Wednesday, October 1, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶችና ነብያት!



 ( ክፍል 3 ) 

ጂም ጆንስ (1931-1978)
በአሜሪካዋ ኢንዲያና ስቴት ህዳር 18, 1931 ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ህውከት ሲደርስ በኢንዲያናፖሊስ ከተማ የኮሙኒስት ፓርቲ አባል በመሆን በህውከት ስራ ላይ መሰማራትን «ሀ» ብሎ ጀመረ። የኮሙኒስት ርእዮት አራማጅ የሆነው ጆንስ በሜቶዲስት፤ በሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት ውስጥ ብቅ ጥልቅ እያለ ከቆየ በኋላ ዓለም በኒውክለር ትጠፋለች ስለዚህ ሐዋርያዊ ሶሻሊዝም በዓለም ላይ መምጣት አስፈላጊነት ይሰብክ ነበር። ጆንስታውን ወደተባለች የጉያና ከተማ በማቅናት «የህዝቦች ቤተ መቅደስ» የተሰኘ ቤተክርስቲያን ከመሠረተና ከተደላደለ በኋላ የእርሻ ተቋም ከፈተ።  በዚህ የእርሻ ተቋም ውስጥ ሶሻሊስታዊ እኩልነት የሰፈነበት ማኅበረሰብ እመሰርታለሁ በማለት የራሱን «የቀይጦር ሠራዊት» አደራጀ። ይህ የቀይ ጦር ሠራዊት ዋና ዓላማው የእርሻውን ሜካናይዜሽንና የቤተ ክርስቲያኑን ህልውና የመጠበቅ ዓላማ ይዞ የተነሳ ቢመስልም በተግባር ግን የጂም ጆንስን አንባገነንነት መንከባከብ ነበር። ወደተቋሙ የገባ ማንም አባል መውጣት አይችልም በማለት ማገድ ጀመረ። በዚህም ሳቢያ በዚያ ማኅበረሰብ ውስጥ የፈለገውን ማድረግ የሚችል አንባ ገነን መሆን ቻለ። ከዚህ ተቋም ሸሽተውና አምልጠው ወደአሜሪካ የገቡ ሰዎች ለአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተርና ለምክርቤቱ አቤቱታቸውን ማቅረብ ቻሉ። በሰብአዊ መብት ጥሰት የተከሰሰው  የጆንስን ጉዳይ የሚያጣሩ በኮንገረስ ማን ሊዮ ሪያን የሚመራ ብዙ የሚዲያ ሰዎችን የያዘ ቡድን ወደጉያና አመራ። ቡድኑ ከቦታው እንደደረሰ ከጆንስ ቀይጦር አባላት የጠበቀው የሞቀ ሰላምታ ሳይሆን የደመቀ የጥይት ተኩስ ነበር። ኮንግረስ ማን ሪያንና ሌሎች ብዙዎቹ በተኩሱ ተገደሉ።  ከፊሎቹም ቆሰሉ። ህዳር 18, 1978 ዓ/ም ጥዋት ላይ ይህ ግድያ ከተፈጸመ በኋላ ጆንስ ወደተከታዮቹ በመመለስ ከሚመጣባችሁ ቁጣ ለመዳን ራሳችሁን አጥፉ፤ ልጆቻችሁንም ጭምር ለመፍጀት ለሚመጡ ጠላቶች አሳልፋችሁ አትስጡ፤ ስለዚህ አብራችሁ ሙቱ በማለት ትእዛዝ ሰጠ።
ሳይናድ መርዝ እየጠጡና እያጠጡ 300 ህጻናት ያሉበት 900 ሰዎች በጥቂት ሰዓት ውስጥ አለቁ።
እኔ ቡድሃን፤ ሌኒንን፤ኢየሱስን እና ሌሎችን ሆኜ ተገልጫለሁ እያለ ያታልል የነበረው ጂም ጆንስ በአውቶማቲክ ጥይት ግንባሩን ብትንትንን አድርጎ ራሱን በራሱ ገደለ።




ማርሻል አፕልዋይት  (1931-1997)
ስፐር ፤ቴክሳስ ተወለደ። እድሜው ለአቅመ ማሳሳት ከመድረሱ በፊት የአሜሪካ ወታደር በመሆን አገልግሏል። በሂውስተንና ኮሎራዶ ትምህርቱን የተከታተለው አፕል ዋይት በአላባማ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ሲሰራ በግብረ ሰዶም ተጠርጥሮ ከስራው ተባሯል። ይህንን ተግባሩን የመሰከረበት ደግሞ በስብከቱ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነትን አስፈላጊነት መናገሩ ነበር። አፕል ዋይት የሙዚቃ ባለሙያ ስለነበር በዚህ ሙያ ያገኘውን ችሎታ ተጠቅሞ «Heaven’s Gate» /የመንግሥተ ሰማይ በር/ የተሰኘ ሃይማኖታዊ ድርጅት መሠረተ።  አፕልዋይት በዩፎዎች መኖር የሚያምንና በነሱ ላይ ጥገኛ የሆነ ስብከት ያስተምር ነበር።
 በ1974  ዓ/ም የተከራያትን መኪና ባለመመለስ ወንጀል ተከሶ ስድስት ወር ተፈርዶበት ከርቸሌ ወረደ። ከዚያም እንደወጣ ጣዖታዊ ስብከቱን ቀጥሏል። መስከረም 25, 1995 ዓ/ም «እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ነኝ» በማለት ለተከታዮቹ አሳወቀ።
በመጋቢት 29/ 1997 ዓ/ም ዩፎዎች መጥተው ወደገነት ስለሚወስዱን ራሳችንን እናጥፋ ብለው በጅምላ ራሳቸውን ገደሉ። ከተከታዮቹ መካከል ማርሻል አፕል ዋይትን ጨምሮ 30 አባላቱ ሞተው ተገኙ። ነገር ግን ሁኔታው እንደተሰማ ከቦታው የተገኘ አንድም ዩፎ አልነበረም። ይልቁንም ፖሊስ ከቦታው ተገኝቶ እነአፕልዋይት ራሳቸውን በራሳቸው ማጥፋታቸውን አረጋግጦ የህዝብ መቃብር ውስጥ እንዲወርዱ አድርጓል።




ያህዌህ ቤን ያህዌህ (1935-2007) 

 ጥንተ ስሙ ኸሎን ሜሼል ጁንየር ይባል ነበር። ይህ ጥቁር አሜሪካዊ እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ለማለት ፈልጎ ስሙን  በ1979 ዓ/ም «ያህዌህ ቤን ያህዌህ» በማለት ቀየረ። ብዙዎቹም ተከታዮቹ ከክርስትናውና ከአይሁድነት ያፈነገጡ ሰዎች ነበሩ። በተለይም ጥቁር አሜሪካውያን ብዙ ቁጥር ያላቸው ሲሆን ትክክለኛው እስራኤላውያን እኛ ነን፤ ይሉ የነበረ ሲሆን በአሜሪካና በዓለም ላይ በ1300 ከተሞች ውስጥ አባላቱን ማደራጀት ችሏል። እግዚአብሔር ጥቁር ነው። እስራኤልውያንም ጥቁሮች ነበሩ። ነጮቹ ታሪካችንን ቀምተው ነው። ሰይጣን ማለት ነጮች ናቸው ይል ነበር። በዚህም ምክንያት ዓርብ ህዳር 13 ቀን አንገታቸው የተቀላ የነጮች ሬሳ በአቅራቢያው ዳዋ ውስጥ ተጥሎ በመገኘቱ ጥቁሩ መሲህ ቤንያህዌህ በ1992 ዓ/ም ሰው በመግደል ወንጀል ተጠርጥሮ ተያዘ። በፍርድ ቤትም በምስክሮች ስለተረጋገጠበት የ18 ዓመታት እስር ተበይኖበት ከርቸሌ ወረደ።  
በእስራቱም ነብይ በሀገሩ አይከበርም ያለው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው ሲሉ ተከታዮቹ ለፈፉ። ከ8 ዓመት እስራቱም በኋላ በ2001 ዓ/ም በምህረት ተለቀቀ። በ2007 ዓ/ም በፕሮስቴት ካንሰር ሞተ። ከሱ ሞት በኋላ ተከታዮቹ በሥጋ የተገለጠው እግዚአብሔር ማለታቸውን አልተዉም። ልቡ የደነደነ ዓለም ዓይኑ ታውሮ ሰው ያመልካል። ለጣዖትና ስዕል ይሰግዳል።

(ይቀጥላል % )

Wednesday, September 24, 2014

ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ ምን ይመስላል?


( ክፍል ሁለት )
 


3/የቅዱሳን መላእክት አገልግሎት


በክፍል አንድ ጽሁፋችን ስለመላእክት ስያሜ ትርጉም፤ ስለአፈጣጠራቸው፤ ስለፈቃዳቸውና ተልእኰአቸው በጥቂቱ ለማየት ሞክረን ነበር። በክፍል ሁለት ጽሁፋችን ደግሞ ቀሪውን ነጥብ እግዚአብሔርን እንደፈቀደ መጠን ለማየት እንሞክራለን።
ቅዱሳን መላእክት የፈጣሪያቸውን ትእዛዝ ሳይጠብቁ  የትም እንደማይንቀሳቀሱ እርግጥ ነው። በዚህም የተነሳ እግዚአብሔር በወደደውና በፈቃደው ቦታ ቅዱሳኑን መላእክት ለእርዳታና ለትድግና ይልካቸዋል። 

«የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል» መዝ 34፤7

እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ሰዎች የእግዚአብሔር ጥበቃና እርዳታ ዘወትር ይደረግላቸዋል ማለት መላእክቱ በራሳቸው ፈቃድ ይንቀሳቀሳሉ ማለት አይደለም። አንዳንዶች ይህንን ጥቅስ በመጠቀም «መላእክት በተጠሩ ጊዜ በተናጠል መጥተው ያድኑናል» ወደሚል ድምዳሜ በመድረስ ከመላእክት አማላጅነት ጋር ለማያያዝ የሚፈልጉ ወገኖች አሉ። ነገር ግን ዳዊት በመዝሙሩ በግልጽ እንደተናገረው
 «በልዑል መጠጊያ የሚኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል» ካለ በኋላ ሰው ሁሉን በሚችል በእግዚአብሔር ፈቃድ ስር ካደረገ «እግዚአብሔርን፦ አንተ መታመኛዬ ነህ እለዋለሁ አምላኬና መሸሸጊያዬ ነው» በማለት እግዚአብሔር ታዳጊ አምላክ እንደሆነ በማሳየት፤  ከእግዚአብሔር ዘንድ ደግሞ ለእንደዚህ ዓይነቱ አማኝ የተሰጠው የጥበቃ ተስፋ በቅዱሳን መላእክቱ በኩል መሆኑን ከታች ባለው ጥቅስ ይነግረናል።

«ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፥ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ አይገባም። በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና» 
 ይላል በዝማሬው። መዝ 91፤ 1-16 (ሙሉውን ያንብቡ)
በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔርን መታመኛቸው ላደረጉ ሰዎች የእግዚአብሔር ጥበቃ በመላእክቱ በኩል ሲፈጸም እንመለከታለን።

«ጴጥሮስም ወደ ልቡ ተመልሶ፦ ጌታ መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና የአይሁድ ሕዝብ ይጠብቁት ከነበረው ሁሉ እንደ አዳነኝ አሁን በእውነት አወቅሁ አለ» የሐዋ 12፣11

 ጴጥሮስን ሄዶ እንዲያድን የላከው ጌታ ነው። መልአኩ የተላከውም ጴጥሮስን እንዲያድን ነው። ቅዱሳን መላእክት እንደስማቸው ለሚገዙለት ጌታ ይላካሉ። አድኑ የተባሉትን ያድናሉ። ለመዓትም ይሁን ለምህረት መላእክቱ የሚላኩት በእግዚአብሔር ትእዛዝ እንጂ ሰዎች ስለጠሯቸው ወይም ስለፈለጓቸው አይደለም።
 በብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ውስጥ ወደቴስቢያዊው ኤልያስ መልአኩ በተላከ ጊዜም  አካዝያስ ስለህመሙ ምክንያት እግዚአብሔርን በጸሎት ከመጠየቅ ፈንታ ወደአቃሮን ብዔል ዜቡል ፊቱን ባዞረ ጊዜ መልአኩ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» በማለት የመጣበት ጉዳይ ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ትእዛዝ ለመፈጸም እንደሆነ አስረግጦ ሲናገር፤

 «የእግዚአብሔርም መልአክ ቴስብያዊውን ኤልያስን፦ ተነሣ፥ የሰማርያን ንጉሥ መልእክተኞች ለመገናኘት ውጣና። የአቃሮንን አምላክ ብዔልዜቡልን ትጠይቁ ዘንድ የምትሄዱት በእስራኤል ዘንድ አምላክ ስለሌለ ነውን? ስለዚህም እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ትሞታለህ እንጂ ከወጣህበት አልጋ አትወርድም በላቸው አለው። ኤልያስም ሄደ» 1ኛ ነገ 1፤3-4

«እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» ማለቱ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ተቀብሎ ለመፈጸም መምጣቱን ያስረዳል። ወደኤልያስ መልእክቱ ይመጣ ዘንድ ያስፈለገውም ኤልያስ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ይከተል ስለነበር መሆኑ እርግጥ ነው። በሌላ ቦታም የእግዚአብሔርን ፈቃድ ይፈጽሙ ከነበሩ ደጋግ ሰዎች መካከል አንዱ ወደሆነው ወደቆርኔሌዎስም ዘንድ ሲልክ  እንመለከታለን።

«ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለው፦ በዚች ሰዓት የዛሬ አራት ቀን የዘጠኝ ሰዓት ጸሎት በቤቴ እጸልይ ነበር፤ እነሆም፥ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ ሰው በፊቴ ቆመና። ቆርኔሌዎስ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ ምጽዋትህም ታሰበ»  የሐዋ 10፤ 30-31

የቆርኔሌዎስ ስለጸሎቱ መሰማትና ስለምጽዋቱም በእግዚአብሔርን ዘንድ መታሰብ የሚናገር መልእክተኛ መላኩን ስንመለከት ዳዊት በዝማሬው እንዳመለከተው በልዑል መጠጊያ ለሚኖሩ ሁሉ መላእክቱ እንደሚላኩላቸው በግልጽ ያረጋግጥልናል። በዚሁ ተመሳሳይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስረጂ በማቅረብ የመላእክቱን ተራዳዒነትና አጋዥነት መግለጽ  ይቻላል። ነገር ግን አስረግጠን ማለፍ የሚገባን ቁም ነገር መላእክቱ የሚመጡት በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ስር ላሉ ሲሆን ሰዎች የፈለጉትን መልአክ ስለጠሩ ወይም በልባቸው አምሮት የመረጧቸውን  መላእክት ስም ስለተናገሩ አለመሆኑን መገንዘብ ይገባናል። በሰዎች ጥሪ እገሌ የተባለ መልአክ መጣልኝ የሚል አንዳችም አስረጂ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ አይገኝም። በተራዳዒነትና አጋዥነት እንደተላኩ የሚነገርላቸው አብዛኛዎቹ መላእክትም በስም ተለይተው አይታወቁም። ቁም ነገሩ የትኛው መልአክ በታላቅ ኃይል ትእዛዙን ይፈጽማል በማለት በኛ ምርጫ የሚወሰን ሳይሆን በስም የተገለጹም ይሁን ያልተገለጹትን እግዚአብሔር መላእክቱን ልኮ የወደዳቸውን እንዴት ይታደጋል? የሚለውን ከመረዳቱ ላይ ልናተኩር ይገባል። ስለዚህም ተልከው ስላገዙን መላእክት የምንሰጠው ክብር እግዚአብሔር ለኛ ያደረገውን ታላቅ ሥራ ቀንሰን የምናካፍለው መሆን የለበትም። በርናባስና ጳውሎስ ከእናቱ ማህጸን ጀምሮ እግሩ የሰለለውን ሰው በፈወሱበት ወቅት የሊቃኦንያ ከተማ ሰዎች «አማልክት ከሰማይ ወደእኛ ወርደዋል» በማለት መስዋዕት ሊያቀርቡላቸው በወደዱ ጊዜ እነጳውሎስ ያደረጉትን ማየቱ ተገቢ ነው።

«ሐዋርያት በርናባስና ጳውሎስ ግን ይህን በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀደው ወደ ሕዝቡ መካከል እየጮኹ ሮጡ፥ እንዲህም አሉ። እናንተ ሰዎች፥ ይህን ስለ ምን ታደርጋላችሁ? እኛ ደግሞ እንደ እናንተ የምንሰማ ሰዎች ነን፥ ከዚህም ከንቱ ነገር ሰማይንና ምድርን ባሕርንም በእነርሱም ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር ትሉ ዘንድ ወንጌልን እንሰብካለ»                የሐዋ 14፤14-15

ጳውሎስና በርናባስ ቅዱሳን በአገልግሎታቸው ሐዋርያት ሆነው ብናከብራቸውና ብንወዳቸውም ቅሉ በእነሱ እጅ በተሰራው አምላካዊ  ድንቅ ሥራ ግን ምስጋናንና ክብርን በጋራ ሊቀበሉ አይችሉም። ክብርና ምስጋና ሁሉ ለእግዚአብሔር ብቻ እንደሆነ ራሳቸው እንደመሰከሩት የእግዚአብሔር  የብቻው የሆነውን ወደፍጡራን መስጠት ተገቢ እንዳልሆነ ማወቅ ይገባናል።

4/ የእግዚአብሔር መላእክት ሳይላኩ በሰዎች ጥሪ ሥፍራቸው ለቀው ይሄዳሉን?

