየጨመረ ሲመጣ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ገብቼ በአራት ዓመቱ ሴሚናር ኮርስ መውሰድ ጀምርኩ። በዚያን ጊዜ አንድ የማህበረ ቅዱሳን አባል በጣም ወዳጅ ሆኖ ቀረበኝ፣ እኔም በጣም ወደድሁት፣ በትርፍ ሰዓቴ ውዳሴ ማርያም አንድምታ አስተምረው ጀምርሁ። እርሱ ግን ታቦት እየቀረጸ ይሸጥ እንደነበር ስላወቅሁ በተለይም ያቡነ ጎርጎርዮስ ታቦት ቀርጾ ሳየው ተቆጣሁ፣ በሲኖዶስ ያልተወሰነ ነገር እንዴት ላንድ ግለሰብ ታቦት ትቀርጻለህ? ብዬ ተቃወምሁት። ወጥመድ ውስጥ የገባሁበት ቀን ይህ ቀን!!!
 ይህ ወዳጄ ከኮልፌ እየተነሣ ወደ ማህበረ ቅዱሳን ቢሮ አምስት ኪሎ ሲመላለስ ነገር እንደሚያመጣብኝ አልጠበቅሁም ነበር። ወዲያውም በማላውቀው ሁኔታ መናፍቅ ተብየ ተከሰስሁ፤ አንተም ዳንኤል ክብረት የስማ ጽድቅ ጋዜጣ አዘጋጅ በነበርህበት ጊዜ እኔን ሳታውቀኝ ስሜን ጠቅሰህ በጋዜጣ መናፍቅ ነው ብለህ አወጅህ። ከዚያ ሰዓት ጀምሮ ሕይወቴ አደጋ ላይ ወደቀች፣ በቆሎ ትምህርት ቤት ውሻ ሲያባርረኝ፣ ባለጌ ሲገፋኝ፣ ቁንጫና ትኋን፣ ሲፈራረቅብኝ፣ ረሃብና ጥም ሲያሰቃየኝ ያደግሁ ሰው ነኝ። ተመርቄ እረፍት አገኛለሁ ስል ዕዳ አመጣህብኝ። ስማ ጽድቅን ያነበቡ ሁሉ ምራቅ ይተፉብኝ ጀመር፣ ከጓደኞቼ አብሮኝ የሚቆም ጠፋ፣ ስበላ ብቻየን፣ ስሄድ ብቻየን ሆነ ኑሮዬ፤ በመጨረሻም የቤተ ክህነቱን ባለሥልጣናት አሳምናችሁ ኖሯል ያለምንም ፍርድ ከት/ቤቱ ተባረርሁ። ዳንኤል አስበው እስኪ እንደ ድሮዬ ለምኜ አልበላ? የማፍርበት ዕድሜ ላይ ነው ያለሁት። በቤተ ክርስቲያን ያደግሁ እንደመሆኔ ደሞዝ መቀበል ሲገባኝ ያንተ ጋዜጣ ዋጋዬን አሰጥቶኛል።

