Tuesday, January 6, 2015

ሰበር ዜና፤ በስደተኛው ሲኖዶስ ሥር ያሉት አያሌ አብያተ ክርስቲያናት ባወጡት የጋራ መግለጫ ሲኖዶሱን የማይቀበሉ መሆናቸውን ገለጡ።

(ደጀ ብርሃን፤ 28/4/2007)
ከምንጮቻችን እንደ ደረሰን አብያተ ክርስቲያናቱ ከዚህ የመረረ የጋራ ውሳኔ የደረሱበት ዋና ምክንያታቸው በጥቅምቱ ሲኖዶስ ስብሰባ የፀደቀው ሕግ/Bylaws መሆኑ ታውቋል። አብያተ ክርስቲያናቱን በቁጣ ያነሳሳው የጥቅምቱ ሲኖዶስ ውሳኔ ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው።

1.    በአዲሱ ሕግ አብያተ ክርስቲያናቱን ለፈለጉት አጀንዳ ማዋል

ስደተኛው ሲኖዶስ ነኝ ባዩ አካል ለሃያ ዓመታት ቤተ ክርስቲያንን ለፖለቲካና ለዘረኝነት ግንባታ ብቻ ሲጠቀም መቆየቱ የሚታወቅ ነው። አሁን ከሃያ ዓመታት በኋላ አዲስ ሕግ ለምን አስፈለገ የሚለው የብዙኃኑ ጥያቄ ሲሆን የአብያተ ክርስቲያናቱንም ቁጣ የቀሰቀሰው ዋና ምክንያት ይኸው ሆኗል። በእርግጥ የዚህ የስደተኛው ሲኖዶስ ነኝ ባይ ቡድን ጅማሬውና ሂደቱም ፖለቲካና የጎጠኝነት ሥራ ብቻ በመሆኑ በሃያ ዓመታት ውስጥ ለቤተ ክርስቲያን ያወጣው መመሪያም ሆነ መዋቅራዊ አስተዳደር እንደሌለ ግልጽ ነው። ቤተ ክርስቲያንን ለሁለት ከፍሎ ራሱን የማደራጀት ዋና ምክንያትም ሥልጣን ያለማግኘት ኩርፊያ እንጂ ሌላ የቀኖና ጉዳይ እንዳልሆነ ዓለም የሚያውቀው ታሪክ ነው። ይኽም እንደሚታወቀው የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ከፕትርክና መውረድን ተከትሎ የቀኖና መፍረስ ጉዳይ ሳይሆን ለፕትርክና የቋመጡት ጳጳሳት ያለመሾም ምክንያት ነው።

 ምክንያቱም ቅዱስነታቸውን በስውር ደባ ያወረዱአቸው ወገኖች ናቸው ኋላ ቀኖና ፈረሰ፤ ፓትርያሪክ እያለ ፓትርያሪክ ተሾመ፤ ሕጋዊ ሲኖዶስ እኛ ነን ብለው ቤተ ክርስቲያንዋን ለሁለት የከፈሉት። ቅዱስነታቸውን ያወረዱት፤ አዲሱን ፓትርያሪክ (ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን) ቁመው ይደልዎ ብለው ያሾሙ፤ የእንኳን አደረሰዎት ድስኩር ያቀረቡ እነዚሁ በአሜሪካን ላይ አዲስ ሲኖዶስ ያቋቋሙት ጳጳሳት መሆናቸው ሀገር ያወቀውና ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው። ልናጽናናችሁ መጣን ብለው የወቅቱን የፖለቲካ አለመረጋጋት ተጠቅመው በወታደራዊ መንግሥትና በወያኔ የቆሰለውን ስደተኛ ሕዝብ ሰበኩት። ወደፈረንጅ ቤተ ክርስቲያን መሔድ እርካታን ያልሰጣቸው ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን ጎጆ ቀልሰው፤ በባህላቸውና በቋንቋቸው ለማምለክ ጀመሩ። በዚያን ጊዜ እገሌ የእነማን ወገን ነው? እገሌ ከየት ክፍለ ሀገር ነው የመጣው? ሳይሉ በአገኙት ካህን መገልገል ነበረ። እነዚህ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን የመክፈል አጀንዳን በውስጥ ሰንቀው፤ የተበተኑትን ምዕመናን ለመሰብሰብና ለማጽናናት መስለው በመቅረባቸው ምዕመናኑም እጃቸውን ዘርግተው ተቀበሉአቸው። ጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለሁለት በመክፈል አሳዛኝ ታሪክ አስመዘገቡ። ቀስ በቀስም ቤተ ክርስቲያንዋን የጎጠኞችና የፖለቲከኞች መደበቂያ አደረግዋት። ያልተለመደና መረን የለቀቀ አስተዳደርንና ሥርዓትን በቤተ ክርስቲያንዋ ዘረጉ። ሃይማኖታችንንና ባህላችንን ጠብቀው ያስጠብቃሉ፤ ሰላም ተፈጥሮ በሀገር ቤትና በውጭ ሀገር ያለችው ቤተ ክርስቲያናችን አንድ ትሆናለች ብለው ምዕመናን እምነት ጥለውባቸው ነበር። ይሁን እንጂ ሰላምን በማወጅ ፋንታ ከእንግዲህ ሰላምና እርቅ የለም ብለው በድፍረት እስከ ማወጅ እምነቱን የጣለባቸውን ሕዝብ ክፉኛ አሳዘኑት። ቤተ ክርስቲያንዋን ለዘለዓለም ከፍለን እንኖራለን የሚለውን ድብቅ አጀንዳቸውን ይዘው አደባባይ ሲወጡ የቤተ ክርስቲያን መከፈልና ተለያይቶ የመኖሩ ጉዳይ እስከ ልጅ ልጁ እንዲቀጥል የማይፈልገውን ሕዝብ ቁጣውን ቀሰቀሱት። የአባትነታቸውን አክብሮት ሳይነፍግ፤ በእምነቱና በአንድነቱ ላይ የሚሠራውን ደባ እንዳላየ ሲታገሥ የኖረ ቢሆንም አሁን ግን ትግሥቱ የተሟጠጠ ይመስላል። ሕዝቡ በጎጥ እንዲለያይ  ጎንደሬ፤ ሸዋ፤ ትግሬ፤ ጉራጌ፤ ኦሮሞ ወዘተ በማለት ከፋፍሎ የመግዛትን ዘይቤ መጠቀም የተለመደ ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ አንድነታቸውን ጠብቀው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውን መለያየትና ዘረኝነትን ለማውገዝ መነሳታቸውን አስተውለናል። ተዳፍኖ የቆየው የሕዝብ ብሶት የሀገር ቤት፤ የውጭ፤ የገለልተኛ የሚለው የመለያየት ምንጭ ከቤተ ክርስቲያን ቅጽረ-ግቢ ፈጽሞ እንዲደርቅ ሕዝባዊ ማዕበልን አስነስቷል። የጎጠኝነት ስብከትና ቀኖና ፈረሰ የሚለው የማስመሰል ሽፋንም ፋሽኑ ያለፈበት ሆኗል።

2.    የአዲስ ፓትርያሪክ ምርጫ

አዲሱ የቤተ ክርስቲያን መተዳደሪያ ተብሎ ያለምልዓተ ጉባኤ የፀደቀው ስለአዲሱ የፓትርያሪክ ምርጫ በዝርዝር ያትታል። የፓትርያሪክን ምርጫ ተከትሎ በጥቅምቱ ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ አመላካች ክንዋኔዎችም ተካሔደዋል። ከእነዚህም መካከል የስደተኛው ሲኖዶስን አቅጣጫ የሚያመላክተው አንዱ አቡነ መልከጼዴቅ ራሳቸውን ምክትል ፓትርያሪክ ብለው መሠየማቸው ነው። በጥቅምቱ ስብሰባ ቅዱስ ፓትርያሪኩ አልተገኙም። ከአሥራ አምስት ጳጳሳት መካከል አምስት ጳጳሳት ብቻ ሲገኙ ከካህናትና ከቦርድ መናብርትም አብዛኛዎቹ እንዳልተገኙ ተገልጿል። አቡነ መልከጼዴቅ አንድ ሁለተኛ የማይሆኑ የሲኖዶሱ አባላት እንኳ ያልተሳተፉበትን ስብሰባ በሊቀ መንበርነት እየመሩ ነው ራሳቸውን ምክትል ፓትርያሪክ ብለው የሾሙት። ይኽም የሚያሳየው የስደተኛው ሲኖዶስ መመሥረትና በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሰው መከፋፈልና መለያየት ምንጩ የአቡነ መልከጼዴቅን የሥልጣን ጥማት ለማርካት መሆኑን ነው። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ በህመም እየተዳከሙ በመጡበት በአሁኑ ሰዓት ምን አልባትም ቅዱስነታቸው ቢያልፉ ፕትርክናው እንዳያልፋቸው የምርጫውን መንገድ መጥረጋቸው እንደሆነ ታምኖበታል። እስከዚያው ወደ ምክትል ፓትርያሪክነት ወምበር መፈናጠጡ ደግሞ የሥልጣን ጥማቱን በሽታ ለማስታገሥ ይመስላል። እግዚኦ አድኅነነ በምህረትከ! እስመ ኢየአምር ሰብእ ዘይመጽእ ላእሌሁ። ትርጉም፦ አቤቱ እንደ ቸርነትህ አድነን፤ ሰው በእርሱ ሕይወት የሚከሰተውን አያውቅምና።
በአንድ ወቅት ቅዱስነታቸው ታመው ሆስፕታል እያሉ አቡነ መልከጼዴቅ ፓትርያሪክ እንደምሆን አስቀድሞ ተነግሮልኛል ብለው በወዳጆቻቸው በኩል በሰፊው ማስወራታቸው ይታወሳል። ይኽ ሁሉ የሚያሳየው እንደምንም ብለው የተመኟትን ሥልጣን ለማግኘት ሲባል የቤተ ክርስቲያን መከፈል እስከ ወዳኛው እንድቀጥል መሆኑን ነው።
ቀደም ሲል በሃያ ዓመታት ጉዞ ውስጥ አቡነ መልከጼዴቅ የአመራር ሥልታቸውን ዘርግተው የነበረው በካህናት ጀርባ ከምዕመናን ጋር ነበር። ለአብያተ ክርስቲያናቱም ይሰጡ የነበረው መመሪያ እንደሚያሳየው ካህናትን ወደ አስተዳደር እንዳታቀርቡ፤ የካህናት ኃላፊነታቸው መቀደስና ማስተማር ብቻ ነው የሚል ነበረ። እንዲሁም በዲሲ ገብርኤል በነበረው ክስ ለፍርድ ቤት በጻፉት ደብዳቤ በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ጉዳይ ቦርድ እንጂ ሊቀ ጳጳሱ አያገባውም ብለው መጻፋቸው ደርሶናል። ካህናትንና ምዕመናንን ለያይተው ከምዕመናን ጋር ብቻ የዘረጉት መሥመር ለቋመጡለት ሥልጣን አመቺ ሆኖ ስላላገኙት የቀድሞ ካባቸውን አውልቀው አዲሱን ካባ ደርበው ብቅ አሉ። አዲሱ ካባ ጎጠኝነትና የሥልጣን ጥማት ያላቸውን ካህናትን ይዞ የፈለጉትን ሥልጣን መቆናጠጡ ነው። ይገርማል! ሊቀ ጳጳሱ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ አይመለከተውም ያለው አንደበት አሁን ምን ስለተገኘ ነው ካህናት ሥልጣኑን መያዝ ይገባቸዋል የሚለው? ስለ ቤተ ክርስቲያን አመራር ተገደው? በፍጹም። መልሱ የራሳቸውን የዓመታት ምኞት ለማሳካት ብቻ መሆኑ ግልጽ ነው።
ምን አልባት አንባቢ ቅዱስ ፓትርያሪኩና የሲኖዶሱ መሥራቾች ጳጳሳት ስንል ግራ ይጋባ ይሆናል። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ በስማቸው ከመጠቀም በስተቀር የሲኖዶሱ መሥራች አልነበሩም። አቡነ መልከጼዴቅና አጋር ጳጳሳት ሲኖዶሱን በአሜሪካ ሲመሠርቱ ቅዱስነታቸው ኬንያ እንደነበሩ ይታወቃል። ወደ አሜሪካ ከመጡም በኋላ ለሲኖዶሱ ባይተዋር ሆነው መኖራቸው ሁሉም የሚያውቀው ሐቅ ነው። በምንም ጉዳይ ላይ ሳይሳተፉ የሚኖሩትም በቤተ ክርስቲያንዋ መከፈል ስለማያምኑበትና የአቡነ መልከጼዴቅም የተንኮል አካሔድ ስለማያስደስታቸው እንደሆነ ብዙዎች የሚያውቁት ነው። ቅዱስነታቸው በራሳቸው አንደበት ለወዳጆቻቸው ይኽን እውነታ ብዙ ጊዜ እንደሚናገሩ ተሰምቷል። ሆኖም ዓቅምና መጠለያ ስለሌላቸው ብቻ እያዘኑ ከሃያ ዓመታት በላይ ዝምታና ትግሥት የተሞላበትን የመገፋት ኑሮ ኖረዋል። አንዳንድ ክንውኖችን በኃይል እየተጫኑአቸው እንዲፈጽሙ መገደዳቸው ይታወቃል። ከዚህም የሊቃነ ጳጳሳቱ ሹመት የሚጠቀስ ነው። ከአራት ኪሎ እስከ አሜሪካ የደረሰባቸው መገፋትና በደል ብዙ ዕዳ ያስከፍላል ብለን እናምናለን። ግና ማን አስተውሎት? መኑ ይሌብዋ ለስሒት ትርጉም፦ ስሕተትን ማን ያስተውላታል? የኢትዮጵያን ምድር ቢናፍቁ፤ በዘመናቸው ቤተ ክርስቲያንዋ አንድ እንድትሆን ቢመኙ ማን ዕድል ሰጥቶአቸው? ሆኖም ጸሎታቸውና ኃዘናቸው አንድ ቀን ምላሽ እንደሚያገኝ እናምናለን።