ቅዱሳን መላእክትን ቅዱሳን ያሰኛቸው ዋናው ቁም ነገር የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ማክበር መቻላቸው ነው። ከእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ውጪ የሆኑትማ  ከማዕርጋቸው ተሰናብተዋል። ስለዚህ ቅዱሳን መላእክቱ ሰዎች ስለጠሯቸው ወይም ስማቸው ነጋ ጠባ ስለተነሳ ተጠርተናል በሚል ሰበብ ወደየትም አይሄዱም። ከላይ በማስረጃ ለማስረዳት እንደተሞከረው ቅዱሳኑ መላእክት የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለፈጸሙ ወይም እግዚአብሔር ፈቃዱ ይፈጸም ዘንድ በወደደበት ቦታ መላእክቱን ከሚልክ በስተቀር የትኛውም መልአክ ስሙ ስለተጠራ ወይም ስለተወሳ ተከብሬአለሁና ልሂድ፤ ልውረድ በማለት ከተማውን ለቆ የትም አይሄድም። አንዳንድ ሰዎች የመላእክቱን ስም ለይተው በመጥራት ናልኝ የሚሉት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ካልሆነ ትምህርት የተገኘ ልምምድ ውጤት ነው።
 ስሙ ተጠርቶ ይቅርና ገና ሳይጠራ ስፍራውን ለቆ የትም የሚዞረው ሰይጣን ብቻ ነው። ሰይጣን ቦታውን ለቆ የትም የሚዞረው ከእግዚአሔር ፈቃድ ውጪ ያፈነገጠ ሽፍታ ስለሆነ ነው። ቅዱሳን መላእክቱ ያለእግዚአብሔር ትእዛዝ ስማቸው ስለተጠራ ብቻ ሥፍራቸውን ለቀው እንደማይንቀሳቀሱ የሚያውቀው ሰይጣን ራሱን የብርሃን መልአክ አስመስሎ ሊያታልል እንደሚችል ወንጌል ያስረዳናል።
«ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና» 2ኛ ቆሮ 11፤14

ሰይጣን በራሱ ፈቃድ የሚተዳደር ዐመጸኛ ስለሆነ በዓለሙ ሁሉ እየዞረ ሰዎችን ሲያሳስት ይውላል። በተለይም የእግዚአብሔርን ፊት በሚሹ ሰዎች ዙሪያ የጥፋት ወጥመዱን ሊዘረጋ አጥብቆ ይተጋል። ጻድቅ የሆነው ኢዮብንም ያገኘው በዚህ የጥፋት አደናው ወቅት ዓለምን ሲያስስ እንደነበር ከንግግሩ ታይቷል።

«እግዚአብሔርም ሰይጣንን፦ ከወዴት መጣህ? አለው። ሰይጣንም። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት፥ በእርስዋም ተመላለስሁ ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ»ኢዮብ 1፣7

ስለዚህ ክርስቲያኖች እንደእግዚአብሔር ፈቃድ እየኖሩ ለትእዛዙ በተገዙ ጊዜ በመልካም ትሩፋታቸው ይሁን በችግራቸው ወይም በመከራቸው ወቅት እንዲራዷቸው ቅዱሳኑ መላእክት ከሚላኩ በስተቀር ሰዎች በቀጥታ መላእክቱን ስለጠሯቸው ወይም በስማቸው ስለተማጸኑ የሚመጡ ባለመሆናቸው ከመሰል ስህተት ልንጠነቀቅ ይገባል። ይልቁንም ከእግዚአብሔር ተልእኮ ውጪ ቅዱሳኑ እንደማይንቀሳቀሱ የሚያውቁት የሰይጣን ሠራዊት የብርሃን መልአክ በመምሰል ራሳቸውን ቀይረው ከሚፈጽሙብን ሽንገላ ልንጠነቀቅ ይገባል።

እንደማጠቃለያ፤

 ቅዱሳን መላእክት ሰዎችን ይራዳሉ፤ ያግዛሉ ማለት በሥልጣናቸው የራሳቸውን ክብር ስም ለማስጠበቅ ይሠራሉ ማለት አይደለም። በተፈጥሮአቸውም ውሱን ስለሆኑ በዓለም ላይ በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት የመገኘት ብቃት የላቸውም። በሁሉም ሥፍራ ተገኝተው ሰዎች ሰለጠሯቸው መልስ አይሰጡም።  ይሁን እንጂ በዓለም ላይ በስማቸው ተሠራ በሚባለው ቤተ ጸሎት በአንድ ጊዜ በስፍሐትና በምልዓት ተገኝተው ጸሎት እንደሚቀበሉ ተቆጥሮ ስማቸው ሲጠራ ይታያል። በቅዱሳን መላእክት ተራዳዒነት እናምናለን ማለት ቅዱሳን መላእክት በራሳቸው ፈቃድ ስለጠራናቸው ይደርሱልናል ማለት አይደለም። ቅዱሳን መላእክት ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ሳይደርሳቸው አይንቀሳቀሱም። የዚህ ጽሁፍ ዋና ዓላማም ቅዱሳኑን መላእክት ስናከብራቸው አስተሳሰባችንን በመለጠጥ የምንጓዝበት የእምነት ጽንፍ ወደስህተት እንዳይጥለን ለማስገንዘብ ነው። ቅዱሳኑን ያለትእዛዝ ስለጠራናቸው ብቻ በማይመጡበት ሥፍራ ሰይጣን የብርሃን መልአክ መስሎ ከሚፈጽመው ማታለል ለመጠበቅ ነው።
በአንዳንድ የእምነት ተቋማት ዘንድ ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ የተዛባ ምስልን እንደያዘ መገንዘብ ይቻላል። 

   በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አንዳንዶች የመላእክቱን ተፈጥሮ ዘንግተው ሁሉን የመስማት፤ የማወቅና በሁሉ ሥፍራ የመገኘት ችሎታ እንዳላቸው ሲቆጥሩ መታየቱ ተለምዷል። መላእክት በተጠሩ ጊዜ መልስ እንደሚሰጡና እንደሚራዱ የሚሰጠውም ግምት ያለትእዛዝ በራሳቸው ፈቃድ እንደሚንቀሳቀሱ ያደርጋቸዋል። ይህም ወደ እግዚአብሔር ሳይሆን በተራዳዒነት ሰበብ ወደ መላእክቱ ጸሎት የሚያደርሱ ሰዎችን አስገኝቷል። «እንደአናንያ፤ እንደአዛርያ፤ እንደሚሳኤል አድነን ገብርኤል» እያሉ መዘመር እንደተገቢ ከተቆጠረ ውሎ አድሯል። ሠለስቱ ደቂቅን ያዳነው ገብርኤል ነው ከሚለው የትርጉም ፍልሰት ጀምሮ «ገብርኤል አዳኝ ነው» ወደሚለው መልአኩን  ለይቶ የማመስገን የፍቺ ጽንፍ ድረስ ስለመላእክት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ ምስል መስጠት ጉዳዩን አደገኛ ያደርገዋል። እኛ የሚያድኑን እግዚአብሔር ፈቃዱን የፈጸመባቸው መላእክቱ ወይስ የእግዚአብሔር ኃይል? በሚለው ሃሳብ ላይም መቀላቀል የታየበት ሁኔታ ሕዝቡ መላእክቱን በተናጠል ወደመጣራት ሲገፋው ይስተዋላል። ከሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ሚካኤል አንተ ታውቃለህ? ብሎ የመጸልይ ልምምድ ስለመላእክቱና ስለእግዚአብሔር ፈቃድ የተቀላቀለ ትምህርት ውጤት ነው።
አንድ ክርስቲያን በአንድ ጊዜ ወደእግዚአብሔርም፤ ወደመላእክቱም ጸሎት ማድረስ አይችልም። ይህ መተላለፍ ነው። እግዚአብሔር ደግሞ ከክብሩም፤ ከምስጋናውም ለማንም አያጋራም። ቀናተኛ አምላክ የሚባለውም ለዚህ ነው። ኢያሱ ወልደነዌ ለህዝቡ እንዲህ አለ።
«ኢያሱም ሕዝቡን፦ እርሱ ቅዱስ አምላክ ነውና፥ እርሱም ቀናተኛ አምላክ ነውና እግዚአብሔርን ማምለክ አትችሉም መተላለፋችሁንና ኃጢአታችሁን ይቅር አይልም» ኢያ 24፤19
ስለዚህ ስለመላእክት ተፈጥሮ፤ ተልዕኰና አገልግሎት በደንብ ማወቅ የሚገባን የእግዚአብሔርን ለመላእክት፤ የመላእክትንም ለእግዚአብሔር በመስጠት የእምነት ሥፍራውን  እንዳናቀላቅል ሲባል ነው። ተፈጥሮአቸውን፤ ተልእኰአቸውንና ተግባራቸውን ለይተን እንወቅ። ከስህተትም ላይ እንዳንወድቅ እንጠንቀቅ። ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን። አሜን!

Wednesday, September 17, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶች!

ክፍል ሁለት )

ዘመኑ የቀሳጥያን፤ የሀሰተኛ ትምህርትና የክህደት መፍለቂያ መሆኑን የበለጠ ለማስረዳት ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ተግባር ላይ ተሰማርተው የነበሩትን ማሳየት ጠቃሚ ይመስለናል። የሰው ልጅ በወንጌል ላይ የተገለጠውን ክርስቶስን ሳይሆን በሰው ብልሃት የተቋቋመችውን ምድራዊ ተቋም፤ የሰዎች ድርጅት፤ የአስተምህሮ መንገድና ስብከት እየተከተሉ ከእውነት ሲያፈነግጡ ማሳየት ተገቢ እንደሆነም ይሰማናል። ዛሬም ቢሆን ሰዎች የድርጅት፤ የተቋምና የሰዎች ተከታዮች ሆነው ይታያሉ። እውነታው ግን ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ የመሠረተው አንድም የእምነት ድርጅት ወይም ተቋም  አለመኖሩ ነው። ጲላጦስ ከመሰቀሉ በፊት ኢየሱስን «እውነት ምንድር ነው?» ብሎ ስለሆነው ነገር ጠይቆት ነበር። ( ዮሐ 18፤38) እውነቱ ግን ሰዎች «እስኪ ራሱን ያድን» እያሉ እየተዘባበቱበት የሰቀሉትን ኢየሱስን ማመን ነበር። አይሁዳውያን ሰዎች ራሷን ማዳን የማትችል ምድራዊት የእምነት ተቋም ስለነበራቸው ከእምነት እንጂ ከተቋም ስላልሆነችው የኢየሱስ ስብከት ጆሮአቸውን አልሰጡም። ስለዚህም እውነቱ አመለጣቸው። ዛሬም ሰዎች ክርስቶስን እናምናለን ቢሉም ከተቋምና ከድርጅት ስብከት አልወጡም። በዓለም ላይ በተለያየ ስም የተከፋፈለው የእምነት ተቋም መሠረቱ በሰዎች አስተምህሮ ላይ የተንጠላጠለ ነገር ግን ክርስቶስ ያጠለቀ በሚመስል ድርጅት የሚጠራ መሆኑ ነው። እውነቱ ግን «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም» ባለው ቃል ጸንቶ መገኘት ብቻ ነው። የምናምነውን ነገር በወንጌል መነጽር እንመርምረው። ወንጌል ካስተማረው ውጪ የሆነው ሁሉ ከሰይጣን የተገኘ ነው።

 
ሚዝራ ጉላም አህመድ (1835-1908)

 ይህ በሃይማኖቱ እስላም የሆነ ሕንዳዊ ዜግነት የነበረው ሰው በአንድ ወቅት ራሱን እንዲህ ሲል ገልጾ ነበር። እስላሞች በመጨረሻው ቀን ከሰማይ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት «ማህዲ» የተባለውን ነብይና ክርስቲያኖች ለፍርድ ዳግም ይመጣል ብለው የሚጠባበቁት «ኢየሱስ»ን የምወክል ስሆን እነሆ ሁለቱም በእኔ ውስጥ በሥጋ ተገልጸዋልና ተከተሉኝ በማለት ሲለፍፍ ቆይቷል። ማሳሳት ጥንተ ግብሩ የሆነው ሰይጣን በህንዳዊው አህመድ ውስጥ አድሮ እሱን ብቻ ሳይሆን ለብዙዎች መሳሳት ምክንያት ሆኖ ከእስልምና ሴክት/ክፍል/ አንዱ የሆነውን «አህመዲያ» የተባለው ቅርንጫፍ ፈጥሮ በማለፍ ዛሬም ድረስ ከ20 ሚሊዮን ያላነሱ አባላትን በዓለም ዙሪያ ማፍራት ችሏል።

ሎ ደ ፓሊንግቦኸር (1898- 1968)

