Wednesday, July 30, 2014

ሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ

 ዘርዓ ያዕቆብ ፈላስፋ (ክፍል አንድ)

እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሁሉ ለነፍስ ያደረጋችሁትን መናገር እጀምራለሁና ኑ ስሙኝ፡ ሁሉን በፈጠረ መጀመሪያና መጨረሻ በሆነ ሁሉን በያዘና የሕይወትና የጥበብ ሁሉ ምንጭ በሆነ እግዚአብሔር በሰጠኝ ረዥም እድሜየ ትንሽ እጽፋለሁ፡፡ ነፍሴ በእግዚአብሔር ዘንድ የተከበረች ትሁን ጆሮዎችም ሰምተው ይደሰቱ፡፡ እኔ እግዚአብሔርን ፈለኩት መለሰልኝ፡፡ አሁንም እናንተ ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችሁማል፤ ፊታችሁንም አያሳፍርም፡፡ እግዚአብሔርን ከኔ ጋር ከፍ ከፍ አድርጉት አብረን ስሙን እናንሳ፡፡

  እኔ የተወለድኩት በአክሱም በካህናት ሀገር ነው፡፡ ነገር ግን እኔ በአክሱም አውራጃ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ በነገሠ በሦስተኛው ዓመት በ1592 ዓ/ም ከ አንድ ገበሬ ቤተሰብ ተወለድሁ፡፡ በክርስትና ጥምቀት ዘርዓ ያዕቆብ ተብየ ተሰየምኩ፡፡ ሰዎች ግን ወርቄ ይሉኛል፡፡ ካደኩ በኋላ ትምህርት እንድማር አባቴ ወደ ትምህርት ቤት ላከኝ፡፡ ዳዊትም ከደገምኩ በኋላ መምህሬ አባቴን ይህ ህፃን ልጅህ ልቦናው የበራ በትምህርት ታጋሽ ነውና ወደ ትምህርት ቤት ብትልከው ሊቅና መምህር ይሆናል አለው፡፡ አባቴም ይህን ሰምቶ ዜማ እንድማር ላከኝ፡፡ ሆኖም ድምጼ ሸካራ ሆኖ አላምር አለኝ፡፡ በዚህ ምክንያት ጓደኞቼ መሳቂያና መዘባበቻ አደረጉኝ፡፡ እዚያም ሦስት ወር ያህል ቆየሁ፡፡ ስላልተሳካልኝ ከልቤ አዘንኩ፡፡ ተነስቼ ሰዋስውና ቅኔ ለመማር ወደ ሌላ አስተማሪ ሄድኩ፡፡ ከጓደኞቼ ፈጥኜ እንድማርም እግዚአብሔር ጥበቡን ሰጠኝ፡፡ ይህም የመጀመሪያ ሃዘኔን አስረሳኝ ፡፡ በጣም ተደሰትኩ፡፡ እዛም አራት አመት ቆየሁ፡፡ በነዚያ ቀኖች እግዚአብሔር ከሞት አዳነኝ፡፡ ከጓደኞቼ ጋር ስጫወት ወደገደል ወደቅሁ፡፡ እግዚአብሔር በታምራቱ አዳነኝ እንጅ ፈጽሞ ልድን አልችልም ነበር፡፡ ከዳንኩ በኋላ ገደሉን በረዥም ገመድ ለካሁት፡፡ ዐሥራ ሦስት ሜትር ሆኖ ተገኝ፡፡ እኔም ድኜ ያዳነኝን እግዚአብሔርን እያመሰገንኩ ወደ መምህሬ ቤት ሄድኩ፡፡ ከዚያም ተነስቼ የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜ ለመማር ሄድኩ፡፡

 በዚያም ዐሥር ዓመት ቆየሁ፡፡ መጻሕፍትን ፈረንጆች እንዴት እንደሚተረጉሟቸው፤ የኛም ምሁራን እንዴት እንደሚተረጉሟቸው ተማረኩ፡፡ ትርጓሜያቸው ግን ከኔ ልቡና ጋር የሚስማማ አልነበረም፡፡ ሆኖም ይህን ስሜቴን፤ ሃሳቤን ለማንም ሳልገልጽ በልቤ ይዠው ቆየሁ፡፡ ከዚያም ወደሃገሬ ወደ አክሱም ተመለስኩ፡፡ በአክሱም ለአራት አመት መጽሐፍ አስተማረኩ፡፡
ይህ ዘመን ክፉ ዘመን ሆነ፡፡ አፄ ሱስንዮስ በነገሠ በ 19ኛው ዓመት የፈረንጆች ተወላጅ አቡነ አልፎንዝ መጣ፡፡ ከ2 ዓመት በኋላም ንጉሡ የፈረንጆቹን ሃይማኖት ስለተቀበለ በኢትዮጵያ ትልቅ ስደት ሆነ፡፡ ይህን ሃይማኖት ያልተቀበለ በሙሉ ግን እጣው ስደት ሆነ፡፡

 አፄ ሱስንዮስ፣ አልፎንዝና ጠላቴ ወልደ ዮሐንስ

እኔ በሃገሬ መጻሕፍት ሳስተምር ብዙዎቹ ጓደኞቼ ጠሉኝ፡፡ በዚህ ዘመን የባልንጀራ ፍቅር ጠፍቶ ነበርና ቅናት ያዛቸው፡፡ በትምህርትና ጓደኛን በመውደድ ከነርሱ እበልጣለሁ፡፡ ከሁሉ ሰው፤ ከፈረንጆቹና ከግብጻውያን ጋር እስማማለሁ፡፡
መጻሕፍትን ሳስተምርና ስተረጉም እንዲህ እንዲህ ይላሉ፤ ግብጻዊያኖች ደግሞ (ኦርቶዶክሶች) እንዲህ እንዲህ ይላሉ እላለሁ፡፡ እኛም ብንመረምር ይህን ሁሉ እናውቃለን እላለሁ እንጅ ይህ መልካም ነው፤ ይህ ደግሞ ክፉ ነው አልልም፡፡ ግብጾቹ የፈረንጅ፣ ፈረንጆቹ ደግሞ የግብጻውያኖቹ እመስላቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ሁሉም ጠሉኝ፡፡ ብዙ ጊዜም ወደንጉሡ ከሰሱኝ፡፡ እግዚአብሔር ግን አዳነኝ፡፡ ከዚህም በኋላ ከአክሱም ካህናት አንድ ወልደ ዮሐንስ የተባለ ጠላቴ፤ የንጉሥ ወዳጅ ስለነበረ፣ የነገሥታት ፍቅር በሽንገላ ምላስ ስለሚያገኝ ወደ ንጉሡ ሄደ፡፡ ወደ ንጉሡም ገብቶ እንደዚህ አለው ፡፡
“ይህ ሰው ህዝብን ያሳስታል፡፡ ስለሃይማኖታችን እንነሳና ንጉሡን እንግደለው፣ ፈረንጆቹንም እናባራቸው ይላል” እያለ ይሄንና ይሄን በመሰለ ውሸት ከሰሰኝ፡፡ እኔም ይህን አውቄ ገና ለገና ይገድለኛል ብዬ ፈርቼ የነበረኝን ሶስት ወቄት ወርቅና የምጸልይበትን መዝሙረ ዳዊት ይዠ በሌሊት ሸሸሁ፡፡ ወዴት እንደምሄድ ለማንም አልተናገርኩም፡፡ ወደተከዜ በረሀ ገባሁ፡፡ በነጋታውም ራበኝ፡፡

  ከሀብታሞች ገበሬዎች እንጀራ ለመለመን እየፈራሁ ወጣሁ፡፡ ሰጡኝና በልቼ እየሮጥኩ ሄድኩ፡፡ እንዲህ እያልኩ ብዙ ቀን ቆየሁ፣ በኋላ ወደ ሽዋ ግድም ስሄድ ሰው የሌለበት በርሃ አገኘሁ፡፡ ከገደሉ በታች መልካም ዋሻ ነበርና ሰው ሳያየኝ በዚህ ዋሻ እኖራለሁ ብየ ወሰንኩ፡፡ ሱስንዮስ እስኪሞትም ድረስ በዚያ 2 ዓመት ቆየሁ፡፡ አንዳንዴ ወደገበያ እየወጣሁ ወይም ወደ አምሐራ ሀገር እሄድ ነበር፡፡ ለአምሐራ ሰዎች የምበላው እንዲሰጡኝ የምለምን ባህታዊ መነኩሴ እመስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከየት እንደምወጣና ወዴት እንደምገባ አያውቁም፡፡ ከዋሻየ ለብቻየ በሆንኩ ጊዜም በመንግሥተ ሰማያት የምኖር መሰለኝ፡፡ ቁጥር የሌለው ክፋታቸውን አውቄ ከሰዎች ጋር መኖር ጠላሁ፡፡ ሌሊት መጥተው የበርሃ አራዊት እንዳይበሉኝም በድንጋይና በአሽዋ አጥር ዋሻየን አጠርኩ፡፡
እሚፈልጉኝ ሰዎች ወደኔ ቢመጡ የማመልጥበት መውጫም አዘጋጀሁ፡፡ እዚያ በሰላም ኖርኩ፡፡ በሚሰማኝ በእግዚአብሔር ተስፋ አድርጌ በሙሉ ልቤ በመዝሙረ ዳዊት ጸለይኩ፡፡

ስለአምላክ መኖርና የሐይማኖት መለያየት

ከጸሎት በኋላም ስራ ስለሌለኝ ሁልጊዜ ስለሰዎች ክፋትና ሰዎች በእርሱ ስም ሲበድሉ፣ ወንድሞቻቸውን ጓደኞቻቸውን ሲያባርሩ እና ሲገድሉ ዝም በማለቱ ስለፈጣሪ ጥበብ አስብ ነበር፡፡ በዚህም ጊዜ ፈረንጆቹ አየሉ፡፡ ነገር ግን ያገሩ ሰዎችም ከነሱ የባሰ ክፋት ሰሩ እንጅ ፈረንጆቹ ብቻቸውን አልነበረም የከፉት፡፡ የካቶሊክ ሃይማኖት የተቀበሉት፤ ኦርቶዶክሶች የመንበረ ጴጥሮስን እውነተኛዋን ሃይማኖት ክደዋልና የእግዚአብሔር ጠላቶች ናቸው አሉ፡፡ ስለዚህም አሳደዱአቸው፡፡
ኦርቶዶክሶችም ለሃይማኖታቸው እንዲሁ አደረጉ፡፡ እግዚአብሔር የሰዎች ጠባቂ ከሆነ ለምን ፍጥረታቸው እንዲህ ከፋ ብየ አሰብኩ፡፡ በአርያም የሚያውቅ አለን ? ኧረ እግዚአብሔርስ ያውቃልን ? በቅዱስ ስሙ ሲበድሉና ሲረክሱ የሚያውቅ ከሆነ እንዴት የሰዎችን ክፋት ዝም ይላል? አልኩ፡፡
ምንም ልብ አላደረኩም ብዙ አሰብኩ፡፡ የፈጠርከኝ ፈጣሪየ ሆይ አዋቂ አድርገኝ፤ የተደበቀውን ጥበብህን ንገረኝ ብየ ጸለይኩ፡፡ ለሞት እንዳይተኙ አይኖችህን አብራቸው፤ እጆችህ አደረጉኝና ሰሩኝ፡፡ ትዕዛዝህን እንድማር ልብ ስጠኝ፡፡ ለኔ ግን እግሮቼ በተፍገመገሙ፤ ተረከዞቼም በተንሸራተቱ ነበር ፡፡ ይህም በፊቴ ስላለው ድካም ነው፡፡ ይህንን እና ይህን የመሰለ ፀሎት አደርግ ነበር፡፡
 አንድ ቀን እኔ ወደ ማን ነው የምፀልየው? አልኩ፡፡ በእውነት የሚሰማኝ እግዚአብሔር አለን? በዚህም አሳብ በጣም አዝኜ እንዲህ አልኩ፡፡ዳዊት እንዳለ እንዴት ምንኛ ልቤን አጸደኳት፡፡ ኋላም አሰብኩ።ይህ ዳዊት እንዲህ የሚለው «ጆሮን የተከለ አይሰማምን ?»  በእውነት እንድሰማበት ጆሮ የሰጠኝ ማነው? አዋቂስ አድርጎ የፈጠረኝ ማነው? በዚህስ ዓለም እኔ እንደምን መጣሁ? ከዓለም በፊት ብኖር የሕይወቴ መጀመሪያና የእውቀቴ መጀመሪያን ባወቅሁ፡፡ እኔ በገዛ እጄ ተፈጠርኩን ? ነገር ግን እኔ በተፈጠርኩ ጊዜ አልኖርኩም፡፡ አባት እናቴ ፈጠሩኝ ብልም እንደገና ወላጆችና የወላጆችን ወላጅ፣ወላጅ የሌላቸው በሌላ መንገድ ወደዚህ ዓለም የመጡትን እንደኛ ያልተወለዱትን የፊተኞቹ ድረስ ፈጣሪያቸውን እፈልጋለሁ፡፡ እነርሱም ቢወለዱ የፈጠራቸው አንድ ህላዌ አለ ከማለት በቀር የጥንት መወለጃቸውን አላውቅም፡፡ ያለና በሁሉም የሚኖር የሁሉ ጌታ ሁሉን የያዘ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው ዓመቱ እማይቆጠር እማይለወጥ ያልተፈጠረ ፈጣሪ አለ አልኩ፡፡ ፈጣሪስ አለ፡፡ ፈጣሪ ባይኖር ፍጥረት ባልተገኘ አልኩ፡፡ እኛ ብንኖር ፍጡራን እንጅ ፈጣሪዎች አይደለንም፡፡ የፈጠረ ፈጣሪ አለ እንል ዘንድ ይገባናል፡፡ ይህም የፈጠረን ፈጣሪ አዋቂና ተናጋሪ ካልሆነ በቀር ከዕውቀቱ በተረፈ አዋቆዎችና ተናጋሪዎች አድርጎ ፈጥሮናል፡፡ ሁሉን ፈጥሯል ሁሉን ይይዛልና እርሱ ሁሉን ያውቃል፡፡ ፈጣሪየ ወደ እርሱ ስጸልይ ይሰማኛል ብየ ሳስብ ትልቅ ደስታ ተደሰትኩ፡፡ በትልቅ ተስፋም እየጸለይኩ ፈጣሪየን በሙሉ ልቤ ወደድኩት፡፡ ጌታየ ሆይ፤ አንተ ሃሳቤን ሁሉ ከሩቅ ታውቃለህ አልኩት፡፡ አንተ የመጀመሪያየ ነህ፡፡ የመጨረሻየን ሁሉን አወቅህ፡፡ መንገዴንም ሁሉ አንተ አስቀድመህ አወቅህ፡፡ ስለዚህም ከሩቅ ታውቃለህ ይሉሃል፡፡ እኔ ሳልፈጠር ሀሳቤን ያውቃልና ፈጣሪየ ሆይ እውቀትን ስጠኝ አልኩ፡፡

ስለ ሃይማኖት ምርመራና ፀሎት

በኋላም ይህ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጻፈ ሁሉ እውነት ይሆን? ብየ አሰብኩ፡፡ በጣም አላወቅሁምና የተማሩና ተመራማሪ ሰዎች እውነቱን እንዲነግሩኝ ሄጄ ልጠይቃቸው ብዬ ብዙ አሰብኩ፣ እንደገናም ሰዎች በየልባቸው ያለውን ካልሆነ በቀር ሌላ ምን ይመልሱልኛል ብየ አሰብኩ፡፡ ሰው ሁሉ የኔ ሃይማኖት እውነተኛ ናት ይላል፡፡ በሌላ ሃይማኖት የሚያምኑ ሐሰተኞች
የእግዚአብሔር ጠላቶች ናቸው፡፡ ዛሬም ቢሆን ፈረንጆች ሃይማኖታችን መልካም ናት፣ ሃይማኖታችሁ ግን መጥፎ ናት ይሉናል፡፡ እኛም መልሰን እንዲዚህ አይደለም፤ የናንተ ሃይማኖት መጥፎ፤ የኛ ሃይማኖት ግን መልካም ናት እንላቸዋለን፡፡
እንደገናም የእስልምና፣ የአይሁድ አማኞችን ብንጠይቃቸው እንዲሁ ይሉናል፡፡ በዚህም ክርክር ፈራጅ ማን ይሆናል? ሰዎች ሁሉ እርስ በእርሳቸው ወቃሾችና ተወቃሾች ሆነዋል፡፡ አንድ እንኳን ከሰው ልጅ የሚፈርድ አይገኝም፡፡ እኔ መጀመሪያ ስለብዙ ሃይማኖቶች ጉዳይ አንድ የፈረንጅ መምህር ጠየኩ፡፡ እሱ ግን ሁሉን እንደራሱ ሃይማኖት አድርጎ ፈታው፡፡ ኋላም አንድ ትልቅ የኢትዮጵያ መምህር ጠየቅሁ ፡፡ እርሱም ሁሉን እንደ ሃይማኖቱ አድርጎ ተረጎመው፡፡ እስልምና እና አይሁድንም ብንጠይቅ እንዲሁ እንደ ሃይማኖታቸው ይተረጉማሉ፡፡ ታዲያ እውነት የሚፈርድ የት አገኛለሁ? የኔ ሃይማኖት ለኔ ትክክል እንደሚመስለኝ እንዲሁ ለሌላውም ሃይማኖቱ እውነት ይመስለዋል፡፡ ነገር ግን ጽድቅ አንዲት ብቻ ናት፡፡

 እንደዚህ እያልኩ አሰብኩ፡፡ ጠቢብና የእውነተኞችም እውነተኛ እኔን የፈጠርክ ሆይ አዋቂ አድርገህ የፈጠርከኝ ሆይ፤ ዳዊት ሰው ሁሉ ዋሾ ነው ካለው በስተቀር በሰው ዘንድ ጥበብና እውነት አይገኝምና አንተ አዋቂ አድርገኝ ብዬ ጸለይኩ፡፡ ሰዎች በዚህ ትልቅ ነገር ነፍሳቸውን ለማጥፋት ስለምን ይዋሻሉ? ብየ አሰብኩ፡፡ የሚዋሹም መሰለኝ፡፡ የሚያወቁ እየመሰላቸው ምንም አያውቁምና የሚያውቁ ይመስላቸዋል፡፡ ስለዚህ እውነትን ለማግኝት ብለው አይመረምሩም፡፡ ዳዊት እንዳለው ልባችን እንደወተት ረካ፡፡ ከአባቶቻቸው በሰሙት ልባቸው ረክቷል፡፡ እውነት ወይም ሀሰት ሊሆን ይችላል ብለው አልመረመሩም፡፡ እኔም ጌታ ሆይ ፍርድህን እንዳውቅ ያሳመንከኝ ይገባኛል አልኩ፡፡
አንተ በእውነት ቅጣኝ፣ በምህረትህም ገስጸኝ፡፡ አንተ አዋቂ አድርገህ የፈጠርከኝ ጥበበኛ አድርገኝ እንጅ የዋሾ መምህራንና የኃጢአት ቅባት እራሴን አልቀባም፡፡
እኔ አዋቂ ብሆን ምን አውቃለሁ ብየ አሰብኩ፡፡ ከፍጥረት ሁሉ የሚልቅ ፈጣሪ እንዳለ አውቃለሁ፡፡ ከታላቅነቱ የተረፈ ታላላቅን ፈጥሯልና፡፡ ሁሉንም የሚያውቅ ነውና፡፡ ከአዋቂነቱ በተረፈ አዋቂዎች አድርጎ ፈጥሮናልና፡፡ ለርሱ ልንሰግድለት ይገባል፡፡ እርሱ የሁሉ ጌታና ሁሉንም የያዘ ነውና ወደርሱ በጸለይን ጊዜ ይሰማናል፡፡ እግዚአብሔር አዋቂ አድርጎ የፈጠረኝ በከንቱ አይደለም፡፡ እንዲህ አድርጎ የፈጠረኝ እንድፈልገውና እርሱ በጥበቡ በፈጠረኝ መንገድ እንዳውቀው እስካለሁም ድረስ እንዳመሰግነው ነው ብየ አሰብኩ፡፡ ሰዎች ሁሉ ሀሰት ካልሆነ በስተቀር ስለምን እውነት አይናገሩም ብየ አሰብኩ፡፡

Saturday, July 26, 2014

መጠጥና ዘፈን ጨለማን ተገን አድርገው መልካም ስብከት ሲሆኑ ልብ በሉ !