  ምን ላድርግ ብዬ አሰብሁ፣ ሰዎችም አላስጠጋ አሉኝ፣ እሙንቱሰ ይጸልዑኒ በከንቱ እነርሱ ግን በከንቱ ጠሉኝ እንደተባለው ባልተጨበጠ ወሬ ተጠላሁ። ረሐቡም እየጸናብኝ ማደሪያም እየቸገረኝ ሲመጣ ስማአ ጽድቅን ጨምሮ ሌሎች ጋዜጦችን ማዞር ጀመርሁ። ስሜን ያጠፋችውን ጋዜጣ እየሸጥሁ ምሳዬን መብላት ችዬ ነበር። ማታ ማታ ያልሸጥኋቸውን ጋዜጦች በረንዳ ላይ አንጥፌ እተኛለሁ። ካልተቀደዱ በማግስቱ እሸጣቸዋለሁ። ማን ይረዳኛል? ዳንኤል? በዚያን ጊዜ አንተና ጓደኞችህ አምስት ኪሎ በሚገኘው የማህበረ ቅዱሳን ሆቴል አልጫና ቀይ ወጥ እየቀላቀላችሁ ትበሉ ነበር። እኔ ሳለቅስ እናንተ ትስቁ ነበር። ጌታ በመንግሥቱ በመጣ ጊዜ ይህን ነገር እንዴት ያየው ይሆን?
   ከላይ የተቀስኋቸውን የትምህርት ዓይነቶች ተንከራትቼ ተምሬ የበረንዳ አዳሪ ስሆን እንኳንስ ሊማሯቸው ስማቸውንና ቅደም ተከተላቸውን እንኳ የማያውቁ ሰዎች የቤተ ክርስቲያን ሰው በመምሰል እያሳዳዱን እንጀራ ይበሉብናል። ዳኛው ማን ይሆን? እያልሁ ሳዝን በከንቱ መገፋቴን ያዩ አንድ አስተዋይ ሰው ወደ ሀገረ ስብከቱ አስተዳዳሪ አቀረቡኝ። እኒያ አስተዳዳሪ እኔን ሲያዩ ያነቡትን እንባ አልረሳውም። ዓይኖቼ ወደ ውስጥ ገብተው አንጀቴ ታጥፎ በየወንበሩ ክልትው ስል ያየ እንዴት አያለቅስ? ቤተ ክርስቲያን ሃያ ዓመት ሙሉ አስተምራ ባንድ ጋዜጣ ምክንያት አውጥታ ስትጠለኝ እንዴት አያስለቅስ? ጌታ በመንግሥቱ በመጣ ጊዜ ይህን ነገር እንዴት ያየው ይሆን?
 ወደ ሀገሬ እንዳልገባ ስሜን በቤተ ክርስቲያን እሁድ ቀን ባንድ ቄስ አማካኝነት አቆሽሻችኋል። ቤተ ሰቦቼ ከዚያ ቄስ ጋር ደም ሊቃቡ ይችሉ ነበር። ጊዜ ይፍታው ብለው ዝም አሉ እንጂ። ዳንኤል ብዙ ለመማር ብዙ ለማደግ ያሰብሁትን ሰው የንጀራ ጉዳይ ብቻ እንዲያሳስበኝ አደረግኸኝ። ዋና ጸሎቴ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቼ በተማርሁት እያገለገልሁ እንጀራ የምበላበትን መንገድ ብቻ ማግኘት ነበር። እንዴት እንደጎደሃኝ አስበው። አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ስሄድ የሚያስገባኝ ባለመኖሩ አምሳ ሳንቲም ለዘበኛ እየከፈልሁ እገባ ነበር። ስብከተ ወንጌል ክፍሉ ብር ያለኝ መስሎት እጅ እጄን እያየ ለረጅም ጊዜ አሰቃየኝ። በስንት መከራ አንድ ቤተ ክርስቲያን በሦስት መቶ ብር ተመደብሁ። የሥቃዬ ዘመን አበቃ ብየ ስጠበቅ በተመድብሁ ባመቴ ስሜን በጋዜጣ እንደ ገና አወጣኸው። ስማ ጽድቅ ጋዜጣን ማየት አልወድም እንደ ተናዳፊ ዕባብ ያህል ስለምፈራው ነው። ስማ ጽድቅ ጋዜጣ ሲዞር ሳይ እራሴን ያዞረኝ ነበር።
  አንድ ቀን አንድ ጓደኛዬ የማታ ፕሮግራም ጋብዤው መጥቶ አስተምሮ ከጨረሰ በኋላ እስከሚሳፈርበት ፌርማታ ድረስ ልሸኘው ተከተልሁት። ዳንኤል ክብረት አለቀቀህም? አይደል? አለኝ ለመሆኑ ያውቀሃል? ሲል ቀጠለ። ምን ነው ደግሞ ምን አመጣ? አልሁት። ስምህን ስማ ጽድቅ ጋዜጣ ላይ አላየኸውም? እንዴ መናፍቅ ብለው አውጥተዋል እኮ! ሲለኝ? ከቆምሁበት ላይ ተዝለፍልፌ ወደቅሁ። ጓደኛዬም እኔን ተሸክሞ ወደ ቤቴ ተመለሰ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለሁለት ወር ያህል ታምሜ ተኛሁ። በዚያን ወቅት እውቀቴ እንጂ እምነቴ ደካማ ነበር። የሰንበት ተማሪዎች ስማ ጽድቀን አንብበው ኖሯል ምንም ሳይጠይቁኝ አባረሩኝ፣ ለአንድ ዓመት ያህል ሳስተምራቸው ያደንቁኝ የነበሩት ሁሉ ስማ ጽድቅን ሲያነቡ ይደቀድቁኝ ጀምር። ስማ ጽድቅ ስላነበቡ እንጂ እኔ ምን እንዳልሁ መረጃ አላገኙም። ዳንኤል መናፍቅ ነው ስላለ ብቻ መናፍቅ ነው ተባልሁ። ጌታ በመንግሥቱ በመጣ ጊዜ ይህን ነገር እንዴት ያየው ይሆን?
  ከቤተ ክርስቲያን ወጥቼ የት ልሂድ? ሌላ ቤተ ክርስቲያን አላውቅ? ሁሉንም ትቼ የቀን ሥራ እየሰራሁ ዘመናዊ ትምህርት ልማር አልሁና ወደ አቃቂ ሄጄ ስሚንቶ ማቡካት ጀመርሁ። ከዚያም የማታ እየተማርሁ ባጭር ጊዜ አንደኛ እየወጣሁ ሰበተኛ ክፍልን አጠናቀቅሁ። እግዚአብሔር ግን አልተወኝም፣ ታምሜ እንዳልሞት፣ እንዳልድን ሆንሁ። አይ ያ ጊዜ አንድ ዳቦ የሚሰጠኝ ያጣሁበት ጊዜ እንዴት የሚያስፈራ ነበር? በዚህ ጊዜ አንድ ነገር ገባኝ እግዚአብሔር ስለስሙ መከራ እንደቀበል እንጂ ኑሮ ተመችቶኝ ዓለማዊ እንድሆን እንደማይፈልግ ተረዳሁ። ሆኖም በእምነት የበሰለ ሰው አግኝቶ እስኪረዳኝ ድረስ እምነቴ ጠንካራ አልነበረም። ከዚህ በኋላ እስኪ ዳንኤል የሚተወኝ ከሆነ፣ ሰውም የማያገለኝ ከሆነ ልመንኩስ ብየ መነኮስሁ። እኔ ማግባት እንጂ መመንኮስ አልፈልግም ነበር። ማህበረ ቅዱሳን መነኩሴ ይወድ እንደሆነ ብዬ አደረግሁት? እውነትም መከራው ቀነሰልኝ ጌታ ግን ይህን አካሄዴን አልወደደውምና ደስታ የለኝም። በመሠረቱ እኔ ግፍን ስቀበል ተሐድሶ አልነበርሁም ተሃድሶ የተባልሁበት ነገር ምንድን ነው? ብዬ ሳጠና ግን ተሐድሶ ሆንሁ። ጌታ ያንን ሁሉ ግፍ እንድመለከት ያደረገኝ ለካ ተሃድሶ እንድሆን ነው። እንዲህ ዓይነቱ የግፍ ሥራ እንዲቆም የማይመኝ ማን አለና?
 ወንድሜ ዳንኤል ሆይ!አንተ በክብር በዝና በብልጽግና እየተጨበጨበልህ እየኖርህ ነው። ግን በዚህ ነገር ንስሐ ግብተህ ይሆን? ወይስ ረስተኸው ይሆን? ስንት ያልታበሱ እንባዎች እንዳሉ ታውቅ ይሆን? ሕይወታቸው የተጎሳቆለ፣ የተሰደዱ የተገደሉ፣ አንገት የደፉ፣ የተደበደቡ፣ ከቤተ ሰባቸው የተፈናቀሉ ስንት እንዳሉ ታውቃለህ? አንተ እኔን ከጨዋታው ሜዳ ገፍተህ አስወጥተህ አንተ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ ስትባል በየትኛው ህሊናህ ተቀበልኸው? ጌታ በመንግሥቱ በመጣ ጊዜ ይህን ነገር እንዴት ያየው ይሆን?
 አይ አንቺ በርባንን እየፈታሽ ክርስቶስን የምትሰቅዪ የይሁዳ ዓለም?! ጌታ በመጣ ጊዜ የሚያድንሽ የለም።
ስሜን ከመጽሐፌ ላይ ታገኛላችሁ ታሪኬን እየጻፍሁ ነው። አሁን ስሜን ብነግራችሁ ለስማ ጽድቅ እጋለጣለሁ ጥቂት ጊዜ ተውኝ እባካችሁ። ታሪኬን ሳልጽፈው መሞት አልፈልግም።

Sunday, January 11, 2015

ግን የምር ምን ዓይነት ትውልድ እያፈራን ነው?