3.    ቤተ ክርስቲያንን ለዘለዓለም የመክፈል ዓላማ

ከላይ በተቀመጡት ነጥቦች መሠረት የስደተኛውን ሲኖዶስ አካሔድ ስናየው ቤተ ክርስቲያንን ለሥልጣንና ለግል ጥቅም ሲባል ለዘለዓለም ተከፍላ እንድትኖር ያለመው ህልም ነው። ይኽንንም ዓላማ እውን ለማድረግ ከሀገር ቤቱ ሲኖዶስ ጋር ሰላምና እርቅ እንደማይኖር አወጀ። ይኽንንም አቡነ መልከጼዴቅ በእሳት ቴሌቪዥን ባደረጉት ንግግር ከኢትዮጵያው ሲኖዶስ ጋር ከእንግዲህ ሰላምና እርቅ የለም በማለት አረጋግጧል። የኢትዮጵያ መንግሥት ሰዎች አሥሯልና ለቤተ ክርስቲያን እርቅና ሰላም የለም ማለት ወይም ቤተ ክርስቲያንዋ እንደተከፈለች ትኖር ማለት መቼም የጤንነት አይመስለንም። የኢትዮጵያ መንግሥትን ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ጉድለትን ለባለሞያዎቹ እንተወውና የቤተ ክርስቲያን መሪ ነኝ የሚል አንድ አባት ቤተ ክርስቲያንን ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት ጋር አነጻጽሮ ሰላምዋን መቃወም እጅግ አሳዛኝ ነው። ምንም እንኳ ወያኔን የምንቃወምበት ብዙ ነገሮች ቢኖሩንም ወያኔን ለመቃወም የቤተ ክርስቲያንን ሰላምና አንድነት ማጨለም የለብንም። ቤተ ክርስቲያንን የተዳፈረ ወታደራዊ መንግሥት እንኳ የውኃ ሽታ ሆኖ እንዳለፈ ወያኔም ነገ ያልፋል። ቤተ ክርስቲያን ግን እስከ ዓለም ፍጻሜ ትኖራለች። በመሆኑም የእግዚአብሔር መንግሥት የሆነችው ቤተ ክርስቲያንን ከፖለቲካ ድርጅት ተርታ ማስቀመጥ አይገባም። ለሀገር ቤቱ ሲኖዶስም በተመሳሳይ መልኩ የምንለው ይኸንኑ ሐቅ ነው። አቡነ መልከጼዴቅ የቤተ ክርስቲያንን ሰላምና እርቅ በአደባባይ መቃወማቸው የተመኙትን ሥልጣን ለመጨበጥ ያላቸውን እቅድ ያሳያል። እምተረፈ ልብ ይነበብ አፍ ይል የለምን? ትርጉም፦ ከልብ ሞልቶ ከተረፈው አፍ ይናገራል እንዲል።
 ከላይ የተቀመጠውን የአቡነ መልከጼዴቅን የሥልጣን ጥማት ለግል ጥቅማቸው ሲሉ የሚጋሩት ጳጳሳትና ካህናትም መኖራቸው ይታወቃል። በስደተኛው ሲኖዶስ ሥር ካሉት ጳጳሳትና ካህናት ኢትዮጵያ ላይ ቤት የሌላቸውና በቤት ኪራይ ያልበለጸጉ ጥቂት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው። የአሜሪካው ኑሮ እንዳይደናቀፍባቸው በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በሚደረገው ስውር ደባ ሁሉ ይስማማሉ። ሕዝቡ ሀገሩን እንዳይረዳ፤ በሀገሩና በቤተ ክርስቲያኑ ላይ መልካም አመለካከት እንዳይኖረው መለያየትን፤ ጎጠኝነትን ይሰብካሉ። እነርሱ ግን በሌላ በኩል ኢትዮጵያ እየተመላለሱ ንብረት ያፈራሉ። ኢትዮጵያ ሲደርሱ የወያኔ፤ አሜሪካ ሲሆኑ የተቃዋሚ መስለውና ተመሳስለው ይኖራሉ። በዚህ ድርጊት የተሰለፉት ጳጳሳትና ካህናት ስም ዝርዝር ስለአለን እንደአስፈላጊነቱ ወደፊት የምናቀርበው ይሆናል። እነዚህ ወገኖች እስከ መቼ ነው ሕዝባችንን የሚያታልሉት? እስከ መቼ ነው ቤተ ክርስቲያን በእነዚህ ወገኖች ሰላምዋን የምታጣው? ይኽንን ብልሹ ታሪክ እንዴት ለልጆቻችን እናወርሳለን? ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናን በአንድነታችን ፀንተን ልንቆምና በቃ ልንላቸው ይገባል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንንም ከወያኔና ከዘረኛው ቡድን ልንታደግ ይገባል።

                                           ቸሩ አምላክ የቤተ ክርስቲያናችንን ሰላምንና አንድነትን ያምጣልን!!!
(ከአዘጋጁ፤  ደጀ ብርሃን መካነ ጦማር ይህን ጽሁፍ ላደረሰን ክፍል ምላሽ መስጠት ለሚሹ የምናስተናግድ መሆኑን እንገልጻለን)

Wednesday, December 31, 2014

በመንበረ ፓትርያርኩ ቅ/ማርያም ገዳም በሚሊዮኖች የሚገመት ገንዘብ መመዝበሩ ተገለጸ

  
 (አዲስ አድማስ፤ ታህሣሥ 29/2007)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የፓትርያርኮች መንበር (መንበረ ፕትርክና) በኾነችው ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብና ንብረት በአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች መመዝበሩን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ጥቆማው የቀረበው፣ የገዳሟ ማኅበረ ካህናትና የልማት ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብና የንብረት አሰባሰብ በተመለከተ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲዘረጋ የገዳሟ ልማት ኮሚቴ የበላይ ጠባቂ ለኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ባቀረቡት ማመልከቻና ሪፖርት ነው፡፡

   የቤተ ክርስቲያኒቱ መተዳደርያ ቃለ ዐዋዲና ደንቡን መሠረት አድርጎ በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ መመሪያ የካህናቱን፣ የምእመናኑንና የእያንዳንዱን ሠራተኛ የሥራ ድርሻና ተጠያቂነት በግልጽ ማስቀመጡን የጠቀሱት ማኅበረ ካህናቱ÷ የገዳሟን ገንዘብና ንብረት የመቆጣጠርና የመከታተል መብታቸው በአስተዳደሩ ሓላፊዎች ተነፍጓቸው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና የንብረት ቁጥጥር ለማድረግ ሳይችሉ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ገዳሚቷ በየዕለቱና በየበዓላቱ ከምእመናን በስጦታና በስእለት የምታገኘው ሀብትና ንብረት ከራስዋ አልፎ ለተቸገሩ ገዳማትና አድባራት የሚተርፍ ቢኾንም ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው የአስተዳደሩ አሠራርና በሰበካ ጉባኤው የቁጥጥር ማነስ ሳቢያ የገቢ አቅሟን ለማጎልበት ከዓመታት በፊት የወጠነችው ኹለ ገብ ሕንፃ ግንባታ ከመጓተቱም በላይ ለሀገረ ስብከቱ መከፈል ለሚገባው ውዝፍ ዕዳ መዳረጓን ካህናቱ አስታውቀዋል፡፡ 

  በገንዘብ አያያዝና በንብረት አሰባሰብ ረገድ በአስተዳደሩ እየተባባሰ የመጣው ሙስና እንዲወገድና ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የተስተጓጎለው የልማት ሥራ እንዲቀላጠፍ በኅዳር ወር አጋማሽ ፓትርያርኩን መጠየቃቸውንም አመልክተዋል፡፡

ከገዳሚቷ የልማት ኮሚቴ ጋራ በመቀናጀት የቀረበውን የማኅበረ ካህናቱን ማመልከቻ መነሻ በማድረግ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በሰጡትና በረዳት ሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጻሚ በኾነው መመሪያ፤ የገዳሟን የገንዘብና ንብረት አሰባሰብ የሚከታተል አምስት ካህናት ያሉት የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ ኮሚቴ ኅዳር 18 ቀን መቋቋሙ ታውቋል፡፡ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ማግሥት አንሥቶ ኅዳር 19 እና 22 ቀናት ባካሔደው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ የተገኘውን ከብር 826‚000 በላይ ገቢ ጨምሮ ከንብረት ሽያጭና በሞዴል 30 የተሰበሰበውን በማካተት ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ አጠቃላይ ገቢ በአንድ ወር ብቻ መመዝገቡ ተገልጧል፡፡ 

በካህናቱ አስፈጻሚነት በአንድ ወር የተወሰነ ቆጠራ ብቻ ይህን ያኽል ገቢ መመዝገቡ፣ የገዳሟ ገቢ ‹‹የግለሰቦች መደራጃ ኾኖ መኖሩን የሚያሳይ ነው፤›› ብለዋል - ማኅበረ ካህናቱ፡፡ አያይዘውም ለሀገረ ስብከቱ መከፈል የሚገባው የኻያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ ሳይፈጸም አኹን በካዝና ያለው ብር 129‚000 ብቻ እንደኾነ በመጥቀስ ገዳሟ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ስትመዘበር እንደኖረችና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ኾነ ሀገረ ስብከቱ በየደረጃው ማግኘት የነበረባቸውን የፐርሰንት ፈሰስ ማጣታቸውን ስለሚያረጋግጥ ‹‹የአስተዳደር ሠራተኞቹን ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡  

    እንደ ማኅበረ ካህናቱ እምነት፣ የገዳሟ ገቢ ለአስተዳደር ሠራተኞቹ ምዝበራ የተጋለጠው የተጠናከረ ሰበካ ጉባኤ ባለመኖሩ ነው፡፡ አኹን ያለው የገዳሙ ሰበካ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው መሠረት፣ የገዳሙን የሥራ ክፍሎች አገልግሎት አፈጻጸም በወቅታዊ የክንውን መግለጫዎች የመከታተል፣ የሒሳብ አያያዙንና የንብረት እንቅስቃሴውን ጊዜውን ጠብቀውና እንዳስፈላጊነቱ በሚቀርቡ ሪፖርቶች የመቆጣጠር ሓላፊነቱን ካለመወጣቱም በላይ ‹‹ገዳሚቷ ችግር ላይ ስትወድቅ ዝም ብሎ የኖረ ተባባሪ›› በመኾኑና የሥራ ጊዜውም በማለፉ ጠንካራና ሓላፊነት በሚሰማው ሰበካ ጉባኤ እንዲተካ መመሪያ እንዲሰጥላቸው፣ ተጀምሮ የቆመው ልማት እንዲቀጥል፣ የገዳሟ ገቢና ወጪም በውጭ ኦዲተሮች እንዲጣራ ማኅበረ ካህናቱ ፓትርያርኩን ጠይቀዋል፡፡ ያለማኅበረ ካህናቱና ማኅበረ ምእመናኑ ፈቃድ ጊዜው በሀ/ስብከቱ ውሳኔ ተራዝሟል የተባለው ሰበካ ጉባኤ፣ በቆጠራ ኮሚቴው የተሰበሰበውን ከብር 440‚000 በላይ የገዳሚቷን ከፍተኛ ገንዘብ ያለተቆጣጣሪ ወጪ ማድረጉን ካህናቱ ገልጸው፣ ሕጋዊ ሰበካ ጉባኤ ሳይቋቋም ቀጣይ ቆጠራ እንደማይካሔድ አስጠንቅቀዋል፡፡

  በገዳሚቷ አስተዳደር ውስጥ ሙስናዊ ጥቅማቸው የተነካባቸው ናቸው ያሏቸው ግለሰቦች፣ የቆጠራ ኮሚቴውን ለማፍረስ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንና ግንቦት ሰባት ናችኹ፤ ምርጫውን ለማወክ ትንቀሳቀሳላችኁ፤ ወደ ሌላ ደብር እናዘዋውራችኋለን›› በሚል ከሚያደርሱባቸው ዛቻና ማስፈራራት እንዲቆጠቡ አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡የማኅበረ ካህናቱንና የልማት ኮሚቴውን ጥያቄ ተከትሎ ፓትርያርኩ በሰጡት መመሪያ÷ ሰበካ ጉባኤው የሥራ ክንውን ሪፖርት ካቀረበ በኋላ የአዲስ ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሔድ፣ የገዳሚቷ ገቢና ወጪ ሒሳብ በአስቸኳይ በውጭ ኦዲተር ተከናውኖ እንዲቀርብ፣ የቆጠራ ኮሚቴው የአስተዳደሩን ዕውቅና አግኝቶ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በ48 ሚልዮን ብር ወጪ በኹለት ምዕራፎች የተጀመረውና የተጓተተው የባለስድስት ፎቅ የአገልግሎትና ኹለገብ ሕንፃ ግንባታ የብቃት ማረጋገጫ ባለው አካል ክትትል እንዲፋጠን ማዘዛቸው ታውቋል፡፡

Tuesday, December 30, 2014

አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋዩ ማነው?