(ከአሌክስ አብረሃም  ጽሁፍ) በመካነ ጦማሩ ተሻሽሎ የቀረበ

ወገኖቸ እሰብካችኋለሁ !! በደሌ ቢራ አትጠጡ እንደተባለ ሰምታችኋል...... እኔ ግን እላችኋለሁ ባጠቃላይ አልኮል መጠጥ አትጠጡ ! ለጤና ጠንቅ ነውና !! መጠሃፉ ‹‹ደሃ ድህነቱን እንዲረሳ የወይን ጠጅ ስጠው ›› ቢልም እኛ ኢትዮጲያዊያን <አስራ አንድ> በመቶ እያደግን ያለን ሃብታም ህዝቦች ነንና እኛን አይመለከትም !
አዎ ! መጠጥ አገር እያጠፋ ነው ትዳር እየበጠበጠ ነው።  ይሄ ሁሉ ያማረበት ጠጭ ብርጭቆውን በቄንጥ ይዞ ውሰኪውን የሚከነብል ይሄን ሆንኩ ሳይል ወጋኝ ፈለጠኝ ሳይል ድንገት የሚከነበለው ለምን ይመስላችኋል ......መጠጥ .....መጠጥ ነው ወገኖቸ !! ህዝቤ ቁሞ ይንከላወሳል እንጅ ጉበቱ እኮ የለም .....ሳንባውኮ በጥቃርሻ ተዥጎርጉሮ የሚያፈስ ኮርኒስ መስሏል። ......ነብሱ አድፏል ! ይሄ ሁሉ የሆነው በምንድን ነው በመጠጥ !! መጠጥ እንዝህላል ያደርጋል፤ ግዴለሽ ያደርጋል፤ ዋጋ ቢስ ያደር .... ጋል ወገኖቸ .....
ዛሬ እኮ ምፅአት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ ሲባል ‹ሎ...ል› የሚል ወጣት ነው እያፈራን ያለነው .... ትውልዱ በቀቢፀ ተስፋ የሚይዝ የሚጨብጠውን አጥቷል ቤተስኪያኖቻችን  ርግብና ዋነስ  ሰፍሮባቸው  ካለሰው  እየዋሉ  ቡና ቤቱ  በሰው ተጨናንቋል ..... ጭፈራ ቤቱ ካፍ እስከገደፉ ሞልቷል ..... ጥርሱ በጫት ያለቀ፤ በሺሻና በሀሺሽ የናወዘ ትውልድ መቅኖ የለውም። ፈጣሪውንም አያውቅም።
ስለሳምሶን ታሪክ ሰምታችኋል (ለነገሩ መቸ መጠሃፉን ታነቡና ፌስ ቡክ ላይ አፍጥጣችሁ እየዋላችሁ ) ሳምሶን ታላቅ የህዝብ ነፃአውጭ ነውና ሲረገዝ እናቱ የአልኮል መጠጥ በአፏ እንዳይዞር እግዜር አዟት ነበር ! ለትውልድ የምታስብ ሴት እንዲያ በክብርና በቅድስና ትኖር ዘንድ መፅሃፉ ያዛል !
ዛሬ ግን ሴቶቻችን በየመሸታው አኮሌ ሙሉ መጠጥ ሲገለብጡና ሲያሽካኩ ያመሻሉ ያድራሉ የረከሰ ትውልድ ከሰካራም  እናት ይወለድ ዘንድ ስምንተኛው ሽ ቀርቧል ! ወንዱ መቸስ አንዴውኑ ጠጥቸ ልሙት ብሏል ! ደግሞኮ የድሮ መጠጥ  ሲያሰክር  ጀግና ያደርጋል የልብን ያናግራል። ጀምበሯ ዘቅዘቅ ማለት ስትጀምር ትውልዱ መጠጥ የሚሉትን የመርዝ ብርጭቆ አፉ ላይ ለግዶ ሞት ይጨልጣል።
.....የለም ! ወንዱ ሰክሮም ፈሪ ባይሰክርም ፈሪ ነው ! ቤቱ ገብቶ ሚስቱና ቤተሰቡ ላይ ነው የሚደነፋው ! ወገኖቸ ስካር ድሮ ቀረ !! ስለዚህ አልኮል መጠጥ አትጠጡ ! እንደአሸን የሚፈላው  የቢራ ፋብሪካና  መጠጥ ቤት የዝሙት ቤት ድራሹ  ይጥፋ ለአንድ ሽ ሰው የስራ እድል ፈጠረ የምንለው የመጠጥ ስራ ሚሊየኖችን ከሰውነት ክብር ካወረደ አትጠጡ !!
ይሄ  ውስጡ ኑሮ የሚጮህበት ህዝብ  ጩኸቱን  በጩኸት ለማጨናበር ዲጀ ማንትስ እከሊት  ጭፈራ ቤት እያለ ሲያላዝን ያመሻል። የውስጥን ጩኸት በውጭ ጩኸት  ለጊዜው  ነው ማጥፋት  የሚቻለው .....እናም  እላለሁ መጠጥ አትጠጡ !! አልኮል በደረሰበት አትድረሱ ! አልፎ አልፎ  ምናለበት ለምትሉ ለእናንተ  እላለሁ!  መጠጥ ሞት አለበት፤ መርከስ፤ ውርደት፤ ክስረት፤ ጩኸት፤ጥልና ክርክር፤ግድያም ሳይቀር አለበት !!
 ወገኖቸ የቴዲ አፍሮን ዘፈን አታዳምጡ እንደተባለ ሰምታችኋል ..... እኔ ግን እላችኋለሁ ባጠቃላይ ዘፈን አታዳምጡ .....መጠሃፉ ዘፋኝነት ዝሙት ሴሰኝነት ሰውን መግደል ..... እኩል  ሃጢያት ናቸው ብሏልና  ትውልዱን  እያዘናጉ ሲያስጨፍሩትና ሲያዘልሉት የሚኖሩትን  ስለምን  ትከተላላችሁ .....ዘፈን  የዝሙት  ቀኝ  እጅ  ነው ! ጥበብ ነው እያሉ ሌላ ነገር እንዳታስቡ የሚያጠቧችሁ ጠላቶቻችሁ ዘፋኞች ናቸው ! ብሶታችሁን  ከመናገር ይልቅ ከበሯቸውን  እየደለቁ  ሴት አሰልፈው  ሲያደንዟችሁ  የሚውሉት  እነሱ አይደሉምን? ጭንሽንና ዳሌሽን የሚል ዘፋኝ የዝሙት ሰባኪ አይደለምን? ፈራሽና በስባሽ ገላን እየጠራ፤ ልብህን ወደዚያ ከሚጎትት ዘፋኝ ወዲያ ዘመናዊ ጠላት ከወዴት ይገኛል? በመጠጥ ያሰክሩሃል፤ በዘፈን ወደዝሙት ይጠሩሃል።
ደግሞስ ጠጪና ዘፋኝ ትውልድ ሀገራዊ ርእይ፤ መንፈሳዊ ህልም እንዴት ይኖረዋል? ትልቁ ሀብቱ የደነዘ አእምሮና የፈጠራ ወሬ ብቻ ነው።
ሰለጠኑ ወይም ሰየጠኑ በሚባሉት ሀገሮች መጠጥ ቤት ተሰልፎ ከጠርሙስ አንገት ስር የሚገኘው ቦርኮ፤ ህልምና ርእዩን የገደለ፤ በሸሺሽ የደነዘዘ፤ በመንግሥት ድጎማ የሚኖር ተስፋ የለሽ እንጂ ጤናማ ሰው አይደለም። በሀገራችን ግን ብርጭቆ ጨብጦ በየሆቴሉ፤ በየድራፍት ቤቱና በየበረንዳው ሲጠጣ አምሽቶ ሲጠጣ የሚያድረው ከላይ እስከታች ከሊቅ እስከደቂቅ መሆኑያሳፍራል፤ ያሳዝናል።  መጠጥና ዘፈን ሁለት የሀገር ጠላቶች ናቸው። በመንፈሳዊው ዓለም ኃጢአቶች ናቸው፤ በሥጋዊውም ዓለም ቢሆን ከመጠጥ ሻጩና ከዘፋኙ በስተቀር ዘፈን እያዳመጠ፤ ሲጠጣ ካደረ ትውልድ ማንም ያተረፈ የለም።  ኪሳራ፤ ኪሳራ፤ ኪሳራ ብቻ!
እናም እላችኋለሁ፤ እባካችሁ መጠጥ አትጠጡ! መጠጥ ቤቶች የበዙት የሚያከስሩትንና የሚገድሉትን ትውልድ ለማብዛት እንጂ አእምሮውንና ኪሱን ለመገንባት አይደለም። ዝሙት ለማስፋፋት፤ ተላላፊ በሽታን ለማዛመት በህጋዊ ፈቃድ ከለላ ስውር ወንጀል የሚፈጽሙ የጥፋት ስፍራዎች ናቸውና መጠጥ ቤቶችን አጥብቃችሁ ሽሹ! ሁለት ሞት ትሞታላችሁ፤ በስጋም በነፍስም!

«ዋይታ ለማን ነው? ኀዘን ለማን ነው? ጠብ ለማን ነው? ጩኸት ለማን ነው? ያለ ምክንያት መቍሰል ለማን ነው? የዓይን ቅላት ለማን ነው? የወይን ጠጅ በመጠጣት ለሚዘገዩ አይደለምን? የተደባለቀ የወይንን ጠጅ ይፈትኑ ዘንድ ለሚከተሉ አይደለምን?
ወደ ወይን ጠጅ አትመልከት በቀላ ጊዜ፥ መልኩም በብርሌ ባንጸባረቀ ጊዜ፥ እየጣፈጠም በገባ ጊዜ። በኋላ እንደ እባብ ይነድፋል፥ እንደ እፉኝትም መርዙን ያፈስሳል። ዓይኖችህ ጋለሞታዎችን ያያሉ፥ ልብህም ጠማማ ነገርን ይናገራል። በባሕር ውስጥ እንደ ተኛ ትሆናለህ፥ በደቀልም ላይ እንደ ተኛ። መቱኝ፥ ያውም አልተሰማኝም ጐሰሙኝ፥ አላወቅሁምም። መቼ እነሣለሁ? ደግሞ ጨምሬ እሻታለሁ ትላለህ»  ምሳሌ 23፤29-35


ጆሮ ያለው ይስማ! ልብ ያለው ያስተውል!

Wednesday, July 23, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!

(እዝራ ስነጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)
የመጨረሻ ክፍል

የተአምረ  ማርያም  ጸሐፊዎች  ሰዎችን  በማስፈራራትና  በማስደንገጥ የማይመረምሩትና  ከገዢው  ቃል  ጋር  የማያስተያዩት  ሃይማኖት  ግዞተኛ አድርገው  ለማኖር  የፈጠሩት  ፈጠራ  ከተፈጥሮና  ከስነ  ፍጥረትም ከአእምሮም  ጋር  የሚጋጭ  ነው።  እነዚህ  ናሙና  ከስነ  ፍጥረት  ሕግ  ጋር የሚጋጩ ያፈነገጡ ታሪኮች ናቸው።

ጥቂት ተጨማሪ ናሙና ግጭቶች

መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚናገረው  መደመጥና  መከበር  እንዳለበት  ሁሉ  ዝም ባለበት  ጉዳይ  ሁሉ  ዝምታውም  መከበር  አለበት  እንጂ  በራሳችን  ምናብ የተፈተሉ  ነገሮችን  እየፈጠርን  ያላለውን  ማስባል  የለብንም።  የኢየሱስ የልጅነቱ  ዘመናት  ታሪኮች  በወንጌላት  ውስጥ  አልተጻፉም።  ያልተጻፉት አስፈላጊ  ስላልሆኑ  ነው።  ቢሆኑ  ኖሮ፥  እኔ  ደግሞ  ስለ  ተማርኸው  ቃል እርግጡን  እንድታውቅ  በጥንቃቄ  ሁሉን  ከመጀመሪያው  ተከትዬ በየተራው  ልጽፍልህ  መልካም  ሆኖ  ታየኝ    ያለውና  ከወንጌላቱ  ሁሉ በዝርዝር የዘገበው ሉቃስ ይህን አይጽፍም ኖሮአል?

   ስሟስ? የማርያምን  የስሟን ትርጉም በመቅድሙ  ላይ  “መንግሥተ  ሰማይ መርታ  የምታገባ”  ማለት  ነው  ሲል  ይተረጉማል።  በሌሎችም  ቦታዎች፥ ለምሳሌ፥  ምዕ.  12፥  74፥  98  ወዘተ፥  በዕብራይስጥ  ማሪሃም  የተባለች እያለ ተመሳሳይ ስምና ትርጉም ያቀርባል። እንዴት ፈጥረው ቢተረጉሙት ነው  ባለ  አራት  ፊደል  ስም  ይህ  ሁሉ  ቃል  ያለበት  ትርጉም  የሚሰጠው?
መምራት፥  ማስገባት፥  እና  መንግሥተ  ሰማያት  የሚባሉት  ቃላት  ማርያም ወይም  ሚርያም  በሚባለው  ስም  ውስጥ  ከቶም  የሉም።  በመጀመሪያ በዕብራይስጥ  ማሪሃም  አትባልም፤  ሚርያም  ናት።  ማርያም  በምንም ቋንቋ፥  በዐረብኛም  እንኳ  ማሪሃም  አልተባለችም።  ደግሞም  የስሟ ትርጉም  የተለያዩ  አገባብ  ትርጉሞችም  እንኳ  ተጨምረው  ዓመጽ፥ እንቢተኝነት፥ መራራ፥ መራራ ባሕር ማለት ነው እንጂ መንግሥተ ሰማይ መርታ  የምታገባ  ማለት  አይደለም።  ይህ  አልዋጥ  ካለንም  በግድ እንዋጠው፤ ዕብራይስጥ ብለን ከጠቀስን ትርጉሙ ይኸው ነው። በተአምር  21  ኢየሱስና  ማርያም  ለሐዋርያት  ተገልጠው  ጌታ  ለሐዋርያት በእርሱና  በእናቱ  ስም  በ4ቱ  ማዕዘናት  አብያተ  ክርስቲያናት  ይሠሩ  ብሎ አዘዘ።  በስሟ  ቤተ  ክርስቲያን  ማነጽ  ቀርቶ  ሐዋርያት  ስሟን  ጠርተው ሰብከው  ያውቃሉ?  በምዕ. 7  ደግሞ  ዕርገቷን  በ4ቱ  ማዕዘን  እንዲያውጁ አዘዛቸው  ይላል።  ሐዋርያት  እንዲህ  ተብለው  ይህን  አለመጻፋቸው ይደንቃል!  የታዘዙትን  ቤተ  ክርስቲያን  አለመሥራታቸውም  ዕርገቷን
አለማወጃቸውም  ያስጠይቃቸዋል።  አንዱን  ቤተ  ክርስቲያን  ጴጥሮስ እዚያው  ማነጹ  ተጽፎአል።  በአዲስ  ኪዳንና  በመጀመሪያዎቹ  የቤተ ክርስቲያን  ታሪክ  ዘመናት  ውስጥ  ክርስቲያኖች  ምእመናንን ሲያንጹ እንጂ ሕንጻ  ሲሠሩ  አይታወቅም።  ያመልኩ  የነበረውም  በምኩራቦችና  በቤት ውስጥ  እንጂ  ሕንጻስ  አላነጹም።  ማርያም  ለመጨረሻ  ጊዜ  በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ  የተጠቀችውም  ይኖሩበት  በነበረው  በተባለው  ሰገነት ውስጥ  ከጌታ  ሐዋርያት፥  ከደቀ  መዛሙርትና  ከወንድሞቹ  ጋር  በጸሎት ስትተጋ  ነው  የታየችው  እንጂ  ሰዎች  ወደ  እርሷና  ወደ  ስዕሏ  ሲጸልዩ አትታይም፤  ሐዋ. 1፥14  እነዚህ ሁሉ  ከሴቶችና  ከኢየሱስ  እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር ይላልና።