(ደጀ ብርሃን፤ 3/5/2007)
ይህን  ጽሁፍ ለሚያስተውለው አስደንጋጭ የዘመኑ እውነት ነው። በየስርቻው በስመ ጸሎት ቤት የሚደረገውና የሚፈጸም ስንት ጉድ አለ? የተቀደሰ ውሃ፤ የተቀደሰ ጨርቅ፤ የተቀደሰ መጽሐፍ፤ የተቀደሰ ፓስፖርት፤ የተቀደሰ ዘይት ኧረ ስንቱ በስመ «የተቀደሰ» ይቸበቸባል? አንድ ቤተ ክርስቲያን በምእመናን ጉባዔ የማትመራ ከሆነና በአንድ ፓስተር ወይም ቄስ ስም በፈቃድ የተመዘገበች ከሆነች የግል ሱቅ ትባላለች እንጂ ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ልትባል አትችልም። በዘመነ ሐዋርያት በግል የተመዘገበች ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን አልነበረችምና ነው። ሩኒ ከሚባል የማንቸስተር ዩናይትድ እግር ኳስ ተጫዋች ደመወዝ ጋር ራሳቸውን እያስተያዩ እነሱ ሰይጣንን በማስወጣታቸው 70 ሺህ ብር ደመወዝ ወይም 80 ሚሊየን ብር በባንክ አካውንታቸው ውስጥ መገኘቱ እንደማያስገርም ሲናገሩ ትንሽ አይሰቀጥጣቸውም። ደመወዝ ማግኘት አንድ ጉዳይ ነው። ሰይጣንን ለምናስወጣ ለእኛ ግን ይህ ትንሽ ገንዘብ ነው ማለት ደግሞ ሌላ ነው። በዚህ ጉዳይ ሌላ ጊዜ እንመለስበታለን። ለዛሬ ግን ከወደ ኬንያ የተገኘውን መረጃ እናካፍላችሁ!