     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ስንት ጠንቅዋይ እንዳለ ሰፊ ጥናት ተደርጎ ነበር። በተገኘው ጥናት የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ቁጥሩ እጅግ አስደንጋጭ ነው። ጥንቆላን መደበኛ ሥራቸው አድርገው ባለጉዳይ አዲስ አበቤዎችን በማስተናገድ ላይ የተሰማሩ 4000 /አራት ሺህ/ ገደማ ጠንቅዋዮች መኖራቸውን የተደረገው የዳሰሳ ጥናት ያረጋግጣል። 4000 ሺህ ገደማ ጠንቅዋይ በአዲስ አበባ ብቻ መገኘቱ እግዚኦ መሐረነ! የሚያሰኝ ነው። በመላ ሀገሪቱ በአጠቃላይ ቢጠናማ ሚሊዮን ጠንቅዋዮች ይኖራሉ ማለት ነው።
  አንዳንዶች «ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ናት» ሲሉ አያፍሩም። ቀላል ቁጥር የማይባለውን ጠንቅዋይ ስንመለከት ለጠንቋዮቹስ ደሴት የማትሆንበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ደግሞም በተደረገው ጥናት እንደተመለከተው አብዛኛዎቹ ጠንቋዮች ክርስቲያን ነን ባዮች ናቸው። ስለዚህ «የክርስቲያን ደሴት ናት» ባዮች ጠንቋይ ክርስቲያኖችንም ጨምረው ከሆነ አባባላቸው እውነትነት ሊኖረው ይችላል። ነገር ግን ክርስቲያን መሆን ማለት ምን ማለት ነው? በሚለው ጉዳይ ላይ ጥያቄን ያስነሳል።  ጠንቅዋይ ክርስቲያኖች በሞሉባትና ክርስቲያን ነን የሚሉ የጠንቅዋይ አገልግሎት ተጠቃሚዎች በበዙባት ኢትዮጵያክርስትናና የክርስትና ደሴት ማለት ከስም ባለፈ ትርጉም የለውም ማለት ነው። በአጭር ቃል ክርስትና ተነገረባት እንጂ አልተኖረባትም ማለት ነው።
ያልተኖረበት ክርስትና ደግሞ ሙት ነው።

«በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው» ኤፌ 2፤1-2

ሐዋርያው ጳውሎስና በርናባስ በቆጵሮስ ደሴት ጫፍ ላይ ወደምትገኝ ጳፉ/ ፓፎስ/ ከተማ በገቡ ጊዜ በርያሱስ የሚባል አንድ አይሁዳዊ ጠንቅዋይና ሐሰተኛ ነብይ አግኝተው ነበር። /የሐዋ 13፤6 / ይህ በርያሱስ /1/  የተባለው ሰው በሃይማኖት አይሁዳዊ በተግባሩ ግን ጠንቅዋይ ነው።  ይህ ሰው የሚያሳስተው የአገሩን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የሚመራ አገረ ገዢውን ጭምር ነበር።  በጠንቅዋይ የጥንቆላ ጥበብ የምትመራ አገር ምን ልትመስል እንደምትችል ለመገመት አይከብድም።  በሌላ ስምም «ኤልማስ» /2/ የተባለው ይህ ጠንቅዋይ አገረ ገዡን መቆጣጠር ማለት አገሪቱን በራሱ የመንፈስ ግዛት ስር ማስተዳደር ማለት በመሆኑ  የጳውሎስንና የበርናባስን የወንጌል ስብከት እንዳይሰማ አጥብቆ ሲቃወም እናያለን።  መንፈሱ እንዳይገለጥና እውነት እንዳይታወቅ አጥብቆ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ ሕዝቡን በመንፈሱ ባርነት ስር ከማስገባት ባሻገር መሪዎችንም አጥምዶ መያዝ ዋና ሥራው ነው። መሪዎች የያዙት ወንበር በሥራቸው ባለው ሕዝብ ላይ የሚፈልገውን ተጽዕኖ ለማሳረፍ እንደሚጠቅመው አሳምሮ ያውቃል። ልክ ማኅበረ ቅዱሳን የሲኖዶስ አባላት የሆኑ ጳጳሳትን በራሱ ፈቃድ ስር መቆጣጠር ማለት የሲኖዶስን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት እንደሆነ ገብቶት እንደሚሰራው ማለት ነው። የሲኖዶሱን ጉባዔ መቆጣጠር ማለት ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መቆጣጠር ማለት ነው።

 ይህ በርያሱስ በተባለው ሰው ላይ ያደረው የጥንቆላ መንፈስ  አገረ ገዢው ወደነጳውሎስ የእውነት ቃል ልቡን እንዳይመልስ አጥብቆ በተቃወመ ጊዜ «ጳውሎስ የተባለው ሳውል ግን በመንፈስ ቅዱስ ትኩር ብሎ ተመለከተውና አንተ ተንኰል ሁሉ ክፋትም ሁሉ የሞላብህ፥ የዲያብሎስ ልጅ፥ የጽድቅም ሁሉ ጠላት፥ የቀናውን የጌታን መንገድ ከማጣመም አታርፍምን?» ሲለው እንመለከታለን።( የሐዋ 13፤10 )

    ስለሆነም ጠንቅ ዋዮችና አሰተኛ ነብያት ሁሉ ተንኰልና ክፋት የሞላባቸው፤ የዲያብሎስም ልጆች፤ የጽድቅ ሁሉ ጠላት፤ ቀናውን የጌታን መንገድ የሚያጣምሙ ናቸው እንጂ ክርስቲያን በመሆናቸው ወይም በመሰኘታቸው ወይም ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች በግልጥም በስውርም የእነሱን አገልግሎት ተጠቃሚዎች ሁሉ የሚባሉት ክርስቲያን ሳይሆን የክፋቱ መንፈስ ተካፋዮች ነው።  እንዲያውም ከአሳቹና ከተቃዋሚው መንፈስ አገልግሎት ማግኘት አይደለም! ሰላም የሚላቸው ቢኖር ከክፉ ሥራቸው ተካፋይ የመሆን ያህል ነውና ሁሉም በመንፈሱ ተይዘዋል ማለት ይቻላል። 

   በዚህ መልኩ ከ4000 የአዲስ አበባ ከተማ ጠንቅዋዮች አገልግሎት የጠየቁ ተራ ሕዝብና ትላልቅ ሹማምንት ስንት ይሆኑ ይሆን? በቀላል ስሌት እያንዳንዱ ጠንቅዋይ በቀን ዐሥር ሰው ቢያስተናግድ 4000 ሲባዛ በ10= 40,000 /አርባ ሺህ/ ሰዎች በየቀኑ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ሆነዋል ማለት ነው። በወራትና በዓመታት ስናሰላው በተደጋጋሚ ሊሄዱ የሚችሉትን የስሌት ግምት ቀንሰን ሚሊዮን ተጠቃሚዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ በቀላል ሎጂክ ማወቅ ይቻላል። ይህ እንግዲህ እንደነታምራት ገለታ ያሉትን በቀን ውስጥ በሺህ ሰው የሚያንጋጉትን ከፍተኛ ቁጥር ሳይጨምር መሆኑን ልብ ይበሉ። እያንዳንዱ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ በሕይወት ዘመኑ ቢያንስ አንድ ጊዜ ከጠንቅዋይ፤ ከቅጠል በጣሽ ደብተራ፤ ከአስማትና ከክታብ ፀሐፊ ዘንድ ሊሄድ እንደሚችል አመላካች መረጃ ነው። እናስ? አገሪቱን የተቆጣጠረው ይህ መንፈስ እግር ተወርች አስሮ የግዛቱ ምርኮኛ በማድረግ የእግዚአብሔር ክብር እንዳይገለጽ ተግቶ እየሰራ አይደለምን?  
   የቀናው የጌታ መንገድ እየተጣመመ እውነት የማይገለጠው ወይም የተገለጠው የሚዳፈነው በዚህ የክፋት መንፈስ የታሰረ ሕዝብ በመኖሩ ምክንያት መሆኑን መካድ አይቻልም።  የክፋት ሠራዊት ራሱ፤ አራዊት ማኅበር ያቋቋመው ቀናው መንገድ እንዳይገለጥ ከሚሰራባቸው መንገዶች አንዱ መሆኑንም ልብ ማለቱ ጠቃሚ ነገር ነው።

   ሰርግዮስ ጳውሎስ የተባለው አገረ ገዢ ሳይቀር ከጠንቅዋይ መንፈስ ጋር ኅብረት ያደርግ እንደነበር ማሳየቱ የሚጠቁመን ነገር ሹማምንትም የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች መሆናቸውንና ከዚህ መንፈስ ምሪት በሚያገኙት ምክር የሚሰሩት ሥራ ምን ሊሆን እንደሚችል ያሳየናል።  ከዚያም ባሻገር ጠንቅዋዮች የባለሥልጣን ከለላ እንዲያገኙና በአገሪቱ ውስጥ ያለሥጋት የመንፈስ ሥራቸውን እንዲፈጽሙ እድል የሚሰጣቸው  እንደሆነ ለመገመት  ይቻላል።  በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የዚህን ያህል ቁጥር ያላቸው ጠንቅዋዮች የመብዛታቸው ምክንያትም ይኸው ነው።  የአዲስ አበባ ጠንቅዋዮች እንዲስፋፉ እድልና ጊዜን የሰጣቸው የመንፈሱ አገልጋዮች መኖራቸው እንጂ እግዚአብሔር ደስ ስለተሰኘና ሰለፈቀደላቸው አይደለም። የቤተ ክህነቱ ጠንቅ-ዋይ ማኅበርም ቢሆን የመቆየት እድል ያገኘው እሱ እንደሚለው እግዚአብሔር ስላቆመው ሳይሆን የጠንቅ-ዋይ ሰላባ የሆኑ የቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አመራሮች አብረው ለመንፈሱ አሰራር ስለተሰለፉ ብቻ ነው። እግዚአብሔር ለክፉው መንፈስ አሠራር ፈቃደኛ የሆኑትን ሰዎች ለፈቃዳቸው አሳልፎ በመስጠት የሚተዋቸው ሰዎች ማድረግ ለሚፈልጉት ነገር ነጻ ፈቃድ ያላቸው ፍጥረቶች ስለሆኑ ብቻ ነው።

   የዚህን ያህል ቁጥር ባለው ጠንቅዋይና አስማተኛ ደብተራ ተገልጋዩ ማነው? ብለን ብንጠይቅ በአብዛኛው እምነት አለን በሚሉ ክርስቲያኖችና ሌሎች ሰዎች መሆናቸውም በተደረገው ጥናት ላይ ተመልክቷል። ከዚህም ውስጥ ሰፊውን ቁጥር የያዙት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ናቸው። የዚህ ታሪክ ፀሐፊ ከአንድ የጥንቁልና አገልግሎት ተጠቃሚ ከነበረ ሀብታም ሰው ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው አዋቂ ከተባለ ባለዑቃቢ የተሰጠው ትእዛዝ « የልደታን ታቦት በደባልነት ከዚህ ቤተ ክርስቲያን አስገብተህ፤ ካህናቱን እየደገስህ አብላ፤ በየዓመቱም ዝክር ዘክር ተብለኻል» በማለት ቃል ያስገባው ሲሆን ይህንኑ ተግባር እስካሁን ሳያቋርጥ እየፈጸመው የመገኘቱ ጉዳይ ነው። ለዚህ ሰው ደባል ታቦት ፈቃጅነት፤ በአገልግሎት ሰጪነት የሚያገለግል ካህን፤ በንግሥ በዓል ላይ የሚሰማራው ሰጋጅና አንጋሽ ሕዝብ  እግዚአብሔርን እያከበረ ቢመስለውም የመንፈሱ አሠራር በሃይማኖት ከለላ ምን ያህል የነፍስ ወረራ እንደሚፈጽም ከሚያሳይ በስተቀር ከእግዚአብሔር ሃሳብ ጋር አንዳችም ግንኙነት የለውም። በተለይም በአዲስ አበባ ሀብታም የሆኑ አፍቃሬ ደብተራ ሰዎች የእገሌን ታቦት እያሉ በስማቸው ደባል አድርገው በማስገባትና በመትከል ላይ ተጠምደዋል።