     ይኼ ሁሉ  የተደረተባት  ድሪቶ  ማርያምን  እንደሚያሳዝናት  የታወቀ  ነው። በእውነቱ  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ደራሲዎቹ  በመልካቸው እንደምሳሌያቸው  የፈጠሯት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ከቶም አይደለችም።  እምነታችንንም  ራስና  ፈጻሚውን  ኢየሱስን  ተመልክተን ከተባለለት  ከኢየሱስ  ሰዎች  ዓይናቸውን  እንዲያነሡ፥  እንዲያውም ከቶውኑ  እንዳያዩት ተብሎ  የተፈጠረችና ማርያም  ተብላ  የተሰየመች  ሴት ናት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሷ  ማርያም  ዛሬም  ብትጠየቅ  ያኔ  እንዳለችው፥ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ የምትል ናት።
በተአምር  4  ላይ  ማርያምን  ለመገነዝ  ሲሄዱ  ታውፋንያ  የተባለ  አይሁድ አልጋዋን  ስለያዘ  እጁ  በመልአክ  ተቆርጦ  አልጋው  ላይ  ቀረ።  ይህ  ሰው ሐዋርያትን  ይቅርታ  ጠየቀ፤  ክርስቶስንም  ይቅር  እንዲለው  ለመነ። ሐዋርያት  ግን  ወደ  እመቤታችን  ለምን  አሉት።  ማርያም  ቀድሞውኑ ከሞት  ተነሥታ  ነበርና  ለመናት።  ማርያምም  ጴጥሮስን  እንዲቀጥልለት ነገረችው። ጴጥሮስም በክርስቶስ ስምና በማርያም ስም እጁን መለሰለት። ይህ  ጴጥሮስ  ሐዋርያው  ጴጥሮስ  ከሆነ  መቸም  ይደንቃል።  ይህ  ጴጥሮስ በሐዋ.  3፥6  ብርና  ወርቅ  የለኝም፤  ይህን  ያለኝን  ግን  እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው ያለውና በኋላ በዚህ ስም ላይ ሌላ የለጠፈበት ነው? ይህ ጴጥሮስ በሐዋ. 4፥12 መዳንም በሌላ  በማንም  የለም፤  እንድንበት  ዘንድ  የሚገባን  ለሰዎች  የተሰጠ  ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና  ያለው ነው? እንዴት ያለ ቁልጭ  ያለ ግጭት ነው?  ይህ  የተከሰተው  ከሐዋ. 3  እና  4  በኋላ  ነው  ቢባል  ጴጥሮስ  ብዙ ቆይቶ  በጻፈው  በመልእክቱ  ምነው  የማርያምን  ስም  እንዲያው  አንዴ እንኳ  ያላስገባው?  ይህ  በኢየሱስና  በማርያም  ስም  ብሎ  እንደተናገረ የተጻፈለት  ጴጥሮስ  በመልእክቱ  ውስጥ  በ1ጴጥ. 4፥14  ስለ  ክርስቶስ  ስም ብትነቀፉ የክብር መንፈስ የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ላይ ያርፋልና ብፁዓን  ናችሁ  ያለውና  የክርስቶስን  ስም  ብቻ  ያጎላውና  የእርሱን  ብቻ ማንነት  አጉልቶ  የገለጠው  ነው?  ነው  ቢባል  እንኳ  የቱን  እንቀበል?  መጽሐፍ ቅዱስን ወይስ መጽሐፍ ቅዱስን የሚጻረረውን ሌላ መጽሐፍ? በተአምር  3  ማርያምን  ለመቅበር  ሲሄዱ  ሐዋርያት  ሁሉ  ጥለዋት  ተበተኑ ከዮሐንስ  በቀር  ይላል።  ልክ  ጌታ  ሲያዝ  እርቃኑን  በነጠላ  ከሸፈነው ዮሐንስ  በቀር  ሁሉ  እንደሸሹ  ይህንንም  የጻፈው  ይህ  ደቀ  መዝሙር መሆኑ  እንደተጻፈ  እዚህም  የፍልሰቱን  መጽሐፍ  የጻፈ  እርሱ  መሆኑ
ተጽፎአል።  የዚህ  ምዕራፍ  ግጭት  ከምዕ.  6  ጋር  ነው።  በተአምር  3  ጥለዋት  ተበተኑ  ሲል  በተአምር  6  ፈጽሞ እንዳልጣሏት፣  ግን  ገንዘው፥ ታቅፈው፥  ተሸክመው  እጅ  ነስተው  በጌቴሴማኒ  ቀበሯት  እንጂ አልጣሏትም ይላል። የቱ ነው ትክክል? ምዕ. 3 ወይስ 6? ለነገሩ የተለያዩ ሰዎች  ያዋጡት  መጽሐፍ  ስለሆነ  እንዲህ  እርስ  በርሱ  ቢጋጭ አያስገርምም።
በምዕ. 10  ኢየሱስ  በዋሻ  ውስጥ  መወለዱና  በጨርቅ  መጠቅለሉ  ሳይሆን የበለስ ቅጠል መልበሱ፥ በምዕ. 11 ደግሞ በጨርቅ መጠቅለሉ ተጽፎአል። በመንገድ  መካከል  ተወለደም  ይላል።  ይህ  የራስ  ከራስ  ግጭት  ነው።
መልአክ  ሄዶ  ለሰብዓ  ሰገል  እንደነገራቸው፥  ሰብዓ  ሰገል  ደግሞ  ሽቱም አምጥተውለት  እንደነበር  ተጽፎአል።  እነዚህ  ሁሉ  የተጻፈ  ታሪክን የሚያፋልሱ ናቸው።

    ከንጉሥ  ልጇ  ደም  በፈሰሰ  ደሟ  እኛን  ንጹሐን  አድርጋ  . . .  ይላል  ምዕ. 12፥54።  የማን  ደም  ነው  የፈሰሰ?  የማን  ደም  ነው  ያዳነ?  የማርያም  ደም ያዳነ በሆነማ  ኖሮ  ክርስቶስ ምነው  በመስቀል መዋሉ? ቃሉ በኤፌ. 2፥13  የሚለው አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ  በክርስቶስ  ደም  ቀርባችኋል  ነው  እንጂ  ከልጇ  በፈሰሰው በማርያም ደም  ቀርባችኋል  አይልም።  ጳውሎስ  ኤፌሶንን  ሲጽፍ ማርያም ሞታ  ወይም  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  አርጋ  ስለነበረ  ጳውሎስ ይህንን  ማወቅ  ነበረበት።  ቆላ.  1፥19  በመስቀሉ  ደም  ሰላም  ማድረጉን ይናገራል፤  ሌላ  ደም  አይናገርም።  ዕብ.  9  በሙሉው  ይህንን  ደም ይናገራል  እንጂ  የማርያም  ደም  አይልም።  1ጴጥ. 1  የተዋጀንበትን  ክቡር ደም የክርስቶስ ደም ይለዋል እንጂ የማርያም አይለውም።
በምዕ.  7  በፍልሰቷ  ቀን  (ለነገሩ  ቀኖቹ  ሁሉ  በኛ  አቆጣጠር  ነው የተጻፉትና  በግብጽ  ወይም  በአይሁድ  ቆጠራ  ተጽፈው  መመንዘራቸው አልተነገረም)  በነሐሴ  16  ተዝካሯን  ለዘከረ  ኃጢአቱ  እንደሚሰረይ  ጌታ እንደሰጠ  ይናገራል።  በጣም  ትልቅ  ግጭት!  ኃጢአት  የሚደመሰሰው በነሐሴ  16  ተዝካር  ማድረግ  ከሆነ  መጽሐፍ  ቅዱስ  ከሚለው  ጋር  ፈጽሞ ይጣላል።  በክርስቶስ  በማመን  በጸጋ  ድኖ  በመስቀል  ላይ  በፈሰሰ  ደሙ የኃጢአት  ማግኘት  ወይስ  ደግሶ  አብልቶ  መዳን?  ወይስ  ከሁለቱ  ደስ ያለንን መርጠን መውሰድ?
በተአምር  32  ስለ  አንዲት  ዘማዊት  ይናገራል።  እንደ  ሙሴ  ሕግ እንድትወገር  እንደተፈረደ  ይናገራል  ደግሞም  ቤተ  መቅደስ  ውስጥ  ገብታ ይላልና  ደግሞም  በአዲስ  ኪዳን  ኃጢአተኛን  በድንጋይ  መውገር  የለምና ይህ  የብሉይ  ኪዳን  ዘመን  ይመስላል።  እንዳይባል  ደግሞ  ዘማዊቷ የማርያምን  ስዕል  አግኝታ  ለመነች  ይላል።  መልእክቱ  ወደ  ስዕል  ለምኖ መፍትሔ  ማግኘት  ቢሆንም  በመቅደስ  ውስጥ  የማርያም  ስዕል  ሊኖር አይችልም።  የቤተ  ክርስቲያን  መቅደስ  ነው  ከተባለ  ደግሞ  በቤተ ክርስቲያን  ወይም  በክርስትና  ዘመን  ኃጢአተኛን  መውገር  ከየት  የመጣ ፍርድ ነው? እርስ በራሱ የተማታ ታሪክ ነው።
ሰይጣን  መንፈስ  ነው  እንጂ  ስጋዊ  አካል  አይደለም።  በምዕራፍ  34  ሰይጣንን ማርያም በጥፊ አጩላው ልቡናውን ሲስት ይታያል። በምዕራፍ 51  ደግሞ  የመነኮሳትን  ምድጃ  ስላፈረሰ  አንድ  ሰይጣን  ተጽፎአል። መነኮሳቱ  ወደ  ማርያም  ጮኹና  ለ12  ዓመታት  ባሪያ  ሆኖ እንዲያገለግላቸው  ምድጃቸውን  ያፈረሰውን  ያንኑ ሰይጣን ሸለመቻቸው።
እነዚህ  መነኮሳት  ሰይጣንን  ተቃወሙት  የሚለውን  ቃል  አይታዘዙም ማለት  ነው።  ወይም  ቃሉን  ጨርሶውኑ  አያውቁም  ማለት  ነው።  ሳያውቁ ግን  መነኩሴዎች  ናቸው።  ማዕድ  ቤት  አስገብተው  እየፈጨ፥  እያቦካ፥ እየጋገረ ዓሳ ነባሪ እያጠመደ ከመርከብ ጋር እየተሸከመ አምጥቶ መርከቡ ውስጥ  የነበሩትን  ሰዎች  የሚያስመነኩስ  ይህ  አገልግሎት  ከማዕድ  ቤት ሥራ ያለፈ ነው!
    በምዕራፍ  37  ማርያም  ቴክላ  ወደተባለች  ሴት  ሄዳ  ስታስተዛዝናት፥ ልጇን  30 ዓመት በሆነው  ጊዜ  ከእርሷ ቀምተው  በእንጨት  ላይ ሰቅለው እንደ  ገደሉት  ነገረቻት። ጌታ ከማርያም  ተቀምቶ  ተገደለ  ወይስ ቀድሞም ሊሞት  ነው  የመጣው?  ደግሞስ  በ30  ዓመቱ  ነው  የተገደለው?  ሉቃ.  3፥23  በሠላሳ  ዓመቱ  አገልግሎቱን  መጀመሩን  ነው  የጻፈው።  ሳያገለግል ነው የተሰቀለው ማለት ነው? ተአምረ ማርያም ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ገድሎች ጋርም ይጋጫል፤  ይጣላል።  አንድ  ብቻ  ምሳሌ  ለመውሰድ፥  በገድለ  ተክለ ሃይማኖት  በመግቢያው  ምዕራፍ  ቁ.  40-46  እና  80-81  “.  .  .  አባቴ የሚለው  ግን  ዝክሩን  የሚዘክር  ስሙን  የሚጠራ  ከሱ  ጋራ  የዘላለም ሕይወት  ያገኛል  ዝክሩን  ያልዘከረ  ቃሉን  ያልጠበቀ  ከርስቱ  ከመንግሥተ ሰማያት  የተለየ  ይሆናል  የሞቱ  ሰዎችን  ነፍስ  ሁሉ  ክርስቲያን  የሚባሉ ጻድቅም  ኃጥእም  ቢሆን  የሞቱትን  ከክቡር  አባታችን  ከተክለ  ሃይማኖት ዘንድ  ሳያደርሱ  አይወስዳቸውምና  . . .  ለሥጋችሁ  መጠበቂያ  ለነፍሳችሁ መዳኛ  ነውና፤  ኃጢአታችሁን  የሚያነጻ  .  .  .”  ይላል።  እዚህ  ተክለ ሃይማኖት  የመንግሥተ  ሰማያት  መንገድ፥  የነፍስ  መዳኛና  የኃጢአት ስርየት  ሆኖ  ተገልጦአል። 16
   ማርያም  ወደ  መንግሥተ  ሰማይ  መርታ የምታስገባ  ተብላለች  ተክለ ሃይማኖትም በሩ  ከሆነ  የመዳን መንገዱ ብዙ ነው ማለት ነዋ! የማርያም ዝክር ነው መዳኛው ወይስ የተክለ ሃይማኖት?
በምዕ.  98  ስለ  ይሁዳ  እግረ  መንገድም  ቢሆን  የተነገረው  ጌታን  ሽጦ እናቱን  አግብቶ  አባቱን  መግደሉ  ተጽፎአል።  ቅደም  ተከተሉ  እንደዚያ ከሆነ  እናቱን  አግብቶ  አባቱን  የገደለው  ጌታን  ከሸጠ  በኋላ  ነው  ማለት ነው።  በትክክል  የሞተው  መቼ  እንደሆነ  ባይታወቅም  ተጸጽቶ  ወዲያው ሄዶ  ነው  ታንቆ  የሞተውና  (ማቴ.  27፥1-10)  ጋብቻውም  ግድያውም በሰዓቶች  ውስጥ  ምናልባት  በደቂቃዎች  መሆን  አለበት።  ያለዚያ  እናቱን አግብቶ  አባቱን  የገደለውንና  የአይሁድ  ሕግ ዝም  ያለውን  ሰው  ነው  ጌታ ከሐዋርያቱ ክልል ያስገባው።
     በምዕ. 121  ኢየሱስን  በ8  ዓመቱ  በጎች  እንዲጠብቅ  ላከችው  ይልና  ወደ ደብረ ዘይት መጥቶ በጎቹን አሰማራ ይላል። ለማያውቅ ሰው ልክ  እሰፈር ዳርቻ  በጎቹን  ወስዶ  የመሰገ  ይመስላል።  የሚኖሩት  ናዝሬት  በጎች የሚጠብቀው  ደግሞ  ደብረ  ዘይት  መሆኑን  እንደገና  እናስተውል።  ደብረ ዘይት እኮ ከናዝሬት የ105 ኪሎ ሜትር ሩቅ አገር ነው። በኛ አገር ከአዲስ አበባ  ናዝሬት  ማለት  ነው።  መልክዓ  ምድሩን  ለማያውቁና  ለማይጠይቁ ወይም  የተባለውን  ሁሉ  እውነት  ነው  ብለው  ለሚቀበሉ  አድማጮች የተጻፈ  በመሆኑ  ደራሲዎቹ  ይህን  እና  ይህን  የመሰሉትን  ግጭቶች ለመመርመር ሙከራ አላደረጉም።
በምዕ.  120  ኢየሱስን  በ5  ዓመቱ  የሚያስተምረው  አስተማሪ፥  “ይህ የመበለት  ልጅ”  ይለዋል።  ማርያም  መበለት  ሆነችሳ!  ዮሴፍ  ሞተ  ይሆን?
መቼም  የኢየሱስ  አስተማሪ  ተአምረ  ማርያም  እንደሚለው  ዮሴፍ “ጠባቂዋ”  መሆኑን  አያውቅም።  በምዕ. 121  ደግሞ  በ8  ዓመቱ  አሳዳጊው ዮሴፍ  ተጠቅሶአል።  በወንጌሉ  ውስጥ  ደግሞ  በ12  ዓመቱም  በሕይወት መኖሩ  ተዘግቦአል።  በተአምረ  ማርያም  ዮሴፍ  የማርያም  እጮኛ  እንኳ ሆኖ  አልቀረበም።
ሲደመደም፥  ተአምረ  ማርያም  ለሥጋዊ  አኗኗርና  ለኃጢአተኛ  ተፈጥሮ የሚስማማ  መጽሐፍ  ነው።  መጽሐፍ  ቅዱሳዊ  የቅድስና  አመላለስ፥ ክርስቶስን  መምሰል፥  ዋጋ  መክፈል፥  ለእውነት  መሰደድ  በውስጡ የሉበትም።  ክርስቶስን  አዳኝ  አድርጎ  መቀበልና  የሕይወት  ጌታ  አድርጎ እርሱን  መከተል  የሉበትም።  በምንም  ኃጢአት  ውስጥ  ተኑሮ  ለስዕል አቤት  ከተባለ፥  ዝክር  ከተዘከረ፥  በማርያም  ስም  አንዳች  ከተደረገ መንግሥተ  ሰማያት  የመግባት  ተስፋ  አለ።  ስለዚህ  እንደፈለጉ  ኖሮ ማርያምን  ጠርቶ  መናገርና  እርሷ  ደግሞ  ለልጇ  ተናግራ  የሚሹትን  ሁሉ ማድረግ ስለምትችል መልካሙን ገድል መጋደል አይታወቅም። ተአምረ  ማርያምን  ማሔስን  ካላቆሙት  በቀር  መቆም  አይችልም።
ምክንያቱም  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ከራሱ  ከመጽሐፉ  ሌላ  ምዕራፍ፥ ከታሪክና  ከእውነት፥  ከአእምሮና  ከተፈጥሮ፥  በተለይም  ከመጽሐፍ  ቅዱስ ጋር  በምሬት  የሚጣላ  መጽሐፍ  ነው።  በአጭር  ቃል  ተአምረ  ማርያም ጠላት ከዘራቸው ብዙ እንክርዳዶች አንዱ ነው።
ጌታ ከአርያም ይባርካችሁ።
ዘላለም መንግሥቱ  © 2012 (፪ሺህ፬) ዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት
1 ሰውና እግዚአብሔር በኃጢአት ምክንያት ተለያዩ
3. ሰው በራሱ ጥረት ወደ እግዚአብሔር መድረስ አይችልም።
በመጣጥፉ ውስጥ የተጠቀሱ መጻሕፍት፤
በአባቶቻችን  አፈርን፥  ባዩ  ታደሰ  እርዳቸው  (መምህር)፥
[ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም] አዲስ አበባ፥ ፪ሺህ፫ ዓ. ም.።
ይነጋል፥  ጽጌ  ስጦታው  (ዲያቆን)፥  አፍሪካ  ማተሚያ፥  አዲስ
አበባ፥ Ŧ ŹƃƂƋ ዓመተ ምሕረት።
ገድለ  አቡነ  እስጢፋኖስ  ዘጉንዳጉንዶ፥ 1997   ዓ.  ም.  አሳታሚ፥
መምህር ወማኅበር ዘጉንዳጉንዶ ደብረ ገሪዛን።
ለእውነት እንቁም፥ ስሜ ታደሰ፥ SIM Publishing፥ አዲስ አበባ፥
፪ሺህ ፬ ዓ. ም.።
ገድለ ተክለ ሃይማኖት፥ [አሳታሚና ማተሚያ ቤት አልተጠቀሰም]
አዲስ አበባ፥ 1989 ዓ. ም. ።
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በአስተዋጽዖ፥ መሠረት ስብሐት
ለአብ፥  አሳታሚ  ፍኖተ  ሕይወት  ማኅበረ  መነኮሳት፥  የኅትመት
ዘመን አይታወቅም፥ አዲስ አበባ።
ገድለ  ክርስቶስ  ሠምራ፥  ትንሣኤ  ዘጉባኤ  ማተሚያ  ቤት፥  አዲስ
አበባ፥  1992ዓ. ም. ።
Schaff, Philip,  History of the Christian Church,  Nicene
and Post Nicene Christianity,  T & T Clark, Edinburgh,
1884.
Tamrat, Tadesse,  Church  and State in Ethiopia  1270-1527, Oxford University Press, London, 1972.