ከዮናስ ሓጎስ ናይሮቢ
#‎አቋራጭ_የለመደ_ትውልድ‬
ልብወለድ…………………………ቢሆን ደስ ባለኝ ነበረ…
አዳራሹ ጢም ብሎ በመሙላቱ መግባት ያልቻሉ በሺህ የሚቆጠሩ «ምዕመናን» በር ላይ ከተመደቡ አስተናጋጆች ጋር ዱላ ቀረሽ ፀብ ላይ ናቸው። አስተናጋጆቹ ግን በተረጋጋ መንፈስ አዳራሹ ውስጥ የሚካሄደው ነገር ሁሉ በአዳራሹ ዙርያ በተተከሉ 80" ቴሌቨዢኖች በቀጥታ እንደሚተላለፍ ሕዝቡን ለማሳመን እየወተወቱ ነው።
ከአዳራሹ በር በስተቀኝ ያለ አንድ ሱቅ የሚመስል መስኮት ጋር በእጃቸው ብር ይዘው የሚያውለበልቡ ሰዎች ወርረዉታል። ፓስተር ኪኛሪ የፀለየበት ነው የተባለ «ቅዱስ» ውኃ እና እንደ መቁጠርያ የመሰለ ነገር እያንዳንዳቸው በ2000 ሽልንግ (400 ብር) እየተሸጡ ነው። ምንም እንኳ ሻጮቹ በብዛት እንዳለና እንደማያልቅ ለማሳመን ቢጥሩም ሕዝቡ እነርሱን መስሚያ ጆሮ ያለው አይመስልም
አዳራሹ ውስጥ ፕሮግራሙ ተጀምሯል። ፓስተር ኪኛሪ «መንፈስ ቅዱስ» በገለጠለት መሰረት ከሕዝቡ መሐል መርጦ ያወጣቸውን ለዕለቱ እንዲድኑ የተመረጡ ሰዎችን በሰልፍ መድረኩ ላይ ደርድሯቸዋል።
አንዱ አስተናጋጅ በእጅ ማስታጠቢያ ጎድጓዳ ሳህን ውኃ ይዞ ወደ መድረኩ ወጣና እጃቸውን ነክረው እንዲታጠቡ ትዕዛዝ ሰጠ። «የተመረጡት» እጃቸውን ሲታጠቡ አጁን ዉኃው ውስጥ በመጨመር እጃቸውን እየፈተገ ማጠብ ጀመረ። ፓስተሩ አሁንም በከፍተኛ ድምፅ ፀሎት እያደረሰ ነው።
በድንገት ማስታጠቢያው ውስጥ ያለው ውኃ እየቀላ እየቀላ ሄደና ደም መሰለ። የምትታጠበዋ ሴትዮ እጇን ከማስታጠቢያው መንጭቃ ለማውጣት ብትሞክርም አስተናጋጁ ጭምቅ አድርጎ በመያዝ አረጋጋት…
«ኃጥያትሽ፣ በሽታሽ፣ መርገምሽና ልክፍትሽ ሁሉ በዚህ ደም አማካይነት ከሰውነትሽ ወጥቷልና ደስ ይበልሽ!» አላት አስተናጋጁ።
ተረጋጋች!
ወድያውኑ በቅፅበት አስተናጋጁ ፈንጠር ብሎ «ፓስተር ፓስተር ና ተመልከት!!» ሲል በከፍተኛ ድምፅ ተጣራ።
ፓስተሩ ማይክራፎኑን ይዞ ወደ አስተናጋጁ ሲጠጋ ካሜራውም ተከተለው
«አየህ ከእጇ የወጣውን!» ሲል ትናንሽ መርፌዎች ከማስታጠቢያው ውስጥ አውጥቶ አሳየው።
«ኃሌሉያ!!!» ሲል ፓስተሩ አዲስ ሳይንሳዊ ግኝት እንዳገኘ ሁሉ ጮኸ። «አስማትና ድግምት ተደርጎብሽ ነበረ። ዛሬ ድነሻል! ፈጣሪ ይባረክ! ዛሬ ከእስራትሽ ነፃ ወጥተሻል!!» ሲል ጮኸ።
ከሰውነቷ መርፌ መውጣቱ የምር ያስደነገጣት ሴት መብረክረክ ስትጀምር አስተናጋጆቹ ደገፏት።
መድረኩ ላይ ያሉት «ዛሬ ለመዳን የተመረጡ ሰዎች በተራ በተራ ከአስማትና ድግምታቸው ተፈትተው ከአዳራሹ ጀርባ ወዳለ ክፍል በተራ ተራ ተወሰዱ።
በመሐል በመሐል በሚደረግ ዕረፍት ላይ የሚተላለፍ ማስታወቂያ አለ።
«ፍቅር ፣ ስራ ፣ ገንዘብ ማጣት አስቸግሮዎታል? ፓስተር ኪኛሪ ሊፀልይሎት ዝግጁ ነው!! አሁኑኑ በሞባይል ገንዘብ መላኪያ 310 ሽልንግ (60 ብር) ወደ ቁጥር ----------- ይላኩና ሁሉን ነገር በእጅዎ ያስገቡ!! ፓስተር ኪኛሪ የፀለየባቸው ውኃ እና መቁጠርያ በመሸጥ ላይ ናቸውና ፈጥነው ይግዙ!!!»
ኃጥያታቸው የተሰረየላቸው ሰዎችም ወደ አዳራሹ ጀርባ ካመሩ በኋላ ኪሳቸውን ሲዳብሱ ይታይ ነበረ።
**************************************************************
ምሽት ላይ የ KTN Investigative journalist JICHO PEVU በተሰኘ ታዋቂ ፕሮግራሙ ስለ ፓስተር ኪኛሪ አቀረበ።
ጋዜጠኛው በዘገባው ፓስተር ኪኛሪ ሕዝቡን እንዴት እንደሚያጭበረብር ወለል አድርጎ አሳየ። አስተናጋጆቹ እጃቸውን ፖታሲየም ተቀብተው በጣቶቻቸው መሐል መርፌ ይዘው በመግባት (ፖታሲየም ውሃ ጋር ሲቀላቀል ቀይ ከለር ይይዛል) ከዛም ባሻገር የእግዚአብሔር ስብከት አሰራጭበታለሁ በሚልበት ሬድዮ ፕሮግራም ላይ የተለያዩ ሐሰተኛ ምስክርነት የሚሰጡ ሰዎችን በገንዘብ እያማለለ እንደሚያቀርብ ተገለፀ። ለማስረጃነት ያህልም አንድ ከዚህ በፊት በፓስተሩ ፀሎት ከኤድስ በሽታ ድኛለሁ ብሎ ሁለት ፖዘቲቭና ኔጋቲቭ የሆነባቸውን የሐኪም ማስረጃ ያቀረበ ግለሰብ መጀመርያውኑም ኤድስ እንዳልያዘውና ፖዘቲቭነቱን የሚያሳየው መረጃ በዘገባው ላይ ቀረበ።
በማግስቱ የኬንያ ጋዜጠኞች ፓስተሩን ኢንተርቪው ለማድረግ ቢሯሯጡም አልተሳካላቸውም። በሁለተኛው ቀን ላይ አንዱ ዕድለኛ ጋዜጠኛ ፓስተሩ ምሳውን ከአንድ ሆቴል በልቶ ሲወጣ አገኘው።
«ፓስተር፤ በ JICHO PEVU ስለቀረበብህ ውንጀላ ምን ትላለህ?»
«ውንጀላ? ኧረ እኔ አልሰማሁም…»
«ከሕዝብ እፀልይላችኋለሁ እያልክ በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብ አካብታሃል ይባላል…»
«ስማኝ ወንድም!!» አለ መኪናው ጋር የደረሰው ፓስተር ለጋዜጠኛው መኪናውን እያሳየው። «እንዲህ ዓይነት መኪና በነፃ ይገኛል እንዴ ታድያ?»
ይሄው ምላሹም በቴሌቪዥን ተላለፈ።
በቀጣዩ እሁድ ፓስተር ኪኛሪ የሚሰብክበት አዳራሽ በብዛቱ ከባለፈው የበለጠ ሕዝብ ተገኘ። አሁንም ድረስ ፓስተሩ የስብከት አገልግሎት እየሰጠ ነው።
እኛም ሐገር ሚሌኒየም አዳራሽን ጢም ብሎ እንዲሞላ ያደረገ በግል ጄት የሚሄድ ፓስተር መጥቶ ሕዝቤን «የተቀደሰ ውኃ» ለመግዛት እርስ በርሱ ሲራገጥ ውሎ ነበር አሉ ባለፈው ሰሞን…
ለነገሩ የአባባ ታምራትን ሽንት ከፍሎ የጠጣ ሕብረተሰብ ለተቀደሰ ውሃ ቢከፍል ምኑ ይገርማል?
አሁን ሰሞን ደግሞ በ350 ብር ገነትን እና ሲዖልን በ preview ለማየት ሕዝቤ እየተጋፋ ነው አሉኝ…
በሕይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ልጆች ባለመውለዴ ተደስቻለሁ!!

Tuesday, January 6, 2015

እንኳን ለአምላካችን፤ ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ክብር አደረሳችሁ!

ኢሳይያስ 9፥6 «ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል»
 ታህሣሥ 29/2007 ዓ/ም




ሰበር ዜና፤ በስደተኛው ሲኖዶስ ሥር ያሉት አያሌ አብያተ ክርስቲያናት ባወጡት የጋራ መግለጫ ሲኖዶሱን የማይቀበሉ መሆናቸውን ገለጡ።

(ደጀ ብርሃን፤ 28/4/2007)
ከምንጮቻችን እንደ ደረሰን አብያተ ክርስቲያናቱ ከዚህ የመረረ የጋራ ውሳኔ የደረሱበት ዋና ምክንያታቸው በጥቅምቱ ሲኖዶስ ስብሰባ የፀደቀው ሕግ/Bylaws መሆኑ ታውቋል። አብያተ ክርስቲያናቱን በቁጣ ያነሳሳው የጥቅምቱ ሲኖዶስ ውሳኔ ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው።