 ከዚህም በላይ ጳጳሳቱ ሳይቀሩ የሚፈልጉትን ነገር በሚፈልጉበት ደብር እያስነገሱ ሕዝቡን ለስውሩ መንፈስ አገዛዝ አሳልፈው መስጠታቸው ሳያንስ ከሰይጣን ጋር የተዋርሶ ኪዳን የፈጸሙ፤ ከጠላት መከላከያ የሚሆን ዐቃቤ ርዕስ የሚል አስማትና ድግምት ጭምር እንደሚይዙ ይነገራል። የጠላት መንፈስ ባለበት ሁሉ አድማ፤ ሁከት፤ ብጥብጥ፤ ክርክር፤ ጥል፤ ጭቅጭቅ፤ ቡድንተኝነት፤ ዝሙት፤ ሙስና መኖሩ በራሱ የክፉው መንፈስ ብርታት ምን ያህል አካባቢውን እንደወረረ ማሳያ ነው።  የመንፈስ ፍሬ የሆኑቱ ምልክቶች የማይታይባቸውም ለዚህ ነው።  እነዚህን ምልክቶችን አይቼባቸዋለሁ ብሎ ምስክርነት ሊሰጥ የሚችል ከተገኘ በእውነት ድንቅ ነው።   
                          
«የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው» ገላ5፤22

 በግልጥ የሚታወቁና ጥንቆላን የሚጠቀሙ ጳጳሳት እንዳሉ በመረጃ አስደግፎ ሥራቸውንና ቦታቸውን ጠቅሶ መናገር ይቻላል። ከብዙዎቹም አንዱ በናይሮቢ ከተማ የሚኖሩ አንዕስት ኢትዮጵያውያትን በስመ «አውቅልሻለሁ፤ አጠምቅሻለሁ» ሰበብ የአስማትና የቅጠላ ቅጠል ጭማቂ እየነከረ የሚያደነዝዛቸውና ኀፍረተ ሥጋቸውን ሳይቀር የሚዳብስ ጠንቅዋይ ጳጳስ የክፉው መንፈስ ተካፋይ ካልሆነ የቅዱስ መንፈስ ማደሪያ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው? ከዚያም በዘለለ ሁኔታ ውስጥ የድርጊቱ ሰለባ  ስለመኖራቸው በሀዘን የሚናገሩም ተገኝተዋል። የአገራችን ሰው ጉዳዩን ማውጣት ሲከብደው «ውስጡን ለቄስ ይላል» እኛም ውስጡን «ወኅቡረ ዐለወ» ለሚባለው ለሲኖዶስ ትተነዋል።

    ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደተቋም በአዋጅ የምትቃወመውና የምታወግዘው ብትሆንም በየትኛውም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጥንቆላ፣ ለአስማት፤ ለምትሃት፤ ለድግምት፤ ለመርበብት፤ ለተዋርሶና ለተመሳሳይ የመናፍስት አሠራር ያልተጋለጠ ሰው ማግኘት እጅግ አዳጋች ነው። ወይ ሰርቷል፤ አለያም አሰርቷል ወይም አይቷል፤ አለያም ከብጥስጣሽ ክታባት ጋር በሆነ አጋጣሚ ተገናኝቷል። ይህ በሕይወት ገጠመኝ ያየነው የማይታበል እውነት ነው። ይህ ልምምድ ሠርጎ ከገባ በኋላ ውስጥ ለውስጥ ነግሶ እንደቆየ ዘመናትን አሳልፏል። በአጠቃላይ ሲታይ አዲስ አበባ ትሁን መላ አገሪቱ በአንድም፤ በሌላ መንገድም የክፉ መንፈስ እስረኛ ሆናለች። «ለሞት መድኃኒት አለን» ከሚለው ማስታወቂያ በስተቀር ለቡዳ፤ ለመጋኛ፤ ለዛር፤ ለውቃቤ/ዐቃቤ/፤ ለሚያስቃዥ፤ ለሟርት፤ ለገበያ፤ ለመስተፋቅር፤ ለእጀ ሰብእ በደፈናው ለሌሎችም ችግሮች ፍቱን መፍትሄ እንሰጣለን» የሚሉ ማስታወቂያዎች ከተማውን ያጠለቀለቁት የክፉው መንፈስ አሠራር ተንሰራፍቶ በአገሪቱ የመንገሱ ምልክት ነው።  

  በአንድ ወቅት ጌታቸው ዶኒ የተባለ ሰው ቡዳ የበላውን መኪና ከቤተ ክርስቲያን ግቢ አስቁሞ ጸበል ሲረጨው ታይቶ ነበር። አሁን መኪናን ቡዳ የሚባለው እንዴት ነው? ድሮ ሰው ነበር ተበላ የሚባለው በዚህ ዘመን ደግሞ መኪናውንም ሳይቀር የሚቀረጥፍ ጥርስ ያለው ቡዳ ተፈጥሯል። ኢትዮጵያ የመኪና አደጋ የተበራከተባት ቡዳ እየበላባት ይሆናል። የትራፊክ መሥሪያ ቤትም የመኪና አደጋውን ለመቀነስ ጸበል እየገዛ መኪኖችን መርጨት አለበት ማለት ነው። የጌታቸው የግብር ታናሽ ወንድም የሆነው ግርማ ወንድሙ ደግሞ የሀገር ቤቱን ቡዳ ገድሎ የጨረሰ ያህል አበሾችን ብቻ የሚከተለውን ቡዳና እጀ ሰብእ ለመግደል ባህር ማዶ ሄዶ የማርከሻ ጸበል እየረጨሁ ነው ይለናል።  የነ ግርማ ወንድሙ ክህነት ሰጪ፤ ሻሚ ሸላሚዎች ደግሞ የመንፈሱ ደጋፊዎች እነዚያው ጳጳሳት መሆናቸውን ስንመለከት የክፉው መንፈስ ኃይል ምን ያህል ስር እንደሰደደ ያሳያል።

ጥንቆላና ቀጠል በጣሽ ደብተራ በአዲስ አበባ ምን እየሰራ እንዳለ የሚያሳይ «ፔሌማ» በሚል ርዕስ የተሠራ ፊልም የድርጊቱን ስፋት በሰፊው ያትታልና ቢመለከቱ ጥሩ ግንዛቤ ሊያገኙ እንደሚችሉ ይገመታል።

እግዚአብሔር አምላክ «አስማተኛም፥ መተተኛም፥ በድግምት የሚጠነቍልም፥ መናፍስትንም የሚጠራ፥ ጠንቋይም፥ ሙታን ሳቢም በአንተ ዘንድ አይገኝ» በዘዳ 18፤11 ላይ ቢናገርም በዚህ ዘመን ከመገኘት ባለፈ መደበኛ ሥራ ሆኗል። ስለዚህም የእግዚአብሔር ረድዔትና በረከት ርቆናል።

እርስዎ አዲስ አበባን በወረራት የጠንቅዋይ መንፈስ ተገልጋይ ማነው ይላሉ? እንቅፋት መታኝ ፤ ጥቁር ውሻ አቋረጠኝ፤ እብድ ለከፈኝ፤ ሲቀዳ ያልሞላ አልጠጣም፤ በቀኝ አውለኝ፤ ኮከቤ አይወደውም፤ ሴጣኔን አታምጣብኝ፤ ዓይነ ጥላ አለበት፤ ገፊ፤ ከማያቁት መልዓከ የሚያውቁት ሴጣን ይሻላል ወዘተ ብሂሎች እርስዎ ብለው ወይም ያለ ሰው ሰምተው ያውቃሉ? እነዚህ አባባሎች ምንን ያመለክታሉ? እስኪ ይመርምሯቸው!
-----------------------------
/1/ በርያሱስ ማለት በአረማይክ ቋንቋ የኢያሱ ልጅ ማለት ነው።
/2/ ኤልማስ ማለት ጥበብ ማለት ነው።

Saturday, December 20, 2014

“ ቅ/ ሲኖዶሱ በአድባራት ሓላፊዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ነው ” /ፓትርያርኩ/


  (  አዲስ አድማስ ) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ‹‹የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና በሰጠችው ማኅበር ላይ ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ባላቸው አንዳንድ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራት አስተዳዳሪዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አፈጻጸም ‹‹ሕገ መንግሥቱንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር ነው›› በሚል ፓትርያርኩ ማገዳቸው ተገለጸ፡፡
ፓትርያርኩ ባለፈው ኅዳር 30 ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ ‹‹አፈጻጸሙ እንዲቆይ›› በማለት ያገዱት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት በተካሔዱ ጉባኤዎች÷ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል፤ ይህም አነጋገር ጉባኤውን ቅር አሰኝቷል፤›› ያላቸው የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ በመንበረ ፓትርያርክና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሾች በተካሔዱት ስብሰባዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም አስተዳደርና ወቅታዊ ችግሮች የተመለከቱ የጉባኤተኞች አስተያየቶችና ሐሳቦች መቅረባቸውን በደብዳቤያቸው ያስታወሱት ፓትርያርኩ፤ ተሰብሳቢዎቹ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ መናገራቸውና አሉ የተባሉ ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ መጠየቃቸው ‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃም ኾነ በሀገራችን ለሕዝብ የተፈቀደ ዴሞክራሲያዊ መብት መኾኑ አያጠያይቅም›› ብለዋል፡፡ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ ያቀረቡ ሰዎችን መገሠጽና መውቀስም ሕገ መንግሥቱን እንደሚፃረር ጠቁመዋል፡፡
ጉባኤዎቹ በቤተ ክርስቲያን ጠሪነት የተካሔዱ እንደነበሩና ተሰብሳቢዎቹም የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት፣ አገልጋዮችና ሠራተኞች መኾናቸውን ፓትርያርኩ ጠቅሰው÷ የጎደለው እንዲሟላ የጠመመው እንዲቃና ያላቸውን አስተያየት በማቅረባቸው ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹የስብሰባ ነፃነትንና መብትን ነፍጎ ሐቁ እንዳይነገር›› የሚከለክልና ውጤቱም ‹‹ጊዜ ያለፈበትን አፈና በማንገሥ ችግሮች ተባብሰው እንዲቀጥሉ የሚያደርግ ነው›› ብለዋል፡፡ “በውይይቱ ወቅት ‹‹የዳኅፀ ልሳን ወለምታ›› አጋጥሞም ከኾነ በወቅቱ ማብራሪያና ማስተካከያ ይሰጥበታል እንጂ እንደ ከባድ ጥፋት ተቆጥሮ ሰዎች ሊገሠጹበትና ሊወቀሱበት አይገባም፤ ሕግም አይፈቅድም፡፡” ሲሉ ገልጸዋል - በደብዳቤያቸው፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ያላቸው አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ቀርበው ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹ሕግንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር›› ብቻ ሳይኾን ‹‹ትልቁን ጉባኤ በታሪክና በሕግ ዐዋቂዎች ዘንድ ግምት ውስጥ የሚጥለው እንዳይኾን አቡነ ማትያስ አስጠንቅቀው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ጉዳዩን እንደገና በጥልቀትና ከሕግ አንጻር ፈትሾ እንዲያጤነው በማለት አፈጻጸሙ እንዲቆይ አስታውቀዋል፡፡
በሕገ ቤተክርስትያን ት/ሲኖዶሱ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈውን ውሳኔ ፓትርያርኩ የማገድ ሥልጣን እንደሌላቸው ያመለክታል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ከተጠቀሰበት አግባብ አኳያም፣ “ቤተ ክርስቲያናችን በቂ ሕግጋት አሏት፤ እነዚህ ሕግጋት ማዕከሉ ተጠብቆ ሊሠራባቸው ይገባል፤” ሲልም ቅ/ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡
ባለፈው መስከረም መጨረሻ “የቤተ ክርስቲንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ” በሚል መርሕ በተካሔደው ስብሰባ አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ ‹‹ፈጣሪ የለም ይላል፤ አሸባሪና አክራሪ ነው፤›› በማለት ቤተ ክርስቲያኗ ዕውቅና የሰጠችውን ማኅበረ ቅዱሳንን ከዓለም አቀፍ ጽንፈኞች ጋራ እያመሳሰሉ መወንጀላቸው ተገቢ እንዳልኾነና የማኅበሩ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን አስፈላጊ እንደኾነ ቅዱስ ሲኖዶሱ አረጋግጧል፡፡
‹‹ቆራጣ ደብዳቤ ይበቃዋል፤ ከመንግሥት ጋራ በመተባበር እስከ ጫፍ አድርሱልን፤ በቶሎ ቁረጡት›› እያሉ መጠየቅ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱንም “ከፈለጉ ቆባቸውን አስቀምጠው ወደዚያው ይግቡ” እያሉ መዝለፋቸውስ በምን መመዘኛ ነው ዴሞክራሲያዊና ሕገ መንግሥታዊ የሚኾነው በማለት የሚገልጹ የስብሰባው ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ ፓትርያርኩ የውሳኔውን አፈጻጸም ማገዳቸው፣ አድሏዊ እንደሚያደርጋቸውና በካህናቱና በምእመናኑ ዘንድ መንፈሳዊ አባትነታቸውንና ታማኝነታቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባው እንደሚኾን ጠቁመዋል፡፡

Saturday, December 13, 2014

በማኅበረ ቅዱሳን ተቃውሞ ባቀረቡ ካህናት ላይ እርምጃ እንዲወሰድ የተደረገው ተጋድሎ ከሸፈ!