Friday, July 18, 2014

በኢየሩሳሌም ገዳም መነኮሳትና በሊቀ ጳጳሱ መካከል የተከሰተውን አለመግባባት ለመመልከት የተሰየመው አጣሪ ጉዳዩን ለማየት መጓዙ ታወቀ።




በኢየሩሳሌም ገዳም መነኮሳትና በገዳሙ ሊቀጳጳስ በአባ ዳንኤል መካከል በተከሰተው አለመግባባት ያለውን ችግር ለመፍታት ቋሚ ሲኖዶስ እንዲጣራ ውሳኔ ማሳለፉ ይታወሳል። ከዚህ በፊት እንደዘገብነው የገዳሙ ሊቀጳጳስ በመነኮሳቱ በኩል በረሃብ እየተቀጣሁ ነው ያለሁት ያሉትን ስሞታና መነኮሳቱ ደግሞ ውሸት ነው በማለት የሰጡትን ማስተባበያ ለአንባብያን መግለጻችንም አይዘነጋም። አሁን ዘግይቶ በደረሰን መረጃ ደግሞ ቋሚ ሲኖዶስ አሳልፎት በነበረው ውሳኔ መሠረት ግራ ቀኝ የተሰሙትን ክሶች ለማጣራት እንዲቻል አጣሪዎቹን ወደ ኢየሩሳሌም እንደላካቸውና ከስፍራው መድረሳቸውን የቤተ ክህነት ዘጋቢያችን ያደረሰን ዜና ያስረዳል።

ዘጋቢያችን የአጣሪዎቹን ማንነት ለማወቅ ጥረት እያደረገ ሲሆን የተላኩት የሲኖዶስ መልእክተኞች ወደእስራኤል መጓዛቸውን ግን ከተጨባጭ ምንጮች የተገኘው ዘገባ አመልክቷል።
ማጣራቱ የሚደረገው የገዳሙ መነኮሳቱ በሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጽሟል የሚሉትን ክሶች መመርመርና ሊቀ ጳጳሱ ደግሞ በመነኮሳቱ በኩል ተፈጽሞብኛል የሚሉትን በደልና ግፍ አንድ በአንድ መርምሮ ለቋሚ ሲኖዶስ ውሳኔ ማቅረብ እንደሆነ ይታወቃል።
የአጣሪዎቹን ማንነት፤ የተደረገውን የማጣራት ሂደትና የተገኘውን አጠቃላይ ውጤት የተመለከተ የመረጃ ዘገባ ተከታትለን ለማቅረብ እንሞክራለን።

Sunday, July 13, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!



( እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)
ክፍል አምስት

6.  የተጣረሰ  ደኅንነትና  የተቃወሰ  ክርስትና።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ ተዝካር  ያድናል፤  ማርያምን  ማመን  ያድናል፤  ተዝካሯን  መደገስ  ያድናል። በምዕ. 67  እረኞች  ያጠመቁት  አይሁድ  ውኃ  በቋጫ  ስለረጩበት  ብቻ ክርስቲያን  ሆነ፤  በ94  በንጹህ  እጅ  መቁረብ  መንግሥተ  ሰማያት ያስገባል።  78  ሰዎች  ቆርጥሞ  በልቶ  በማርያም  ስም  ጥርኝ  ውኃ  ከተሰጠ  ያ  ሚዛኑን  ደፍቶ  ከገሃነም  ፍርድ  ነጻ  ያወጣል።  ምጽዋት  መስጠት መንግሥተ  ሰማያት  ያስገባል፤  ምዕ.  44፤  ወዘተ።  ክርስትና  በተአምረ ማርያም  መመነን፥  መመንኮስ፥  ያለማግባት  ወይም  ጋብቻን  መጠየፍ፥ ከተጋቡም  በኋላ  አብሮ  ከመተኛት  ያለመገናኘት፥  ወደ  ስዕል  መጸለይና  መስገድ፥ ወዘተ፥ ናቸው። በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ግን  ደህንነትና  የክርስትና  ኑሮ  በቃልና  በሥራ ክርስቶስን  እየመሰሉ፥  እየተከተሉ  የመኖር፥  መስቀሉን  የመሸከም  የደቀ መዝሙርነት  ኑሮ  ነው።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  መዳን  በሌላ  በማንም እንደሌለ፥  እንድንበት  ዘንድ  የተሰጠ  የኢየሱስ  ስም  ብቻ  መሆኑ፥ ክርስቶስን  የተቀበሉ  ሁሉ  የእግዚአብሔር  ልጆች  መሆናቸው፥  ለመዳን ማመን  ብቻ  እንጂ  ልፋት  እንደማያስፈልግ፥  ያመነ  የተጠመቀ እንደሚድን፥  መዳን  ደግሞ  የሚታወቅና  የሚረጋገጥ  እንደሆነ  በግልጽ  ቋንቋ  ተጽፎአል።  በተአምረ  ማርያም  ግን  ይህ  አዳኝ  እና  የማዳኑ  ደስታ  ሲሸፈንና  እንዳይታይ  ሲደበቅ  ይስተዋላል። በምዕ.  41፥13  “በእግዚአብሔር  አምነው፥  በወለደችውም  በእመቤታችን አምነው  ከቤተ  ክርስቲያን  ወጡ”  ይላል።  ቁ.  25  እምነቱን  በናቱና  በእግዚአብሔር  ላይ  ያደረገ  ሁሉ  አያፍርምና  ይላል።  53፥55  ላይ  እግዚአብሔርን  አመሰገኑ  እመቤታችንንም  አመሰገንዋት  ይላል።  እምነት ክርስቶስ  ሲደመር  ሌላ  ነገር  ሆነ  ማለት ነው! በምዕ. 56  ማርያም  አንዱን መነኩሴ፥ “ከሚያልፈው ዓለም እስክወስድህ  ድረስ  ልጄ  ካንተ  አይለይም”  አለችው። ወሳጇ  እርሷ ስትሆን እስክትወስደው  ከመነኩሴው  የማይለየው  ልጇ  ነው።  ልክ  እንደ  አገልጋይ  ማለት  ነው።  በመጽሐፉ  ማርያም  ብቻ “ከልጇ  ጎን  በፈሰሰው  ደሟ”  አዳኝ  ሆና  ቀርባለች።  ታዲያ  ይህ የሰሚዎችን  ጆሮ  እያደነቆረ  የጠፉቱ  የምሥራቹን  ወንጌሉን  እንዴት ይስሙ?

7.  የተላቀቀ  መልክዓ  ምድር።

 በተአምረ ማርያም  ውስጥ  የተናጋ  መልክዓ  ምድርም  ይታያል።  ኢየሱስ  በዋሻ  ውስጥ  ተወለደ  ይላል፤  ለምሳሌ፥  ምዕ. 10።  ግርግምና  ዋሻ  እንደምን  አንድ  ሆኑ?  በ106  በኢያሪኮ  ባህር  ዳርቻ  ገዳም  ያለባት  ደሴት  መኖሯን  ይናገራል።  ደሴት  በባህር  ውስጥ  እንጂ  በባህር  ዳርቻ  አይኖርም።  ይሁን  እዳሩጋ  ጠጋ  ብሎ  ነው  ይባል።  ግን ኢያሪኮ  እኮ  ከተማ  እንጂ  ባህር  አይደለችም።  ኢያሪኮ  የሚባል  ባህር ኖሮም  አያውቅም።  በኢያሪኮ  አቅራቢያ  የዮርዳኖስ  ወንዝ  ነው  ያለው፤ ያም ቢሆን ገዳም የተገደመበት ደሴት የለበትም። ምዕ. 9  እና  ምዕ. 118  ከእስራኤል  ወደ  ግብጽ  ወይም  ከግብጽ  እስራኤል ሲሄዱ  ባህር  ሲሻገሩ  ይታያሉ።  በሁለቱ  አገሮች  መካከል  የየብስ  መንገድ ሳለ  በባህር  የሚያስዞር  ምክንያት  የለም።  ምናልባት  ከእስራኤል  ባህረ  ኤርትራን  መሻገር  ጋር  ለማቆራኘት  ይሆናል።  ወይም  ምናልባት  ከክብረ ነገሥት  ታሪክ  ጋር  ለማመሳሰል  የተደረገ  ሙከራ  ነው።  በጉዞውም  ተጋንነው  የተጻፉት  ነገሮች  ከክብረ  ነገሥት  ጋር  መመሳሰል  ስላላቸው  ከዚያ  የተኮረጀ  ይመስላል።
በምዕ. 72  ከሄሮድስ  ሸሽታ  ወደ  ዮሳፍጥ  ሸለቆ  ሄዳ  መሸሸጓ  ተጽፏል። ሊያያት  የመጣው  ገዢ  ከሄሮድስ  ሌላ  ሲሆን  ይህ  ሰው  ከሄሮድስ  ጋር ሊዋጋ  ዘምቶ  በማርያም  አማላጅነት  ተመለሰ።  እንደ  ፀሐይ  የሚያበራ ግርማ  ኖሯት  መሸሿ ወደ  ጎን ይቅርና፥ ጫካውም  ጫካ  ሆኖ ገዳም  መሆኑ ወይም  መባሉም  ይቅርና  በዮሳፍጥ  ሸለቆ  መደበቋና  ሁለቱ  ኃያላን  ሊዋጉ  መሰላለፋቸው  ሁለት  አገሮች  ብቻ  ሳይሆኑ  የሩቅ  አገሮችም  ያስመስላቸዋል።  ግን  የዮሳፍጥ  ሸለቆ  ከኢየሩሳሌም  በ20  ኪሎ  ሜትር ርቀት  የሚገኝ  ስፍራ  ነው።  በዚህ  አጭር  ርቀት  በሄሮድስ  ግዛት  ውስጥ ሌላ ገዥ ያውም  ከሄሮድስ  ሊዋጋ  የቃጣ  አልኖረም።

8.  የተዋረደ  ጋብቻ። 

መጽሐፍ  ቅዱስ  ጋብቻ  ክቡር  መኝታውም  በሁሉ  ቅዱስ  መሆኑን  ያስተምራል።  ጋብቻ  በማኅበራዊ  ረገድ፥  ለቤተ  ሰብ  ጤናማነት፥  በቅድስና  ለመኖር፥  ዘርን  ለመጠበቅ  በሙሉ  መልኩ፥ የተከበረ  ተቋም  ነው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የሚታየው  ግን  የዚህ ተቃራኒ  ነው።  ጋብቻ  የተናቀ  ነው።  ያላገቡ  ሰዎች  በተአምረ  ማርያሟ ; ማርያም  እንዳያገቡ  ይመከራሉ።  የተጋቡም  ሳይቀሩ  ትዳራቸው  ፈርሶ  እንዲመንኑ  ይደፋፈራሉ።  ምዕ.  65፥  66፥  68፥  75፥  86፥  92፥  100 እንዳያገቡ  የተከለከሉ  ሰዎች  ታሪኮች ይነበባሉ።
በምዕ. 30  ካህን  ዘራፊዎችን  ግደሉ  አባለ  ዘራቸውንም  ስለቧቸው  ብሎ  ሲያዝ  ይታያል።  ለነገሩ  ከተገደሉ  በኋላ  ብልት  ዋጋ  የለውም፤  ግን የተደረገው  ሁሉ  ተደርጎ  ይህ  ሁሉ  በማርያም  አማላጅነት  ተደረገ  ብሎ ይደመድማል።  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  አባለ  ዝርም  እንዲሰለብ  ታደርጋለች።  በምዕ. 85  ከገዛ  ሚስቱ  ጋር  መተኛቱ  እንደ  ኃጢአት  ሆኖበት  አባለ  ዘሩን  የቆረጠ  ሰው  ይገኛል።  ይህ  ሰው  ከደም  ፍሰት  የተነሣ  ሞቶ  መንግሥተ  ሰማያት  ሄዶ  በማርያም  ትእዛዝ ነፍሱ  ወደ  ሥጋዋ  ተመለሰችና  በሕይወት ኖረ።  መንግሥተ  ሰማያት  ከገባ  በኋላ  ነፍሱን  ብትመልስም  ቅሉ  ብልቱን ግን  አልቀጠለችለትም።  የሽንት  መሽኛ  ቀዳዳ  ብቻ  ተደርጎለት  መንኩሶ ኖረ።  በተአምረ  ማርያም  ትዳር  የቀለለ  ብቻ  ሳይሆን  የረከሰ  ነገር  ነው።
ከመነኮሰች  በኋላ  በፈቃደ  ሥጋ  ተሸንፋ  ከገዳም  የወጣችና  ያገባች  ሴት በመካንነት  ተቀጥታ  ወደ  ገዳሟ  ተመለሰች።  ሌሎችም  ይህም  የመሰሉ ታሪኮች ታጭቀውበታል።