በዜግነቱ ኔዘርላንዳዊ የሆነው ፓሊንግቦኸር በሙያው የተዋጣላት ዓሳ አጥማጅ ነበር። በዓሳ አጥማጅነት ሥራው ከሱ ዘንድ ዓሳ ለመግዛት ለሚመጡ ሸማቾች በትንሹ የጀመረውን ስብከት አሳድጎ በስህተት ሰው ወደ ማጥመድ ሥራ አሳደገው። ተከታዮችን ማፍራቱን እንዳረጋገጠ የዓሳ ጀልባውን በመሸጥ ስብከቱን የሙሉ ጊዜው ሥራው በማድረግ የቀጠለ ሲሆን ዓለም ከክፉ ነገር ሁሉ የምትድነው እኔን በማመን ነው እያለ በየጎዳናው ይለፈልፍ ነበር። ትምህርቱን እንደትክክለኛ አድርገው የተቀበሉ ተከታዮቹ ትልቅ የመኖሪያ ቤት ገዝተው የሰጡት ሲሆን በስተመጨረሻም እኔ «ኢየሱስ» ነኝ በማለት ስብከቱን ገፍቶበታል። አንዳንዶች ይህ ሰው ከሀዲ ነው ብለው ቢያወግዙትም ፓሊንግቦኸር «እግዚአብሔር» ወደመሆን ይለወጣል በማለት ይከራከሩለት የነበሩ ተከታዮችን ማፍራት ችሏል። ይሁን እንጂ ብዙ ጊዜ አግብቶ በመፍታት የሚታወቀው ይህ ቀሳጢ እንኳን ሌሎችን ሊያድን ይቅርና ራሱን ከሞት ማዳን ሳይችል ቀርቶ እስከወዲያኛው አሸልቧል።

ኃይለሥላሴ (1892-1975)

 የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት የነበሩት አፄ ኃይለ ሥላሴ ራሳቸውን እንደመሲህ አድርገው ባይቆጥሩም መሢህ ናቸው የሚሏቸው ወገኖች አሉ። ንጉሡ በአንድ ወቅት በሳቸው ዙሪያ ስለሚባለው ነገር ተጠይቀው «እኛ ሰው ነን እንጂ መሲህ አይደለንም» ብለው የመለሱ ቢሆንም ተከታዮቻቸው በንጉሡ ምላሽ ዙሪያ የሰጡት ማስተባበያ «የኛ መሲህ ያለውን ትህትና ተመልከቱ» በማለት የንጉሡን ምላሽ ከአትህቶ ርእስ ጋር በማያያዝ ለማሳመን ቢሞክሩም እውነታው ግን አፄው መሲህ አለመሆናቸው ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ ለመታሰቢያቸው አርኬ እና መልክእ በመድረስ በነግህና በሰርክ ጸሎት ታስባቸው ነበር። አንዳንዶች የዋሃን አፄው አይሞቱም የሚል ግምት የነበራቸው ቢሆንም ደርግ የገደላቸው መሆኑ ይታወቃል። ከጃማይካ ህዝብ 5% የሚሆነው የራስ ተፈሪያን እምነት ተከታይ ሲሆን በአሜሪካም ብዙ አባላት አሉት።

ኤርነስት ኖርማን (1904-1971)


  አሜሪካዊ የኤሌክትሪካል ኢንጂነር ባለሙያ የነበረና (ዩራንየስ አካዳሚ ኦፍ ሳይንስ) መስራች የሆነ ሰው በአንድ ወቅት ከሙያው ውጪ እብደት መሰል ስብከት ጀምሮ ነበር። ከዚህ በፊት በዚህ ምድር ላይ የተገለጸው «ኢየሱስ» እኔ ነበርኩ። ወደሰማይ ባርግም በዚህ ምድር ላይ በሊቀ መልአክ ሩፋኤል አምሳል ነበርኩኝ እያለ ቢቀላምድም ተከታዮችን ከማፍራት የከለከለው ነገር አልነበረም። ይሁን እንጂ ይህ የዘመኑ ቀሳጢ እንኳን ለሌሎች ሊተርፍ ይቅርና ለራሱም መሆን ሳይችል ቀርቶ በጉሮሮ ህመም ሲሰቃይ ቆይቶ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

ክሪሽና ቬንታ (1911-1958)

 ቬንታ በሳንፍራንሲስኮ የተወለደው ሲሆን በሁለተኛው ዓለም ጦርነት የአሜሪካ ወታደር በመሆን አገልግሏል። ከተመለሰም በኋላ ቀደም ሲል አቋቁሞት የነበረውን ተቋም በማንቀሳቀስ 1948 ዓ/ም «የጥበብ፤ የእውቀት፤ የእምነትና የፍቅር ፏፏቴ» የተሰኘ የክህደት ድርጅት ሥራውን ጀምሯል። ቬንታ የክህደት ደረጃውን በማሳደግ «እኔ ኢየሱስ ነኝ» ከማለቱም ባሻገር የማኅበሩ አባል ለሚሆኑ ሰዎች «ያላችሁን ሀብትና ንብረት ለማኅበሩ ገቢ አድርጉና ሰማያዊ መዝገብ አከማቹ» በማለት ሀብታቸውን በመሰብሰብ ለበጎ አድራጎት ሥራ ለማዋል የሞከረ ቢሆንም ሀብታቸውን ተሞልጨው፤ ሚስቶቻቸውን በቬንታ የማማገጥ ተግባር የተፈጸመባቸው ሁለት ተከታዮቹ በቂም በቀል ተነሳስተው ቦንብ በማፈንዳት አብረው ሊሞቱ ችለዋል። የክሪንሽና ቬንታ የክህደት ተግባርም እስከወዲያኛው በዚያው አክትሟል።

አህን ሳንግ ሆንግ (1918- 1985)

 በደቡብ ኮሪያ የተወለደ ይህ ሰው  በ1964 ዓ/ም «የአዲስ ኪዳን ፋሲካ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን» የሚል የሃይማኖት ተቋም መስርቶ ነበር። በኋላ ላይ ደግሞ «ዓለም አቀፍ የተልእኮ ማኅበር የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን»  የሚል ሁለተኛውን ድርጅት አቋቁሟል። ሳንግ ሆንግ እሱ የኢየሱስ ዳግም ምጽአት ምልክት መሆኑን ይሰብክ ነበር። በአዲስ ኪዳን ፋሲካ ቤተ ክርስቲያኑ እንደመምህር ሲቆጠር በዓለም አቀፍ የተልእኮ ቤተክርስቲያኑ ደግሞ እንደእግዚአብሔር ይቆጠራል።  የቤተክርስቲያኒቱ ዋና አመራር የሆነችው ዛንግ ጊልጃህ የተባለችው ሴት በገላትያ 4፤26 ላይ የተመለከተውን ትንቢት የምታሟላ እሷ ናት ስለሆነች «የኢየሩሳሌም እናት» ወይም «የእግዚአብሔር እናት» ተብላ ትጠራለች።
የቤተ ክርስቲያኑ መሥራች ሳንግ ሆንግ ደግሞ «እግዚአብሔር አብ» ተብሎ ይጠራል።


ሱን ሚዩንግ ሙን (1920- 2012)


 በሰሜን ኮሪያ ተወልዶ በደቡብ ኮሪያ ያደገው ሙን «የውህደት ቤተ ክርስቲያን» መሥራች ሲሆን ራሱን ሁለተኛው ኢየሱስ እንደሆነና  ከዚህ ቀደም ኢየሱስ በሥጋ ተገልጦ ሳለ ሳይጨርሳቸው የሄደውን ጉዳይ የሱ መገለጽ ማስፈለጉን በአደባባይ የሚናገር ሰው ነበር። ሚስተር ሙን ባለቤቱን « ሃክ ጃን ሃን»ን የሚጠራት አዳምና ሔዋን ያበላሹትን ዓለም በማጽዳት መልካም ቤተሰብን በዓለም ላይ ለመመሥረት የተፈጠረች ናት በማለት ያሞካሻት ነበር። ሙን «የተባረከ የኅብረት ጋብቻ» በሚል ዘመቻ በአንድ ቀን እስከ 30 ሺህ የሚቆጠሩ ጥንዶችን  አሜሪካ ባለችው በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ጋብቻ በማስፈጸም ዝናው ይታወቃል። ሙን በአሜሪካን ሀገር ሳለ በፈጸመው የታክስ ማጭበርበር ወንጀል ተከሶ 18 ወራት ተወስኖበት፤ ከዚህ ውስጥ የ13 ወራት እስራቱን ቅሞ በአመክሮ ሊለቀቅ ችሏል። ሱን ሙን  ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ ሃብት ያለው ሲሆን የተለያዩ ኮርፖሬሽኖችንና የአክሲዮን ማኅበራት አሉት። ሃሳዊው ሙን በተወለደ በ92 ዓመቱ በኒሞንያ በሽታ ሞቶ እስከወዲያኛው ተቀብሯል። እሱ ቢሞትም በሱ የሀሰት ትምህርት የተታለሉ 4 ሚሊዮን አባላት በተለያዩ የዓለም ሀገራትን ለማፍራት ችሏል።

ይቀጥላል%

Wednesday, September 10, 2014

በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ!



እኛ ነን ወደአዲሱ ዓመት የደረስነው ወይስ ዘመኑም እንደእኛው እየሄደ ነው? 

  ቆሞ የሚጠብቅ ዘመን የለም። ዘመኑም እኛም በዘመኑ ውስጥ እየሄድን ነው። እግዚአብሔር በዓመት፤ በዓመቱ የሚሰራው አዲስ ዘመን የለም። እግዚአብሔር ዘመናትን የሠራው አንድ ጊዜ ነው።  በእግዚአብሔር አስቀድሞ የተሠራው ዘመን በራሳችን እድሜ ላይ ሲቆጠር «አዲስ ዘመን» ከማለታችን በስተቀር ዘመኑም ለማለቅ ራሱ ወደእርጅና እየተጓዘ ነው።  ሰውም ዘመናትም የማለቂያ እድሜ አላቸው። ዘመናት የተሠሩት፤ ለሰው ልጆች አገልግሎትና የእግዚአብሔርን ፈቃድ አውቀው መልካሙን ሁሉ ይሠሩባቸው ዘንድ ነው። እንኳን «ለአዲሱ ዘመን አደረሰን!» ስንል እኛ በዘመን ውስጥ መታደሳችንንና መለወጣችንን መናገራችን ነው። እንደዚያ ካልሆነማ ዘመናት የተሠጣቸውን ግዳጅ እየፈጸሙ ወደተሰጣቸው እርጅና እየሄዱ እንጂ መቼ ቆመው ይጠብቁናል? ክረምትና በጋ፤ ብርሃንና ጨለማ፣ ዘርና ማዕረርን ዘመናት ከመስጠት አለማቆማቸውና በዘመን ስሌት መፈራረቃቸው እስከጊዜው የተሰጣቸውን ግዳጅ እየተወጡ መሆናቸውን ልብ ልንል ይገባል። እድሜአቸው አልቆ እስኪጠቀለሉም ይህንኑ ግዳጃቸውን ይወጣሉ። 

  መዝ 102፤25-26 «አቤቱ፥ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ፥ ሰማያትም የእጅህ ሥራ ናቸው። እነርሱ ይጠፋሉ፥ አንተ ግን ትኖራለህ ሁላቸው እንደ ልብስ ያረጃሉ፥ እንደ መጐናጸፊያም ትለውጣቸዋለህ፥ ይለወጡማል»

ሐዋርያው ጴጥሮስም በመልዕክቱ አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደምንጠባበቅ መናገሩ አሁን ያለን ሰማይና የምንኖርባት ምድር አርጅተው እንደሚለወጡ በግልጽ ያስረዳናል።

2ኛ ጴጥ 3፥13 «ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን»

 ስለዚህ በዘመን ውስጥ በእድሜ ጣሪያ የምንጓዝ እኛ የሰው ልጆች ምን ማድረግ ይገባናል?
በጎ መመኘት በጎ ነው። በጎ መመኘት ብቻውን በጎ ነገር አያመጣም። የተመኘነውን በጎ ነገር ለመሥራት በጎ ጥረት ያስፈልገናል። አዲስነት ከእኛነታችን ውጪ የሚገኝ አይደለም። ዘመን በተቆጠረ ቁጥር «እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሳችሁ» መባባሉ ጥሩ ቢሆንም ባልተለወጠ ማንነታችን ውስጥ ምን አዲስ ለውጥ አይመጣም። መታደስ፤ መለወጥ ለሰው ልጆች ማንነት ልዩ ግኝት ስለሆነ መለወጥ ያለብን እኛ ነን።

 ቁጡና ቂመኛ ሆነን ስለአዲሱ ዘመን ማውራት ምን ይጠቅማል? በውሸትና በቅድስና ጉድለት እየኖርን ከጉዞው ጨብጠን ልናስቀረው ስለማንችለው አዲስ ዘመን መልካምነት መመኘት በራሱ የሚጨምርልን አንዳች ነገር የለም።
ይልቁንስ ሐዋርያው ጳውሎስ የተናገረውንና ሁልጊዜ እያነበብን ለመተግበር የተቸገርነውን በጎ ነገር እየፈጸምን ስለአዲስ ዘመን በጎ ምኞት እናስብ። 

 «በእርግጥ ሰምታችሁታልና፥ እውነትም በኢየሱስ እንዳለ በእርሱ ተምራችኋል፤ ፊተኛ ኑሮአችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ፥ በአእምሮአችሁም መንፈስ ታደሱ፥ ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ። ስለዚህ ውሸትን አስወግዳችሁ፥ እርስ በርሳችን ብልቶች ሆነናልና እያንዳንዳችሁ ከባልንጀሮቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ። ተቆጡ ኃጢአትንም አታድርጉ፤ በቁጣችሁ ላይ ፀሐይ አይግባ፥ ለዲያብሎስም ፈንታ አትስጡት። የሰረቀ ከእንግዲህ ወዲህ አይስረቅ፥ ነገር ግን በዚያ ፈንታ ለጎደለው የሚያካፍለው እንዲኖርለት በገዛ እጆቹ መልካምን እየሠራ ይድከም። ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ። ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ። መራርነትና ንዴት ቁጣም ጩኸትም መሳደብም ሁሉ ከክፋት ሁሉ ጋር ከእናንተ ዘንድ ይወገድ። እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ»  ኤፌ 4፤21-32

አለበለዚያ ዘመን ካልሰራንበት «እንኳን አደረሳችሁ ሲባባሉብኝ ጊዜያቸውን በከንቱ ፈጸሙ\ ብሎ በኋለኛው ቀን እንዳልሰራንበት ይመሰክራል።
«ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፥ የሰማይም ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል» ስለዚህ ንስሐ እንግባ፤ በልባችንም መታደስ እንለወጥ! ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን!

Saturday, September 6, 2014

በምድራችን ላይ በክፉ መንፈስ ተነድተው ሕዝብን ያሳሳቱ ሀሰተኛ ክርስቶሶችና ነብያት!