1.    በአዲሱ ሕግ አብያተ ክርስቲያናቱን ለፈለጉት አጀንዳ ማዋል

ስደተኛው ሲኖዶስ ነኝ ባዩ አካል ለሃያ ዓመታት ቤተ ክርስቲያንን ለፖለቲካና ለዘረኝነት ግንባታ ብቻ ሲጠቀም መቆየቱ የሚታወቅ ነው። አሁን ከሃያ ዓመታት በኋላ አዲስ ሕግ ለምን አስፈለገ የሚለው የብዙኃኑ ጥያቄ ሲሆን የአብያተ ክርስቲያናቱንም ቁጣ የቀሰቀሰው ዋና ምክንያት ይኸው ሆኗል። በእርግጥ የዚህ የስደተኛው ሲኖዶስ ነኝ ባይ ቡድን ጅማሬውና ሂደቱም ፖለቲካና የጎጠኝነት ሥራ ብቻ በመሆኑ በሃያ ዓመታት ውስጥ ለቤተ ክርስቲያን ያወጣው መመሪያም ሆነ መዋቅራዊ አስተዳደር እንደሌለ ግልጽ ነው። ቤተ ክርስቲያንን ለሁለት ከፍሎ ራሱን የማደራጀት ዋና ምክንያትም ሥልጣን ያለማግኘት ኩርፊያ እንጂ ሌላ የቀኖና ጉዳይ እንዳልሆነ ዓለም የሚያውቀው ታሪክ ነው። ይኽም እንደሚታወቀው የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ከፕትርክና መውረድን ተከትሎ የቀኖና መፍረስ ጉዳይ ሳይሆን ለፕትርክና የቋመጡት ጳጳሳት ያለመሾም ምክንያት ነው።

 ምክንያቱም ቅዱስነታቸውን በስውር ደባ ያወረዱአቸው ወገኖች ናቸው ኋላ ቀኖና ፈረሰ፤ ፓትርያሪክ እያለ ፓትርያሪክ ተሾመ፤ ሕጋዊ ሲኖዶስ እኛ ነን ብለው ቤተ ክርስቲያንዋን ለሁለት የከፈሉት። ቅዱስነታቸውን ያወረዱት፤ አዲሱን ፓትርያሪክ (ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን) ቁመው ይደልዎ ብለው ያሾሙ፤ የእንኳን አደረሰዎት ድስኩር ያቀረቡ እነዚሁ በአሜሪካን ላይ አዲስ ሲኖዶስ ያቋቋሙት ጳጳሳት መሆናቸው ሀገር ያወቀውና ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው። ልናጽናናችሁ መጣን ብለው የወቅቱን የፖለቲካ አለመረጋጋት ተጠቅመው በወታደራዊ መንግሥትና በወያኔ የቆሰለውን ስደተኛ ሕዝብ ሰበኩት። ወደፈረንጅ ቤተ ክርስቲያን መሔድ እርካታን ያልሰጣቸው ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን ጎጆ ቀልሰው፤ በባህላቸውና በቋንቋቸው ለማምለክ ጀመሩ። በዚያን ጊዜ እገሌ የእነማን ወገን ነው? እገሌ ከየት ክፍለ ሀገር ነው የመጣው? ሳይሉ በአገኙት ካህን መገልገል ነበረ። እነዚህ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን የመክፈል አጀንዳን በውስጥ ሰንቀው፤ የተበተኑትን ምዕመናን ለመሰብሰብና ለማጽናናት መስለው በመቅረባቸው ምዕመናኑም እጃቸውን ዘርግተው ተቀበሉአቸው። ጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለሁለት በመክፈል አሳዛኝ ታሪክ አስመዘገቡ። ቀስ በቀስም ቤተ ክርስቲያንዋን የጎጠኞችና የፖለቲከኞች መደበቂያ አደረግዋት። ያልተለመደና መረን የለቀቀ አስተዳደርንና ሥርዓትን በቤተ ክርስቲያንዋ ዘረጉ። ሃይማኖታችንንና ባህላችንን ጠብቀው ያስጠብቃሉ፤ ሰላም ተፈጥሮ በሀገር ቤትና በውጭ ሀገር ያለችው ቤተ ክርስቲያናችን አንድ ትሆናለች ብለው ምዕመናን እምነት ጥለውባቸው ነበር። ይሁን እንጂ ሰላምን በማወጅ ፋንታ ከእንግዲህ ሰላምና እርቅ የለም ብለው በድፍረት እስከ ማወጅ እምነቱን የጣለባቸውን ሕዝብ ክፉኛ አሳዘኑት። ቤተ ክርስቲያንዋን ለዘለዓለም ከፍለን እንኖራለን የሚለውን ድብቅ አጀንዳቸውን ይዘው አደባባይ ሲወጡ የቤተ ክርስቲያን መከፈልና ተለያይቶ የመኖሩ ጉዳይ እስከ ልጅ ልጁ እንዲቀጥል የማይፈልገውን ሕዝብ ቁጣውን ቀሰቀሱት። የአባትነታቸውን አክብሮት ሳይነፍግ፤ በእምነቱና በአንድነቱ ላይ የሚሠራውን ደባ እንዳላየ ሲታገሥ የኖረ ቢሆንም አሁን ግን ትግሥቱ የተሟጠጠ ይመስላል። ሕዝቡ በጎጥ እንዲለያይ  ጎንደሬ፤ ሸዋ፤ ትግሬ፤ ጉራጌ፤ ኦሮሞ ወዘተ በማለት ከፋፍሎ የመግዛትን ዘይቤ መጠቀም የተለመደ ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ አንድነታቸውን ጠብቀው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውን መለያየትና ዘረኝነትን ለማውገዝ መነሳታቸውን አስተውለናል። ተዳፍኖ የቆየው የሕዝብ ብሶት የሀገር ቤት፤ የውጭ፤ የገለልተኛ የሚለው የመለያየት ምንጭ ከቤተ ክርስቲያን ቅጽረ-ግቢ ፈጽሞ እንዲደርቅ ሕዝባዊ ማዕበልን አስነስቷል። የጎጠኝነት ስብከትና ቀኖና ፈረሰ የሚለው የማስመሰል ሽፋንም ፋሽኑ ያለፈበት ሆኗል።