9.  ያፈነገጠ  ተፈጥሮ።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የበዙ  ከተፈጥሮ ሥርዓት  ጋር  የማይስማሙና  የሚቃረኑ  ነገሮች  ይነበባሉ።  በምዕ.  70  አንድ  ሰው  ሥጋ  ወደሙን  ከወሰደ  በኋላ  አውጥቶ  በንብ  ቀፎው  ውስጥ አደረገው።  በኋላ  ሥጋ  ወደሙ  ወደ  ብርሃንና  የማርያም  ስዕልነት  ተለወጠ።  በእጅግ  ብዙ  ቦታዎች  የማርያም  ስዕል  ከስዕል  ተፈጥሮ  ውጪ  ድምጽ ሲወጣው፥  ሲደማ፥  ወዝ  ሲወጣውና  ሰዎች  ያንን  እየተቀቡ  ሲፈወሱ ይታያል።  እጅ  ዘርግቶ  ከተንቀሳቀሰ  ወይም  ሌላ  ስዕል  ከሰጠ፥  የቆሰለበት  ስፍራ  ጠባሳ  ከኖረው፥  ስዕል  ሲወጉት  ከደማ  (ለምሳሌ፥  ምዕ. 31)  ስዕሉ  ሕይወት  አለው  ማለት  ነው።  ምክንያቱም  መጽሐፍ  ቅዱስ  ሕይወት በደም  ውስጥ  መኖሩን  ይመሰክራል።  ከላይ  እንደተጠቀሰው  ስዕል  በራሱ  የተፈጠረ  ካልሆነ  ስዕል  እየሠሩ፥  እየሸጡ  የሚተዳደሩ  ሰዎች  አሉና  ስዕሎቹ  በሰው  የተሠሩ  ለመሆናቸው  ጥርጥር  የለበትም።  የስዕል  አምልኮ  በመጽሐፍ  ቅዱስ  የተወገዘ  መሆኑ  እንዳለ  ሆኖ  ስዕሎቹ  ተአምራት ካደረጉ፥  ሲወጉአቸው  ከደሙ  ሕይወት  አላቸውና  ሠሪዎቹ  ምን  ሊባሉ ነው?  ፈጣሪ?  አምላክ?  በተአምረ  ማርያም  ስዕል  ብቻ  ሳይሆን  ዳቦም ሲቆርሱት ደምቷል። በተአምረ  ማርያም  ወደ  ዓሳነት  ሳይለወጡ  በባህር  ውስጥ  ሆኖ  መተንፈስም፥  መጸለይም፥  እንዲያውም  መውለድም  ይቻላል።  በተአምር 97  አንድ  መነኩሴ  የውኃ  ሙላት  አማታውና  ሰይጣን  ወስዶ  እባህር ከተተው። እዚያ ሳለ ማርያምን  ጠርቶ ሲጸልይ ማርያም  መጥታ  ሰይጣንን  ገሰጸችለት።  እሱም  ውዳሴውን  ቀጠለ፤  የሚጸልይበትን  ቦታ  አሳየችውና በዚያ  ሲጸልይ  አደረ።  ዋናተኞች  ለፍለጋ  ሲጠልቁ  ውዳሴዋን  ሲደግም  አግኝተው  አወጡት።  እዚያ  ለመቆየት  ሲል  ባትመጡብኝ  ይሻለኝ  ነበር አላቸው።  በተአምር  88  ደግሞ  አንዲት  ነፍሰ  ጡር  ከመስጠም  መዳኗ  ብቻ ሳይሆን  በባሕር  ውስጥ  ሳለች  በቤት  ውስጥ  እንዳለች  ሆና  በማርያም  ተሸፍና  ወልዳለች።  ያውም  ያለምጥ  ነው  የወለደችው።  ከተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ሌላ  ያለምጥ  የወለደች  ሴት  ናት  ይህች  ሴት።  በ375  ዓመቷ  የሞተችው  ክርስቶስ  ሠምራ  በጣና  ባህር  ውስጥ  ሰውነቷ  ተበጣጥሶ  ዓሳዎች  በውስጧ  እየሾለኩ  12  ዓመት  ጸልያ  ወጣች  እንደሚባለው  የመሰለ  ታሪክ  ነው። 15 በምዕ. 59  አንድ  የቤተ  ክርስቲያን  ጠባቂ  አንድ  ቀን  ከራት  በኋላ  የሥጋ ድቀት  አግኝቶት  ዝሙት  ፈጸመ።  በመልአክ  ተነክቶ  የሴት  መርገም ደረሰበትና  ከዚያ  በኋላ  ማርያም  ያደረገችበትን  ይህን  ነገር  አገር  ላገር  እየተናገረ  በመዞር  ኖረ።  መልአክ  ቢነካውም  ይህን  ያደረገችው  ማርያም  ናት።  ይህች  የዚህ  መጽሐፍ  ማርያም  ምንም  ነገር  ማድረግ  ትችላለች።

ሰብዓዊ  ተፈጥሮንም  ትቀይራለች።  የወር  አበባ  ካየ  ማኅጸን  ተሠራለት ማለት  ነው።  ማመንዘሩ  ኃጢአት  ሳለ  ቅጣቱ  ሴት  መደረግ  ወይም  እንደ ሴት  መደረግ  ከሆነ  ይህች  ማርያም  ሴትነቷንም  ትጠላዋለች  ማለት ይሆን? በምዕ.  107  ብዙ  ኃጢአት  ፈጽማ  ተስፋ  የቆረጠች  ተቅበዝባዥ  የሆነች ሴት  ታሪክ  ይገኛል።  ይህች  ሴት  ወደ  በረሃ  ሂዳ  ጊንጥ  አገኘችና ዋጠችው።  መርዙ  በሰውነቷ  ተሰራጭቶ  ስትሰቃይ  የማርያም  ስዕል  መጥቶላት  በዚያ  ሆዷን  እያሸች  ማርያምን  ለመነች።  ማርያም  ወደ  ቄስ ልካት  ለዚያ  ቄስ  ተናዝዛ  አምጣ  ወለደች።  የወለደችው  ሕጻንን  ሳይሆን 40  ትልልቅና  ትንንሽ  ጊንጦችን  ነው።  ወደ  አፍ  የገባ  ወደ  እዳሪ እንደሚወጣ  ጌታ  የተናገረው  ስሕተት  ተደርጎ  ወደ  ማሕጸን  ገብቶ  በ40  ተባዝቶ ወጣ!  እንደዚህ  ትምህርት  ከሆነ  ሴቶች ላም  እንወልዳለን  ብለው  በመፍራት  ወተት  መጠጣት  ማቆም  አለባቸው።  ወይም  አስር  ዶሮ  እንወልዳለን  ብለው  እንቁላል  መብላት  መተው  ይኖርባቸዋል።  ደግሞ  ሁሉም  እንደየወገኑ  እንዲዋለድ  በፍጥረት  መጀመሪያ  የተነገረውም  ተሰረዘና  ሴት  ጊንጥ  ወለደች።  ለተአምሩ  ትክክልነት  ሲባል  መጽሐፍ ቅዱስ  መስተካከል  አለበት።
ጊንጥ ብቻ  ሳይሆን  ሌላም  የከፋ  ወሊድ ታሪክ  አለ። በምዕ. 55 የሌላ  ሴት  ባል  የቀማች  አንዲት  ሴትና  ሌላኛዋ  ሴት  በማርያም  ታቦት  ፊት  እውነተኞች  መሆናቸውን  ይማማላሉ።  የቀማችው  ሴት  ኃጢአተኛ  ኖራለችና  እርጉዝም  ነበረችና  ቆይታ  ወለደች። የወለደችው  ሕጻን  ሳይሆን  በትል  የተሞሉ  ሁለት  የላም፥  ሁለት  የበግ  ቀንዶችን  ነው።  ይህች  ሴት እብድ  ሆና  እየዞረች  ይህንኑም  ያደረገችው  ማርያም  መሆኗን  እየተናገረች  ቆይታ  ሞተች። ቀንዶቹ  ደግሞ  ከማኅጸን  እንደወጡ  እንኳ  አልተቀበሩም።
በማርያም  ቤተ  ክርስቲያን  መስኮቶች  ተሰክተው  ይኖራሉ።  የትኛዋ  ቤተ ክርስቲያን  እንደሆነች  እንኳ  ቢናገሩ  ጉዱ  ይታይ  ነበር።  አገሩ  ብሔረ አግዓዚ  ከመባሉ  ሌላ  አይታወቅም።  በቀጣዩ  ምዕራፍ  (ምዕ. 56)  የያሬድ ቅኔ  ማኅሌት  እውስጡ  ስለተጠቀሰ  ብሔረ  አግዓዚ  የኛው  አገር  መሆኑን  እንረዳለን።  ቀድሞውኑም  የሌለ  ነገር  ስለሆነና  እንዲጠየቅና  እንዲመረመርም  ስለማይፈለግ  ስፍራው  አይገለጥም።  ወይስ  ዛሬም  ቀንዶቹ  ከአገራችን  ቤተ  ክርስቲያኖች  ባንዷ  መስኮቶች  እንደተሰኩ  ይሆኑ?

Tuesday, July 1, 2014

በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ማኅበር አቡነ ዳንኤልን የበደላቸው ነገር የለም!!



( ለዘሐበሻና ሌሎች ኦርቶዶክሳውያን መካነ ጦማሮች በተለይ የተላከ)

በአባ ሰላማና ደጀ ብርሃን የተሐድሶ መካነ ጦማሮች ለወጣው የቤተ ክርስቲያናችንን ክብር ለማይጠብቅ ጽሁፍ እናዝናለን!
በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተመደቡት አቡነ ዳንኤል ከመጡበት ከነሐሴ 2005 ዓ/ም ጀምሮ የገዳሙ ማኅበር ለአንድ ሊቀ ጳጳስ የሚገባውን ክብርና የሥራ ትብብር በማድረግ ሲፈጽም ቆይቷል። ይሁን እንጂ በቆዩበት ለአንድ ዓመት የስራ ሂደታቸው ጉድለት ሲገመገም በዚህ ጽሁፍ ለመዘርዘር የሚከብዱና የሚቀፉ ቃላትን በማውጣትና ተግባራትን በመፈጸም  አባታዊ ደረጃቸውን ለመጠበቅ በጣም የሚቸገሩ እንደነበሩ አይካድም። ይህም ሆኖ  ገዳሙ የራሱን ስምና ደረጃ ለመጠበቅ ሲል ሁሉንም በትዕግስት ተሸክሞ ቆይቷል።
  ችግሮቹ ይሻሻሉ ዘንድ ነገሮችን በትዕግስት መጠበቁ ገዳሙን የሚጎዳ ደረጃ ላይ የሚያስደርስ ሁኔታ በመፈጠሩ በብጹዕነታቸው የተፈጸሙ 10 / አስር/ የስራ ጉድለቶችን በመዘርዘር አጠቃላይ የማኅበሩ አባላት በውሳኔ አሳልፈውና ተፈራርመው ቅዱስ ሲኖዶስ ችግሩን እንዲያጣራና ባለው ስልጣን መሰረት የእርምት እርምጃ እንዲወስድ በደብዳቤ ለግንቦት /2006 ዓ/ም የሲኖዶስ ጉባዔ በደብዳቤ ጠይቋል። ደብዳቤው ለቋሚ ሲኖዶስ ቀርቦ ከታየ በኋላ መወሰድ ስለሚችለው ቀጣይ ጉዳይ ውሳኔ የተላለፈ በመሆኑ አፈጻጸሙን ገዳሙ በትዕግስት እየተጠባበቀ ይገኛል።
ይሁን እንጂ የሊቀ ጳጳሱን የማዕርግ ደረጃ በማይጠብቅና የኦርቶዶክሳውያንን የእምነት አቋም በማይከተል መንገድ በሊቀ ጳጳሱ በራሳቸው የተጻፈ ይሁን  ወይም በሌሎች የገዳሙን ስም ለማጉደፍ የቆሸሸ ምግባራቸው እየተከተለ ማንነታቸውን በሚያሳብቅባቸው  ስም አጥፊ ግለሰቦች እጅ እንደተጻፈ ለጊዜው ባልታወቀ መንገድ በተሐድሶ/ፕሮቴስታንታዊ ብሎጎች ላይ ሊቀ ጳጳሱ በረሃብ እየተቀጡ መሆናቸውን የሚገልጽ ጽሁፍ በመውጣቱ በጣም አዝነናል።
«እውነትና ንጋት እያደረ ይጠራል» እንዲሉ ገዳሙ ተበድሏል ወይስ ሊቀ ጳጳሱ? የሚለው ጉዳይ ወደፊት የሚታይ ሆኖ ገዳሙ  በሊቀጳጳሱ የደረሰበትን የስራ በደል የሚገልጸውን ዝርዝር ጉዳይ እዚህ ጽሁፍ ላይ ቢያወጣ የአባቶችን ደረጃ ማቃለልና  የቤተ ክርስቲያናችንንም  ችግር በራሳችን የስልጣን እርከን መፍታት እንደማንችል የሚቆጠር በመሆኑና ለቤተ ክርስቲያናቸው ክብር ዘወትር የሚቆረቆሩ ምእመናንንና ምእመናትን ልቡና ማሳዘን በመሆኑ ሊቀ ጳጳሱ በተሐድሶ ብሎጎች ላወጡት የተበደልኩ አቤቱታ የምንሰጠው ዝርዝር ነገር አለመኖሩን መግለጽ እንወዳለን።
ስለሆነም  ለኦርቶዶክሳውያን በሙሉ የምናሳውቀው ነገር በተሐድሶ/ፕሮቴስታንታዊ መጦመርያዎች የወጣው ጽሁፍ የተሳሳተና የገዳሙን ስም ለማጉደፍ ተላላኪዎች የፈጸሙት የትስስር ድርጊት እንጂ መሬት ላይ ያለውን እውነታ የሚያንጸባርቅ አይደለም። ሊቀ ጳጳስ አባ ዳንኤልን በተመለከተ ለሲኖዶስ በተገለጸ ጽሁፍ ገዳሙ በስራ መግባባት ባለመቻሉ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲሰጥ የተጠየቀ ስለሆነ የዚያን ውሳኔ በመጠባበቅ ላይ ስለምንገኝ ውሳኔውን ወደፊት የምናሳውቅ መሆናችንን በአክብሮት እንገልጻለን።
                                                                 እግዚአብሔር አገራችንንና ሕዝባችንን ይባርክ!


Monday, June 30, 2014

በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሊቀጳጳስ በብፁዕ አቡነ ዳንኤል ላይ የገዳሙ መነኮሳት አድመው በረሃብ እየቀጧቸው መሆኑ ተሰማ!



( ምንጭ፤ አባ ሰላማ ድረ ገጽ)



በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቀጳጳስ በሆኑት በብፁዕ አቡነ ዳንኤል ላይ አባ ገብረ ወልድ በተባሉ መነኩሴ አሳዳሚነት ሊቀጳጳሱ ላይ ልዩ ልዩ የአድማ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆናቸውንና ሊቀጳጳሱ ላይ አደጋዎች መደቀናቸውን ከስፍራው የደረሰን ዜና አመለከተ፡፡ ብፁዕነታቸው የሲኖዶስን ስብሰባ ለመካፈል ከመጡ ወዲህ ተመልሰው ቢመጡ አናስገባቸውም በሚል የተጀመረው አድማ ምግብ እንዳይቀርብላቸው፣ ሾፌራቸውም መኪናቸውን እንዳያንቀሳቅስ እስከ ማሳደም የደረሰ አሳዛኝ እርምጃ እየተወሰደባቸው መሆኑን ምንጮቻችን የገለጹ ሲሆን ይህም ድርጊት በአንዳንድ ክፉ ቀን ግብጻውያን መነኮሳት ኢትዮጵያውያን መነኮሳት በበሽታና በረሃብ እንዲያልቁ ለማድረግ በራቸውን ዘግተውባቸው እርዳታ ሳያገኙ እንዲሞቱና ገዳማቶቻችን ያለ ሰው እንዲቀሩ ለማድረግ ከሚጠቀሙባቸው በጭካኔ የተሞሉ ስልቶች ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ ከዚህ እርምጃ በስተጀርባ የማን እጅ እንዳለ ለጊዜው የታወቀ ነገር ግን የለም፡፡


ብፁዕ አቡነ ዳንኤል የስኳር በሽተኛ ከመሆናቸው አንጻር በረሃብ እንዲቀጡ አድማ መመታቱ እጅግ አሳዛኝ ተግባር መሆኑ እየተነገረ ሲሆን፣ በብፁዕነታቸው በኩል እስካሁን ነገሩን በትዕግስት ማሳለፋቸው የቤተክርስቲያን ስም በዚህ መንገድ እንዳይነሣ ከማሰብ እንደሆነ የተናገሩት ምንጮች፣ ብፁዕነታቸው የዲፕሎማት ፓስፖርት ያላቸውና እንደዲፕሎማት ስለሚታዩ ለሚመለከተው አካል አቤት ቢሉ ይህን ባደረጉት መነኮሳት ላይ ሕጋዊ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚችል ስለጉዳዩ የሚያውቁ ይናገራሉ፡፡
በአባ ገብረወልድ የተመራው የአድማ ማኅበር እንዲህ ለማድረግ ያነሳሳው ምን እንደሆነ እስካሁን የታወቀ ነገር ባይኖርም ብፁዕነታቸው የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ ሆነው ከተሾሙ በኋላ በዚህ ወቅት ሊሆን የማይችለውን በጎልጎታ ምዕራፍ ስምንት የተባለውን ቦታ ለቤተክርስቲያናችን በመግዛት ትልቅ ስራ መስራታቸው ይነገራል፡፡ የመነኮሳቱ ቅናትና አድማ የተነሳው ከዚህ መልካም ስራ ሳይሆን እንደማይቀር አንዳንዶች ይገምታሉ፡፡ የመነኮሳቱ ማኅበርም አይዟችሁ ያላቸው አካል ሳይኖር አይቀርም የሚል ግምት አለ፡፡

Sunday, June 29, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!


