Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts
Showing posts with label ማብራሪያ. Show all posts

Saturday, April 20, 2024

ጸጋ ምንድነው? (What is grace?)

ጸጋ ምንድነው? (What is grace?) ክፍል ዐራት በባለፉት ክፍሎች የተመለከትነው በኢየሱስ አምነን ለዳንን ሰዎች ሁሉ የጸጋ ኃይል የሚያስፈልገን ለምንድነው? ለሚለው ጥያቄ ሦስት የኃጢአት በሮችን ለመዝጋት ነው በሚለው ሃሳብ ዙሪያ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማብራሪያ ስንሰጥ መቆየታችን ይታወሳል። በዚሁ መሠረት ከሦስቱ የኃጢአት በሮች መካከል 1/ሥጋ 2/ ዓለም እንዴት ሊፈትኑን እንደሚችሉና ከሁለቱም የሚመጡ ፈተናዎች እንዴት መዋጋት እንደሚገባን ተመልክተናል። ሥጋ ማለት የተሸከምነውና የራሱ መሻት ያለው በነፍስ ሕያውነት የሚንቀሳቀስ አካላችን ሲሆን ይህም የሚኖረው በዚህች ምድር ላይ እንደመሆኑ መጠን ዓለም ሥጋን በባርነት እንዳትገዛ በሚዛን ለመኖር የሚያስችለን ጸጋ የሚባል ጉልበት እንደሚያስፈልገን አይተናል። ዛሬ ደግሞ ሦስተኛው ክፍል የሆነውንና የክፋት ሁሉ የኃጢአት ሹም ስለሆነው ስለወደቀው መልአክ እንመለከታለን። ይህ ፍጥረት በትዕቢት፣ በተንኮልና በክፋት የተካነ ነው። ረጅም እድሜና ብዙ ልምድ ያለው የሰው ልጆች ሁሉ ጠላት ነው። የዚህ ዓለም ገዢ የተባለውም ዓለሙን ሁሉ በዐመፃና በኃጢአት ስለያዘው ነው። “ከእግዚአብሔር እንደ ሆንን ዓለምም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን።”1ኛ ዮሐ 5፥19 ይህ ጥንተ ጠላታችን ወደጥልቁ ወርዶ ለዘለዓለም እስኪታሰር ድረስ ለሰው ልጆች ምንም ዓይነት ርኅራኄ የለውም። ራእይ 20:10 የወደቀው መልአክ እብሪትና ትዕቢትን ሞሪስ የተባለ የነገረ መጻሕፍት ተርጓሚ “ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፥ በልዑልም እመሰላለሁ አልህ።” ኢሳ 14፥14 ያለውን ቃል ሲተረጉም የወደቀው መልአክ ምኞቱ የመላእክት ሁሉ አለቃ መሆን ብቻ ሳይሆን አምላካዊ ሥፍራንም መፈለጉን ያሳያል ሲል ይፈታዋል። የትኛውም ምኞትና አደገኛ የአምልኮ መሻት ሁሉ ምንጩ የዚህ የወደቀው መልአክ ውጤት ነው። የናቡከደነጾር የዱራ ሜዳ ሐውልት (ዳን3:1) የምናሴ የማመለኪያ አፀድ (2ኛ መዋዕል 33)፣ ዳጎን (መሣ16:23)፣ ቤል (ኤር 50:2) ወዘተ ሁሉም የወደቀው መልአክ ሥራዎች ናቸው። ይህንንም መዝሙረኛው እንዲህ ይላል። “የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸውና፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።” መዝ 96፥5 ይህ የወደቀው መልአክ ለራሱ ብቻውን ወድቆ አልቀረም፣ የመጀመሪያዎቹንም የሰው ልጆች ጣለ እንጂ። የሚገርመው ነገር ሰዎቹ ሳይጠይቁት ራሱ ሰላማዊ ጠያቂ ሆኖ ነው የቀረበው። ከጠያቂነቱ ባሻገር እንዳይበሉ የተከለከሉት ተክል ስለመኖሩ እያወቀ፣ እንደማያውቅ ፍጥረት ሆኖ ነበር የቀረባቸው። "...ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት።”ዘፍ 3፥1 ስለመከልከላቸው እውቀቱ ከሌለው ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? ብሎ ባልጠየቀም ነበር። በሚመልሱት መልስ ለማጥመድ ነው። ይህንን በቃል የማጥመድ ተንኮል በኢየሱስ ላይም ሞክሮት ነበር። “በሕዝቡም ፊት በቃሉ ሊያጠምዱት አልቻሉም በመልሱም እየተደነቁ ዝም አሉ።”