አን ኤልዛቤጥ  ሊ (1736-1784)
በእንግሊዝ አገር የተነሳችና «ተንቀጥቃጮች» የተሰኘ ሃይማኖት የፈለሰፈች፤ ተከታዮቿም «እናታችን» እያሉ የሚጠሯት ሀሳዊ ክርስቶስ ሆና ተነስታ ነበር። ስታስተምርም ራሷን የምትገልጸው እኔ በሴት መልክ የተገለጥኩ ሁለተኛው ኢየሱስ ነኝ እያለች ብትሰብክም እንኳን ለሌላው ልትተርፍ ይቅርና እራሷን ማዳን ሳትችል ቀርታ እስከምጽአት የመጨረሻውን ፍርድ ድረስ ላትነሳ ሞታ በድንጋይ ታትማለች።


        **************************************************


ጆን ኒኮላስ ቶም (1799-1838)
በእንግሊዝ ሀገር ኮርንዎል ተወልዶ ያደገና  የወይን ነጋዴ ሆኖ ሲሰራ የቆየ ሰው ነው። በሥራውም ላይ በታክስ ማጭበርበር ተከሶ እንደነበር የህይወት ታሪኩን የመዘገበው የኮርንዎል ቤተ መዛግብት ፋይል ያስረዳል። ቶም ሽቅርቅርና መዓዛው በሚያውድ ሽቶ ልብሱን ነክሮ፤ ጢሙን አሳድጎ የሚዞር ሰው ሲሆን የብዙዎችንም ቀልብ መሳብ የቻለ ነበር። ቶም ከወይን ነጋዴነት፤ ከጋዜጣ አዘጋጅነትና ገበሬዎችን ከአነስተኛ ንግድ ባለቤቶች ጋር በጥምረት የዐመጽ መሪነት ድረስ ሲ,ሰራ ቆይቷል። የሕይወት ስኬት ሲጎድለው ከእለታት አንድ ቀን ድንገት ተነስቶ «ሁለተኛው ኢየሱስ ሆኜ በሥጋ ተገልጫለሁ» በማለት ወደስብከት የገባ ሲሆን ተከታዮችን ካፈራ በኋላ በ1834 ዓ/ም ጀምሮ ወደቅዱስ መንፈስ ተቀይሬአለሁ ቢልም ባልተላቀቀው የዐመጽ መሪነቱ ተግባሩ ቀጥሎ በግንቦት 31/1838 ኬንት ከተማ ላይ በጥይት ተገድሎ እስከወዲያኛው ላይነሳ ያሸለበ ሰው ነው።

**************************************************


አርኖልድ ፖተር (1804-1872)
«የኋለኛው ቀን ቅዱሳን» የተባለው የክርስትና ክፍል መሪ የነበረ ሰው ነው። ፖተር በኒውዮርክ ተወልዶ፤ በኢንዲያና ውስጥ በኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለ ቤተ ክርስቲያን የተጠመቀ ሲሆን በኢሊኖይስ ላይ ደግሞ የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን መሥራች በሆነው በጆሴፍ ስሚዝ «ካህን፤ ሽማግሌና የቡራኬ አበው» ተብሎ ደረጃ በደረጃ የተሾመ ሰው ነበር። እስከአውስትራሊያ ድረስ ለስብከት የተጓዘው ፖተር «የኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ በኔ ውስጥ በመግባቱ ከዛሬ ጀምሮ እኔ ሌላው ኢየሱስ ነኝ» እያለ ሲያስተምርና ተከታዮችን ሲያፈራ ቆይቷል። በኋላ ላይ ወደካሊፎርኒያ ተመልሶ በ1872 ዓ/ም ወደሰማይ የማርግበት ሰዓት ደርሷል በማለት የአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ከገደል አፋፍ ላይ በደመና ለማረግ ሲጋልብ ወደላይ መውጣቱ ቀርቶ ቁልቁል እስከነ አህያዋ በመምዘግዘግ  ፖተር ዳግም ላይመለስ እስከወዲያኛው አሸልቧል።

         **************************************************

ጆንስ ቬሪ 1813-1880
 ፀሐፊ ተውኔት፤ ገጣሚና በሐርቫርድ የግሪክ ቋንቋ መምህር የነበረ ሰው ነው። ቬሪ እጅግ የጠለቀ እውቀትና ሙያ ያለው ሰው ቢሆንም ከእለታት አንድ ቀን  ለተማሪዎቹ «በማቴዎስ 24 ላይ ዳግም ይመለሳል የተባለው ኢየሱስ እኔ ነኝ» በማለት የተናገረ ሲሆን ይህንኑ ስብከቱን ቀጥሎበት ቀይቷል። በኋላ ላይ  በአእምሮ በሽታ ክፉኛ በመጠቃቱ ለከፍተኛ ጭንቀት ህመም ተጋልጦ  እህቱ እሱን የማስታመም ኃላፊነት ወድቆባት ነበር።  ቬሪ «ኢየሱስ ነኝ» እያለ ቢሰብክና ብዙዎችንም ቢያታልል ከአእምሮው በሽታ ሳይድን  በ1880 ዓ/ም በተወለደበት በማሳቹሴትስ ሞቶ በትልቅ ሃውልት መቃብሩ ተደፍኖ ዛሬ ድረስ ይታያል።




******************************************



ባሃ ኡላህ (1817-1892)
የእስልምናው አንዱ ክንፍ ከሆነውና በዛሬይቱ ኢራን ያለው የሺአይት እስላም ቤተ ሰብ የተወለደው ባሃኡላህ በዚሁ እምነት ስር ያደገ ሲሆን ሃይማኖታዊ ፍልስፍናው በፈጠረበት ስሜት ተነሳስቶ ዓለም በአንድ እምነትና መተሳሰብ ስር መጠቃለል አለባት ብሎ በመነሳት ራሱን «የባቢ እምነት» ፍጻሜ ነብይ አድርጎ በመቁጠር ከሺአት ተገንጥሎ በስሙ የባሃኡላህ እምነትን የመሠረተ ሰው ነው። ትምህርቱንም በባግዳድ ጀምሮ በእስልምና ህግ ተይዞ በሃይፋ/ እስራኤል/ እስከተሰቀለበት ቀን ድረስ እኔ የመጨረሻው የእግዚአብሔር ነብይ ነኝ፤ በኋለኛውም ቀን ለፍርድ እመጣለሁ ሲል የነበረ ሰው ነው። ይህ የሃይፋው ዋናው የባሃኢ እምነት ማእከል በዓለም ላይ ላሉ የእምነቱ ተከታዮች ቅዱስ ስፍራ ሲሆን አጠቃላይ መመሪያው የሚመነጨው ከዚሁ ከሃይፋው ማእከል ነው። 
 እግዚአብሔር ራሱን በሰው አምሳል ከገለጸባቸው መንገዶች አንዱ ባሃኡላህ ሲሆን የሰዎችን ነፍስ በማጥራት ምድርን ወደገነት የመቀየር ተልዕኮ ያነገበ እሱ ብቻ መሆኑን ሲሰብክ ቆይቷል። ባሃኢዎች እንደመንፈስ አባታቸው ሲዖልና ገነት ተብለው በሰዎች አእምሮ የተሳሉ ግምቶች እንጂ በእውን ሰዎችን ለመቅጫ በእግዚአብሔር የተፈጠሩ አይደለም ይላሉ። ባሃኡላህ የሞተው በ1892 በስቅላት ነው።
ሃይፋ/እስራኤል የባሃኢ ዋና ማእከል


*******************************************


ዊሊያም  ዳቪየስ (1833-1906)
የሞርሞን ቤተ ክርስቲያን ቅርንጫፍ በሆነውና የኋለኛው ቀን ቅዱሳን በተባለው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መሪ የነበረ ሰው ነው። በደቡብ የዋሽንግተን ስቴት ዋላዋላ ከተማ ላይ «የእግዚአብሔር መንግሥት» ማኅበርን መስርቷል። ተከታዮቹንም «እኔ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚካኤል ነኝ» በማለት ያስተማረ ሲሆን «አዳም፤ አብርሃም፣ ዳዊት» ሆኖ ከዚህ በፊት በምድር ላይ የመጣውም እሱ ራሱ መሆኑንም በድፍረት ይናገር ነበር። በኋላ ላይ ሚስት አግብቶ በየካቲት 11/1868  «አርተር» የተባለ ልጁን እንደወለደ  ልጁን «በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ» ነው በማለት ሲናገር «ዴቪድ» የተባለ ሁለተኛ ልጁን ሲወልድ ደግሞ እኔ ወደ «እግዚአብሔር አብነት» ተቀይሬአለሁ እያለ ይሰብክ ነበር። ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ ሁለቱም ልጆቹ በጉሮሮ በሽታ ሲሞቱ ተከታዮቹ ባቀረቡበት ክስ የቤተ ክርስቲያኑን ንብረት ሸጦ በመክፈልና ከተማውን ለቆ ወደካሊፎርንያ በመሰደድ መልሶ ለመደራጀት ሞክሮ ሳይሳካለት ልጆቹን እንደቀበረ ሁሉ እሱም ሞቶ ድንጋይ ተጭኖት ይገኛል።



 ይቀጥላል%

Saturday, August 30, 2014

ስለመላእክት ያለው አስተምህሮ ምን ይመስላል?




(ክፍል አንድ)

በዓለማችን ላይ ባሉ በኦርቶዶክሳዊያንና በካቶሊካዊያን  ቤተ እምነቶች ውስጥ  ከሰማያውያን ፍጥረቶች ውስጥ መላእክት በእምነት ህግጋቶቻቸው ከፍተኛውን ስፍራ ይዘው ይገኛሉ።  እንደጥንታውያኑ ቤተ እምነቶች አይሁን እንጂ በወንጌላውያን ቤተ እምነቶችም ውስጥ ከተወሰኑቱ በስተቀር ስለመላእክት ያላቸው እምነትና እውቀት ጥቂት አይደለም።   የሰው ልጆች ስለቅዱሳን መላእክት ያለን እውቀት ከፍ እንዲልና ትኩረት እንድንሰጥ የሚያደርገን ምክንያት መኖሩ እርግጥ ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችንም ስለመላእክት ምንነትና ተግባር  በብዙ ቦታ ላይ ጠቅሶ የሚገኘው ያለምክንያት ባለመሆኑ በዚያ መነሻነት ስለመላእክት ያለን ግምት ከፍ ቢል የሚያስደንቅ አይሆንም። እግዚአብሔር በቅዱስ ቃሉ ውስጥ ይህንን ዓይነት መልእክት ማስቀመጡም ስለመላእክት ያለን ግንዛቤ እንዲያድግ ስለፈለገ በመሆኑ ዘወትር ቃሉን በማንበብ እንመረመራለን። መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን መገለጥም ስለመላእክት ያለን እውቀት ከፍ ይላል። ምክንያቱም በሰው ልጆችና በመላእክት መካከል ያለው ግንኙነት እጅግ የጠበቀ በመሆኑ ስለመላእክት ማወቁ እጅግ ጠቃሚ ነው።
      በተመሳሳይ መልኩም ስለመላእክት ያለን እምነትና በቅዱስ ቃሉ ላይ ያልተመሠረተ እውቀት እንደዚሁ የሚኖረንን ግንኙነት ከማበላሸቱም በላይ የሰው ልጆችንም ይሁን መላእክትን በፈጠረው በእግዚአብሔር ላይ ያለንን የአምልኰ መንገድ ከመስመሩ ሊያወጣ ስለሚችል እጅግ ብርቱ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ነገር መሆኑም ሊሰመርበት ይገባል። የአምልኰ ስህተት እንደጊዜያዊ እክል የማይታይና በቀላሉ ሊታረም እንደሚችል የሚታሰብ ባለመሆኑ ስህተቱ ዘላለማዊነት ባላት በነፍስ ላይ ዘላለማዊ ዋጋን የሚያስከፍል ጉዳይ ስለሆነ እጅግ ብርቱ ጥንቃቄ ሊደረግበት ይገባል። 
  ስለሆነም  የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት ባደረገ መልኩ ስለመላእክት ያለን እውቀት መልካም የመሆኑን ያህል ቃሉን በሳተ መንገድ ያለን እውቀትም በተቃራኒው የጎደለ ከሆነ ጎጂነቱ የከፋ መሆኑን ለማስገንዘብ እንዲቻል በተለያየ አቅጣጫ ስለመላእክት የሚሰጠውን ትርጉምና የእምነት አስተምህሮን በተመለከተ ቅዱስ መጽሐፍን ዋቢ በማድረግ ለማሳየት እንሞክራለን።

1/ ስለመላእክት ማወቅ ለምን አስፈለገ?

እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ያስተምረናል።  የቃሉ ምንጭ በሆነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለመላእክት እግዚአብሔር በብዙ ቦታ ተናግሯል፤ ተግባራቸውንም በተወሰነ መልኩ አሳይቶናል። እግዚአብሔር በቃሉ የሚነግረን ለእኛ እንዲበጀን ስለሆነ ስለመላእክት እንድናውቅለት ይፈልጋል ማለት ነው። በመሆኑም ስለመላእክት ማወቅ ያስፈለገን እግዚአብሔር በቃሉ አማካይነት ስለመላእክት እንድናውቅ ስለነገረን  ነው። ስለመላእክት ማንነትና ተግባር የነገረንን ካወቅን እግዚአብሔር ለምን እንደፈጠራቸው እንረዳለን። በዚህም የተነሳ ስህተት ላይ ከመውደቅ እንጠበቃለን። ስለመላእክት ነግሮን ሳለ በእኛ ስህተት የተነሳ ከእውቀት ብንጎድል እግዚአብሔር ስላልነገረን ሳይሆን ቃሉን ለመስማት ካለመፈለጋችን የተነሳ ይሆናል ማለት ነው። ማንም ስህተትን ቢያደርግ በተሰጠው ቃል መሠረት ተጠያቂነት አለበት። ስለሆነም ከተጠያቂነት ለመዳን ስለመላእክት ማንነት ማወቅ ያስፈልገናል። ችግሩ ስለመላእክት ያለን ስህተት የሚነሳው እግዚአብሔር በቃሉ ከተናገረው ውጪ የራሳችንን ግምትና ስሜት ስንጨምርበት ነው። ስለዚህ በዚህ ጽሁፍ የሚዳሰሰው ክርስቲያኖች ሁሉ በእጃቸው የያዙትን መጽሐፍ ቅዱስ ዋቢ በማድረግ ነው። ሌላ የትኞቹም ስለመላእክት የተጻፉ አስረጂዎች መነሻቸው ወይም መለኪያቸው ቅዱሱ መጽሐፍ ከሆነ ስለመላእክት የሚኖረው እውቀት ያልተዛነፈ ይሆናል።
«ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል አንተም እውቀትን ጠልተሃልና» ሆሴዕ 4፤6 እንዳለው እንዳንጠፋ ስለመላእክት ማንነትና ምንነት ማወቅ አለብን።