(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

ክፍል አራት

አንዳንድ  ሰዎች  ማርያምን  እንደሚያከብሩ  እንጂ  እንደማያመልኩ  የሚናገሩት  የቃል  ጨዋታ  ነው።  መጽሐፍ  ቅዱስን  እየጠሉ  ራዕየ ማርያምን  በቃል  እየሸመደዱ  “እንወዳታለን  እንጂ፥  እናከብራታለን፥  የጸጋ ስግደት  እናቀርብላታለን  እንጂ  . . .  አናመልካትም”  ማለት  የራስ  ድለላ ነው።  እንዲህ  ከላይ  እንደጠቀስኳቸው  ያሉቱ  ምዕራፎች  የሚናገሩት  እየተከበረች  ሳይሆን  እግዚአብሔርን  ተክታ  እየተመለከች  መሆኗን  ነው። ደግሞ  ማክበርስ  ከሆነ  መከበር  የሚገባው  ማን  ብቻ  ነው?  ይህ  እኮ አንድን  ባለሙያ  ሰው  ለማድነቅና  ለማመስገን  ከስዕሎቹ   ወይም  ከቅርጾቹ  አንዱ  ፊት  ሄጄ  ለሥራው  ውጤት  ምስጋናና  ውዳሴን  ብደረድር እንደማለት  ነው።  ይህ  እንዲህ  በሚለው  በሮሜ  1፥25  ቃል  ፈጽሞ  የተወገዘ  ነው፤  ይህም  የእግዚአብሔርን  እውነት  በውሸት  ስለ ለወጡ በፈጣሪም  ፈንታ  የተፈጠረውን  ስላመለኩና  ስላገለገሉ  ነው፤  እርሱም ለዘላለም  የተባረከ  ነው፤  አሜን።  ማክበር  ወይም  ማምለክ  የቃል  ጉዳይ አይደለም።  መስተዋል  ያለበት  ተግባሩና  ድርጊቱ  ነው።  ለእግዚአብሔር ብቻ  እንጂ  ለሌላ  ለማንም  መደረግ  የሌለበትን  ነገር  ለሌላ  ማድረግ፤ ለምሳሌ፥  ጸሎትንና  ልመናን፥  ውዳሴና  ስግደትን  ማቅረብ  ማምለክ  እንጂ ሌላ  አይደለም። በአፌ  አላመልካትም  ብል  እና  ውዳሴና  ልመናን ስዕለትንና  ስግደትን  ባቀርብላት  ራሴን  እየደለልኩ  ነኝ።  ወይም  በእርሷ መጋረጃ  ውስጥ  እየተደበቅሁ  ከእውነት  እየሸሸሁ  ነኝ።  ራእ.  4፥10-11፤ 15፥3-4፤  ነህ.  9፥6  ሁሉ  ሊሰግዱለት፥  ሊያከብሩት፥  ሊያመልኩት፥ ሊወድሱት፥  ሊያመሰግኑት  የተገባ  ብቻውን  የሆነ  አምላክ  እግዚአብሔር  ብቻ  መሆኑን  ከሚነግሩኝ  ጥቅሶች  ጥቂቱ  ናቸው።

4.  የተፈናቀለ  ታሪክ።

 በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ታሪክ  የሚያውቃቸው፥  በታሪክ  ውስጥ  ስማቸው  የተጠቀሰና  ዘጋቢዎች  ያወሷቸው፥  ራሳቸውም ታሪካቸውን  የጻፉ  በንጽጽር  እውነቱን  ማረጋገጥ  የሚቻልባቸው  ሦስት ሰዎች  ተጠቅሰዋል።  መጽሐፉ  እነዚህን  የመሰሉ  ታሪካዊ  ገጸ  ባህርያትን  የከተተው  እና  አንድ  ሁለት  ምዕራፎች  ውስጥ  ዓመተ  ምሕረቶችን  ያስገባው  ታሪካዊ  ስርና  መሠረት  ያለው  ለመምሰል  ይህናል  ብዬ እገምታለሁ።  ይህ  መጽሐፍ  እነዚህን  ሰዎች  ሊጠቅሳቸው  ከደፈረ  እኔም ከታሪክ  አንጻር  ልጥቀሳቸው።  እነዚህ  ሰዎች  ንጉሥ  ማርቆስ፥  ዮሐንስ  አፈወርቅ፥  እና ዮስጢን  ሰማዕት ናቸው። ኋላ ላይ  ጥጦስም  ወንበዴ ሆኖ ተጠቅሶአል። ግን ይህ ጥጦስ ኋላ ኢየሩሳሌምን  ያወደመው  ይሁን  ወይም ሌላ  ቀጣይ  ታሪኩ  በዚህኛው  ተአምረ  ማርያም  ውስጥ  አልተነገረም።
ሦስቱን ግን እንመልከት።

ሀ.  ዮሐንስ  አፈወርቅ። 

ታሪኩን  ከእንግሊዝኛ  መዛግብት  የምታውቁ  በተጨማሪ  ከሌላ  ምንጮች  ለመመርመር  ለምትሹ  ይህ  ሰው  እንግሊዝኛው  አጠራር  John  Chrysostom  የሚባለው  ነው።  የዮሐንስ  አፈወርቅ  ተአምረ  ማርያምኛ  ታሪክ  በምዕ.  48  ተጽፎአል።  ታሪኩ  በአጭሩ ምዕመናንን  ሥጋ  ወደሙን  ሲቀበሉ  አንዲት  ሴት  በመርገመ  ደሟ ሳለች  መጣች።  ሕዝቡም  የመንፈስ  ቅዱስ  ረድዔት  እንደራቃት  አውቀው  ወደ  ንስጥሮስ  ፊት  አመጧት።  ጠይቆ  ከተረዳ  በኋላ  ራቁቷን  ተዘቅዝቃ  እንድትሰቀልና  ሕዝቡም  በኀፍረተ  ሥጋዋ  ጢቅ  እንዲሉ  አዘዘ።  እንደ ተአምረ  ማርያም  ጸሐፊ  ንስጥሮስ  ይህን  ያደረገው  እግዚአብሔር  እንዲህ  ከመሰለ  ቦታ  የሚወለድ  እንደሆነ  የሚያምን  የተረገመ  ነው  አሰኝቶ  ነው። ዮሐንስ  የሚባል  ቄስ፥  “እኔ  እግዚአብሔር  በሴት  ሥጋ  እንደተወለደ  አምናለሁ”  ብሎ  ኃፍረተ  ሥጋዋን  ባፉ  ሳመ።  በዚህ  ጊዜ  የማርያም  ስዕል በቤተ  መቅደስ  ውስጥ  ነበረችና፥  “አፈወርቅ”  ብላ  ጠራችው።  ቄሱ ዮሐንስ አፈወርቅ  የተባለው  እንዲህ ነው። ይህ  ምዕራፍ  የንስጥሮስን  ክፋት  ለመግለጥና  ማርያምን  ያለስፍራ ለማግነን  ተብሎ  ረጅም  ርቀት  የተሄደበት  ትረካ  ነው።  መርገመ  ሴትን  አርክሶ  ሥጋ  ወደሙን  ከከለከለ  ኀፍረተ  ሥጋን  ማየትና  በላዩ  መትፋት ዮሐንስን  ከማስመስገን  ይልቅ  የአድራጊዎችን  ሁሉ  ኅሊናን  አያረክስም?  ንስጥሮስ  ኋላ  በ431  በተደረገው  በኤፌሶኑ  ጉባኤ  እርሱም  ትምህርቱም የተወገዙበትን  ክርስቶስ  ሁለት  አካል  የሚል  ትምህርትን  ያስተማረ  ሰው ነው።  ለዚህ  ምላሽ  ሆኖ  ኋላም  በክርክር  የቆየ  የሁለት  ባህርይ (dyophysitism)  እና  አንድ  ባህርይ  (monophysitism)  ጉዳይ ቀጥሎአል።  ሁለት  ባህርይ  ኢየሱስ  ክርስቶስ  አንድ  አካል  ሁለት  ባህርይ ሲል  ተዋህዶ  የኢየሱስ  ስብእና  በመለኮትነቱ   የተዋሃደ  ወይም  ተዋህዶ  ነው  የሚሰኘው  ንድፈ  አሳብ  ነው።  የንስጥሮስ  ትምህርት  ግን  ኢየሱስን  ሁለት  ባህርይ  ሳይሆን ሁለት  አካል  የሚያደርግ  ነው።

 ንስጥሮስ  የማርያምን  ወላዲተ  አምላክነት  (θεοτόκος  ቴኦቶኮስ  መሆን)  የሚቃወም  ሰው  ነው።  ማርያም  ቢበዛ  ሥጋ  የለበሰው  ክርስቶስ  እናት (ክሪስቶቶኮስ)  እንጂ  የአምላክ  ወይም  የእግዚአብሔር  እናት  መባል የለባትም  ያለ  ሰው  ነው።  θεοτόκος  ባለፈው  መጣጥፍ  በመጠኑ የጠቀስኩት  ወላዲተ  አምላክ  ተሰኝቶ  በስሱ  የተተረጎመ  ቃል  ይሁን  እንጂ ትርጉሙ  ከዚህ  የጠለቀ  ነው።  ቀጥተኛ  ትርጉሙ  “የአምላክ  ተሸካሚ፥ የአምላክ  አምጪ፥  አምላክን  ያመጣች፥  ወይም  እንዲመጣ  ያደረገች”  (bringer forth of God)  ማለት  ነው።  Theotokosን  ያጸደቀው  በ431  የተደረገው  የኤፌሶኑ  ጉባኤ  ነው።  ከዚያ  በኋላ  ነው  የማርያም  ስዕሎች ስፍራ  ሊያገኙ  የበቁት።  ቀድሞ  ስዕሎች  የነበሩ  ቢሆኑም  ከስነ  ጥበብ አንጻር  የሚታዩ  እንጂ  ከአምልኮ  ጋር  የተቆራኙ  አልነበሩም።  ኋላ ንስጥሮስ  በስደት  በአንጾኪያ፥  በዐረቢያ  እና  በግብጽ  ኖሮ  በ451 ሞቶአል። 12 የንስጥሮስ  ትምህርት  ዋና  ስሕተት  በክርስቶስ  የመስቀል  ላይ ሞት  ከሁለቱ  አካላት  አንዱ  ሰው  የሆነው  አካል  ብቻ  ከሆነ  የሞተው ለኃጢአት  የተከፈለውን  ዋጋ  መለኮታዊ  ልቀት  ያሳጣዋል የሚል ነው።

ወደ  ዮሐንስ  አፈወርቅ  ስንመለስ፥  ይህ  ሰው  በታሪክ  በጣሙን  የታወቀ ሰው  ነው።  ከሰበካቸው  ስብከቶች  600  ያህል  በጽሑፍ  እና  ወደ  200  ደብዳቤዎቹ  እስከዛሬ  ተጠብቀው  ይገኛሉ።  እንዲህ  እንደ  ተአምረ  ማርያሙ  የመሰለ  ታሪክ  ግን  ከቶም  የለም።  ዮሐንስ  ነበልባል  የሆነ  ሰባኪ ነው።  እነዚህ  ስብከቶቹ  ናቸው  አፈወርቅ  የሚል  ቅጽል  እንዲሰጠው  ያደረጉትም።  ዮሐንስ  ከንስጥሮስ  ጋር  በአንድ  ዘመን  የነበረ  ሰው  ነው። ዘመናቸው  በአጭር  ይገናኝ  እንጂ  የሚተዋወቁና  በአንድ  ላይ  ያመለኩ ሰዎች  ግን  አልነበሩም።  ዮሐንስ  ከ347-407  ዓ.  ም.  13 ንስጥሮስ  ደግሞ ከ386-451  ዓ.  ም.  የኖሩ  ናቸውና  ዘመናቸው  በ21  ዓመታት  ብቻ ይገናኛል።  ንስጥሮስ  ሲወለድ  ዮሐንስ  39  ዓመቱ  ሲሆን  ዮሐንስ  ሲሞት ደግሞ  ንስጥሮስ  ገና  21  ዓመቱ  ነው።  ሁለቱም  በቁስጥንጥንያ  ሊቃነ ጳጳሳት  የነበሩ  ሲሆኑ  ዮሐንስ  ጵጵስና  የተሾመው  በ397  በአምሳ  ዓመቱ ነው።  ንስጥሮስ  የቁስጥንጥንያ  ሊቀ  ጳጳስ  የሆነው  ደግሞ  በ428 (ከ428-431)  ነው።  ዮሐንስ  ከሞተ  ከ21  ዓመታት  በኋላ  ማለት  ነው።  ዮሐንስ  በሚሞትበት  ጊዜ  ንስጥሮስ  ገና  21  ዓመቱ  ነበርና  በተአምረ  ማርያም   እንደ ተጻፈው ጳጳስም  በአንብሮተ  እድ የሚሾም  ሰውም  አልነበረም። ኋላ  የተጻፉ  ምንጭ  የሌላቸው  ታሪኮች  ቢኖሩም  ዮሐንስ  በቀረቤታ  ሲታይ  በተአምረ  ማርያም  የጻፈውን  ማድረጉ  በታሪኮቹ  ሁሉ  የማይገኝ ብቻ  ሳይሆን  እንዲያውም  በተቃራኒው   ዮሐንስ  ሴትን  የመናቅና  ያለማድነቅ  አዝማሚያ  የሚታይበት  ሰው  ነው።  የሴትን  አብዝቶ  ማሸብረቅ  ይጠላ ነበርና  በጵጵስናው  ዘመን  ከንጉሡ  ሚስት  ከአውዶክሲያ  ጋር  ዓይንና  ቁልቋል  ሆነው  ኖረዋል።  ይህችን  ሴት  ከሄሮድያዳ  ጋር እያነጻጸረ  ስለተናገረባት  ሌሎችን  አስተባብራ  ለስደት  የዳረገችውም  እርሷ ናት።  “ከዱር  አራዊት ሁሉ እንኳ  ሴትን  የሚያህል  ጎጂ  ፍጡር አይገኝም”  ብሎ  ስለ  ሴት  ጾታ  ያተተ  አንድ  መጽሐፍ  ዮሐንስን  ተጠቃሽ አድርጎታል። 14 እንዲህ  ለአንስታይ  ጾታ  ወደ  ጥላቻ  የተጠጋ  ንቀት እንዳለው  የሚባልለት  ሰው  ነው  በተአምረ  ማርያም  መርገመ  ደም  ያለባትን  ሴት  ኀፍረተ  ሥጋ  የሳመውና  ስዕሊቱ  አፈወርቅ  ብላ  የሰየመችው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የማርያም  ስዕል  እስኪሰለች  ድረስ  ነው  ድምጽ  እያሰማች  የምትናገረውና  ይህ  ሲጨመርበት  ታሪክ ወደ  ተረትነት  በቀላሉ  ይሻገራል።  እነዚህ  እርስ   በርሳቸው ከተጋጩ  እንደ ባለ  አእምሮ  በመዛግብት  የተጻፈውን  ተጨባጭ  ታሪክ  እንቀበል  ወይስ  በተአምረ ማርያም   የተጻፈውን  ከታሪክ   ጋር የሚጣላ ፈጠራ?

ለ.  ንጉሥ  ማርቆስ።

 የንጉሥ  ማርቆስ  ታሪክ  በተአምረ  ማርያም  በምዕ.  100  የተጻፈው  እንደሚተርከው  ድንግል  ሳለ  በሮም  መንገሡ  ተጽፎአል። 10 ዓመታት  ከነገሠ  በኋላ  ሠራዊቱ  ሚስት  ማግባት  ሞገስ  የሚያስገን  ቁም  ነገር  ስለሆነ  ሚስት  እንዲያገባ  ማለዱት።  እርሱም  ማርያምን  ልማከር  ብሎ  በስዕሏ  ፊት 7 ቀን  ቆሞ ጸለየ።  በጸሎቱ  መጨረሻ  የስዕሊቱ  ፊት  ቦግ  ብላ  በራችና  በድምጽ  እንዳያገባና  በድንግልና   እንዲኖር፥  እንዲያውም  መንግሥቱን  ትቶ  ደብረ  ቶርማቅ  ገዳም  ሄዶ  እንዲኖር  ነግራው  እዚያ  ለመኖር  ማንም  ሳያየው  ጠፍቶ  ሄደ።  በተአምረ  ማርያም  ድንግልና  እጅጉን  የተወደደ  ከመሆኑ  የተነሣ  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያምና  የማርያም  ስዕል  ሰው  ሁሉ  ሳያገባ  እንዲኖር  ይፈልጋሉ።  ይህ  ከመጽሐፍ ቅዱስ  ጠቅላላ አሳብ ጋር በትጋት የሚጣላ ነው።
ማርቆስን  በተመለከተ  በሮም  ግዛት  ውስጥ  በታሪክ  የታወቀ  በዚህ  ስም የተጠራ  ንጉሥ  ማርቆስ  አውራልዮስ (Marcus Aurelius)  ነው።  ይህ ሰው  ሳይሆን  ሌላ  ነው  ከተባለ  ታሪካዊ  ማስረጃ  ያስፈልገዋል።  በተአምረ ማርያም  ውስጥ  ስም  ሳይጠቀስም  ‘በአንድ  አገር  የነገሠ  ንጉሥ’  ይባልና  የንጉሡ  ስም  ሳይነገር  መተረክ  የተለመደና  ቀላል  ነገር  ነው።  ስለ  ማርቆስ በታሪክ  መዛግብት  የተጻፈ  ታሪኩ  የሚናገረው  ግን  ከዚህ  የተለየ  ነው።
ማርቆስ  ከ161-180  ለሃያ  ዓመታት  የነገሠ  ንጉሥ  ነው።  ከ20ው  ውስጥ 9ኙን  አብሮት  የነገሠ  ሉቂዮስ  ቬሮስ  የተባለ  ሰው  አለ።  ንጉሥ  ማርቆስ ከታሪኩ  እንደምናነብበው  ሳያገባ  የኖረ  እና  መንግሥት  ትቶ  ገዳም  የገባ መነኩሴ ሳይሆን  14 ልጆች ከወለደችለት ፋውስቲና  ከተባለች  ሚስቱ  ጋር  ለ30  ያህል  ዓመታት  ተጋብቶ  የኖረ  ሰው  ነው።  የቱ  ነው  ትክክል?  በማረጋገጫ  የሚፈትሹትና  ማስረጃ  የሚያቀርቡለት  ታሪክ?  ወይስ ከታሪክ  ጋር  የሚጋጭና  ምንጩ  የማይታወቅ  ተረት?