   ( 4/4/ 2007 )
 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የጥምቅት ወርን መባቻ ተከትሎ የአጠቃላይ ሰበካ ጉባዔ ዓመታዊ ስብሰባና የሲኖዶስ ጠቅላላ ጉባዔ እንደሚደረግ ይታወቃል። በዚህ ዓመት የተለየ የሚያደርገው ከሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ ቀደም ብሎ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የስብሰባ አዳራሽ በቅዱስ ፓትርያርኩ የተደረገ የሀ/ስብከቱ አድባራትና ገዳማት ልዩ ልዩ ኃላፊዎች በተጠራ ጉባዔ ላይ የተካሄደው ውይይት ዋነኛው ጉዳይ ሆኖ አልፏል። በወቅቱ ከተደረገው ውይይትና ከተሰብሳቢዎቹ ድምጽ ለማወቅ እንደተቻለው በአጭር ቃል «ማኅበረ ቅዱሳን» ስለተባለው ማኅበር እንቅስቃሴ ላይ ያጠነጠነ ውይይት መሆኑ የተለየ አድርጎታል።

  ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ድርጅት እንቅስቃሴ፤ በቤተ ክህነቱ ዙሪያ ያለው የሥራ ድርሻ፤ የአባላት ምልመላ፤ የገንዘብ አሰባሰብና ውጪን ስለማሳወቅ፤ ሊኖረው ሲለሚገባው ገደብና ሌሎች  አሳቦች ተነስተው ሰፊ ውይይት የተደረገባቸው እንደነበር ይታወሳል። በማኅበሩ ዙሪያ በተነሱት የማኅበረ ካህናቱና የፓትርያርኩ ውይይት ደስተኛ አለመሆን ከማኅበሩ ዘንድ የሚጠበቅ ቢሆንም በአስገራሚነቱ የተመዘገበው ተቃውሞ የተነሳው ቤተ ክርስቲያኒቱን ይመራሉ ተብለው በከፍተኛ ስልጣን ላይ በተቀመጡት በዋና ሥራ አስኪያጁና ከዋና ፀሐፊው በኩል መሆኑ ነው። የማኅበሩ አባል የመሆን መብታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ማኅበሩን በተመለከተ ፓትርያርኩ ማኅበረ ካህናቱን የማወያየት አቅምና ሥልጣን የሌላቸው በማስመሰል መቃወም ግን በምንም መመዘኛ ተቀባይነት ያለው አይደለም። ማኅበሩ ምን እየሰራ ነው? እንቅስቃሴው ምን ይመስላል? ቤተ ክርስቲያን የምትቆጣጠረው እንዴት ነው? ለሚሉ ጥያቄዎች የማኅበረ ካህናቱን ድምጽ የመስማትና የማወያየት አቅም ፓትርያርኩ የላቸውም ከተባለ ዋና ሥራ አስኪያጁ ስለማኅበሩ የመጮህ ሥልጣንን ከየት አገኙ? የሚል አንጻራዊ ጥያቄን ማስነሳቱ የግድ ነው ።

  ሌላው ስለማኅበሩ የጦፈ ክርክር ተደርጎ የነበረው ከአዲስ አበባው ሀ/ስብከት ጉባዔ በኋላ በተፈጸመው የሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ ላይ በድጋሜ መነሳቱ ነበር። በዚህ ጉባዔ ላይ ስለማኅበረ ቅዱሳን ያልተነገረና የቀረ አንዳች ነገር አልነበረም። የተናገሩትን ሰዎች ማንነት ለጊዜው ወደጎን ትተን በተነገረው ጉዳይ ላይ ስናተኩር ከተነገረው እውነት የቀረ ነገር ካልሆነ በስተቀር የተጨመረ አዲስ ነገር ምንም አልነበረም ማለት ይቻላል። ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ጣልቃ ይገባል? ያልተፈቀደ ጉባዔ ይጠራል? የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት ለራሱ አባልነት ይመለምላል? ቤተ ክርስቲያኒቱ የማታውቀውን ገቢ ይሰበስባል?  የቤተ ክርስቲያኒቱን የኦዲት ምርመራ አልቀበልም ይላል?  ለሁሉም አንድ መልስ «አዎን» ነው። በነዚህ አንኳር ነጥቦች ላይ የካህናቱና የፓትርያርኩ መነጋገር የሚያንገበግበው ቢኖር ማኅበሩና ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ ለማኅበሩ ጥብቅና የሚቆሙ ወገኖች ብቻ ናቸው። ካልሆነ ስለማኅበረ ቅዱሳን ተግባር መነጋገር ለምን ያናድዳቸዋል?

   ማኅበሩ የተሳሳተውን መንገድ አውቆ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ ማሳሰብና የማኅበሩ ቅን አባላት ለተሻለ መንፈሳዊ ተግባር ትኩረት እንዲሰጡ የሚያስችል ውይይት ማድረግ ተገቢና ተቀባይነት ያለው መሆኑን የሚክድ ያለ አይመስለንም። ቅዱስ ፓትርያርኩ ያደረጉትም ይህንኑ ነው። በጠራ ቃል «ማኅበሩን ይፈረስ ያለ ማንም የለም» ብለዋል። ከዚህ ውጪ እነዚህ ቡድኖች ምን እንዲሆን  ይፈልጋሉ? በዚህ ዙሪያ የሚታመም ሊቀ ጳጳስ ወይም ተመሳሳይ ሰው ቢኖር ራሱን መመርመር ያለበት ራሱን ነው። ህመሙ የጤንነት ምልክት አይደለም። ዘረኝነት፤ ጥቅምና ጭፍን ደጋፊነት ብቻውን ማንነትን ከሚያጋልጥ በስተቀር የትም አያደርስም። ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አባ ማቴዎስ ለቅዱስ ፓትርያርኩ የተናገሩት « ማኅበረ ቅዱሳንን ከነኩ እርስዎም እንደአባ ጳውሎስ ይሞታሉ» ማለታቸውን ሰምተን ጤንነታቸውን ተጠራጥረን ነበር። ቅዱስ ፓትርያርኩ ከእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ጋር እንዴት አብረው ሊሰሩ እንደሚችሉ ስናስብ እጅግ ያስገርመናል። ዓይን ያወጣ ጥላቻና አንድን ቡድን መደገፍ አሳዛኝም አስገራሚም ነው። በዚህ ዓይነት ጉዞ ቤተ ክርስቲያን ወዴት እየሄደች እንዳለ ለማወቅ አስቸጋሪ አይደለም። ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ ለራስ ክብርና ለማኅበር መቆም ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ውድቀት እየገፏት መሆኑን ለማወቅ ምርምር አይጠይቅም። ባለፉት 23 ዓመታትም ከቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት መካከል ከ16 ሚሊየን በላይ ልጆቿ ወጥተው የቀሩትም በዚህ ዓይነት ቡድናዊ አስተዳደርና ደካማ አስተምህሮ የተነሳ ነው።

 የሰበካ አጠቃላይ ጉባዔ እንደተፈጸመ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ቀጥሎ ነበር። በዚህ የሲኖዶስ ጉባዔ ላይም በግንባር ቀደምትነት የተነሳው ጉዳይ ቢኖር ማኅበሩ ለምን ተነክቶ? የሚሉ የጳጳሳት ቡድን በአንድ በኩል፤ ቅዱስ ፓትርያርኩ ብቻቸውን በሌላ በኩል ሆነው የጦፈና የከረረ ውይይት ማድረጋቸውን ከውስጥ አዋቂ ምንጮች ሰምተን ነበር።  ማኅበሩን የሚያወግዙና የሚወቅሱ የማኅበረ ካህናት አባላት እኛንም ከማኅበሩ ጋር ቀላቅለው ስለዘለፉን ቀኖና እንዲሰጣቸውና እንዲቀጡ ይደረግ የሚሉ አፍቃሬ ማኅበረ ቅዱሳን ጳጳሳት የጉባዔውን አቅጣጫ ለማሳት ሙከራ አድርገው ነበር። ፓትርያርኩ ምንም እንኳን ለጉዳዩ መልስ በመስጠት ዝም ለማሰኘት ሞክረው የነበረ ቢሆንም «ወደ ገዳማችን እንሄድልዎታለን፤ ሲኖዶሱን ሊያከብሩ ይገባል፣ እርስዎ በአቡነ ጳውሎስ ዘመን ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን አለው፤ ሲሉ የነበር  ዛሬ እርስዎ ለምን ይሽሩታል?» ወዘተ መከራከሪያ ነጥብ ለማንሳት ተሞክሮም ነበር። ይህ ሁሉ የሆነው የሲኖዶስ ውሳኔ ስለተሻረ ሳይሆን በሲኖዶሱ ሉዓላዊ ስልጣን ከለላ በማኅበረ ካህናቱ ዘለፋና ውግዘት የደረሰበትን ማኅበር ለመካስ ሲባል በማኅበሩ ላይ የተናገሩት ካህናት ሁሉ እንዲቀጡና ቀኖና እንዲሰጣቸው ለማስቻል ነበር።

  ማኅበሩን አጋልጠው ለአጋላጭ ሰጥተዋል የተባሉት በዋናነት አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል፤ ሊቀትጉኃን ዘካርያስ ሐዲስ፤ መልዓከ መንክራት ኃይሌ አብርሃ፤ ዲያቆን አበበ፤ ዲያቆን ዘመንፈስ አብርሃ፤ አባ ነዓኩቶ ለአብ የመሳሰሉት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያና ቀኖና እንዲሰጣቸው እንዲሁም ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ በተለይ ከፓትርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት እንዲባረሩ ይደረግ የሚል ውሳኔ ለማሳለፍ ተሞክሮ ነበር። በተካፈሉበት ጉባዔ ላይ ሁሉም አሳብ ሰጪዎች የተናገሩት በማኅበሩ ዙሪያ ብቻ ሆኖ ሳለ ከእስከዛሬው በተለየ ሁኔታ በእነዚህ ካህናት ላይ የበቀል እርምጃ እንዲተላለፍ የተፈለገው ለምንድነው? ዋና የስም ማጥፊያ ማጠንጠንጠኛው ሙሰኞችና አማሳኞች ናቸው የሚል ቢሆንም ማን ምን ሰረቀ? ስንት ሰረቀ? መቼ ሰረቀ? የት ሰረቀ? ለሚለው የጥያቄ ጭብጥ መልስ የሚሰጥ አካል የለም። በወሬ ደረጃ የምናየውንና የምንሰማውን ይዞ ካልሆነ በስተቀር ማስረጃውን በነጥብ የሚያስረዳ አካል የለም። የተጠቀሱት ግለሰቦች በሥራቸው ያልተመሰረከላቸው መሆኑ ወይም የሙስና ተሳታፊ ስለመሆናቸው መጠርጠራቸው ብቻውን ስለማኅበረ ቅዱሳን መናገራቸውን ስህተት ሊያደርገው አይችልም። ታዲያ ቅዱስ ሲኖዶስ በነዚህ ሰዎች ላይ እርምጃ ይወሰድ! የሚለው በምን መነሻ ነው? ሲኖዶስ ሊያደርግ የተገባው ሀቅ ቢኖር ማኅበሩንም ይሁን በማኅበሩ ዙሪያ ተቃውሞ ያነሱ ሰዎች ያጠፉት ነገር ካለ መርምሮ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም የእርምት እርምጃ መውሰድ ነበር። ነገር ግን አንዱን አጥፊ ደግፎ ሌላው አጥፊ ላይ ጣትን መቀሰር ቅንም፤ መንፈሳዊም አካሄድ አይደለም።