2.    የአዲስ ፓትርያሪክ ምርጫ

አዲሱ የቤተ ክርስቲያን መተዳደሪያ ተብሎ ያለምልዓተ ጉባኤ የፀደቀው ስለአዲሱ የፓትርያሪክ ምርጫ በዝርዝር ያትታል። የፓትርያሪክን ምርጫ ተከትሎ በጥቅምቱ ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ አመላካች ክንዋኔዎችም ተካሔደዋል። ከእነዚህም መካከል የስደተኛው ሲኖዶስን አቅጣጫ የሚያመላክተው አንዱ አቡነ መልከጼዴቅ ራሳቸውን ምክትል ፓትርያሪክ ብለው መሠየማቸው ነው። በጥቅምቱ ስብሰባ ቅዱስ ፓትርያሪኩ አልተገኙም። ከአሥራ አምስት ጳጳሳት መካከል አምስት ጳጳሳት ብቻ ሲገኙ ከካህናትና ከቦርድ መናብርትም አብዛኛዎቹ እንዳልተገኙ ተገልጿል። አቡነ መልከጼዴቅ አንድ ሁለተኛ የማይሆኑ የሲኖዶሱ አባላት እንኳ ያልተሳተፉበትን ስብሰባ በሊቀ መንበርነት እየመሩ ነው ራሳቸውን ምክትል ፓትርያሪክ ብለው የሾሙት። ይኽም የሚያሳየው የስደተኛው ሲኖዶስ መመሥረትና በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሰው መከፋፈልና መለያየት ምንጩ የአቡነ መልከጼዴቅን የሥልጣን ጥማት ለማርካት መሆኑን ነው። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ በህመም እየተዳከሙ በመጡበት በአሁኑ ሰዓት ምን አልባትም ቅዱስነታቸው ቢያልፉ ፕትርክናው እንዳያልፋቸው የምርጫውን መንገድ መጥረጋቸው እንደሆነ ታምኖበታል። እስከዚያው ወደ ምክትል ፓትርያሪክነት ወምበር መፈናጠጡ ደግሞ የሥልጣን ጥማቱን በሽታ ለማስታገሥ ይመስላል። እግዚኦ አድኅነነ በምህረትከ! እስመ ኢየአምር ሰብእ ዘይመጽእ ላእሌሁ። ትርጉም፦ አቤቱ እንደ ቸርነትህ አድነን፤ ሰው በእርሱ ሕይወት የሚከሰተውን አያውቅምና።
በአንድ ወቅት ቅዱስነታቸው ታመው ሆስፕታል እያሉ አቡነ መልከጼዴቅ ፓትርያሪክ እንደምሆን አስቀድሞ ተነግሮልኛል ብለው በወዳጆቻቸው በኩል በሰፊው ማስወራታቸው ይታወሳል። ይኽ ሁሉ የሚያሳየው እንደምንም ብለው የተመኟትን ሥልጣን ለማግኘት ሲባል የቤተ ክርስቲያን መከፈል እስከ ወዳኛው እንድቀጥል መሆኑን ነው።
ቀደም ሲል በሃያ ዓመታት ጉዞ ውስጥ አቡነ መልከጼዴቅ የአመራር ሥልታቸውን ዘርግተው የነበረው በካህናት ጀርባ ከምዕመናን ጋር ነበር። ለአብያተ ክርስቲያናቱም ይሰጡ የነበረው መመሪያ እንደሚያሳየው ካህናትን ወደ አስተዳደር እንዳታቀርቡ፤ የካህናት ኃላፊነታቸው መቀደስና ማስተማር ብቻ ነው የሚል ነበረ። እንዲሁም በዲሲ ገብርኤል በነበረው ክስ ለፍርድ ቤት በጻፉት ደብዳቤ በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ጉዳይ ቦርድ እንጂ ሊቀ ጳጳሱ አያገባውም ብለው መጻፋቸው ደርሶናል። ካህናትንና ምዕመናንን ለያይተው ከምዕመናን ጋር ብቻ የዘረጉት መሥመር ለቋመጡለት ሥልጣን አመቺ ሆኖ ስላላገኙት የቀድሞ ካባቸውን አውልቀው አዲሱን ካባ ደርበው ብቅ አሉ። አዲሱ ካባ ጎጠኝነትና የሥልጣን ጥማት ያላቸውን ካህናትን ይዞ የፈለጉትን ሥልጣን መቆናጠጡ ነው። ይገርማል! ሊቀ ጳጳሱ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ አይመለከተውም ያለው አንደበት አሁን ምን ስለተገኘ ነው ካህናት ሥልጣኑን መያዝ ይገባቸዋል የሚለው? ስለ ቤተ ክርስቲያን አመራር ተገደው? በፍጹም። መልሱ የራሳቸውን የዓመታት ምኞት ለማሳካት ብቻ መሆኑ ግልጽ ነው።
ምን አልባት አንባቢ ቅዱስ ፓትርያሪኩና የሲኖዶሱ መሥራቾች ጳጳሳት ስንል ግራ ይጋባ ይሆናል። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ በስማቸው ከመጠቀም በስተቀር የሲኖዶሱ መሥራች አልነበሩም። አቡነ መልከጼዴቅና አጋር ጳጳሳት ሲኖዶሱን በአሜሪካ ሲመሠርቱ ቅዱስነታቸው ኬንያ እንደነበሩ ይታወቃል። ወደ አሜሪካ ከመጡም በኋላ ለሲኖዶሱ ባይተዋር ሆነው መኖራቸው ሁሉም የሚያውቀው ሐቅ ነው። በምንም ጉዳይ ላይ ሳይሳተፉ የሚኖሩትም በቤተ ክርስቲያንዋ መከፈል ስለማያምኑበትና የአቡነ መልከጼዴቅም የተንኮል አካሔድ ስለማያስደስታቸው እንደሆነ ብዙዎች የሚያውቁት ነው። ቅዱስነታቸው በራሳቸው አንደበት ለወዳጆቻቸው ይኽን እውነታ ብዙ ጊዜ እንደሚናገሩ ተሰምቷል። ሆኖም ዓቅምና መጠለያ ስለሌላቸው ብቻ እያዘኑ ከሃያ ዓመታት በላይ ዝምታና ትግሥት የተሞላበትን የመገፋት ኑሮ ኖረዋል። አንዳንድ ክንውኖችን በኃይል እየተጫኑአቸው እንዲፈጽሙ መገደዳቸው ይታወቃል። ከዚህም የሊቃነ ጳጳሳቱ ሹመት የሚጠቀስ ነው። ከአራት ኪሎ እስከ አሜሪካ የደረሰባቸው መገፋትና በደል ብዙ ዕዳ ያስከፍላል ብለን እናምናለን። ግና ማን አስተውሎት? መኑ ይሌብዋ ለስሒት ትርጉም፦ ስሕተትን ማን ያስተውላታል? የኢትዮጵያን ምድር ቢናፍቁ፤ በዘመናቸው ቤተ ክርስቲያንዋ አንድ እንድትሆን ቢመኙ ማን ዕድል ሰጥቶአቸው? ሆኖም ጸሎታቸውና ኃዘናቸው አንድ ቀን ምላሽ እንደሚያገኝ እናምናለን።