ሐ.  ዮስጢን  ሰማዕት። 

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የተጻፈው  በምዕ. 99  ሲሆን ከዮስጢን  ይልቅ  ስለሚስቱ  ታውክልያ  በተጻፈው  ውስጥ  የተካተተ ነው።  የተአምረ  ማርያሙ  ታሪክ  ታውክልያ  የዲቅልጥያኖስን  ክህደት ስለማወቅ  በጸሎት  ላይ  ሳለች  ማርያም  ከእናቷና  ከኤልሳቤጥ  ጋር ትገለጥላታለች።  የዲዮቅልጥያኖስ  ክህደት  በልጇ  (በኢየሱስ)  ዘንድ  የታወቀ  መሆኑን፥  ኢየሱስ  ለዮስጢን  በሰማይ  ስለሚደረገው  ሠርግ (ተዋህዶ)  ሊነግረው  እንደሄደና  እርሷ  ደግሞ  ወደ  እርሷ  እንደመጣች፥ ሁለቱም ከልጃቸው  ጋር  እንደሚሰዉ  ነግራት አበረታታት  ተሰወረች።
እዚህ  ያለው  ትልቅ  ታሪካዊ  ግጭት  ዮስጢን  ከ100-165  የኖረ  መሆኑ የታወቀ  ሆኖ ታውክልያ  የምትጸልየው  ስለ ዲዮቅልጥያኖስ ክህደት  መሆኑ ነው።  ሌላ  ዮስጢን  ካልሆነ  በቀር  ይህ  በታሪክ  የታወቀው  Justin  Martyr  ነው።  ዲዮቅልጥያኖስ  ክርስቲያኖችን  በእጅጉ  ያሳደደ  ሰው ቢሆንም  የኖረበት  ዘመን  ከ244-311  ሆኖ  የነገሠው  ደግሞ  ከ284-305  ድረስ  ነው።  ታውክልያ  ከ120  ዓመታት  በኋላ  ስለሚመጣው  ከሐዲ እያሰበች  ነበር  ካልተባለ  በዚያን  ዘመን  ዲዮቅልጥያኖስ፥  ክህደቱና  አሳዳጅነቱም  አልነበሩም።  ዲዮቅልጥያኖስ  የተወለደው  ዮስጢን  ከሞተ ከ80  ዓመታት  በኋላ  ነውና  ዮስጢን  የተሰዋው  በዲዮቅልጥያኖስ  ሳይሆን  ከላይ  በተጠቀሰው  ማርያም  ከንጉሥነት  ወደ  ገዳም  አስኮበለለችው  በተባለው  በማርቆስ  አውራልዮስ  ዘመነ መንግሥት  ነው።

5.  የተምታታ  ሲዖልና  መንግሥተ  ሰማያት።

በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  የሚታዩት  ከሞት  በኋላ  የሚሆኑት  ነገሮች  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ከተነገሩት  የተለዩ  ናቸው።  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ሰዎችንና  ነፍሳትን  ከሲዖል ታወጣና  ወደ  መንግሥተ  ሰማያት  ታስገባቸዋለች።  ሥጋዋ  ወይም  በድኗ በገነት  በሕይወት  ዛፍ  ስር  ተደርጎ  ነበር።  ያደረጉት  ደግሞ  ሬሳውን  ተሸክመው  የነበሩት  ሰዎች  ናቸው።  ስለዚህ  በአካል  ወደ  ገነትና  ወደ ሕይወት  ዛፍ  ይደረሳል  ማለት  ነው።  ሰዎች  ሲሞቱ  ማርያም  አንዳንዴ  ከመላእክት  ጋር፥  አንዳንዴ  ደግሞ  ከደናግል  ጋር  እየታጀበች  ትመጣና  ትወስዳቸዋለች፤  ለሌሎችም  ትታያለች።
ሰዎች  ከሞቱ  በኋላ  ማርያም  መልሳ  አምጥታ  ታሳያለች።  በምዕ. 18-19 እነ ጊዮርጊስ፥  ቴዎድሮስ፥  መርቆሬዎስ፥  የተመልካቾች  ዘመዶቻቸው  ሁሉ፥ በሕዝቡ  ጥያቄ ደግሞ  አዳምና  ሔዋን፥  አብርሃም፥  ይስሐቅ፥  ያዕቆብ፥  እነ ሙሴና  ዳዊት፥  ነቢያትና  ሐዋርያት፥  ወዘተ  እየተሰለፉ  መጥተው  ከመጋዘን  እያመጡ  ለሸማች  እንደሚያሳዩት  ዕቃ  ይታያሉ።  ከዚያ  በኋላ ምን  እንደሚሆኑ  አልተጻፈም።  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ሰዎች  ከሞት የተነሡባቸው  ጊዜያት  አሉ።  ግን  በሰልፍ  መጥተው  ሊሰወሩ  ሳይሆን ታይተው  ኖረው ሞተዋል።  የዓይንዶሯ  መናፍስት  ጠሪ  ለሳኦል ሳሙኤልን  አስነሥታለች።  በአስማት  የምትሠራ  ሙታን  ሳቢ  ናትና  እንዳስነሣች  መሰለ  እንጂ  ሳሙኤልን  በእርግጥ  አላስነሣችም፤  ልታስነሣም  አትችልም። ሳሙኤል  ተነሥቶ  ኖሮ  ቢሆን  ሳኦልም  ያየው  ነበር  እንጂ  ምን  እንዳየች  አይጠይቃትም  ነበር።  ይህ  በነዚህ  ምዕራፎች  የሚታየው  የመናፍስት ጠሪዎች አሠራር  ሆኖ ልዩነቱ  ለጥቂት  ጊዜ መታየታቸው  ነው።
በምዕ.  28  ጌታ  ለሐዋርያት  በገነት  ተገለጠላቸው  ይላል።  በአካል  ገነት ገብተው  ማለት  ነው።  በምዕ.  54  የአንድ  ደብር  አለቃን  ወደ  ሰማይ አሳረገችው።  ሳይሞቱ  የሚነጠቁበትም  ነው።  በ77  የለማኙን  ፊት  በዳቦ  የገመሰው  ሰው  ሞቶ  ሲዖል  ሄደ።  ማርያም፥  “የለም  ይህ  የኔ  ነው”  ብላ ወደ ሲዖል  እንዳይወርድ  ተከራከረች። ዳቦውን  የተቀበለው  ፊቱ  የተገመሰ  ለማኝ  ሄዶ  መሰከረና  ሰውየው  ሲዖል  መግባት  ቀርቶለት  ነፍሱ ተመለሰችና  ከሞት  ዳነ።  ጌታ  እየተሳሳተ  ወይም  እየተጸጸተ  አሳቡን የሚቀይር  ወይም  የሰው  ምስክር  የሚያስፈልገው  የሰው  ዳኛ  መምሰሉም መታለፍ  የሌለበት  ስሕተት  ሆኖ ሳለ ለማኙ  በምን  አካል  ወደ  ዙፋን  ቀርቦ መሰከረ? በአካል  ወይስ  ያለአካል?

12 ለታሪካዊ ሰዎቹ  Schaff, [electronic version] vol. 3, ch. 1-3. History  of the Christian Church, እና Schaff, Nicene and Post Nicene  Christianity, እንዲሁም ታሪካዊ ክርስትና ላይ ከሚያተኩሩ ድረ ገጾች ያገኘኋቸው ተጨምረውበታል፡
13 በዚህ መጣጥፍ ዓመተ ምሕረቶቹ በግዕዝ ቁጥሮች ካልተጻፉ በጎርጎራውያን አቆጣጠር ነው።
14 http://en.wikipedia.org/wiki/John_Chrysostom
ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,

Tuesday, June 24, 2014

ተአምረ ማርያም የተባለው መጽሐፍ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እናት የቅ/ማርያምን የቅድስና ባህርይ አይወክልም!


ካለፈው የቀጠለ (ክፍል ሦስት)
(እዝራ ስነ ጽሁፍ፤ ዘላለም መንግሥቱ)

በምዕ.  24  የተጻፈው  ለማርያም፥  ለመስቀልና  ለስዕል  የማይሰግዱ የተባሉት  የአባ  እስጢፋኖስ  እና  የነደቀ  እስጢፋ  ታሪክ  መጽሐፉ ተተረጎመ  በተባለበት  ዘመን  እንኳ  ተፈጽሞ  ያላለቀና  ገና  እየተከሰተ  ያለ ነገር  ሆኖ ሳለ  ገና  ያልተፈጸመውን  ነገር  ከብዙ  ዓመታት  በፊት  ግብጽ  አገር  እንደተፈጸመ ተደርጎ የመጣና  የተተረጎመ  ማለት  ጥሬ  ውሸት  ነው።  ዘርዓ  ያዕቆብን ንጉሣችን  እያለ  ከተናገረ  ደራሲው  የዘርዓ  ያዕቆብ  ዜጋ  ነው  ማለት  ነው። ተርጓሚው  ማለት የተጻፈውን  ተርጓሚ  እንጂ  ያልተጻፈውን  ጨማሪ  አለመሆኑ የታወቀ ነው።

2.  የተቃለለ  ክርስቶስ።

 በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  የምናየው  ኢየሱስ  ለመሞትና ለኃጢአታችን  ስርየት ደሙን  ለማፍሰስ  ከማርያም  ሥጋን  ነስቶ ሰው  የሆነ አምላክና  ፈጣሪ ጌታና  እግዚአብሔር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  ውስጥ  ከአምላክና  ጌታ  ይልቅ  የተነገረውን  በፍጥነት  የሚፈጽም ቀልጣፋ  ተላላኪና አገልጋይ  ሆኖ  ነው  የቀረበው። ከመጀመሪያ  እስከ  መጨረሻ  ክርስቶስ  የማርያም  ልጅ  ነው።  ኢየሱስ  ከድንግል  ማርያም  ሥጋን  መንሳቱ  እውነት  ቢሆንም  ማርያምን ጨምሮ የፍጥረታት ሁሉ  ፈጣሪ  በመሆኑ  በግዕዘ  ህጻናት ዘወትር እናቱን ለመላላክና ለማገልገል  የመጣ በማስመሰል አምላካዊ  ኃይሉን በሰውኛ ፈቃድ ፈጻሚነት ስር ማስቀመጥ ትክክል አይደለም።  ሥጋ  የለበሰው  ኢየሱስ  እናትነት  አንድ  ነገር ነው።  የዘመን  መጀመሪያ  ለሌለው  አምላክ  እናት መሆኗ ብቻውን  ማርያምን  ከፍጥረቷ  በላይ  ሊያደርጋት  የተገባ  አይደለም።

 ነገር ግን  በተአምረ  ማርያም ውስጥ  ከማርያም  ጋር  በተጻፈባቸው  ቦታዎች  ስትጠራው  ልጄ  ወዳጄ  ብላ  ነው።  ሰዎች  ደግሞ  ወደ  ማርያም  ሲጸልዩ  እርስዋን  እመቤታችን  (እግዝእትነ)  ብለው  ነው። ክርስቶስን ከመለመን ይልቅ ማርያምን በመለመን ከልጇ ምህረት ማግኘት የቀለለ ይመስላል። አንዳንድ የተአምራት ጽሁፎች ላይ ስንመለከት ኢየሱስ ለሰዎች ፈቃደኛ ያልሆነበትን ጉዳይ ማርያም ስትነግረው ቃሉን ሲያሻሽል ይታያል።  ከክርስቶስ ርኅራኄ ይልቅ የማርያም ልመና ምህረት ያስገኛል የሚል ሃሳብን የያዘ ነው። «ዓለም ያለማርያም አማላጅነት አይድንም» የሚለው አባባል ዓለም በኢየሱስ አምላካዊ ፈቃድ የተደረገለትን ድኅነት አምዘግዝጎ የሚጥል ነው።  ኢየሱስን  ግን  በቀጥታ  ሲያናግሩት  ወይም  ወደ  እርሱ  ሲጸልዩም  ሳይሆን  “ከልጅሽ  ከወዳጅሽ”  እያሉ እርሷኑ  ሲለምኗትና ሲጠይቋት ነው  የሚታየው።  «ለምኑ ይሰጣችኋል፤ አንኳኩ ይከፈትላችኋል» የሚለው የወንጌል ቃል ተሰርዞ በማርያም አማላጅነት ላይ ብቻ ተስፋ ጣሉ የሚለው ክህደት ትምህርት መነሻው ምንድነው?
የክርስቶስ ዘላለማዊ ኅላዌነት ማርያምን ያስገኘ ሳይሆን የማርያም መኖር ኢየሱስን እንዳስገኘ ከሚታሰብ ጭፍን ክህደት የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው።  የፈጠረ፤ የቀደሰ፤ ያነጻና ሥጋን የለበሰው በአምላካዊ ፈቃዱ መሆኑ መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ ነው።  ይህንን መዘንጋት ኢየሱስ  በብዙ  የማርያም  ስዕሎች  ላይ  እንደሚታየው  የማርያም  አራስ  ልጅ፥  ጨቅላ  ልጅ፥  ወጣት  ልጅ፥  ታዛዥ  ልጅ፥ ሁሌ ጭኗ ላይ ሲቀመጥ የሚታይ፤ አንድ  ጊዜም  እርሷ የጠየቀችውን  ነገር  እንቢ  ያላለ፥  የተጠየቀውን  ሁሉ  በቅልጥፍና  የሚፈጽም፥  የተሳሳተ  ነገር ጠይቃ እንኳ  ቢሆን  አሳቡን  ስለ  ልመናዋ  ሲል የሚቀይር  ለስላሳ  ልጅ  ነው።

 አንዳንዴ  ስታስፈራራው፥  ለምሳሌ፥ ኢየሱስን  ክዶ ማርያምን  ያመነን  አንድ ሰው  ይቅር እንዲለው በለመነችው ጊዜ  እንደማይሆን  ሲነግራት፥  ልብሷን  ቀዳ፥  “እኒህን  ጡቶቼን እቆርጣቸዋለሁ”  ብላ  ፍርዱን  አስቀይረዋለች፤  (ምዕ.  110ን  ተመልከቱ )። ኢየሱስም  አሳቡን  ቀይሮ  ይቅር  አለው።  በታሪኮቹ  ሁሉ፥  ከትንሣኤ  በኋላ እንኳ፥  ኢየሱስ  በሚታይባቸው  ጊዜያት  ሁሉ  እንደ  ባለ  ግርማ  አምላክ ሳይሆን እንደ ሕጻን  ሆኖ ነው የሚታየው። እዚሁ ምዕራፍ 110 ላይ እንኳ ኢየሱስ  ከዙፋኑ ተነሥቶ  በደረቷ  ላይ ተቀምጦ ተብሎ ተጽፎአል። በምዕ.  90  ልጇ  የተሰቀለባት  አንዲት  ሴት  ማርያም  ልጇን  ከተሰቀለበት ካላወረደችው  እሷም፥  “ልጅሽን  (ኢየሱስን)  ከጭንሽ  እወስደዋለሁ”  አለች።  ኢየሱስ  ሁሌ  በማርያም  ጭን  ተቀምጦ  የሚኖር  ብቻ  ሳይሆን ነጥቀው የሚወስዱትም  ዓይነት ነው። በምዕ. 43  ጴጥሮስ  ለተባለ  ቤተ  ክርስቲያንን  ላነጸ  ሰው  መልኩ  ያማረ ልጅ  ሆኖ  ተገለጠለት።  ‘ቤተ  ክርስቲያን  ያሠራ  ሰው’  ስለተባለ  ምናልባት  በብዙ  መቶ  ዓመታት  በኋላ  ነው  ቢባል  እንኳ  በዚያን  ጊዜ  ጌታ  ሕጻን  አለመሆኑ  ግልጽ  ነው።  ግን ልጅ  (የግዕዙ ሕጻን ነው የሚለው) ሆኖ ነው የተገለጠው።  ኅብስቱ  ሲቆረስ  ደግሞ  የዚህ  ሕጻን  ደም  ፈሰሰና  ታቦቱንና  ልብሱን ሁሉ  አራሰ።  በምዕ. 82  ኢየሱስ በዓለም  ሁሉ ገዢ  የነበረ ንጉሥ  ሳቤላ  የምትባል  ሴት  አስጠርቶ  (ሴቲቱ  በስም  ስትጠቀስ  ንጉሡ አልተጠቀሰም፤  ይህ  የመጽሐፉ አንድ  ደካማ ገጽታ ነው) ምክር  ሲጠይቅ ሴቲቱ  ራእይ አይታ  ለንጉሡ  አሳየችው፤ ያም ማርያም  ሕጻን  አቅፋ  ነው። ኢየሱስ  ሁሌም  ሲታይ፥  ዛሬም  ጭምር፥  በእቅፍ  ያለ  ሕጻን  ሆኖ  ነው ለማርያም  አምላኪዎች  የሚታየው። ኢየሱስ የቀረበበት  አቀራረብም  ከማንነቱ  አውርዶ  ያቃልለዋል።

 በተአምረ ማርያም  ሕጻኑ  ኢየሱስም  ሲራገም  አይጣል  ነው፤  ማርያምም  ስትበቀልና  ስትራገም  የተለመደ  መሆኑ  በቀጣዩ ነጥብ  ይታያል።  በምዕ. 101  ቁ. 108፥ ያፈለቀውን  ውኃ  ለአገሩ  ሰዎች  «መራራ  ይሁንባቸው  የጠጣውም  አይዳን  ብሎ  ባረከው»  ይላል።  ረገመው  ላለማለት  ባረከው  አሉት  እንጂ  ቃሉ ግልጽ  እርግማን  ነው።  በቁ.  125  ግመሎችን  ድንጋይ  ሁኑ  ብሎ  አደነገያቸው።  [“እስከ  ዛሬ  ድረስ  ደንጊያ  ሆኑ”  ይላል።  ኋላ  ኢትዮጵያ ቆይተው  ሲመለሱ  ነፍስ  ተዘርቶባቸው  ተመልሰው  ግመል  ሆነው  ዕቃ ተጭነው እንደሄዱ  የተረሳ  ይመስላል።] በቁ.  159  ኢየሱስ  የግብጽን  አገር  ምድሩንም  ሕዝቡንም  መርገሙ  ተጽፎአል።  ይህ  እዚህ  መርገም የሚያፈስሰው  ኋላ  ላይ  ገና  አፉንም  አልፈታም  የተባለው  ኢየሱስ  ነው። ግጭቱን  ብንተወው  እንኳ  ይህ  የተአምረ  ማርያም  ፈጣሪዎች  የፈጠሩት  እንጂ  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  አይደለም።  የመጽሐፍ  ቅዱሱ  ኢየሱስ  ያስተማረውም  ያደረገውም  ጠላትን መርገም  ሳይሆን  መውደድ ነው። «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ ወደባህርይ አባቱ የጸለየው ኢየሱስ የአገሩ ውሃ መራራ ይሆንባቸው፤ የጠጣውም አይዳን፤ ድንጋይ ሁናችሁ ቅሩ» እያለ በጭራሽ  አይራገምም።