 ይህንን ዘገባ እስካወጣንበት ጊዜ ድረስ ከላይ በጠቅስናቸውና በሌሎች ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ማኅበሩ ከኋላ እየገፋ ብዙ ተጽዕኖ ሲያደርግ ቆይቷል። በአባ ማቴዎስና በአባ ሉቃስ አሳሳቢነት ቋሚ ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ ጉዳዩን እያነሱ የሲኖዶስ ጠቅላላ ጉባዔ ካሳለፋቸው ውሳኔዎች እንደአንዱ ተቆጥሮ በተጠቀሱት ሰዎች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ላለፈው አንድ ወር ሙሉ ጽኑ ክርክር ሲያደርጉ መቆየታቸው ተሰምቷል። ከተወሰኑ ጉባዔዎች በስተቀር ያልተነሳበት ስብሰባ አልነበረም። በተለይም አባ ሉቃስ «ሊቃነ ጳጳሳት ተዘልፈዋል፤ የቤተ ክርስቲያን ክብር ሲነካ ዝም ማለት አይቻልም፤ ማኅበሩም ቢሆን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ እየሰራ ነው» በሚል መከራከሪያ በተቃዋሚ ካህናት ላይ እርምጃ ለማስወሰድ ብዙ ተጉዘው ነበር። ነገር ግን በፓትርያርኩ በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ውድቅ ተደርጓል።
    የፓትርያርኩ አቋም ማኅበረ ካህናቱን ሰብስቦ ለማናገር የማንንም ፈቃድ አልጠይቅም። ቅዱስ ፓትርያርክ የሚመራቸውን ካህናት የማናገር መብቱን የሚያገኘው ሥልጣኑን  ከተቀበለት ሰዓት ጀምሮ ነው። ካህናቱንም የተሰማቸውንና የታያቸውን ጉዳይ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ ማቅረባቸው ትክክልና ተገቢ ነው። አያስወቅሳቸውም። ከዚያ በተረፈ የሊቃነ ጳጳሳቱን ስም አንስቶ ጸያፍ ቃል የተናገረ ካለ በቦታና በስም ተለይቶ ይነገረንና ምክርና ተግሳጽ እንሰጠዋለን እንጂ የመናገር መብቱን ተጠቅሞ የመሰለውን ሃሳብ ያንጸባረቀ ሁሉ ጥፋተኛ አይባልም» በማለት የማኅበሩን ደጋፊ ጳጳሳት ኩም አድርገዋቸዋል። በተለይም ባለፈው አንድ ሳምንት በማኅበሩ በኩል ከኋላ ይገፉ የነበሩትና አሳባቸው ውድቅ የሆነባቸው አባ ማቴዎስንና አባ ሉቃስን ያየ መጨረሻቸውን ለማየት ናፍቆ ነበር።
ሁልጊዜም የሚሸሸጉበት ስነ ሞገት «የሲኖዶሱ ውሳኔ ይከበር» የሚል ሲሆን ሲኖዶስ የማንን የመናገር መብት እንደከለከለ የሚገልጽ ማስረጃ ግን ማቅረብ አልቻሉም። ወደፊትም አይችሉም።

 ከዚሁ ጋር ተያይዞ የደረሰን መረጃ እንደሚያስረዳው ማኅበሩን በመቃወም ድምጻቸውን ያሰሙ ካህናት መብታቸው በመሆኑ የትኛውም አካል ይህንን መብታችሁን ለምን ገለጻችሁ?ብሎ እርምጃ የሚወስድ አካል ቢኖር የሕግ ጥበቃ እንዲደደረግላቸው ለመንግሥት አካላት ባቀረቡት አቤቱታ መሠረት ቃል የተገባላቸው መሆኑ ታውቋል።

Wednesday, December 3, 2014

ሰበር ዜና፤ አባ እንባቆም ኢየሩሳሌም ገቡ፤ አባ ዳንኤል ደግሞ ሚኒያፖሊስ ከተሙ!

(ደጀ ብርሃን፤ሕዳር 24/2007 )

 አባ እንባቆም እስራኤል በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀጳጳስ ሆነው በጥቅምቱ የሲኖዶስ ጉባዔ መመደባቸው ይታወሳል። በዚሁ መሠረት ቀደም ሲል የገዳማቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩትና ባለመግባባት ከቦታው እንዲነሱ በተደረጉት በአባ ዳንኤል ምትክ የተመደቡት አዲሱ ሊቀ ጳጳስ አባ እንባቆም ትናንት በ23/3/ 2007 ዓ/ም ኢየሩሳሌም መግባታቸውና ደማቅ አቀባበል እንደተደረገላቸው ተያይዞ የደረሰን ዜና ያስረዳል።

    አባ እንባቆም ቀደም ሲል በድሬዳዋ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ይሰሩ እንደነበር ሲታወቅ በቆይታቸውም ከሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች ጋር ከፍተኛ አለመግባባት ላይ ደርሰውና ከቦታው እንዲነሱ የሕዝብ ግፊት አይሎ በነበረበት አጋጣሚ ወደኢየሩሳሌም መመደባቸው ለጊዜውም ቢሆን ትንፋሽ የመግዢያ ጊዜ ሊሆናቸው እንደሚችል ተገምቷል።

 በተመሳሳይ መልኩ ሊቀጳጳሱ በደብረ ሊባኖስ ገዳም ከፍተኛ ጥላቻና ተቃውሞ ሲደርስባቸው የቆየ ሲሆን የጉዳዩን ዝርዝር ምክንያት ለመግለጽ የተቆጠቡት ምንጮቻችን ሊቀጳጳሱ ከኢየሩሳሌም መነኮሳት ጋር ተግባብተው መስራት ይችላሉ ወይ? የሚለው ጉዳይ እንደሚያሳስባቸውና በሂደት ምን ሊፈጠር እንደሚችል ወደፊት የሚታይ ይሆናል ሲሉ አክለው ገለጸውልናል።
በሌላ በኩል ከገዳሙ አባቶች ጋር ባለመግባባት የተነሱት አባ ዳንኤል የተመደቡበትን ሀገረ ስብከት ሳይረከቡ እስካሁን አሜሪካ በሚኒሶታ ስቴት ሚኒያፖሊስ ውስጥ በምትገኘው የግላቸው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከትመው የሚገኙ ሲሆን  ታቦተ ኪዳነ ምህረትን ከአዲስ አበባ ተሸክመው እንዲሄዱና ከመድኃኔዓለም ታቦት ጋር በደባልነት እንዳስገቡ ለመረዳት ችለናል። ሀገረ ስብከቱ በአቡነ ዘካርያስ የሚመራ ቢሆንም የሲኖዶሱን ህግ በመጻረር አንዱ በሌላው ሊቀ ጳጳስ ሀ/ስብከት ውስጥ ጣልቃ ገብቶ የፈለገውን መሥራት የለመደ አሰራር ሆኗል። በተለይም በአሜሪካ የመኖሪያ ፈቃድ ያለው ሊቀ ጳጳስ ጡረታውንና ድጎማውን እየተቀበለ በስሙ ያቋቋማትን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በግሉ ያለከልካይ ያስተዳድራል።



Sunday, November 30, 2014

በምድር ላይ በክፉው መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ አሰተኛ ክርስቶሶች (ክፍል 4 )

ላዝሎ ቶት(1938-2012) 

በትውልዱ ሀንጋሪ፤ በዜግነት አውስትራሊያዊ የሆነ ሰው ነው። በትውልድ ሀገሩ በጂኦሎጂ ትምህርት ዲፕሎማ የነበረው ቢሆንም የእንግሊዝኛ ቋንቋው ደካማ ስለነበርና የሙያ ክህሎቱም ተቀባይነት ባለማግኘቱ አውስትራሊያ እንደገባ ሀንጋሪ በተማረው ሙያ መስራት አልቻለም። በኋላም በአንድ ሳሙና ፋብሪካ በቀን ሰራተኝነት ተቀጥሮ ጥቂት ከቆየ በኋላ በ1971 ዓ/ም ወደኢጣሊያ አቅንቷል።  ጣልያን እንደደረሰም እኔ «ኢየሱስ» ነኝ እያለ ለመስበክ ቢሞክርም ጣሊያንኛ ባለመቻሉ ስብከቱን ያዳመጠው አልነበረም። ከሮማው ካቶሊክ ፖፕ ጳውሎስ 6ኛ ለመገናኘትና የራሱን ማንነት ሊገልጽላቸው እንደሚፈልግ ደብዳቤ ጽፎላቸው ደብዳቤው ከፖፑ ሳይደርስ መንገድ ላይ ቢቀርበትም በሌላ መንገድ ለመገናኘት ያልተሳካ ሙከራም አድርጓል። ይሁን እንጂ በዚህ ሁሉ ተስፋ ያልቆረጠው «ቶት» የመጨረሻ ሙከራውን ለማድረግ በ33ኛው ዓመት ዕድሜው ግንቦት 21 ቀን 1972 ዓ/ም ጂኦሎጂስቶች በተለይ የሚጠቀሙበትን ትንሽ መዶሻ ከፍ አድርጎ በመያዝና በአደባባይ እየጮኸ «እኔ ኢየሱስ ነኝ፤ ሞቼም ነበር፤ ሕያው ነኝ» እያለ ይረብሽ ጀመር። ከዚያም ወደ ቫቲካን ሲቲ በመግባት በሚካኤል አንጄሎ የተሰራውን ቅርጽ ማለትም ኢየሱስ ከመስቀል ላይ ወርዶ በእናቱ በማርያም እቅፍ ላይ ሆኖ ከአንገቱ ዘንበል ብሎ የሚታየውን ምስል በያዘው መዶሻ መደብደብ ጀመረ። በድብደባውም የማርያምን ምስል ቀኝ ክንድ፤ የአንድ ዓይን ክፍሏንና አፍንጫዋን ሰብሮ ጥሏል።


 በቦታው ከነበሩ ጎብኚዎች አንዱ የሆነው ቦብ ካሲሊ የተባለ ሰው ቶት ላይ ተጠምጥሞ በመያዝ ሊያስጥለው ችሏል። ቶት በቁጥጥር ስር ውሎ ህክምና ሲደረግለት የአእምሮ በሽተኛ መሆኑ በመረጋገጡ ከጣሊያን ወደአውስትራሊያ በአስቸኳይ እንዲባረር ተደርጓል። አውስትራሊያም እንደደረሰ በተመሳሳይ ድርጊት ላይ በመገኘቱ ከህሙማን ክብካቤ ማዕከል እንዲገባ ተደርጎ ህይወቱ እስካለፈችበት 2012 ዓ/ም ድረስ በዚያው ሲረዳ ቆይቷል።

===============================================================================

ዌይን ቤንት ወይም ማይክል ትራቬሰር (ከ1941- እስካሁን በሕይወት ያለ)

 በ1941 ዓ/ም የተወለደ ሲሆን  በአይዳሆ ሴንትፖይንት ከተማ በምትገኝ «ጌታ የኛ ቅድስና ቤተ ክርስቲያን» መሪ የነበረ ሰው ነው። ቤንት የዚህች ቤተክርስቲያን መሪ ከመሆኑ በፊት «በሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን» ፓስተር ሆኖ ያገለግል ነበር። በ1987 ዓ/ም ቤተ ክርስቲያኒቱን በይፋ ለቆ ሲወጣ «ሰባተኛ ቀን ቤተ ክርስቲያን የታላቂቱ ጋለሞታ ሴት ልጅ ናት» ብሎ በአደባባይ ተናግሮ ነበር። ይህንን ለማለት ያበቃውን ምክንያት ግን በወቅቱ አልተናገረም።  ከዚያም ወደ አይዳሆ በማምራት ጥቂት ጊዜ በአባልነት ከቆየ በኋላ በ2000 ዓ/ም «ጌታ የኛ ቅድስና» በተባለችውና አነስተኛ ቁጥር በያዘችው ቤተ ክርስቲያን መሪ  ለመሆን ቻለ። በዚያው ዓመት «እግዚአብሔር፤ አንተ ኢየሱስ ነህ ብሎ ተገልጾ ነገረኝ» በማለት ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት አወጀ። ጥቂት ቆይቶም ከሰባት ደናግላን ጋራ ለወሲብ እንድትተኛ የሚል ትዕዛዝ ስለመጣልኝ ደናግል ልጆቻችሁን እንድትሰጡኝ በማለት ጥያቄውን አቀረበ። ገሚሶቹ የቡድኑ አባላት ሃሳቡን ውድቅ ያደረጉበት ቢሆንም በግላጭ ሴት ልጁን አሳልፎ የሰጠው ማን እንደሆነ ሳይታወቅ በምስጢር ከደናግላን ጋር ወሲብ መፈጸሙ በኋላ ላይ በፖሊስ በተደረገበት ምርመራ ሊረጋገጥ ችሏል። ቻናል 4 የተባለው የዩኬ ቴሌቪዥን ጣቢያ በ2007 ዓ/ም ከዌይን ቤንት ጋር ባደረገው ቃል ምልልስ ስለደናግላኑ ወሲብና ከእግዚአብሔር ስለሚመጣለት ትዕዛዛት ተከታታይ ፕሮግራም አስተላልፎ ነበር።(ከቪዲዮዎቹ አንዱን ለማየት እዚህ ይጫኑ)
  የዓለምም መጨረሻ ጥቅምት 31/2007 ዓ/ም እንደሚሆንና ተከታዮቹም ለመነጠቅ እንዲዘጋጁ የተናገረ ቢሆንም ቀኑ ሲደርስ እንዳለው የሆነ ነገር ምንም አልነበረም።  ይልቁንም ቤንት ከልጁ ሚስት፤ ከደናግላን ጋር እንዲሁም ለአቅመ ሄዋን ካልደረሱ ታዳጊዎች ጋር ወሲብ በመፈጸም ወንጀል ተከሶ በ2008 ዓ/ም የ18 ዓመታትን እስራት ተከናንቦ ከርቸሌ ወርዷል። ዌይን ቤንት ከርቸሌ ከወረደ በ2014 ዓ/ም ገና 6ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን ቢያንስ በአመክሮ ለመፈታት ከእንግዲህ 3 ዓመት ገደማ በዚያው መቆየት ይጠበቅበታል። 

==============================================================================

አሪፊን ሙሐመድ ( 1943- እስካሁን ያለ)