2/ የመላእክት ተፈጥሮ

የመላእክትን ተፈጥሮ በተመለከተ በመጽሐፍ ቅዱስ  ሰፊ የሆነ ማብራሪያ አይሰጠንም።    ያ ማለት ግን ስለመላእክት ተፈጥሮ ለአማኞች የሚበቃ ትምህርት የለውም ማለት አይደለም። በመሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ የዘመን መነሻና ፍጻሜ ከሌለው ከእግዚአብሔር እውቀት ውስጥ ለሰው ልጅ በሚመጥነው መልኩ የተሰጠው ቃል በመሆኑ ብዙ ማብራሪያ መስጠት አይጠበቅበትም። በዮሐንስ ወንጌል ላይ መጽሐፍ ቅዱስ ዓለም ራሷ ሰሌዳ፤ ውቅያኖሶች ሁሉ የብርዕ ቀለም ቢሆኑ መያዝ እንደማይችሉ ያስረዳናል።
ዮሐ 21፥25 «ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል»
ስለዚህ የመላእክትን ማንነትና ተፈጥሮ ለማወቅ መጽሐፍ ቅዱስ የነገረንን ይዘን እየተማርን፤ ያልነገረንን ደግሞ በእምነት እንደተነገረን ያህል ተቀብለን እንጓዛለን እንጂ ያልተነገረውን ለመናገር የግድ የራሳችንን ስሜቶችና ፍላጎቶች በመናገር በማንወጣው አዘቅት ውስጥ ገብተን አንዳክርም። «ለጠቢብሰ አሐቲ ቃል ትበቍዖ» እንዲሉ።
 ስለዚህ መላእክት በቁጥር ስንት ናቸው? አፈጣጠራቸው እንዴት ነው?  ሥልጣናቸው?  ስማቸው? ወዘተ የተመለከተውን ነጥብ ከተወሰኑት በስተቀር  መጽሐፍ ቅዱስ ዝም ስላለ እኛም ዝም እንላለን እንጂ  መጽሐፍ ቅዱስ ያልጠራቸውን በጕስአተ ልብ አንጠራቸውም።  ይልቅስ መጽሐፍ ቅዱስ የነገረንን መረጃ እንመልከት። በመዝሙረ ዳዊት ላይና በዕብራውያን መልእክት ላይ የተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ስለመላእክት ተፈጥሮ  ያስተምረናል።
መዝ 104፥4  «መላእክቱን መንፈስ የሚያደርግ፥ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል»
 ዕብ 1፥7 «ስለ መላእክትም። መላእክቱን መናፍስት አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል የሚያደርግ» ይላል።
ከዚህ የእግዚአብሔር ቃል ተነስተን መላእክቱ መንፈስና የእሳት ነበልባል መሆናቸውን እንረዳለን።  መናፍስትም፤ የእሳት ነበልባልም ያደረጋቸው እግዚአብሔር ነው። እነዚህ መንፈሳውያንና እሳታውን መላእክት ከፍጥረታት መካከል አንዱ ክፍል ናቸው ማለት ነው። መላእክቱ መናፍስት (ረቂቃን) እና እሳታውያን  መሆናቸው የሚያሳየን ነገር ቢኖር እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በፈጠረበት መንገድ አልፈጠራቸውም ማለት ነው። መንፈስም፤ እሳትም በመሆናቸው  መላእክት እንደሥጋውያን  እርጅናና ሞት አያገኛቸውም።
ኢዮብ 34፥15 «ሥጋ ለባሽ ሁሉ በአንድነት ይጠፋል፥ ሰውም ወደ አፈር ይመለሳል» እንዳለው።
በሌላ ቦታም  መላእክት ሕያው መንፈሳዊ ፍጥረታት መሆናቸውን ቅዱስ ቃሉ ሲነግረን፤ ሥጋውያን የሆንን  እኛ ትንሣዔ ሙታን እንደማይመለከታቸው እንደመላእክት እንደምንሆን ተነግሮናል።
ማር 12፥25  «ከሙታንስ ሲነሡ በሰማያት እንዳሉ መላእክት ይሆናሉ እንጂ አያገቡም፥ አይጋቡምም»
    ስለመላእክት አፈጣጠር የሚናገር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ  በተለምዶ «አክሲማሮስ» ወይም  በመጠሪያው «ሔክሳሄሜሮስ» የተባለ መጽሐፍ አለ። በስድስት ቀን ውስጥ እግዚአብሔር ስለፈጠራቸው ሃያ ሁለቱ ስነፍጥረታት አመጣጥ የተነገረበት ይህ መጽሐፍ በዘፍጥረት መጽሐፍ ላይ ያልተነገረውን  በዝርዝር ይተርካል።  በጽርዕ ቋንቋ «ሔክሳ» ማለት «ስድስት» ማለት ሲሆን «ሄሜር» ማለት «ቀን» ማለት ነው። ይህም የስድስቱ ቀናት ሥነ ፍጥረትን ለማመልከት የገባ ቃል ነው።  ሔክሳ ሄሜሮስን የበረሺት መጽሐፍ ባለቤቶች የሆኑቱ  ዕብራውያን የማያውቁትን ይህን ከ4ኛው ክ/ዘመን በኋላ የተጻፈውንና ስለሥነ ፍጥረት የሚናገረውን መጽሐፍ መጠቀም ሳያስፈልግ እግዚአብሔር በቅዱስ ቃሉ በገለጠው በመጽሐፍ ቅዱስ  ብቻ መላእክት ሞት የማያገኛቸው፤ እሳታውያንና መንፈሳውያን ፍጥረቶች ናቸው ብሎ አፈጣጠራቸውን በአጭር ቃል መግለጽ ይቻላል።

3/ የመላእክት ጠባይና ግብር

ከላይ ባነሳናቸው ርእሶች ላይ ስለመላእክት ማወቅ የሚገባንን ምክንያትና የመላእክትን ተፈጥሮ ከተረዳን ዘንዳ በቀጣይነት ሥራቸውን ልናውቅ ይገባል። ይህም ማንነታቸውንና ከሰው ልጆች ጋር ያላቸው ግንኙነት ምን እንደሆነ እንድናውቅ ያግዘናል። በዚህ መጠይቃዊ ርእስ ስር የሚካተቱ ንዑስ ርእሶች አሉን።

        ሀ/ የመልአክ ስማዊ ትርጉም 

ቁጥራቸውን ብዙ መሆኑን ለማመልከት «መላእክት» የምንላቸው ፍጥረቶች በነጠላ  ስያሜ «መልአክ» ስንል ምን ማለታችን ነው? የሚለውን መረዳት ይገባናል። ይህም የመላእክትን ሥራ ለማወቅ ይጠቅመናል። ሥራቸውን ካወቅን መላእክት ከእኛ ጋር እኛም ከመላእክቱ ጋር ያለንን ግንኙነት ለመለየት ያግዘናል። ያለበለዚያ ከላይ ስናነሳ የቆየንባቸው የማወቅ እድላችን እርስ በእርሱ ይምታታና ባለማወቅ ውስጥ ሆነን የምናውቅ ሊመስለን ይችላል። ይህም ትልቅ ጉዳት ያስከትላል።
 አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ (በማኅበረ ቅዱሳን ተሃድሶ ተብለዋል) «መጽሐፈ፡ሰዋስው፡ወግስ፡ወመዝገበ፡ቃላት፡ሐዲስ» በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 549 ላይ እንዲህ ሲሉ  ስለ«መልአክ» ግሳዊ ትንታኔን  አትተዋል።
ድርጊቱን ሲገልጡልን «ልኢክ፤ ልኢኮት(ለአከ፤ይልእክ) መላክ፤መስደድ»  ማለት  እንደሆነ በመግለጽ አድራጊውን ሲነግሩን «ለአኪ ማለት ላኪ ወይም ሰዳጅ ማለት ነው ይሉናል። ተደራጊውን ደግሞ «መልአክ ማለት በቁሙ ሹመኛ፣ አለቃ ሲሆን  የእግዚአብሔር መላእክቶችን  ነጠላ የወል ስም  «መልአክ» የሚለው እንደሚወክል ያብራሩልናል።
በሌላ ቦታም የሰባ ሊቃናት ትርጉም እንደሚያስረዳን «ἄγγελος» የሚለው የልሳነ ጽርዕ ትርጉም «ኤንጄሎስ» ማለት «መልእክተኛ» ማለት እንደሆነ እናገኛለን። ዕብራይስጡም «מלאך אלהים » «ሜሌኽ ኤልሂም» ይለዋል። የእግዚአብሔር መልዕክተኛ ማለት ነው።
 ከዚህ የትርጉም  ጽንሰ ሃሳብ የምንረዳው መላእክት ማለት የሚላኩ፣ የሚታዘዙ ፍጥረታት ሲሆኑ ላኪያቸው ወይም ሰዳጃቸው የፈጠራቸው እግዚአብሔር ነው ማለት ነው።  ስለዚህ መልአክ ማለት የሚላክ፤ የሚታዘዝ፤ ተላኪ፤ አገልጋይ፤ አመስጋኝ ማለት ነው።  የአለቃ ኪዳነ ወልድ ትርጉም ከጽርዑና ከዕብራይስጡ ጋር ይስማማል። 

     ለ/ መላእክት በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት ይችላሉን?

መላእክት ፍጡራን ናቸው ካልን ከፍጡርነት ባህርይ አንጻር ውሱንነት መኖሩ እርግጥ ነው። በዚያ ላይ የሚላኩ፤ የሚታዘዙ፤ አገልጋዮች መሆናቸው በራሱ መነሻና መድረሻ እንዳላቸው ያሳያል። መልእክት ከሚቀበሉበት መንበረ ጸባዖት ተነስተው ከሚደርሱበት የተልእኰ ሥፍራ ድረስ መውጣትና መውረድ አለባቸው ማለት ነው።  መላእክት የሚወጡበትና የሚወርዱበት መሰላል የእግዚአብሔር ኃይል እንደመሆኑ መጠን መላእክቱን የፈጠረ አምላክ እንዲህ ሲል ይነግረናል።
ዮሐ1፥52  «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ አለው»
በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃት ስለሌላቸው የመውጣትና የመውረድ አገልግሎት ይፈጽማሉ ማለት ነው። መላእክቱ ከታዘዙበት ሲወጡ ከነበሩበት ሥፍራ  ለቀው ወደሌላ ሥፍራ ይሄዳሉ። ስለዚህ  ለቀው ከወጡ በኋላ በምስጋና ከተማቸው ውስጥ በመልአካዊ ባህርያቸው አይገኙም ማለት ነው። ከተልእኮአቸውም ሲመለሱ ከፈጸሙበት ሥፍራ ወደቀድሞ ቦታቸው ይመለሳሉ እንጂ በምስጋና ከተማቸውም ሆነ በተልእኰ ስፍራቸው በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃት የላቸውም። ይህንን በደንብ የሚገልጽን የትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ነው።
አንድ ስሙ ያልተገለጸ የእግዚአብሔር መልአክ በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ ሳለ ወደነብዩ ዳንኤል በተላከ ጊዜ የፋርስ መንግሥት አለቃ (የፋርስ መንግሥትን የያዘ ተቃዋሚ መንፈስ ማለት ነው) ከተላከው መልአክ ጋር ለ21 ቀናት በመዋጋት ከዳንኤል ዘንድ ቶሎ እንዳይደርስ አግዶት ነበር። በኋላም ቅዱስ ሚካኤል ሊረዳው ከመጣ በኋላ ከሌሎች የፋርስ መንግሥታት መናፍስት ጋር ሚካኤልን በዚያ ትቶት ወደተልእኰ ሥፍራው ወደ ነብዩ ዳንኤል መሄዱን ይነግረናል።
ዳን 10፤12-14  «እርሱም እንዲህ አለኝ። ዳንኤል ሆይ፥ አትፍራ ልብህ ያስተውል ዘንድ፥ ሰውነትህም በአምላክህ ፊት ይዋረድ ዘንድ ካደረግህበት ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ቃልህ ተሰምቶአል እኔም ስለ ቃልህ መጥቻለሁ። የፋርስ መንግሥት አለቃ ግን ሀያ አንድ ቀን ተቋቋመኝ እነሆም፥ ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ እኔም ከፋርስ ነገሥታት ጋር በዚያ ተውሁት። ራእዩም ገና ለብዙ ዘመን ነውና በኋለኛው ዘመን ለሕዝብህ የሚሆነውን አስታውቅህ ዘንድ አሁን መጥቻለሁ»
 (የፋርስ መንግሥት አለቃ ማለቱ በፋርስ መንግሥት ላይ አድሮ ዳንኤልንና ወገኖቹን የሚዋጋው መንፈስ አለቃ ማለት ነው) የዚህን እንዴትነት ወረድ ብለን በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ እንመለከታለን።
ነገር ግን ከላይኛው ጥቅስ ውስጥ የምንረዳው ቁም ነገር፤
የተላከው መልአክ ለ21 ቀናት በውጊያ ላይ በመዘግየቱ ወደተላከበት ሥፍራ ለመድረስ አለመቻሉ፤
 * ሚካኤል ለእርዳታ ከመጣለት በኋላ ወደዳንኤል ከመሄዱ በስተቀር  ከሚካኤል ጋር በውጊያውም እየተሳተፈ፤ ወደዳንኤልም መልእክት እያደረሰ ባንድ ጊዜ በሁለቱም ሥፍራ አለመገኘቱ የመላእክትን ውሱንነት ይገልጥልናል።
«ሚካኤልን በዚያ ተውኩት» ማለቱ የነበረበትን ሥፍራ ለቆ መሄዱን ይገልጣል። ስለዚህ መላእክት በሁሉም ሥፍራ አይገኙም። መእክተኛ እንደመሆናቸውም መጠን ሳይላኩ አይሄዱም።  በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ መገኘት /Omnipotent/ የእግዚአብሔር የብቻው ባህርይ ነው።
መላእክት የእግዚአብሔር ፍጥረት እንደመሆናቸው መጠን ሁሉን የማወቅ ሥልጣን አልተሰጣቸውም፤ በሁሉም ሥፍራ በአንድ ጊዜ የመገኘት ብቃትም የላቸውም። በፈጣሪያቸው ሲላኩ ወይም ሲታዘዙ ለአገልግሎት የሚሄዱት እግዚአብሔር ብቻ ስለሚያውቀው ሃሳብና ዓላማ ብቻ በመሆኑ ነው።  የእግዚአብሔርነት ሙላት በሆነው ባህርይ መሠረት ሁሉን የመስማት፤ ሁሉን የማየት፤ ሁሉን የማወቅ ብቃት የላቸውም።  ይልቁንም መላእክቱን በነዚህ ሦስት ጥቅሶች ምስጋናን፤ ተአዝዞንና ተልአኪነትን ሲፈጽሙ እናያለን።
v  መዝ 148፤2  «መላእክቱ ሁሉ፥ አመስግኑት ሠራዊቱ ሁሉ፥ አመስግኑት»
v  መዝ 91፥11 «በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋል»
v  ማቴ 13፥41  «የሰው ልጅ መላእክቱን ይልካል፥ ከመንግሥቱም እንቅፋትን ሁሉ ዓመፃንም የሚያደርጉትን ይለቅማሉ»

    ሐ/ የመላእክት ሥልጣንና ተልእኰ

መላእክት ተፈጥሮአቸው አንድ ዓይነት ቢሆንም በክብርና በሥልጣን ልዩነት እንዳላቸው  ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። ስለዚህ በክብር፤ በሥልጣንና በአገልግሎት የተለያዩ እንደመሆናቸው መጠን የመላእክቱ ተልዕኰና ሥልጣንም የተለያየ ነው። ለምሳሌ ቅዱስ ሚካኤል የመላእክት አለቃ እንደሆነ በይሁዳ መልእክት (ምዕ 1፤ቁጥር9) ላይ ሚካኤል ከዲያብሎስ ጋር ስለመከራከሩ በተጠቀሰበት አንቀጽ ላይ «የመላእክት አለቃ» ተብሎ ሥልጣኑ ተጠቅሷል።
 በሌላ መልኩም  ምንም እንኳን ስሙ በትክክል ባይገለጽም ለእግዚአብሔር በማይታዘዙ፤ በበደልና በኃጢአት ሙት በሆኑ በዚህ ዓለም ልጆች ላይ ለሚሠራው መንፈስ አለቃ የሆነ በአየር ላይ ሥልጣን የተሰጠው አለቃ እንዳለም ቅዱስ ወንጌል ይነግረናል።   ( ኤፌ 2፤1-2 ) በሌላ ቦታ «ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፤ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና»  1ኛ ዮሐ 3፤8  ስለሚል በስም የተጠራውና በኃጢአት ላይ የሰለጠነው ይህ አለቃ ዲያብሎስ ነው ማለት ነው።
ከዚህ ቃል ተነስተን መላእክትን ሥልጣንና ተግባራቸውን በመመልከት የሚያመሰግኑ፤ የሚላኩትንና የሚታዘዙትን «ቅዱሳን» መላእክት ስንል፤  ለእግዚአብሔር በማይታዘዙ ላይ የሰለጠኑትና በኃጢአት ላይ ሥልጣን ያላቸውን ደግሞ «ርኩሳን» ብለን ልንከፍላቸው እንችላለን። ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝበትን አገልግሎት የሚፈጽሙ ሲሆኑ ርኩሳኑ መላእክት ደግሞ በጥፋት ላይ የተሰማሩ ናቸው ማለት ነው።
 ንስሐ በሚገባ አንድ ኃጢአተኛ የተነሳ በሰማይ ባሉ መላእክት ዘንድ ደስታ እንደሚሆነው ሁሉ ( «እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት ደስታ ይሆናል» ሉቃ 15፤10 )
 እንደዚሁ ሁሉ ኃጢአተኛ ሲቀጣ ለተልዕኰው የሚወጡ ክፉዎች መላእክት ስለመኖራቸውም («የመዓቱን መቅሠፍት በላያቸው ሰደደ መቅሠፍትን መዓትንም መከራንም በክፉዎች መላእክት ሰደደ » መዝ 78፤49  ) ሲል ክፉዎች መላእክት መኖራቸውን እንረዳለን።
ስለዚህ በሰው ልጆች ወደእግዚአብሔር መመለስ የሚደሰቱ  ቅዱሳን መላእክት እንዳሉ ሁሉ መቅሰፍትን፤ መዓትንና መከራን የሚያመጡ ክፉዎች መላእክትም አሉ ማለት ነው። ከዚህ ተነስተን መላእክትን በሁለት ልንከፍል እንችላለን።