3. የተጋነነች ማርያም።

 ተአምረ ማርያም  እንደ ስሙ የማርያም  ተአምራት  መጽሐፍ ነው። ተአምራቱ  ብዙና የተለያዩ  ናቸው። ማርያም  ብቻ  ሳትሆን በስሟ  የሚደረጉ  ነገሮች  ሁሉ  ክብራቸውና  ክብደታቸው  እጅግ  ነው።
ለምሳሌ፥  በተአምር  12  ውስጥ  78  ሰዎች  የበላ  ጭራቅ  በማርያም  ስም ውኃ  ስላጠጣ  ሞቶ  ወደ  ሲዖል  እንዲሄድ  ጌታ  ፈረደበት።  ማርያም  ቀርባ  78ቱ  ነፍሳትና  ውኃው  በሚዛን  ይደረጉ  ብላ  ተደርጎ  የውኃው  ክብደት  እንዲመዝን በዘዴ ጥላዋን እንዳሳረፈችበት፤ የሞቱት ሰዎች ነፍሳት ስለቀለሉ  ጌታ  አሳቡን  ቀይሮ  ወደ  መንግሥቱ  ያስገባዋል ሲል እናገኘዋለን። ይህ እንግዲህ የፈለጋችሁትን ዓይነት ኃጢአት ብትፈጽሙና አምላክን ስለበደላችሁ ቢፈረድባችሁ እንኳን «ማርያምን ካመናችሁ ትድናላችሁ» ለማለት የተዘየደ የመዳኛ ምክንያት ነው።  የተአምሯ ማርያም ፍርዱን ለመቀየር በጥላዋ ሳይቀር እስከማታለል የመሄድ ብቃት እንዳላት ጥንካሬዋን ለማጎልበት ሲጠቀሙበት ይታያል። በአምሳለ እግዚአብሔር  የተፈጠሩ  78  ሰዎች  ነፍሳት  ከጥርኝ  ውኃ  መቅለላቸው አሳዛኝ ነው።  በምዕራፎቹ  ሁሉ  ማለት  እስከሚቻል  ማርያም  ከእግዚአብሔር  ጋር ተስተካክላ  ነው  የምትገለጠው።  ለምሳሌ፥  በ41፥13  “በእግዚአብሔር  አምነው፥ በወለደችውም  በእመቤታችን  አምነው  ከቤተ  ክርስቲያን ወጡ”  ይላል።  በማን  አምነው?  በእግዚአብሔርና  በማርያም!  እዚሁ  ምዕራፍ  ቁ.  25፥  “እምነቱን  በናቱና  በእግዚአብሔር  ላይ  ያደረገ  ሁሉ  አያፍርምና”  ይላል።  እዚህ  እንዲያውም  ማርያም  ቀድማ  እግዚአብሔር  ተከተለ!  ምዕ.  76  መነኮሳቱ  ሲጸልዩ  እግዚአብሔርንና  ማርያምን  ነው፤  “እንለምንሃለን  .  . .  እንለምናታለን”  ቁ. 15።

  አንዱ  ቄስ  ደግሞ  የማርያምን  ውዳሴ  ብቻ እንጂ  ሌላ  የማያውቅ  ነው፤  ምዕ.  76።  ይህንን  ቄስ  ሌላ  ካላወቀ እንዳይቀድስ  የከለከለውን  ኤጲስ  ቆጶስ  ወደ  አገልግሎቱ  ካልመለሰው በ30  ቀን  ትሞታለህ  አለችው።  ከግዝቱ  ፈታውና  እርሱም  ማርያምን እያደነቀ  አብረው  ኖሩ።  እዚህ  የምትታየው  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም እርሷ እስከተወደሰች ድረስ  እግዚአብሔር  ባይመሰገንም  ደንታ  እንደሌላት ነው።
በምዕ. 86 ማርያምን በፍጹም አሳቧ፥ በፍጹም ልቧ የምትወድ የተባለላት ሴት  ታሪክ  ይገኛል።  እንዲህ  ባለ  መውደድ  መወደድ  ያለበት እግዚአብሔር  ብቻ  መሆኑን  ነው  መጽሐፍ  ቅዱስ  የሚያስተምረን።  እና በቃሉ  (ዘዳ. 10፥12-13፤  ማቴ. 22፥37፤  ማር. 12፥30-32፤  ሉቃ. 10፥27)  እንደተጻፈው ሰው በፍጹም ልቡ መውደድ ያለበት  እግዚአብሔርን  ነውና  ማርያም  ይህንን  ማሳወቅ  ሲኖርባት  አለማድረጓ  የመለኮትን  ፍቅር ማስቀነሷ ነው። በዚህ  ምዕራፍ  የተጠቀሰው ሰው ጠንቋይን  ምክር  የጠየቀ ሰው  ሆኖ  ምንም  ወንጌል  ሳይሰማ  ግን  የማርያምን  ስም  ሲነገረው  በነፋስ  ፊት  እንዳለ  ገለባ  ሆነ።  ሲሞትም  ማርያም  ሬሳውን  አንሥተው  በገዳም እንዲቀብሩት ተናገረችለት።  ማርያም ሰው  የሚሞትበትን  ቀን  የምታውቅ ናት።  ከላይ ለቄሱ  በ30 ቀን እንደሚሞት  ተናግራው  እንደነበር  አይተናል።  ሌላ  ምሳሌ፥  በምዕ.  81  አንድ  መነኩሴን  በአንድ  ሌሊት  ተገልጣ  ወደ  ኢየሩሳሌም  ወስዳ  አዙራ አስጎብኝታ፥  በዮርዳኖስም  አጥምቃ  የሚሞትበትን  ጊዜ  ነገረችው፤ እንደተናገረችው  ጊዜ  ዐረፈ።  ከእግዚአብሔር በቀር የሚያውቃቸው የሌሉ ነገሮችን  ካወቀች  ሁሉን  አዋቂ  ናት  ማለት  ነው?  ሁሉን  አዋቂ  ከሆነች አምላክ ናት ማለት ነው? የዚህ  መጽሐፍ  ማርያም  ስትፈልግ  ርኅሩኅ  ሳትፈልግ  በቀለኛ  ናት።

  ለምሳሌ፥  በምዕ  35  አንድ  እስላም  ዘራፊ  የዘረፈው  በገዳም  የሚኖር  ቄስ ወደ  ማርያም  ስዕል  ሄዶ  ተማጸነ፤  ጸልዮ  ሲወጣ  ዘራፊው  ወድቆ  እጁ ተሰብሮ  አጥንቱ  ገጦ  ወጥቶ  አየው።  እስላሙ  ይቅርታ  ሲጠይቀው ሽማግሌው  ማርያም  ይቅር  ብትልህም  ባትልህም  እንደወደደች  አለው፤ ይህ  ሰው  ቄስ  ሆኖ  ስለ  ይቅርታ  አያውቅም።  ቄስ  ነው  እንጂ  ክርስቲያን  አይደለም  ማለት  ነው።  ክርስቲያን  ቢሆን  ክርስቶስን  ሊመስል  ይሞክር ነበር።  እስላሙ ስላደረገው ጥፋት ይቅርታ ሲጠይቅ፤ ቄሱ «ይቅር ብትልህ ባትልህ» ካለ  እስላሙን ማን አስተምሮና አሳምኖ ሊለውጠው ነው? የሚገርመው ደግሞ ቄሱ ብቻ ሳይሆን የተአምሯ የማርያም  ስዕል  አፍ አውጥታ  «በቄሱ  ላይ  ደፍሯልና  ይቅርታ አይገባውም  አለችው»  የሚለው የበለጠ አስገራሚ ነው።  ስለዚህ  እስላሙ  በቄሱም፤ በተአምሯ  ስዕል አንደበት ወንጌልም  ሳይሰማ፥  ይቅርታም ሳያገኝ ሞተ።  ነገር ግን በተአምር 33፥39 ላይ ደግሞ ማርያም የይቅርታ ሳጥን ተብላለች።  እዚህ ላይ ደግሞ ተቃራኒ ናት። በቀለኛና  የደግነት ባህርይዋ  በወንጌል ላይ ሳይሆን በድርጊቱ  የአተራረክ ሁኔታ ላይ የሚደገፍ ነው።

 በምዕ. 39 ላይ ደግሞ በቀለኛ ማርያም ትታያለች። ሌላ  እስላም  ዘራፊ  ገዳም  ዘርፎ  ሲሄድ  ሰዎች  አግኝተው  ገደሉት፤  ከቤተ  ሰቡ  10  ሰዎች  ከዘመዶቹ  18  ገደሉና  የተዘረፈውን  አምጥተው  ለገዳሙ  ሲመልሱ  በቁ.  35፥ “ልቡናችንን  እርሱን  ለመግደል  ያነሣሳችን  ማርያም  እንደሆነች  ፈጥነን አወቅን”  አሉ።  «መጎናጸፊያህን ለሚወስድ እጀ ጠባብህን ተውለት» ለሚለው የወንጌል ቃል ግድ የሌላቸው መነኮሳቱ  ዘራፊውን  ከመግደላቸውም በላይ በቦታው ያልነበሩትን 10 ቤተሰቦቹንና 18 ዘመዶቹን በመግደላቸው ደስ ተሰኝተዋል። ይህንን የግድያ ስራ እንዲፈጽሙ ያነሳሳቻቸው ማርያም ናት ይላሉ። የተአምሯ ማርያም  ሰዎችን  አስነሥታ  ታስፈጃለች። የሚያሳዝነው  መነኮሳቱም  በዚህ  ነገር  ፍጹም  ደስታ  ተደሰቱ።  ኃጢአተኛ ሲድን  ሳይሆን  ሲሞት  የሚደሰቱ  መነኮሳት  ወንጌልን  ያውቃሉ  ይባላል?  በምዕ.  98  ከአንድ  ሽማግሌ  አስተማሪያቸው  ጋር  ፍልሰቷን  ለማክበር ሲሄዱ  አስተማሪያቸውን  ወደ  ገደል  የጣሉ  40  ተማሪዎች  በእሳት  ጦር እየወጋ  የሚገድላቸው  መልአከ  ሞት  አዘዘችና  በአንዴ  አለቁና  ሽማግሌውን  ግን  ወደ  በዓሏ  መከበሪያ  አደረሰችው።

  በምዕ.  15  አንድ  ግመል  ጫኝን  ጎድኑን  ወግታ  ስትገድለው  ትታያለች።  ደራሲዎቹ  ማርያምን  በቀለኛ  ሲያደርጓት  እርሷን  ለማግነን  ሲሉ  አስቀያሚ  ቀለም እየቀቧት  መሆናቸውን  እንኳ  አያውቁም።  ወይስ  አውቀው  ነው  አያደረጉ ያሉት? የተአምረ ማርያሟ  ማርያም  በቀለኛ ብቻ  ሳትሆን ቀናተኛም  ናት።  በምዕ.  92  የአንድ  ንጉሥን  ወጣት  ልጅ  እርሱ  ከሚወዳት  የበለጠ  እርሷ እንደምትወደውና  እንደምትቀናበት፥  ሚስት  ሳያገባ  እንዲኖርም እንደመከረችውና  በእጇ  ስዕሏን  እንደሰጠችው  ተጽፎአል።  ንግግራቸው  የሁለት  ፍቅረኞች  ይመስላል።  ልጁ  ሲሞትም  ብዙ  መላእክት  እና  ደም ግባቷ  ያማረች  ማርያም  መጥተው  በሰው  ሁሉ  እየታዩ  ይዛው  ሄደች። በእግዚአብሔር  የተደነገገ  ጋብቻ  የተናቀበትና  የተዋረደበት  እንደዚህ  ያለ መጽሐፍ  አላነበብኩም።  ያላገቡ  እንዳያገቡና  ድንግልናቸውን  ለማርያም  ስዕለት  አድርገው  እንዲሰጡ  የሚበረታቱበት  ብቻ  ሳይሆን  የተጋቡ  እንኳ  ከተቀደሰ  መኝታ  የሚከለከሉበት  ነው። መመነን፥ መመንኮስ፥ ተሰባስበው  በገዳም  መኖር  በመጽሐፍ  ቅዱስ  የተደነቀና  የተመሰገነ  ልምድ አይደለም።
ምንኩስናና  ገዳማዊነት  በክርስትና  ታሪክ  ውስጥ  ብቅ  ያለው  ቤተ ክርስቲያን  ከምድራዊ  መንግሥት  ጋር  እንደ  ውኃና  ወተት በተደባለቀችባቸው  ዘመናት  ከምድራዊ  ርኩሰትና  መንግሥታዊ  ሃይማኖት  ጋር  ላለመርከስ  የተደረገ  ሽሽት  ነው።  በዚህ  መጽሐፍ  ግን  ነባር  ልማድ  ብቻ  ሳይሆን  የተሞገሰ  አኗኗር፥ እጅጉን  የተጋነነ ሥርዓትም  ሆነ። ተአምራት  በመጽሐፍ  ቅዱስ  ውስጥ  ብዙ  ጊዜያት  የተደረጉ  ሲሆን የተአምራት  ዋነኛ  ግብ  የእግዚአብሔር  ክብር  ነው።  በተአምረ  ማርያም  በተደረጉት  ተአምራት  ግን  ክብር  እግዚአብሔር  ሲሰጥ  ከቶም  አይታይም።  እያንዳንዱ  ምዕራፍ  ሲጀምር  የእመቤታችን  ተአምር  .  .  .  ብሎ  ይጀምርና  ሲጨርስ  በረከቷና  .  .  .  ይደርብን  ይላል።  ሲጀምር ማርያም፥  ሲጨርስ  ማርያም።  ክብር  ለማርያም  እንጂ  ለእግዚአብሔር  የሚባል  ቋንቋ የለም።
 የኢትዮጵያ  ሰዎች  ለማርያም  የተሰጡ  ዐሥራት  ሆነው  ቀርበዋል።  ዐሥራት ማለት ከዐሥር አንድ እጅ ማለት ነው። ይህ አጠያያቂ  ቃል ነው። የኢትዮጵያ  ሕዝብ እንዴት ነው  1/10ኛ የሆኑት?  9ኙ እነማን  ናቸው?  ሕዝብ  እንደሕዝብ አስራት  ተደርጎ  የተሰጠበት  ታሪክ  ኖሮ  ያውቃል?  እንኳን  ሕዝብ  በሙሉ  ይቅርና  ከአዳም  ጀምሮ  ፈቃድ ያለው  አንድ ሰውስ  ያለ  ፈቃዱ  በመንፈሱ  ላይ  ሌላ  ሊሰለጥን  እንዴት ይገደዳል?  ደግሞስ  አስራት የሰጠው  ኢየሱስ ከሆነና ማርያም  አስራት ተቀባይ ከሆነች በተአምረ  ማርያም  ላይ  ምን  እየተነገረ  ነው?  አስራት ለማን  ነው  የሚሰጠው?  አምላክ  አስራት  ሰጪ፤  ማርያም  ደግሞ  አስራት ተቀባይ  ከሆነች ማርያምን መለኮት ማድረጋቸውም  አይደል? ከመለኮትም  በላይ እንጂ!  እግዚአብሔር ነዋ!  አስራት ሰጪው።
 በምዕ. 84 ሰንበትን  የሻረ አንድ አገልጋይ  ድዳ ሆነ። ጌታው ወደ ማርያም  ጸለየና  ፈወሰችው።  የተሻረው  ሰንበት  ነው።  የምትጠየቀው  ደግሞ ማርያም  ከሆነች  እርሷ  የሰንበት  ባለቤት  ናት  ማለት  ይመስላል።   «የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነውና» ማቴ 12፤8 የሚለው ቃል በተአምረ ማርያም ላይ ተቀባይነት የለውም።
በምዕ.  110  «እግዚአብሔርን  ክዶ  ማርያምን  ግን  አልክድም»  ያለ  ሰው  በማርያም  ኢየሱስን  አስፈራሪነት  ይቅርታ  ሲያገኝ  ይታያል።  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  ማምለክ  ክቡር  ቦታ  አግኝቶአል።  ጌታ  እግዚአብሔርን  ክዶ ማርያምን  አለመካድ  ወይም  ማምለክና ማንን  የማግነን  ጉዳይ ነው?  የተአምረ  ማርያሟ  ማርያም  ማዕረጓ  ብዙ  ነው።  እመቤት  ናት፤  የአርያም ንግሥት  ናት  ወዘተ፤  ችሎታዋ  ድንቅ  ነው፤  ተፈጥሮ  በቁጥጥሯ  ስር  ነው፤ ተአምራት  ታደርጋለች፤  በሰው  ልብ  የታሰበውን  ታውቃለች፤  በሞትም  ላይ  ሥልጣን  አላት  ወዘተ፤  ሥልጣኗ  የመለኮት  ነው፤  መላእክት ይገዙላታል፥  ፍጡራን  ሁሉ  ያገለግሏታል፤  የመመረቅ፥  የመርገም፥ የመግደል፥  ከሞት  የማንሣት፥  ከእግዚአብሔር  ጋር  በእኩል  የምትለመንና የምትመሰገን  ናት  ወዘተ።  እንዲያውም እግዚአብሔርን የካዱ እርሷን ካመኑ ማዳን የሚያስችል አቅም አላት። እግዚአብሔርን ማመን አያስፈልግም። ማርያምን ብቻ ማመን በቂ ነው። ተአምረ  ማርያም  እንዲህ  በመሰሉ  ማርያምን በመጽሐፍ  ቅዱስ  ካላት  ትክክለኛ  ስፍራ  ፈንቅሎ፥  ተገቢ  ቦታዋን  ነጥቆ፥ ያልሆነችውን  አድርጎ፥  ያልተሰጣትን  ሰጥቶ፥  ያልለበሰችውን  ደርቶ የሚጸለይላት፥  የምትለመን፥  የምትመለክ  አድርጎ  መለኮታዊ  ሥልጣንና ኅልውና  ሰጥቶአታል። 

 ይቀጥላል,,,,,,,,,,,,,,,