 አሪፊን ሙሐመድ በ1943 ዓ/ም ከሙስሊም ቤተሰብ በማሌዢያ ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ህውከት እንደደረሰ በ1980ቹ አጋማሽ  በማላያን ቋንቋ «ካራጃአን ላንጊት» ወይም በእንግሊዝኛው «የሰማይ መንግሥት» የተሰኘ ድርጅት አቋቋመ። በአክራሪ ሙስሊሞች በምትታወቀው ማሌዢያ ውስጥ አሪፊን ሙሐመድ «እኔ አልመሲህ ዒሳ፤ ቡድሃ፤ ሙሐመድ ሺቫ ነኝ» እያለ በመስበክ ተከታዮችን ለማፍራት ጊዜ አልፈጀበትም። በዚህ አድራጎቱ ብርቱ ተቃውሞ ገጠመው። በተደጋጋሚ ሲታሰር፤ ሲፈታ ቆይቶ መንግሥታዊ ስርዓቱን በዓመጽ ለመገልበጥ በመሞከርና ሃይማኖታዊ ብጥብጥን በመፍጠር ወንጀል ተከሶ ድርጅቱ እንዲዘጋ፤ በአባልነት የተሳተፉትም እንዲታሰሩ ሲወሰን አሪፊን ሙሐመድ ሾልኮ አመለጠ። ከአራቱ ሚስቶቹ ሦስቱና ከተከታዮቹም 58 ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ።

 እያንዳንዳቸውም 3000 የማሌዢያን ገንዘብ እንዲከፍሉና ሁለት ዓመት እንዲታሰሩ ፍርድ ቤት ወሰነባቸው።  የድርጅታቸውም ህንጻና ማንኛውም ንብረት እንዲፈርስ ተደረገ። አሪፊን ሙሐመድ አንዴ ኢየሱስ ነኝ፤ አንዴ ማህዲ ነኝ እያለ ተከታዮቹን ቢያጭበረብርም በማሌዢያ መንግሥት በወንጀል ከሚፈለጉ ሰዎች ቀንደኛው ሲሆን ማሌዢያን ለቆ ከጠፋ በኋላ በታይላንድ ውስጥ ተሸሽጎ እንደሚገኝ ይገመታል።
==================================================================================

ማታዮሺ ሚትሱኣ (1944- እስካሁን በሕይወት ያለ) 

በጃፓን፤ ኦኪናዋ ከተማ በጥር 5/ 1944 ዓ/ም ተወለደ። ከዚያም ለአቅመ ትምህርት እንደደረሰ በመጀመሪያ በተወለደት ቦታ በኋላም በቶኪዮ ቹዋ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ድግሪውን አግኝቷል። በ1997 ዓ/ም «ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚያዊ ኅብረት ፓርቲ» የተባለውን ሃይማኖትንና ፖለቲካን በጥምር የሚያንቀሳቅስ ፓርቲ መሰረተ። እንደሃይማኖት ሥርዓት ዓለም በኔ እንዲገዛ «እኔ ኢየሱስ ነኝ» አለ። እንደፖለቲካ አስተዳደር ደግሞ ዓለም በኔ እንዲመራ «የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ መሆን ያለብኝ እኔ ነኝ አለ»። የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ለመሆን ባለው ከፍተኛ ጉጉት የርሱ ፓርቲ በተደጋጋሚ በምርጫ ቢወዳደርም  እንኳን ከትልቅ ስልጣን ሊደርስ ቀርቶ የመንደር ምርጫም ማሸነፍ ሳይችል ቀርቷል። በምርጫ የተፎካከሩትን ሰዎች ለዚህ ድርጊታችሁ የምሰጣችሁ ምክር «ራሳችሁን አጥፉ»  ያላቸው ሲሆን ስልጣን ብይዝ ደግሞ ሁሉንም ሰብስቤ እሳት ውስጥ እጨምራቸው ነበር እያለ ሲለፍፍ ተሰምቷል።

== ==============================================================



ጆሴ ሉዊስ ደ ጂሰስ ሚራንዳ ( 1946- 2013) 

 ፖርቶሪኮ ውስጥ ፖንሴ በተባለች ከተማ በ1946 ዓ/ም ተወለደ። ወላጆቹ በጣም ድሃ ስለነበሩ የሴቶችን ቦርሳ መመንተፍ የተለማመደው በልጅነት ዕድሜው ነበር። ገና የ14 ዓመት ዕድሜ ሳለም የሔሮይን አደገኛ ተጠቃሚ እስከመሆን ደርሷል።  ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ በፖንሴ ከተማ በነበረችው መጥምቃውያን ቤተ ክርስቲያን ተቀላቀለ። እግዚአብሔር ባደረገልኝ ጥሪና እገዛ ከነበረብኝ ደባል ሱስ ሁሉ ተላቅቄአለሁ አለ።  ጆሴ ሚራንዳ በ1973 ዓ/ም  ሁለት መላዕክት መጥተው በነገሩኝ መሠረት «እኔ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ሆኜ በምድር ላይ መገለጤን ነግረውኛል» ብሎ መለፈፉን «ሀ»ብሎ ጀመረ። በማያሚ፤ ፍሎሪዳ የስደት ኑሮውን የቀጠለው ሚራንዳ የ15 ደቂቃ የሬዲዮ ፕሮግራም በማሰራጨት የሱን ኢየሱስነት ይሰብክ ገባ። በስብከት መርሐ ግብሩ «ሚኒስትሮ ግሬሴንዴ  ኤን ግራሲያ» ወይም « በጸጋው የማደግ አገልግሎት» የተሰኘ ድርጅት ከመሰረተ በኋላ በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች ማስፋፋቱን ቀጠለ። በ35 ስቴቶች በከፈተው ተቋም 287 የሬዲዮ ጣቢያዎችና በእንግሊዝኛና ስፓኒሽ ቋንቋ የሚተላለፍ የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን ስርጭትም እስከማስተላለፍም ደርሷል።
ጆሴ ሚራንዳ አንድ ጊዜ ሐዋርያው ጳውሎስ ነኝ፤ አንድ ጊዜ ደግሞ ኢየሱስ ነኝ እያለ ከቆየ በኋላ በ2006 ዓ/ም ክህደቱን በማጠናከር ከዛሬ ጀምሮ «እኔ የኢየሱስ ተቃዋሚ ነኝ» ሲል አወጀ።  «Anti Christ» ወይም ተቃዋሚው ስለሆንኩኝ መለያ ምልክቴ በራእይ 13 ላይ የተጠቀሰው«666» ቁጥር ነው በማለቱ  ተከታዮቹ ሁሉ በሰውነታቸው ላይ እንዲነቀሱ ትዕዛዝ አስተላለፈ። ተከታዮቹም «666» ቁጥርን በሰውነታቸው ላይ በሰልፍ ተነቀሱት።
የሚራንዳ ወርሃዊ ደመወዝም ልዩ ልዩ ክፍያና አበልን ሳይጨምር 228,000 ዶላር ገደማ ነበር። ሚራንዳ ባደረበት የጉበት ህመም በተወለደ በ67 ዓመቱ በ2013 ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል። ከ2 ሚሊዮን በላይ በሚገመቱ ተከታዮቹም ዘንድ «እንደመልከ ጼዴቅ ለዘለዓለም የሚኖር» ተብሎለታል።
በአንድ ወቅት CNN ካቀረበው የጆሴ 666 ታሪክ የተወሰደ ቪዲዮ ይመልከቱ።





Monday, November 24, 2014

ኡጋንዳዊቷ የቤት ሠራተኛ ሕይወት ለማጥፋት በመሞከር ወንጀል ተከሠሠች!

( ዕድሜአቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ እንዲመለከቱ አይመከርም ) The film is not suitable for viewing by anyone under 18 years of age

ባለፉት ቅርብ ቀናት በኢትዮጵያ ውስጥ ሐና በተባለች ታዳጊ ወጣት ላይ አስነዋሪና እጅግ አሳሳቢ ድርጊት ተፈጽሞ የብዙዎችን ልብ እንደሰበረ ይታወቃል። ማኅበራዊ አኗኗራችን ከመተሳሰብ እያፈነገጠ፤ ሥነ ምግባራዊ አስተሳሰባችን እያደፈ የመሄዱ ምልክት ነው። ዓለም አንድ መንደር እየሆነች ነው ሲባል በመሰልጠኑ ብቻ ሳይሆን በመሰይጠኑም ጭምር በመሆኑ ስግብግብነት፤ ራስ ወዳድነት፤ ብልግናና ዐመፃንም ዓለማዊ መንደርተኝነት እያካፈለው ይገኛል። ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጸመው አስነዋሪ ድርጊት ትኩሳቱ ሳይበርድ አንድ መንደር የሆነችው ዓለም ከወደዑጋንዳ ሌላ ዜና ብቅ አለች። በአንዱ ጫፍ የተፈጸመው ወሬ ወደሌላ ጫፍ ለመድረስ ደቂቃ የማይፈጅባት ዓለማችን ካስተናገደቻቸው ብዙ ዜናዎች መካከል አንዱን አሳዛኝ ድርጊት አሰማችን። ጉዳዩ እንዲህ ነው።

  ድርጊቱ የተፈጸመው በዑጋንዳ፤ ኪዋቱሌ በተሰኘች አነሰተኛ ከተማ ነው። ድርጊቱን የፈጸመችው የ22 ዓመቷ ጆሊ ቱሙሂርዌ የተባለች የቤት ሠራተኛ ስትሆን በተቀጠረችበት ቤት ውስጥ እንድትንከባከብ ከአሰሪዎቿ አደራ የተሰጣትን ሕጻን በዘግናኝ ሁኔታ ስትደበድብ በቤት ውስጥ ስውር ካሜራ የተቀረጸ ቪዲዮ ያሳያል። በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተሠራጨው ይህ ቪዲዮ ብዙዎቹን አሳዝኗል። በጣም የሚረብሸው ይህ ምስል ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ እንደዋለ ዓለም ዐቀፍ ትኩረት ስቧል።  የሕጻኗ ወላጅ አባት የሆነው ኤሪክ ካማንዚ ቪዲዮውን እንደተመለከተ ለኪዋቱሌ  ፖሊስ ጣቢያ በማመልከቱ ፖሊስ ደብዳቢዋን የቤት ሠራተኛ በቁጥጥር ስር አውሎ «በማሰቃየትና ለመግደል ሙከራ በማድረግ» ወንጀል የክስ ፋይል ከፍቶ ለፍርድ ቤት እንዳቀረባት የተገኘው ዜና ያስረዳል።  የቤት ሰራተኛዋ ከተቀጠረች 26 ቀናት ብቻ ያስቆጠረች ቢሆንም የፈጸመችው ድርጊት በተመሳሳይ ሁኔታ የቆየች እንደሚመስል ፖሊስ ግምቱን የሰጠ ሲሆን  ስለሰራተኛዋ ማንነትና የቀደመ ተግባር ምርመራ ለማድረግ የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ለፍርድ ቤቱ በማመልከቱ ለታህሳስ 8/2014 እንዲያቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል። ሕጻኗ በደረሰባት ጭካኔ የተሞላበት ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባት ቢሆንም እስካሁን ህክምና እየተደረገላት በሕይወት እንደምትገኝ ታውቋል።
ሕጻናት የተለየ ክብካቤና ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው ቢሆንም ዓለም በምታስተናግደው የሥነ ልቡና ማኅበራዊ ቀውስ የተነሳ ለጥቃት እየተጋለጡ ይገኛሉ። ፍሪሃ እግዚአብሔር የሌለው ትውልድ ከሥነ ምግባር ውጪ በመሆን ለማኅበራዊ ኑሮ የአስተሳሰብ ቀውስ መጋለጡ አይቀሬ ነው። አሳዛኝና አስነዋሪ ድርጊት የመፈጸሙ ምክንያትም ይህ ነው።  በየቤታችን ለሕጻናት፤ በየአካባቢው ለሴቶችና ለታዳጊ ወጣቶች፤ ለአረጋውያንና ረዳት ለሌላቸው የምናደርገውን ክትትልና ቀና ድጋፍ በማጎልበት «የአባቴ ብሩካን» ተብሎ የተነገረውን የሕይወት ዋጋ ለማግኘት ዛሬውኑ እንነሳ!!

«ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደ ሆነ፥ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ» 1ኛ ጴጥ 2፤2



Friday, November 21, 2014

ፍሪማሰንሪ /freemasonry/ ምንድነው?