   መ/ ቅዱሳን መላእክትና ክፉዎች መላእክት 

« ንቁም በበኅላዌነ እስከ ንረክቦ ለአምላክነ» በማለት ያረጋጋው ገብርኤል ነው፤ የካደውና እኔ ፈጣሪ ነኝ ብሎ የታበየው ሣጥናኤል ነው የሚል አስተምህሮ አለ።  በሌላ ጊዜም ይህ ገብርኤል መልአክ የወረወረው ሰይፍ እስከምጽአት ድረስ ወደመሬት ውስጥ እየተምዘገዘገ እየወረደ ነው የሚልም ትምህርት ይሰማል። ገብርኤል «ንቍም በበኅላዌነ» ማለቱን በወቅቱ የሰማና ጽፎ ያቆየልን የለም። መጽሐፍ ቅዱሳችንም ይህን ስለማለቱ አልገለጸውም። ስለዚህ እግዚአብሔር በፈቃዱ ሳይነግረን ወደተወው ጉዳይ ገብተን አንዳክርም። ነገር ግን በክፋትና በኃጢአት ላይ የሰለጠነው ዲያብሎስ በትዕቢት ከማዕርጉ መውረዱን መጽሐፍ ስለሚነግረን ያንን በመቀበል «አለቃ» እንደመባሉ መጠን በአለቅነቱ አብረውት የተሰለፉ ሠራዊት መኖራቸውንም እንገነዘባለን  
   ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ቅዱሳን መላእክት የእግዚአብሔርን ፈቃድና ደስ የሚያሰኘውን አገልግሎት ፈጻሚዎች ሲሆኑ ክፉዎቹ መላእክት ደግሞ የጥፋትና የዐመጻ ኃይሎች ናቸው። ቅዱሳኑ መላእክት ቅዱሳን ያሰኛቸው ዋናው ምክንያት እግዚአብሔርን በመፍራት የሚያገለግሉ፤ ፈቃዱንም ለመፈጸም ፈቃደኞች የሆኑ፤ በተቀመጡበትን ሥፍራ በአምልኰ ጸንተው የተገኙ ናቸው። ክፉዎቹ መላእክት ደግሞ በእግዚአብሔር ሥልጣን ሥር ቢሆኑም ከእግዚአብሔር ፈቃድ ያፈነገጡ፤ የተቀመጡበትን ሥፍራ ትተው የወጡ የጥፋት ኃይሎች ናቸው።
ይሁዳ 1፤6 «መኖሪያቸውንም የተዉትን እንጂ የራሳቸውን አለቅነት ያልጠበቁትን መላእክት በዘላለም እስራት ከጨለማ በታች እስከ ታላቁ ቀን ፍርድ ድረስ ጠብቆአቸዋል»
በቅዱሳኑ መላእክት ላይ የአለቅነት ሥልጣን ያለው ቅዱስ ሚካኤል ነው።
ራእይ12፥7 «በሰማይም ሰልፍ ሆነ፤ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ። ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ፥ አልቻላቸውምም»
ዳን 12፥1 «በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል ሕዝብም ከሆነ ጀምሮ እስከዚያ ዘመን ድረስ እንደ እርሱ ያለ ያልሆነ የመከራ ዘመን ይሆናል በዚያም ዘመን በመጽሐፉ ተጽፎ የተገኘው ሕዝብህ ሁሉ እያንዳንዱ ይድናል»
በክፉ መናፍስት ላይ ሥልጣን ያለው ደግሞ ሰይጣን (ተቃዋሚ)፤  እባብ (ጠላት)፤ ዲያብሎስ (ከሳሽ) የተባለው ዓለሙን ሁሉ የሚያስተው ዘንዶ ነው። ( ራእይ 12፤9 )  ከቅዱሳኑ መላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልና ከመላእክቶቹ ጋር ይኼው ዲያብሎስ  ተዋግቶ ተሸንፏል።
ስለዚህም ይህ የተሸነፈው ዲያብሎስ በዚህ ዓለም ላይ ከነሠራዊቱ አሳች ሆኖ ይገኛል። በዚህ ምድር ላይ ለሚፈጸመው ጥፋት፤ ኃጢአትና ዐመጻ ሁሉ ዋናው አስፈጻሚ ይህ ሰይጣን የተባለውና ሠራዊቱ ናቸው።

3/ የቅዱሳን መላእክት አገልግሎት

ይቀጥላል%

Thursday, August 28, 2014

«ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ የተሰወረ ሊሆን አይችልም» አምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ለአፄ ኃ/ሥላሴ በ1957 ዓ/ም ከጻፉት ደብዳቤ







ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ

አዲስ አበባ

ግርማዊ ሆይ፣

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት የሚታየውን ምሬትና ግፍ፣ የፍትሕም መጓደል ምክንያት በማድረግ ወደ አገሬ ለመግባት ያለኝን አሳብ ማቆየት ግድ እንደሆነብኝ ለግርማዊነትዎ መግለጥ አስፈላጊ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ይህ ሁኔታ የሚታረምበትን በኅብረት ለመሥራት ባንሞክር ታላቅ ብጥብጥ እንደሚያስከትልብን ከታሪክ መማር ካልቻልን፣ ከተከታዩ መቅሰፍት የምናመልጥበትና የምንከለልበት ሰው ሠራሽ ዘዴ ይገኝለታል ብሎ ራስን መደለል በሕልም ዓለም ውስጥ ለመኖር እንደ መፈተን ይቆጠራል፡፡
ከዚህም በቀር ለተተኪው ትውልድ አቋም ይሆናሉ ብለን ተከባክበን ልናሳድጋቸው አላፊነት ያለብንን ሕፃናትና ውለታ ትተው ለማለፍ የተደራጁትን ሽማግሎቻችንንም ደህና ዕረፍት እንዳያገኙ ከአገሪቱ በተፈጥሮ ያገኙትን ዕድል መንፈግ ያሰኛል፡፡ በዚህም ምክንያት በፈጸምነው ስህተት ታሪክ ምሕረት ሊያደርግልን በፍጹም አይችልም፡፡
ይህን የመሳሰለው ሁኔታ በብርቱ የሚያሳስበን መሆኑን ስንገልጥ ምንም እንኳ አንዳንድ ሰዎች ‹‹አንተ ምን አገባህ?›› በማለት በጉዳዩ ባለቤትነት ክፍያ ድርሻችንን ለማሳነስ ቢሞክሩም በኢትዮጵያዊነት ትክለኛ መብት ላይ አጥብበው ያሰመሩትን የወሰን ክልል አሜን ብሎ ለመቀበል ከቶ ስለሚያስቸግር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አላፊነቱን የማስወረድ ተግባር እንዳለበት አይካድም፡፡ እኔም ይህን ምክንያት አድርጌ በአሁኑ የመንግሥት አስተዳደር የደረሰውን ሕገ ወጥ አፈጻጸም ሁሉ ለማረምና ፍትሕን ለማደላደል የሚቻልበትን አሳብ በነፃ ለመግለጥ ስል እውጭ አገር መቆየትን መረጥሁ፡፡
በአሁኑ አያያዝ እንዲቀጥል የተተወ እንደሆነ በኢትዮጵያ የወገን መለያየትና የደም መፍሰስ እንደሚያሠጋ የመላው ኢትዮጵያውያን ግምት የወደቀበት ነው፡፡ ዋናው አላማ ይህ እልቂት የሚወገድበት መድኃኒቱ ምንድነው? ለተባለው ጥያቄ ለመመለስ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ መቸም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በሚመስለውና በሚያምንበት ረገድ መልሱን ለመስጠት ሞክሯል፡፡ አሁን የጐደለ መስሎ የሚታየው ከዙፋኑ በኩል የሚጠበቀው ይሁንታ ብቻ ነው፡፡ ነገሩን በመጠኑ ለማብራራት ያህል በሚከተሉት መስመሮች አስተያየቴን ለመግለጥ እሰነዝራለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዙፋኑ የሰጠው ልባዊ አክብሮት ዘላቂ ሆኖ በታሪካዊ ቅርስነት እንዲጠበቅ በቤተ መንግሥቱ በኩል አልታሰበበትም ለማለት ያስደፍራል፡፡ ባለፈው ‹‹መለኮታዊ መብት›› የተባለው የዘውድ ቴዎሪ የተሳሳተ መሆኑን ቢረዳውም፣ ሕዝቡ፣ ዘውዱን ታሪካዊ ሲምቦል ወይም ምሳሌ አድርጐ በክብር ሊያኖረው ሲፈቅድ ወደ መለኮታዊ መብት አስተያየት እንደገና እንዲመለስና ጣኦታዊ ስግደት እንዲያደርግ ማስገደድ፣ በእልህ ዘውዱን ለማስረገጥ ካልሆነ በቀር ለሌላ አያገለግልም፡፡
ጃንሆይ፣ ባለዘውድ፣ አስተዳዳሪ፣ ሕግ አውጭ፣ ዳኛ፣ ምስለኔ፣ ፖሊስ፣ ጭቃ ሹም ሆኜ ልሥራ ሲሉ፣ በ፳ኛው [20ኛው] ክፍለ ዘመን የሚገኝ ሕዝብ ይህን መብት አጠቃሎ በፈቃዱ ለዘውዱ ብቻ ይለቃል ማለት የማይታመን ነው፡፡ መቸም እየተደጋገመ የሚሰጠው ምክንያት ‹‹ሕዝቡ ኃላፊነትን ለመቀበል አልደረሰም›› የሚል መሆኑን በየጊዜው ሰምተናል፡፡ በውነቱ ከአፍሪካና ከኤሻ ሕዝብ መካከል አልደረሰም ተብሎ በኢትዮጵያ ሕዝብ መፍረድ ይገባልን? ደግሞስ ያለመድረስ ትርጓሜው ምንድነው? ምናልባት የማሰብ፣ የመምረጥ፣ የማመዛዘን፣ የመፍረድ ሴንስ አልተፈጠረለትም ማለት ነው? እንደዚህማ ከሆነ በ፫ሺሕ [በ3 ሺሕ] ዘመን ውስጥ ለዚህ ሕዝብ ጭንቅላት ሆኖ ያሰበለት፣ ዓይን ሆኖ ያየለት፣ ጆሮ ሆኖ የሰማለት የዛሬው ዘውድ ነው ማለት ነዋ! የሚፈተነው ይህን የመሰለ አስተያየት ለማቅረብ እንደሆነ ምሕረት የሌለው በደል ነው፡፡
ይልቁንስ ጃንሆይ የሕግ ጠባቂነትን ልብስ ተጐናጽፈው በዚህ መንፈስ ፍትሕን ከሚያጓድሉ፣ ሥልጣኑን ለሕዝብዎ ሰጥተው እርሱ ቢጨነቅበት እንደሚሻል ጥርጥር የለውም፡፡ ያለዚያ ከዚህ ማስታወሻዬ ውስጥ ለስማቸው እንኳ ሥፍራ ለመስጠት ዋጋ የሌላቸውና ሕሊና ቢሶች የሚያቀርቡልዎትን ‹‹ደህና ታይቷል›› እያሉ ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ እንደሚኖር የተሰወረ ሊሆን አይችልም፡፡
ይህን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ለማሻሻል የሚቻለው ጃንሆይ ዘውዱን ለራስዎ አስቀርተው አስተዳደሩን ለሕዝብ በመስጠትና የዴሞክራሲን መንፈስ በማስገባት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አስተያየት ለግርማዊነትዎ ሰውነት አለርጂ ሆኖ ቢያስቸግርም እንኳ ሌላ ማማረጫ ይኖራል፡፡ ይኸውም ዘውዱን ለልዑል አልጋ ወራሽ ማስተላለፍና አብዲኬት ማድረግ ነው፡፡ እርሳቸው ሕገ መንግሥት ጠብቀው ለመኖር ፈቃደኛ እንደሆኑ አያሌ ሰዎች ሲመሰክሩላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ያለዚያ ተከታዩ ትርምስና ደም መፋሰስ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡
ይህ አቤቱታ ከኔ ብቻ የቀረበ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍርኃት ታፍኖ ነጋም መሸም የሚያጕተመትመው ይህንኑ ነው፡፡ ድምፁን ከፍ ለማድረግ ግን አካባቢው አልፈቀደለትም፡፡ እኔም ከርሱ የተለየሁ መስዬ ታይቼ እንደሆነ ያጋጣሚ ነገር ብቻ ነው፡፡ አዲስ አበባ የታፈንኩትን ያህል እዚህ ከተነፈስሁ በኋላ ወደ አገሬ እንድመለስ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምናልባት ይህን አቤቱታ በመጻፌ እወነጀል ይሆናል፡፡ ግድ የለም፡፡ የሆነ ሆኖ በትእዛዝ ሳይሆን በነፃ የሚፈርድና በግልጽ የሚያስችል ፍርድ ቤት ተቋቁሞ ራሴን በሕጋዊ ጠበቃ አማካይነት ለመከላከል ጃንሆይ የሚፈቅዱልኝ ከሆነ በአገሬ ውስጥ ለመተንፈስ ዕድል ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡
ከዚህም ሁሉ ጋር ላስታውሰው የምፈቅደው፣ ይህን ማስታወሻ በመጻፌ ተቀይመው የእኔን ሕይወት ለማስጠፋት በሺሕ የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚወጣ ጥርጥር የለውም፡፡ አዝናለሁ፡፡ እኔ ለሞት የተዘጋጀሁ ስለሆነ ገንዘቡ ባይባክንና ለነፍሰ ገዳይ በመስጠት ፈንታ ለጦም አዳሪ ችግረኛ ቢውል የበለጠ እንደሚጠቅም ጥርጥር የለውም፡፡ በበኩሌ በአገራችን ሬሾሉሽን እንዲነሣና የማንም ደም እንዲፈስ አልፈቅድም፡፡ በዚህ ባቤቱታዬ የምወተውተውም ሰላማዊ ለውጥ እንዲሆንና የምንፈራው ደም መፋሰስ እንዳይደርስ ስለሆነ ጃንሆይ አንድ ቀን ‹‹ለካ ብርሃኑ ውነቱ ኖሯል!›› ሳይሉ አይቀርም፡፡
እንኳን ዘውድ የጫነ ሰውነትንና ማናቸውንም ሰው የማክበር ልምድ ስላለኝ፣ ይህ አቀራረቤ ክብርን ለመድፈር እንደማያስቆጥርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ውነት ሁል ጊዜ መራራ ናት፡፡ የመድኃኒት ፈውሱ እንጂ ምሬቱ አይታሰብም እንደተባለው ይህ በቅን ልቡና የቀረበው ውነተኛ አቤቱታዬ የግርማዊነትዎን ልብ አራርቶ ለኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት አንድ ፈውስ እንዲያመጣለት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ጃንሆይ! በኢትዮጵያ ወጣቱ ሽማግሌው ሴቱ ወንዱ የአኗኗሩ ዘዴ ውሉ ተዘባርቆበታል፡፡ አምላካችን፣ ፈጣሪያችን እያለ ቢደልልዎት አይመኑት፡፡ ጨንቆት ነው፡፡ ከልብ የሚመርቅዎት ግን ራስህን አስተዳድር ብለው አርነት ሲያወጡትና ወደ ዴሞክራሲ ሲመሩት ነው፡፡ ይህንንም ስል ሕዝብ በራሱ ሲተዳደር ችግር አይገጥመውም ማለቴ አይደለም፡፡ እስከዚህ አልሳሳትም፡፡ ነገር ግን ሌላው ለፍቶ ከሚጥለውና ላንሣህ ከሚለው፣ ራሱ ወድቆ በራሱ መነሣትን ይመርጣል፡፡ ይኽም በሥሕተት መማር ይባላል፡፡ ስለዚህ ጃንሆይም ተሳሳቱ እያለ ከሚከስዎት እርሱ ለሥሕተት እንዲጸጸትና እንዲማር ቢያደርጉት ትልቅ ውለታ ይቆጠራል፡፡
የዛሬው ሕገ መንግሥት ዴሞክራሲን ለማስገንባት የሚረዳ ካለመሆኑም በላይ ያንኑም ቅሉ አክብሮ ለመጠበቅ በአንቀጽ ፳፩ [21] እንደተመለከተው ከንጉሠ ነገሥቱ በመሐላ የተሰጠው ቃል ፈርሷል እያሉ አያሌ ኢትዮጵያውያን እንደሚያማርሩ ግርማዊነትዎ ሳይሰማው አይቀርም፡፡ መቸም ሕገ መንግሥቱን፣ ለመጣስ አንድ የጽሕፈት ሚኒስቴር ደብዳቤ ይበቃል፡፡ እንግዴህ ሕዝቡ ወይም ሹማምቱ ለንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ነኝ እያሉ ቢምሉም፣ ንጉሠ ነገሥቱ በበኩሉ መሐላውን የሚጠብቅ ካልሆነ በመሐላቸው ታስረው እንደማይኖሩ በልጅ ኢያሱ ጊዜ የደረሰው ሁኔታ ምሳሌ ሊሆን ይችል ይመስለኛል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የገጠመንን ፕሮብሌም እንደ መጠኑ ለመግለጥ ‹‹በግርማዊነታቸው መንግሥት ያገኘሁት ኤክስፔሪያንስ›› የሚለው መጽሐፌ በሙሉ ታትሞ እስከወጣ ድረስ ፲፪ኛውን [12ኛውን] ምዕራፍ ከዚህ ጋር አያይዤ ለግርማዊነትዎ በትህትና አቀርባለሁ፡፡