3.    ቤተ ክርስቲያንን ለዘለዓለም የመክፈል ዓላማ

ከላይ በተቀመጡት ነጥቦች መሠረት የስደተኛውን ሲኖዶስ አካሔድ ስናየው ቤተ ክርስቲያንን ለሥልጣንና ለግል ጥቅም ሲባል ለዘለዓለም ተከፍላ እንድትኖር ያለመው ህልም ነው። ይኽንንም ዓላማ እውን ለማድረግ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ ጋር ሰላምና እርቅ እንደማይኖር አወጀ። ይኽንንም አቡነ መልከጼዴቅ በእሳት ቴሌቪዥን ባደረጉት ንግግር ከኢትዮጵያው ሲኖዶስ ጋር ከእንግዲህ ሰላምና እርቅ የለም በማለት አረጋግጧል። የኢትዮጵያ መንግሥት ሰዎች አሥሯልና ለቤተ ክርስቲያን እርቅና ሰላም የለም ማለት ወይም ቤተ ክርስቲያንዋ እንደተከፈለች ትኖር ማለት መቼም የጤንነት አይመስለንም። የኢትዮጵያ መንግሥትን ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ጉድለትን ለባለሞያዎቹ እንተወውና የቤተ ክርስቲያን መሪ ነኝ የሚል አንድ አባት ቤተ ክርስቲያንን ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት ጋር አነጻጽሮ ሰላምዋን መቃወም እጅግ አሳዛኝ ነው። ምንም እንኳ ወያኔን የምንቃወምበት ብዙ ነገሮች ቢኖሩንም ወያኔን ለመቃወም የቤተ ክርስቲያንን ሰላምና አንድነት ማጨለም የለብንም። ቤተ ክርስቲያንን የተዳፈረ ወታደራዊ መንግሥት እንኳ የውኃ ሽታ ሆኖ እንዳለፈ ወያኔም ነገ ያልፋል። ቤተ ክርስቲያን ግን እስከ ዓለም ፍጻሜ ትኖራለች። በመሆኑም የእግዚአብሔር መንግሥት የሆነችው ቤተ ክርስቲያንን ከፖለቲካ ድርጅት ተርታ ማስቀመጥ አይገባም። ለሀገር ቤቱ ሲኖዶስም በተመሳሳይ መልኩ የምንለው ይኸንኑ ሐቅ ነው። አቡነ መልከጼዴቅ የቤተ ክርስቲያንን ሰላምና እርቅ በአደባባይ መቃወማቸው የተመኙትን ሥልጣን ለመጨበጥ ያላቸውን እቅድ ያሳያል። እምተረፈ ልብ ይነበብ አፍ ይል የለምን? ትርጉም፦ ከልብ ሞልቶ ከተረፈው አፍ ይናገራል እንዲል።
 ከላይ የተቀመጠውን የአቡነ መልከጼዴቅን የሥልጣን ጥማት ለግል ጥቅማቸው ሲሉ የሚጋሩት ጳጳሳትና ካህናትም መኖራቸው ይታወቃል። በስደተኛው ሲኖዶስ ሥር ካሉት ጳጳሳትና ካህናት ኢትዮጵያ ላይ ቤት የሌላቸውና በቤት ኪራይ ያልበለጸጉ ጥቂት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው። የአሜሪካው ኑሮ እንዳይደናቀፍባቸው በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በሚደረገው ስውር ደባ ሁሉ ይስማማሉ። ሕዝቡ ሀገሩን እንዳይረዳ፤ በሀገሩና በቤተ ክርስቲያኑ ላይ መልካም አመለካከት እንዳይኖረው መለያየትን፤ ጎጠኝነትን ይሰብካሉ። እነርሱ ግን በሌላ በኩል ኢትዮጵያ እየተመላለሱ ንብረት ያፈራሉ። ኢትዮጵያ ሲደርሱ የወያኔ፤ አሜሪካ ሲሆኑ የተቃዋሚ መስለውና ተመሳስለው ይኖራሉ። በዚህ ድርጊት የተሰለፉት ጳጳሳትና ካህናት ስም ዝርዝር ስለአለን እንደአስፈላጊነቱ ወደፊት የምናቀርበው ይሆናል። እነዚህ ወገኖች እስከ መቼ ነው ሕዝባችንን የሚያታልሉት? እስከ መቼ ነው ቤተ ክርስቲያን በእነዚህ ወገኖች ሰላምዋን የምታጣው? ይኽንን ብልሹ ታሪክ እንዴት ለልጆቻችን እናወርሳለን? ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናን በአንድነታችን ፀንተን ልንቆምና በቃ ልንላቸው ይገባል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንንም ከወያኔና ከዘረኛው ቡድን ልንታደግ ይገባል።

                                           ቸሩ አምላክ የቤተ ክርስቲያናችንን ሰላምንና አንድነትን ያምጣልን!!!
(ከአዘጋጁ፤  ደጀ ብርሃን መካነ ጦማር ይህን ጽሁፍ ላደረሰን ክፍል ምላሽ መስጠት ለሚሹ የምናስተናግድ መሆኑን እንገልጻለን)

Wednesday, December 31, 2014

በመንበረ ፓትርያርኩ ቅ/ማርያም ገዳም በሚሊዮኖች የሚገመት ገንዘብ መመዝበሩ ተገለጸ

  
 (አዲስ አድማስ፤ ታህሣሥ 29/2007)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የፓትርያርኮች መንበር (መንበረ ፕትርክና) በኾነችው ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብና ንብረት በአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች መመዝበሩን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ጥቆማው የቀረበው፣ የገዳሟ ማኅበረ ካህናትና የልማት ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብና የንብረት አሰባሰብ በተመለከተ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲዘረጋ የገዳሟ ልማት ኮሚቴ የበላይ ጠባቂ ለኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ባቀረቡት ማመልከቻና ሪፖርት ነው፡፡

   የቤተ ክርስቲያኒቱ መተዳደርያ ቃለ ዐዋዲና ደንቡን መሠረት አድርጎ በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ መመሪያ የካህናቱን፣ የምእመናኑንና የእያንዳንዱን ሠራተኛ የሥራ ድርሻና ተጠያቂነት በግልጽ ማስቀመጡን የጠቀሱት ማኅበረ ካህናቱ÷ የገዳሟን ገንዘብና ንብረት የመቆጣጠርና የመከታተል መብታቸው በአስተዳደሩ ሓላፊዎች ተነፍጓቸው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና የንብረት ቁጥጥር ለማድረግ ሳይችሉ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ገዳሚቷ በየዕለቱና በየበዓላቱ ከምእመናን በስጦታና በስእለት የምታገኘው ሀብትና ንብረት ከራስዋ አልፎ ለተቸገሩ ገዳማትና አድባራት የሚተርፍ ቢኾንም ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው የአስተዳደሩ አሠራርና በሰበካ ጉባኤው የቁጥጥር ማነስ ሳቢያ የገቢ አቅሟን ለማጎልበት ከዓመታት በፊት የወጠነችው ኹለ ገብ ሕንፃ ግንባታ ከመጓተቱም በላይ ለሀገረ ስብከቱ መከፈል ለሚገባው ውዝፍ ዕዳ መዳረጓን ካህናቱ አስታውቀዋል፡፡ 