ከዚህ በፊት በአንድ ጽሁፍ «ስለኤርያ 51» አጭር ምስጢራዊ ጽሁፍ ማስነበባችን ይታወሳል። አሜሪካና ዲሞክራሲ፤ ሥልጣኔና አሜሪካ መሳ ለመሳ ናቸው። እንደዚሁ ሁሉ ሌላው ዓለም ይቅርና የሀገሪቱ ዜጋ የማያውቃቸው ብዙ ምሥጢሮችም ያሉባት ሀገር ናት። ላይ ላዩን በዲሞክራሲው ዕድገት ጫፍ ረግጫለሁ በማለቷና በሥልጣኔውም መጥቄአለሁ እያለች ከመለፈፏ ጀርባ ብዙ ጉድ እንዳዘለች ብዙው ሰው አያውቅም፤ ቢያውቅም ትኩረት አይሰጠውም።  በነገረ መለኮት የበሰሉና የትንቢቱ ፍጻሜ ሰዓት መድረሱን በደንብ ያጠኑ ምሁራን ግን አሜሪካንን «ታላቂቱ ባቢሎን» ይሏታል። ምክንያቱም በአደባባይ ከሚታወቅላት የዲሞክራሲውና የሥልጣኔው እርከን ባሻገር የተሸከመችው ጉድ የት የለሌ ነውና። ሁሉም ነገር ከብረት በጠነከረ ምስጢርና ከምስጢሩ አጠባበቅ ጋር ሕይወት በሚያስከፍል ዋጋ፤ የረቀቀ መዋቅር በተዘረጋበት ሥርዓት የምትመራ ሀገር በመሆኗ እያወቁ ወይም ሳያውቁ ታደነዝዛለች።  በህጋዊ ደረጃ ከ«Church of Satan” አንስቶ እስከመጨረሻው ክሂዶተ እግዚአብሔር  «Atheism” ድረስ በነጻ የሚንቀሳቀሱባትና ለዓለሙ ሁሉ ማዕከል ሆና የምታገለግለዋ አሜሪካ ጾታን በመቀየር እንዲሁም የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻንም በመፍቀድ መሪ በመሆን ታገለግላለች።

      ሌላው ቀርቶ በየዓመቱ የሚከበረውን የሀለዊን /Halloween/ በዓል ጥቅምት/31 ቀን ከጫፍ ጫፍ በማክበር አሜሪካንን የሚቀድማት የለም። ለነገሩ «ሀለዊን» የሞቱ ቅዱሳንን ለማሰብ በሚል ይጀመር እንጂ ድርጊቱ የሙት መንፈስ የሆነውን ሰይጣንን ለማሰብ የተሰራ ለመሆኑ የድርጊቱ ክንዋኔ ያስረዳል። የሚያስፈራ ምስልና ቅርጽ፤ ጥርሱ ያገጠጠ፤ ዓይኑ ያፈጠጠ፤ አጽሙ  የተቆጠረ ማስጠሎ ነገር ለብሶ ወይም አጥልቆ  ሰውን በማስደንገጥና በማስፈራራት ቅዱሳንን ማክበር ነው ቢባል እንዴት ሊሆን ይችላል? ለነገሩ ቅዱሳንን ተጠግቶ ይህንን ማድረጉ ራሱን የቻለ ሌላ ምስጢር ስላለው እንጂ ቅዱሳንን ስለሚወክል አይደለም። (የዚህን ምስጢር ፍቺ በዚህ ጽሁፍ ቀጣይ ክፍሎች ለመዳሰስ ይሞከራል) አሜሪካ ለመጨረሻው ዘመን የተዘጋጀችና ለጥፋት ነጋሪት የምትጎስም ሀገር በመሆንዋ ነገሩ ሁሉ እየተበላሸ ሄዷል። ባለፈው ጥቅምት 31/ 2014 ዓ/ም በሚዙሪ፤ ሴንት ሉዊስ ከተማ ዓለም አቀፍ የ«ሀሎዊን» በዓል እንደሚደረግ የተላለፈው የጥሪ ምስል እንደሚያሳየን የጨለማውን ኃይል ካልሆነ በስተቀር ሌላ ማንን ሊሆን ይችላል? እስኪ ምስሉን አይተው ግምትዎን ይስጡ!!
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነን አሜሪካ ከምታስተናግዳቸው እንግዳ ነገሮች አንዱ ክፍል ስለሆነው ስለ«ፍሪማሰንሪ»/freemasonry/ ውቅያኖስ ታሪክ ጥቂቱን በጭልፋ ልናካችላችሁ ፈልገን ነው። ምክንያቱም የአንድ ዓለም አገዛዝ /One World Order/ እንዴት እየሰራ እንዳለ በማወቅ ከሚመጣው የስህተት መንፈስ እንድንጠበቅ አበክረን ለማስገንዘብ ነው። በዚህ ዙሪያ ምሁራኑ በሀገርኛ ቋንቋ ጽፈው በሰፊው እስኪያስነብቡን ድረስ ለጥንቃቄ እንዲበጅ በጥቂቱ እንዲህ አቅርበነዋል። መልካም ንባብ!

ፍሪማሰንሪ ምንድነው?

     «ማሰን» የሚለው ቃል ከላቲኑ / machio/ ከሚለው ቃል የተወረሰ ነው።  ትርጉሙም «ድንጋይ ጠራቢ ፈላጭ ወይም ግንበኛ  ማለት ነው።  ቃሉም ከ1155 እ,ኤ,አ ጀምሮ አገልግሎት ላይ ውሏል። freestone-mason ማለት «ነጻ ድንጋይ ጠራቢ፤ ግንበኛ ሰው ማለት ሲሆን ይህም ስያሜ በዚህ ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች «free mason» ፍሪማሰን በሚል አኅጽሮት አገልግሎት ላይ እንደዋለ በ1908 ዓ/ም የታተመው የፍሪማሰን ዜና መዋዕል መጽሐፍ ያስረዳል።  የላቲኑን ውርስ ቃል ተከትሎ “free” እና “mason” ከሚለው የእንግሊዝኛ ጥምር ቃላት የተገኘው ይህ ስያሜ ድንጋይ የመጥረብ፤ የመቁረጥና የመገንባትን ድርጊት ሲያመለክት «ፍሪማሰንሪ» /freemasonry/ ይባላል።  ይህም በነጻ ፈቃድ፤ በራስ ውሳኔ ዓለቱን ጠርቦ የማይነቃነቅና የማይናወጥ መሠረት ያለው ግንብ የመገንባት ዓላማ ነው ማለት ነው።  

«ፍሪማሰን» የተባለው ስያሜ በግንበኝነት ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሰዎች በተናጠል ሲጠሩበት የቆየ ቢሆንም ከ14ኛው ክ/ዘመን መጨረሻ ጀምሮ በአውሮፓ የህንጻ ምህንድስና ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች በጥቂት ሰዎች ተደራጅተው ራሳቸውን የመጥራት እንቅስቃሴ ጀምረው ነበር። ይሁን እንጂ የማሰን የተናጠል እንቅስቃሴ ቀደም ሲል እንደነበረ ቢሆንም ድርጅታዊ ሕግና ፒራሚዳዊ የብቃት የእርከን ደረጃ ወጥቶለት የተመሰረተው በ1717 ዓ/ም በለንደን ከተማ ነው።። በ1731 በአሜሪካ ፤ በ1736 በስኮትላንድ መሰረቱን አስፋፋ። ከዚያም በ1725 በአየር ላንድ እንደተጀመረ ይነገራል።  አሜሪካ ውስጥ የተቋቋመው በጣም ደርጅቶና ጎልብቶ ዓለም ዐቀፍ ቅርጽ ለመያዝ በቅቷል። 

      ይህ የፍሪማሰን ማኅበር የአውሮፓን የኢንዱስትሪ አብዮት ተጠግቶ የተመሰረተው የህንጻና የምህንድስና ባለሙያዎችን የያዘው እንቅስቃሴ ቅርጹንና መልኩን ለውጦ በሰው አእምሮና አስተሳሰብ ላይ እንደህንጻ የሚያድግ ግብረገብነትን፤ በጎ አድራጎትንና  መልካም ስብእና ያለው ሕብረተሰብን የመፍጠር ዓላማ ባለው መመሪያ ላይ ራሱን በማቆም ሕግና ደንብ አውጥቶ መሥራት መጀመሩን የተጻፈ ታሪኩ ያስረዳል። 

  ምንም እንኳን የፍሪማሰንሪ ማኅበር በኦፊሴል ከአምልኮና ከፖለቲካ አስተሳሰብ ነጻ ነኝ ቢልም በ1723 እና በ1738 ዓም ተሻሽሎ በወጣው የፍሪማሰንሪ ሕገ መንግሥት ላይ እንደተመለከተው የሁሉም ነገር ንድፍ / architect/ ባለቤት «እግዚአብሔር ነው ስለሚል እንቅስቃሴው ሃይማኖት ለበስ እንደሆነ ፍንጭ ከመስጠቱም በላይ ድርጅቱ የራሱ የሆነ ዶግማና መመሪያ ስላለው የእምነት ድርጅት አይደለሁም የሚለው አባባሉ ተቀባይነት እንዳይኖረው አድርጓል።  ድርጅቱ የአንድ ወጥ የሃይማኖት ተቋም ላለመሆኑ እንደመከራከሪያ የሚያቀርበው ጭብጥ የፍሪማሰንሪ አባል ለመሆን  የየትኛውንም ሃይማኖት ተከታይ ወይም የሃይማኖት መጽሐፍ ተቀባይ ወይም የትኛውንም የፖለቲካ መስመር የያዘ ሰው በአባልነት መቀበል መቻሉን በማስረጃነት ያቀርባል።  ድርጅቱ ይህንን ይበል እንጂ አባል የሚሆን ሰው ቀድሞ የነበረውን እምነቱን ይሁን አመለካከቱን እንዲጥል ሳይገደድ የፍሪማሰንን አስተምህሮና ሕግ በተከታታይ ተምሮ በድርጅቱ የረቀቀ አስተሳሰብ ውስጥ እንዲሰጥም ማድረግ በራሱ ቀድሞ የነበረውን የማስቀየር ዘዴ እንደሆነ በተሞክሮ ያዩት ሰዎች በተግባር ያረጋገጡት ሀቅ ነው።

    እንደፍሪማሰንሪ አባባል የጥበቦች ሁሉ /Architect/ የንድፍ ባለቤት እግዚአብሔር ሲሆን ያገኙትን ጥበብ ወደተግባር የሚለውጡት ደግሞ የፍሪማሰንሪ እውቀት የተሰጣቸው ሰዎች ናቸው ይላሉ። ለምሳሌም የኖኅ መርከብ የተሰራቸው በኖኅ የፍሪማሰን እውቀት ነው። የባቢሎን ግንብ ይሁን የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ያለፍሪማሰን እውቀት ፍጻሜ አያገኝም ነበር ባዮች ናቸው። የግብጽ ፒራሚዶች የፍሪማሰን ጥበብ ውጤት ነው። የኖስቲኮች እውቀት፤ የግሪክ ፍልስፍና፤ የፓይታጎረስ ስሌት፤ የዞሮአስተር ትምህርት፤ የቻይና ጥበብ፤ የአልኬሚስቶች ፈጠራ ሁሉ በፍሪማሰን እውቀት ጎልምሶ ወደተግባር የተለወጠ መሆኑን ያምናሉ። 

   ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ሲመለመል የትኛውንም ሃይማኖት የሚከተል ወይም የትኛውንም የሃይማኖት መጽሐፍ የሚቀበል ሰው መሆኑ ችግር የለውም። እንዲተውም አይጠበቅም። ቁምነገሩ አንድ ጊዜ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባል ከሆኑ በኋላ ድርጅቱን መልቀቅ እንደማይቻል ወይም በምክንያት ከለቀቁ ደግሞ የቆዩበትን የድርጅቱን ምስጢር ማውጣት የሞት ዋጋ እንደሚያስከፍል አስቀድሞ ቃለመሃላ ይፈጽማል። ፍሪማሰንሪ በስብከትና በድለላ የአባልነት ምልመላ አያደርግም። አብዛኛው የዚህ ድርጅት አባላት ፕሬዚዳንቶች፤ ጠቅላይ ሚኒስትሮች፤ ዶክተሮች፤ ፕሮፌሰሮች፤ ጀነራሎች፤ ዳኞች፤ የሴኔትና የምክር ቤት አባላት፤ ቢሊየነሮች፤ ታዋቂ ሰዎችና ከፍተኛ ነጋዴዎች ናቸው። ከአሜሪካ 44 ፕሬዚዳንቶች ውስጥ 14ቱ የፍሪማሰንሪ ድርጅት አባላት እንደነበሩ በግልጽ ሲታወቅ  ከተቀሩትም ውስጥ በምስጢራዊ አባልነት የነበሩ እንዳሉ ይነገራል።

ፍሪማሰንሪ ካሉት 330 (ሠላሳ ሦስት ድግሪ) ማእርጋት አንዱ በሆነው የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ የተወሰኑ ትምህርቶችን አስቀድሞ ከወሰደ በኋላ ወደድግሪ ትምህርቱ ሲገባ ይህንን መሃላ ይፈጽማል።

« ዛሬ የፍሪማሰንሪ አባል ከሆንኩ በኋላ አባል ለሆንኩበት ድርጅት ካልታመንኩ ወይም ብከዳ ወይም ምስጢር ባወጣ በጎሮሮዬ ላይ ስለት ይረፍ፤ ምሳሴ ከስሩ ተነቅሎ ይጣል፤ አጽሜ አመድ ሆኖ ከውቅያኖስ የጥልቁ አሸዋ ውስጥ የተሰወረ ይሁን» ይላል። ለምን?

የፍሪማሰንሪ ዓርማና ሌሎች ምልክቶች ምንድናቸው? ከኢሉሚናቲ ጋር ያላቸው ግንኙነት ምንድነው? ይህንንና ሌሎች ምስጢሮችን በቀጣይ ክፍል ለማቅረብ እንሞክራለን።