                          ዋሽንግተን ግንቦት ፳፭/፶፯ [ግንቦት 25/57]
                                ከታላቅ አክብሮታዊ ፍርሐት ጋራ
                                          ብርሃኑ ድንቄ


Friday, August 22, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

 (ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ

ስለ አምላክ  ሕግና ስለ ሰው ሕግ

እግዚአብሔር  የገዛ  ሕዝቡን  እንዲያስቷቸው  ስለምን  ዋሾ  ሰዎችን  ይተዋል  ብዬ  አሰብኩ፡፡  እግዚአብሔር  ግን  ለሁሉም
ለእያንዳንዱ  እውነትንና  ሐሰትን  እንዲያውቅ  ልቦና  ሰጥቶናል፡፡  እውነት  ወይም  ሐሰት እንደፈቃዱ  የሚመርጥበት
መምረጫም ሰጠው፡፡ እውነትን ብንወድ ለፍጥረት ሁሉ አስፈላጊና ተገቢ የሆነውን እርሱም እንድናይበት እግዚአብሔር
በሰጠን ልቦናችን ውስጥ እንፈልጋት፡፡ ሰው ሁሉ ዋሾ ነውና እውነትንም በሰዎች ትምህርት አታገኟትም፡፡ ከእውነት ይልቅ
ሐሰትን ብንመርጥ ስለዚህ እኛ በስህተታችን እንጠፋለን እንጂ ለፍጥረት ሁሉ የተሰራው የፈጣሪ ሥርዓትና ሕግ አይጠፋም፡፡
እግዚአብሔር ማንንም በሠራው ሥራ ይጠብቀዋል፡፡ ከሰው ሥራ ግን የእግዚአብሔር ሥራ ይጸናል፡፡ የሰው ሥራ ሊያጠፋው
አይችልም።  ስለዚህም  ከጋብቻ  ይልቅ  ምንኩስናን  ይበልጣል  ብለው  የሚያምኑ  እነርሱ  በፈጣሪ  ሥራ  ጽናት  ወደ  ጋብቻ
ይሳባሉ፡፡ ፆም ነፍስን እንደሚያፀድቅ የሚያምኑ እነርሱ ደግሞ ረሃብ በበዛባቸው  ጊዜ ይበላሉ፡፡ ገንዘቡን የተወ ፍፁም
እንዲሆን  የሚያምኑ በገንዘብ  ለሚያገኙት   ጥቅም  ወደ  ገንዘብ  መፈለግ  ይሳባሉ፡፡  ብዙዎች  የሀገራችን  መነኩሴዎችም
እንደሚደርጉት ከተዉት በኋላ እንደገና ይፈልጉታል፡፡ እንደዚሁ ዋሾዎች ሁላቸው የተፈጥሮን ሥራ ሊያፈርሱ ይፈልጋሉ፡፡
ነገር ግን ደካማነታቸውን ያሳያሉ እንጂ አይችሉም፡፡ ፈጣሪም ይስቅባቸዋል፡፡ የፍጥረት ጌታም በላያቸው ይሳለቅባቸዋል፡፡
እግዚአብሔር የእግዚአብሔርን ፍርድ ማድረግ ያውቃልና ኃጥአንም በእጁ ሥራ ወጥመድ  ተጠመደ፡፡ ስለዚህም የጋብቻን
ሥርዓት የሚያስነውር መነኩሴ በክፉ በሽታና ፍጥረቱ ባልሆነ በሌላ የሴት አበሳ በዝሙት ተጽዕኖ ይጠመዳል፡፡ ገንዘባቸውን
የሚንቁ  ገንዘብ  እንዲያገኙ  በሀብታሞችና  በነገሥታት  ዘንድ  ግብዞች  ይሆናሉ፡፡  ለእግዚአብሔር  ብለው  ዘመዶቻቸውንም
በሽምግልናቸውና በችግራቸውም ረዳት ባጡ ጊዜ የተዉ በነሱ ሽምግልና ጊዜ ሰውና እግዚአብሔርን ወደ ማማት፤ መሳደብ
ይደርሳሉ፡፡  እንደዚሁም  የፈጣሪን  ሥርዓት   የሚያፈርሱ  ሁሉ  በእጃቸው  በሰሩት  ወጥመድ  ይወድቃሉ፡፡  እንደገናም
እግዚአብሔር  ክፋትን፤ ስህተትን  በሰው  መካከል  ይተዋል፡፡  ነፍሶቻችን  በዚህ  ዓለም  የእግዚአብሔር ጥበብ  የፈጠረውን
የፈተና ቀን ይኖራሉ፡፡

ጠቢቡ ሰለሞን

"እግዚአብሔር  ፃድቃንን  ፈተናቸው፡፡  ወርቅ  በእሳት  እንደሚፈተን  ይፈትናቸዋል፡፡  ለእርሱ  የተዘጋጁ  ሆነውም
አግኝቷቸዋልና፡፡ እንደተወደደ ዕጣን መዐዛም ይቀበላቸዋል" ይላል፡፡
ከሞታችን በኋላም ቢሆን ወደፈጣሪያችን በገባን ጊዜ እግዚአብሔር በእውነትና በትልቅ በጥበብ ከሠራው ሁሉ እውነትና ቅን
የሆነውን መንገድ ሁሉ እንለያለን፡፡ ነፍሳችንም ከሥጋዊ ሞታችን በኋላ እንደምትድን ይታወቃል፡፡ በዚህ ዓለም ውዴታችን
አይፈፀምምና የሌላቸው ይፈልጋሉ፤ ያላቸው ባላቸው ላይ እንደገና ሊጨምሩ ይፈልጋሉ፡፡ሰው በዚህ ዓለም ያለው ሁሉ
እንኳን  ቢኖረው  እንደገና  ይወዳል  እንጅ  አይጠግብም፡፡  ይህም  የፍጥረታችን  ጠባይ  ለሚመጣው  ንብረት  እንጂ  ለዚህ
ዓለም ንብረት ብቻ እንዳልተፈጠርን ያመለክታል፡፡ በዚያውም የፈጣሪያቸውን ፈቃድ የፈፀሙ ነፍሳት ፍፁም ይጠግባሉ
እንጂ ከእንግዲህ ሌላ አይወዱም፡፡ አለዚያ ግን የሰው ፍጥረት አስፈላጊውን ሁሉ አላገኝምና ጎዶሎ በሆነ ነበር፡፡ እንደገናም
ነፍሳችን  እግዚአብሔርን  ማሠብ  ትችላለችና  በሃሳቧም  ታየዋለች፡፡  እንደገናም  ለዘላለም  መኖር  ማሰብ  ትችላለች፡፡
እግዚአብሔርም ይህን ማሰብ በከንቱ አልሰጣትም፡፡ ነገር ግን እንደሰጣት ልታስብና  እንድታገኝም ሰጣት፡፡ ደግሞ በዚህ
ዓለም ፅድቅ ሁሉ አይፈፀምም፡፡ ክፉ ሰዎች ከዚህ ዓለም መልካም ይጠግባሉ፡፡ ደጋጎች ይራባሉ፡፡ የሚደሰት ክፉ አለ፣
የሚያዝን ደግ አለ፣ የሚደሰት ዐመፀኛ አለ፣ የሚያለቅስ ፃድቅም አለ፣ ስለዚህም  ከሞታችን በኋላ ለሁሉ እንደየምግባሩ
የሚከፍለው  ሌላ  ኑሮና  ፍፁም  ፅድቅ  ያስፈልጋል፡፡  በብርሃን  ልቦናችን  ተገለፀላቸው፡፡  የፈጣሪን  ፈቃድ  የፈፀሙና
በተፈጥሯቸውም ፀባያዊ ህጉን የጠበቁ ዋጋቸው ይከፈላቸዋል፡፡ የተፈጥሮን ሕግ ከመረመርን የተረጋገጠ መሆኑን ልቦናችን
በግልፅ  ይነግረናል፡፡  ነገር  ግን ሰዎች  ሊመረምሩ  አልፈለጉምና  የፈጣሪያቸውን  ፈቃድ በእውነት  ከመፈለግ  የሰዎችን  ቃል
ማመን መረጡ፡፡

 ስለ ባህሪያዊ ዕውቀት

የፈጣሪ ፈቃድ ግን ለእግዚአብሔር ለፈጣሪህ ስገድ ፣ ሰውንም ሁሉ እንደነፍስህ አፍቅር ይላል፡፡ ይህ በልቦናችን እውነት
መሆኑ  ይታወቃል፡፡  እንደገናም  በልቦናችን  እውነትነቱ  የሚታወቅ  ሌላ  እውነት  "ሊያደርጉብህ  የማትፈልገውን  በሰው
አታድርግ፡፡  ላንተ  ሊያደርጉልህ  የምትፈልገውን  አድርግላቸው"  ይላል፡፡  የሰንበትን  ማክበር  የሚለው  ካልሆነ  በቀር  ዐሥሩ
የኦሪት  ትዕዛዛት  የፈጣሪ  ናቸው፡፡  ሰንበትን  ለማክበር  ግን  ልቦናችን  ዝም  ይላል፡፡ ልንገድልና  ልንሰርቅ፣  ልንዋሽና  የሰው
ሚስት  ልንሰርቅ  ይህን  የሚመስለውን  ልናደርግ  እንደማይገባን  ልቦናችን  ይነግረናል፡፡ እንዲሁ  ስድስቱ  የወንጌል  ቃላት
የፈጣሪ  ፈቃዶች  ናቸው፡፡  እኛ  ይህን  የምህረት  ሥራ  ሊያደርጉልን  እንፈልጋለን፡፡  በሚቻለን  ለሌሎች  ልናደርግላቸው
ይገባናል፡፡ ደግሞም በዚህ ዓለም ሕይወታችን፣ ንብረታችን እንድንጠብቅ የፈጣሪ ፈቃድ ነው፡፡ ከፈጣሪ ፈቃድ ወጥተን
በዚህ ሕይወት እንኖራለን፡፡ በተቀደሰ ፈቃዱ ካልሆነ በቀር ልንተወው አይገባንም፡፡እርሱ ፈጣሪያችን ለሁሉ ልቦናና ችሎታ
ስለሰጠ ኑሯችንን በዕውቀትና በሥራ እንድናሳምረው ይፈቅድልናል፡፡ ይህ ካልሆነ በቀር የሕይወታችን ፍላጎት አይገኝም፡፡
እንዲሁ  አንዱ  ካንዷ  ጋር  መጋባትና  ልጆች  ማሳደግን  ፈቅዷል፡፡  ደግሞም  ከልቦናችን  ጋር  የሚስማማ  ለህይወታችንም
ለሁሉም  የሰው  ልጆች  ኑሮ  የሚያስፈልጉ  ሌሎች  ብዙ  ሥራዎች  አሉና  የፈጣሪ  ፈቃድም  እንዲሁ  ስለሆነ  ልንጠብቀው
ይገባናል፡፡ እግዚያብሔር ፍፁማን አድርጎ እንዳልፈጠረን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ለመፈፀማችን የተዘጋጀን አዋቂዎችና በዚህም
ዓለም  እስካለን  ድረስ  እንድንፈፅምና  ፈጣሪያችን  በጥበቡ  ላዘጋጀልን  ዋጋ  የተዘጋጀን እንድንሆን  አድርጎ  ፈጠረን፡፡  በዚህ
ምድር ፍፁማንና ብፁዓን አድርጎ ሊፈጥረን ለእግዚአብሔር ይቻለው ነበር፡፡ ነገር ግን ለመፈፀማችን የምንዘጋጅ አድርጎ
ፈጠረን እንጅ እንዲሁ ሊፈጥረን አልፈቀደም፡፡ ከሞታችን በኋላ ፈጣሪያችን ለሚሰጠን ዋጋ የተዘጋጀን ፍፁማን እንድንሆን
በዚህ የፈተና ዓለም መካከል አኖረን፡፡ በዚህ ዓለም እስካለንም ወደ እርሱ እስኪወስደን ድረስ እየታገስን ፈቃዱን እየፈፀምን
ፈጣሪያችን  ልናመሰግነው  ይገባል፡፡  የፈተናችንንም  ጊዜያቶች  እንዲያቀልልን  ባለማወቃችን  ሠራነውን  የእብደት  አበሳ
እንዲተውልን የተፈጥሮ ሕግጋትን አውቀን እንድንጠብቃቸው ልቦና እንዲሰጠን ወደቸርነቱ እንለምን፡፡ ፀሎት ደግሞ ላዋቂ
ነፍስ  አስፈላጊ  ነውና  ዘወትር  ልንፀልይ  ይገባናል፡፡  አዋቂ  ነፍስ  ሁሉን  የሚያውቅና ሁሉን  የሚጠብቅ  ሁሉን  የሚገዛ
እግዚአብሔር እንዳለ ታውቃለች፡፡ ወደ እርሱ እንድትፀልይም ከእርሱ መልካም እንድትለምን፣ ከክፉ እንድትድንና ሁሉን
ወደሚችል እጅ እንድትማፀን ወደ እርሱ ትሳባለች፡፡ እግዚአብሔር ምሁርና ትልቅ ነው፡፡ የሚሳነውም የለም፡፡ ከበታቹ
ያለውን ያያል፣ ሁሉንም ይይዛል፣ ሁሉን ያውቃል ፣ ሁሉን ይመራል፣ ሁሉን ያስተምራል አባታችን ፈጣሪያችን ጠባቂያችን
ነው፡፡  የነፍሳችን  ዋጋ  ቸርና  ይቅር  ባይ  ችግራችንን  ሁሉ  የሚያውቅ  ነው፡፡  ለሕይወት  እንጂ  ለጥፋት  አልፈጠረንም፡፡
በትዕግስታችን ይደሰታል፡

Thursday, August 14, 2014

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሥርዓተ አልበኝነት ነግሷል!

  • የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲፈራርስ ዝምታው እስከመቼ?
  •  
  •  ቅዱስ ፓትርያርኩ በዚህ ጉዳይ ምላሻቸው ምን ይሆን?

ዛሬ ዛሬ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሚለው ቃል ከወረቀት ባለፈ በመሬት ላይ ተፈሚነቱ የሚታየው በጣም በጥቂቱ ነው። በተለይም ቤተ ክርስቲያኒቱ አለኝ በምትለው ማእርገ ክህነት በኩል ዲቁና፤ ቅስና ( ምንኩስና) ቁምስና በሙሉ የሚሰጠው ለማንና መስፈርቱ ምን እንደሆነ በማይታወቅ መልኩ ሥርዓተ የለሽ ሆኖ ይታይበታል። እነ መቶ አለቃ ግርማ ወንድሙ ሳይቀሩ በር የሚዘጋ መስቀል ተሸክመው እያሳለሙ በአጥማቂነት ተሰማርተው ገንዘብ ይሰበስባሉ። ከዚህ በፊት ወደእስራኤል አቅንቶ የነበረው ግርማ ወንድሙ ገና ገንዘብ መሰብሰብ ሲጀምር አንዷን ሴት ሲያጠምቅ ጎረቤቷ ቡዳ ሆና በላቻት በማሰኘቱ፤ ቡዳ ናት የተባለችው ሴት ፍርድ ቤት በስም አጥፊነት ከሳው መጥሪያ ብታመጣበት ሌሊቱኑ ፈርጥጦ ወደኢትዮጵያ ማምለጡን ጉዳዩን በቅርበት ከሚያውቁ ሰምተን ተገርመን ነበር። ባለቤት የሌላትን ቤተ ክርስቲያን እየተዘዋወረ በክፉ መንፈስ የሚበጠብጠው ግርማ አሁን ደግሞ ወደአውሮፓ ዘልቆ በጣሊያን የዘረፋውንና የቡዳ በላሽ ዜማውን እያስነካው ይገኛል። እነባህታዊ ገብረ መስቀል ማርያምን ተገለጸችልኝ እያሉ ህዝቡን ሲያጭበረብሩ እንዳልነበር ብህትውናውን እርግፍ አድርገው ቆንጆ መርጠው ሚስት አግብተው ልጆች ወልደው ማርያም ተገለጸችልኝ፤ ገብርኤልን አየሁት ከሚል ማደናገሪያ ነጻ ወጥተዋል። ከማጭበር በር ይህኛው የተሻለ አማራጭ ይመስለናል።
ይህ ማእርገ ክህነት የሚባለው ሹመት በአንዳንዶች ዘንድ የክብር ዶክትሬት ይመስል ከስም ባለፈና የሕዝቡን ግንባር ከሚገጩበት በስተቀር እንደማኅበረ ቅዱሳን ባሉ ማኅበራት ዘንድም የአገልግሎት ዋጋ የሌለው መሳሪያ ሆኖ ይገኛል። በየትኛውም ቤተ ክርስቲያን ሲያገለግሉበት አይታይም። የማዕረጉን ስም የሚፈልጉት ክህነት የላቸውም እንዳይባሉና በክህነት ሽፋን በሚገኘው ክብር የመበለቶችን ቤት ለመዝረፍ ስለሚረዳ እንጂ ከመጀመሪያው በድንግልና ጸንተው ለማዕርገ ዲቁና በቅተው «ተንሥኡ፤ ጸልዩ» እያሉ ሲያገለግሉበት ቆይተው፤ በኋላም በስርዓተ ቤተ ክርስቲያን በተክሊል በድንግልና የጸናች አግብተው አይደለም። ሲጀመር ጀምሮ ዲቁናም ይሁን ቅስና የተቀበሉት ሰዎች ድንግላቸው የፈረሰበትን ጊዜ ራሳቸው በትክክል አያውቁትም። ራሳቸው በድንግልና ሳይቆዩ፤ ድንግልና እንደፈንጣጣ በጠፋበት ዘመን ድንግል አግብተው አይቀስሱም።  በተለይ ወንዶቹ አጭበርባሪዎች፤ ቀሳጮችና መልቴዎች ናቸው። በዚህ ዙሪያ ሀገር ሰፈሩን ሲያዳርሱ የኖሩ የዘመኑ ቀሳውስትና መነኮሳት ነን ባዮች ቅስናን እንደማጭበርበሪያ ይጠቀሙበታል። ቅዱስ በተባለው መቅደስ ገብተው በርኩስናቸው ሕዝቡን ያታልሉበታል። ይህ ዐመፃና ማታለል በሀገር ላይ ጥፋትን፤ በሕዝብ ላይ ቁጣን ማምጣቱ አይቀርም። ማንም እመራበታለሁ ብሎ ላወጣው ለራሱ ሕግ የማይታዘዝ ከሆነ የሚጠፋው በዚያው በራሱ ሕግ ነው።
«ያለ ሕግ ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለ ሕግ ደግሞ ይጠፋሉና፤ ሕግም ሳላቸው ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ በሕግ ይፈረድባቸዋል» ሮሜ 2፤12
ዛሬ ሁሉም ከዚህ ከራሳቸው የሕግ ክብር ስለወረዱ ማንም ምንንም አይቆጣጠርም። ሥርዓት ፈረሰ፤ ሕግ ተጣሰ የሚል አንድም ስንኳ የለም። «ኩሉ ዐረየ፤ ወኅቡረ ዐለወ» እንዳለው ዳዊት በመዝሙሩ ሁላቸውም ተሳስተዋል፤ ሁላቸውም በዐመጻ ስለተስተካከሉ ዲቁና ሰጪውም ተቀባዩም ከሥርዓት ውጪ ሆነዋል።  ከዚህ በታች የቀረበውም ጽሁፍ ይህንን መሠረት ያደረገ ነው።
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነን «እንበለ አሐዱ ኄር፤ ኢይኀድጋ ለሀገር» ለሀገር እንዲሉ አንድ ተቆርቋሪ ኤርትራዊ ቄስ ከሀገረ እስራኤል-ቴል አቪቭ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ለልዩ ልዩ ድረ ገጾች በግልባጭ ሲልክ ለእኛ የደረሰውን ጽሁፍ እንዳለ አቅርበነዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምን ሆነች?

በታሪክ አጋጣሚ ኢትዮጵያና ኤርትራ ከመለያየታቸው በስተቀር በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ዛሬም ድረስ አንድ ነን። ሥርዓቱና ሕግጋቱ የተለያየ አይደለም። በማዕረገ ክህነት አሰጣጥ ልዩነት ያለን አይመስለንም።  ነገር ግን እጅግ አሳዝኝና አስገራሚ ነገር ስናይ የምንጠይቀው አጥተናል። በተደረገው ሁኔታ እኛ በእስራኤል የምንገኝ ኤርትራውያን በተደረገው አድራጎት ተጎድተናል። ይኸውም ለሰሚ የሚከብድና ከምናውቃት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ህግጋት ውጪ ማዕረገ ክህነት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳም ውስጥ ሲሰጥ በማየታችን በጣም አዝነናል። ነገሩን በአጭሩ አስረዳለሁ።
ሰውየው በትግራይ ክፍለሀገር ሰንቃጣ እንደተወለደ አውቀነዋል። ስሙም ሓጎስ አስገዶም ይባላል። በትግራይ ክፍለ ሀገር ይህ ሓጎስ አስገዶም የተባለ ሰውዬ አባ ሰላማ የሚባል ማኅበር አቁሞ ህዝብ ለህዝብ ሲያጋጭ ተይዞ ሶስት አመት ወኅኒ ታስሮ ነበር። በአቡነ መርሐ ክርስቶስ ማኅበሩ በትእዛዝ ፈረሰ። በሲኖዶስም ተወሰነበት። ተስፋ ያልቆረጠው ይህ ሓጎስ አሰገዶም የተባለ ሰውዬው ወደ ሽመልባ የኤትራውያን ስደተኛ ካምፖ በመግባት ባሕታዊ ወልደ ሥላሴ እባለሎህ በማለት ማደናገር ጀመረ።
ባህታዊ ነኝ የሚለው ሓጎስ አስገዶም

በዚያም በእሱ የተጀመረ ረብሻ በሽመልባ ባሉ የኤርትራ ቤተክርስቲያን በመበራከቱ ጥቂት ተከታዮች አስከትሎ በሱዳን አድርጎ ሊቢያ ገባ። ሊቢያ ሲገባም አባ ሰላማ መልዕክት ነግረውኛል ከዛሬ ጀምሮ አንተ ሞኖክሴ ነህ ብለውኛል ብሎ አባ ሳሙኤል ነኝ አለ። ከዚያም ይህ ሓጎስ አስገዶም ከሊቢያ ወደእስራኤል ሀገር ከኤርትራውያን ጋር ገብቶ ኤርትራዊ ነኝ ብሎ የስደተኛ ወረቀት ከወሰደ በኋላ ሳይሞኖክስ አባ ሳሙኤል ተብሎ እየተጠራ ቆየ። አጠምቃለሁ እያለ ሲያታልል፤ ህዝብ ሲያሳብድ፤ ገንዘብ ሲሰበስብ ቆይቶ ብዙ ኤትራውያን ደግሞ አንተ ሞኖክሴ አይደለህም፤ ለምን አባ ትባላለህ። ክህነት የለህም ለምን ታሳልማለህ።  ንስሀ ለምን ትሰጣለህ ስንለው የእኔ ክህነት በአባ ሰላማ ፍሬምናጦስ አማላጅነት ከሰማይ ነው የተሰጠኝ፤ የእናንተ ክህነት ግን ከኃጢአተኛ ጳጳስ እጅ የተሰጠ ነው እያለ ሲሳደብ በማየታችን ህዝቡ በዚህ አታላይ ሰው እንዳይታለል ስናስተምር ተናዶ ወደኢየሩሳሌም በመሄድ ከኢትዮጵያ ሊቀጳጳስና አንዳንድ መነኮሳት ጋር በስውር መገናኘቱን ቀጠለ።
ባህታዊ ወልደ ሥላሴ ነኝ እያለ በሽመልባ ሲያታልል

 ከዚያም ከሊቀ ጳጳሱ አባ ዳንኤል ዘንድ ዲቁና ተቀበልኩ አለና በአስማቱ ለሚያታልላቸው ደጋፊዎቹ  ማዕረጉ ሲሰጠው የሚያሳይ ፎቶና ፊልም አሳየ። ትንሽ ቆይቶ ሞኖኮስኩኝ ብሎ እንደቦብ ማርሊ ያሳደገውን ጸጉሩን ቆርጦ ጥቁር ቆብና ቀሚስ አድርጎ መጣ። አንተን አመነኮሰች ቤተ ክርስቲያን? ብለን አዘንን። አለቀስን።
በአባ ሳሙኤል ስም ቄስና መነኩሴ ነኝ አለን ደግሞ

ከሱ ጋር የነበሩና ስናስተምራቸው የተመለሱ ሁለት ዲያቆናት ለመመንኮስ 50 ሺህ ሼቄል ከፍሏል አሉን። ለሊቀ ጳጳሱና ከመነኮሳቱ መካከል አባ ፍስሐና አባ ብርሃና መስቀል የተባሉም ገንዘብ መቀበላቸውን አሁንም ይመሰክራሉ። የሰው ማስረጃ አለን። ሌሎችም መነኮሳት የተቀበሉ አሉ። ይህ አታላይ አባ ሳሙኤል የተባለው ትንሽ ቆይቶ የቅስና ማዕረግ ከአባ ዳንኤል ተሰጠኝ ብሎ በደብረ ገነት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን የተፈጸመውን ሥርዓት በቢዲዮና በፎቶ  ቴልአቪቭ አምጥቶ ለተከታዮቹ አሳየ። ይህ ሁሉ ማስረጃ በእጃችን ይገኛል።
ምንም የቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሙያ ለሌለው፤ ዲቁና ሳይኖረው  ለሓገስ አስገዶም ቅስና ሲሰጡት አቡነ ዳንኤል ናቸው

 የዚህ ሁሉ አስተባባሪ አባ ፍስሐ ይባላሉ። አባ ብርሃነ መስቀል የተባሉት፤ አባ ተወልደ የተባሉትም አብረውት አሉ። ገንዘብ የተቀበሉ መኖክሴዎች ዝርዝር በእጃችን አለ። በቁጥር ትንሾች ቢሆኑም የቤተ ክርስቲያን ስርዓት ጠፋ ብለው የተናገሩ ቢኖሩም የሰማቸው የለም።  ገንዘብ የሁሉንም አፍ ዝም አሰኝቷል።



 እኛ የምናዝነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ሹማምንት በገንዘብ ስልጣነ ክህነት እየሰጡ ለምን ቤተ ክርስቲያንን ያሰድባሉ? የኢየሩሳሌም ገዳም ሞኖክሴዎችስ ለምን በገንዘብ ይደለላሉ? ክህነት እንደዚህ ነው? ሙንኩስናስ እንደዚህ ነው? በበኩላችን ይህን ሰውዬ ያለአግባብ እያታለለ ከኤርትራውያን እጅ የወሰደውን በብዙ መቶ ሺህ ሼቄል ለማስመለስና በህግ ፊት ለማቆም ማስረጃዎቻችንን ይዘናል። እናንተ በሰጣችሁት ክህነት አንታለልም። አንታወክም። ለነገሩ ቤተ ክርስቲያንን አዋርዳችሁታል። ሓጎስ አስገዶም ቄስ ሆነ? ሚስቱንም አምጥቶ አመነኮሰ። አንድ ቤት አንድ ላይ ይኖራሉ። አይ ኦርቶዶክስ፤ እንደዚህ መሆና ያሳዝናል። ሕግ ካለ፤ ዳኛ ካለ ኢየሩሳሌም ያሉ ሞነኮሳትን ከገዳሙ ማባረር ነበር። ለሓጎስ አስገዶም ቅስና የሰጡ ሊቀጳጳሱም መቀጣት ነበረባቸው።
ያሳዝናል። ያሳዝናል። በትክክልም ዘመኑ ተጨርሷል። ክህነትና ሙንኩስና  በገንዘብ ሆነ። ኤሎሄ ኤሎሄ ይባላል።

ለምእመን በገንዘብ ክህነት እንዲያገኝ ያደረጉ አባ ብርሃነ መስቀል የሚባሉት በቀኙ፤ አባ ፍስሐ የሚባሉት አባ ፍስሐ የሚባሉት በግራ በመሀል አቡነ ዳንኤልና ሲሆኑ በደብረ ገነት ቤተመቅደስ ውስጥ ሓጎስ አስገዶም ፤ ወልደሥላሴና አባ ሳሙኤል የተባለው ቅስና ሲቀበል የሚያሳይ ፎቶ። የዚህ ሥርዓት ሙሉ ቪዲዮ በእጃችን አለን።
             
                     ፍትዊ አንገሶም ቴልአቪቭ