  በገንዘብ አያያዝና በንብረት አሰባሰብ ረገድ በአስተዳደሩ እየተባባሰ የመጣው ሙስና እንዲወገድና ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የተስተጓጎለው የልማት ሥራ እንዲቀላጠፍ በኅዳር ወር አጋማሽ ፓትርያርኩን መጠየቃቸውንም አመልክተዋል፡፡

ከገዳሚቷ የልማት ኮሚቴ ጋራ በመቀናጀት የቀረበውን የማኅበረ ካህናቱን ማመልከቻ መነሻ በማድረግ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በሰጡትና በረዳት ሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጻሚ በኾነው መመሪያ፤ የገዳሟን የገንዘብና ንብረት አሰባሰብ የሚከታተል አምስት ካህናት ያሉት የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ ኮሚቴ ኅዳር 18 ቀን መቋቋሙ ታውቋል፡፡ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ማግሥት አንሥቶ ኅዳር 19 እና 22 ቀናት ባካሔደው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ የተገኘውን ከብር 826‚000 በላይ ገቢ ጨምሮ ከንብረት ሽያጭና በሞዴል 30 የተሰበሰበውን በማካተት ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ አጠቃላይ ገቢ በአንድ ወር ብቻ መመዝገቡ ተገልጧል፡፡ 

በካህናቱ አስፈጻሚነት በአንድ ወር የተወሰነ ቆጠራ ብቻ ይህን ያኽል ገቢ መመዝገቡ፣ የገዳሟ ገቢ ‹‹የግለሰቦች መደራጃ ኾኖ መኖሩን የሚያሳይ ነው፤›› ብለዋል - ማኅበረ ካህናቱ፡፡ አያይዘውም ለሀገረ ስብከቱ መከፈል የሚገባው የኻያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ ሳይፈጸም አኹን በካዝና ያለው ብር 129‚000 ብቻ እንደኾነ በመጥቀስ ገዳሟ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ስትመዘበር እንደኖረችና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ኾነ ሀገረ ስብከቱ በየደረጃው ማግኘት የነበረባቸውን የፐርሰንት ፈሰስ ማጣታቸውን ስለሚያረጋግጥ ‹‹የአስተዳደር ሠራተኞቹን ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡  

    እንደ ማኅበረ ካህናቱ እምነት፣ የገዳሟ ገቢ ለአስተዳደር ሠራተኞቹ ምዝበራ የተጋለጠው የተጠናከረ ሰበካ ጉባኤ ባለመኖሩ ነው፡፡ አኹን ያለው የገዳሙ ሰበካ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው መሠረት፣ የገዳሙን የሥራ ክፍሎች አገልግሎት አፈጻጸም በወቅታዊ የክንውን መግለጫዎች የመከታተል፣ የሒሳብ አያያዙንና የንብረት እንቅስቃሴውን ጊዜውን ጠብቀውና እንዳስፈላጊነቱ በሚቀርቡ ሪፖርቶች የመቆጣጠር ሓላፊነቱን ካለመወጣቱም በላይ ‹‹ገዳሚቷ ችግር ላይ ስትወድቅ ዝም ብሎ የኖረ ተባባሪ›› በመኾኑና የሥራ ጊዜውም በማለፉ ጠንካራና ሓላፊነት በሚሰማው ሰበካ ጉባኤ እንዲተካ መመሪያ እንዲሰጥላቸው፣ ተጀምሮ የቆመው ልማት እንዲቀጥል፣ የገዳሟ ገቢና ወጪም በውጭ ኦዲተሮች እንዲጣራ ማኅበረ ካህናቱ ፓትርያርኩን ጠይቀዋል፡፡ ያለማኅበረ ካህናቱና ማኅበረ ምእመናኑ ፈቃድ ጊዜው በሀ/ስብከቱ ውሳኔ ተራዝሟል የተባለው ሰበካ ጉባኤ፣ በቆጠራ ኮሚቴው የተሰበሰበውን ከብር 440‚000 በላይ የገዳሚቷን ከፍተኛ ገንዘብ ያለተቆጣጣሪ ወጪ ማድረጉን ካህናቱ ገልጸው፣ ሕጋዊ ሰበካ ጉባኤ ሳይቋቋም ቀጣይ ቆጠራ እንደማይካሔድ አስጠንቅቀዋል፡፡

  በገዳሚቷ አስተዳደር ውስጥ ሙስናዊ ጥቅማቸው የተነካባቸው ናቸው ያሏቸው ግለሰቦች፣ የቆጠራ ኮሚቴውን ለማፍረስ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንና ግንቦት ሰባት ናችኹ፤ ምርጫውን ለማወክ ትንቀሳቀሳላችኁ፤ ወደ ሌላ ደብር እናዘዋውራችኋለን›› በሚል ከሚያደርሱባቸው ዛቻና ማስፈራራት እንዲቆጠቡ አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡የማኅበረ ካህናቱንና የልማት ኮሚቴውን ጥያቄ ተከትሎ ፓትርያርኩ በሰጡት መመሪያ÷ ሰበካ ጉባኤው የሥራ ክንውን ሪፖርት ካቀረበ በኋላ የአዲስ ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሔድ፣ የገዳሚቷ ገቢና ወጪ ሒሳብ በአስቸኳይ በውጭ ኦዲተር ተከናውኖ እንዲቀርብ፣ የቆጠራ ኮሚቴው የአስተዳደሩን ዕውቅና አግኝቶ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በ48 ሚልዮን ብር ወጪ በኹለት ምዕራፎች የተጀመረውና የተጓተተው የባለስድስት ፎቅ የአገልግሎትና ኹለገብ ሕንፃ ግንባታ የብቃት ማረጋገጫ ባለው አካል ክትትል እንዲፋጠን ማዘዛቸው ታውቋል፡፡