ሉቃ 20፥26 ሔዋን እንዳትበሉ አዝዞአልን? ብሎ ለጠየቃት የማጥመጃ ቃል የሰጠችው መልስ እንዲህ የሚል ነበር። (ዘፍጥረት 3:2—3) ሴቲቱም ለእባቡ አለችው፦ በገነት ካለው ከዛፍ ፍሬ እንበላለን፤ ነገር ግን በገነት መካከል ካለው ከዛፉ ፍሬ፥ እግዚአብሔር አለ፦ እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም። ሔዋን ሞትን ሞታ ስለማታውቅ ይሄ ጠላት በገዛ ቃሏ ምን እንደሚመስል ሊያሳያት ነው። (ዘፍጥረት 3፣3—4) እባብም ለሴቲቱ አላት፦ ሞትን አትሞቱም፤ ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ። ይህ ጠላት ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ይልቅ የሱ ድምፅ የተሻለ ፍቺና ምስጢር እንዳለው እየተናገረ ሰዎቹን ወደቤተ ሙከራ እየወሰዳቸው እንዳለ እናያለን። በሚያምረውና በሚያስጎመጀው የጠላት ቤተ ሙከራ የገቡት እንግዶች አብሯቸው የነበረው ፍሬ የተለየ ውበት እንዳለው ያንጊዜ እንደአዲስ የተገለፀላቸው ይመስል ነበር። “ሴቲቱም ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደ ሆነ፥ ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ፥ ለጥበብም መልካም እንደ ሆነ አየች፤ ከፍሬውም ወሰደችና በላች፤ ለባልዋም ደግሞ ሰጠችው እርሱም ከእርስዋ ጋር በላ።” ዘፍ 3፥6 የወደቀው ጠላት አዲሶቹንም ፍጥረቶች ይዞ ወደምድር ተፈጠፈጠ። ይሄንን ሀተታ እዚህ ላይ ማንሳት ያስፈለገው ለመጽሐፍ ቅዱስ አንባቢያን ያልተነበበ ታሪክ ለመንገር ሳይሆን ይሄ ረጅም እድሜ፣ ልምድና ሁሉንም ክፋት የያዘ ፍጡር ዛሬም እየሰራ ያለ መሆኑን ለማስገንዘብ ነው። ዛሬም ያማልላል፣ ያስጎመጃል፣ ያስመኛል፣ ያስፈፅማል፣ ያጋድላል፣ ያፋጃል፣ ሁሉንም ክፋት በሰው ልጆች መሀል ያስፈፅማል። ስለዚህ ይሄንን ባለብዙ ልምድ ጠላት ለመዋጋት "ጸጋ" የተባለ መመከቻ የእምነት ጋሻ የግድ ልንታጠቅ ይገባል። ያለበለዚያ የመጫወቻው ሜዳ ከመሆን ልታመልጥ አትችልም። ይህ ጸጋ እንዴት እንደሚሰራ የጳውሎስ ተማሪ የነበረው ቲቶ በመልእክቱ እንዲህ እያለ ይነግረናል። “ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤” ቲቶ 2፥12-13 ጸጋ በክርስቶስ ኢየሱስ አምነው የዳኑ ሰዎች የክርስቶስን መገለጥ እየጠበቁ፣ ራሳቸውን እየገዙ፣ በጽድቅና በቅድስና እየኖሩ ዘመኑን የሚሻገሩበት ሰማያዊ መሣሪያ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ በጻፋቸው መልእክታት በሙሉ የመዝጊያ ቃል አድርጎ ከሚጠቅሳቸው የጸሎት መደምዲያው ክፍል "ጸጋ" ከእናንተ ጋር ይሁን እያለ ይለምን የነበረው አለምክንያት አልነበረም። ሦስቱን የኃጢአት በሮች መዝጋት የሚቻለው ከእግዚአብሔር በሚሰጠን ጸጋ ብቻ ነው። ይህ ጸጋ እንዴት እንደሚገለጥና እንደሚሰራ እግዚአብሔር ቢፈቅድና ብንኖር በቀጣይ ፅሑፋችን ለማየት እንሞክራለን።

Tuesday, March 12, 2024

እግዚአብሔር ሰው በሠራው ቤተ መቅደስ አይኖርም!

ይህ አባባል እግዚአብሔር ሰው በሠራው መቅደስ ዛሬ ይኖራል ብለው ለሚያምኑ ሰዎች ጆሮን ጭው የሚያደርግ ቃል ነው። ነገር ግን እውነቱ እግዚአብሔር ዛሬ ሰው በሠራው መቅደስ አለመኖሩ ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር አዝዞት፣ ወርድና ቁመቱን ነግሮት የተሠራ ምድራዊ ቤተመቅደስ ዛሬ የለምና ነው። የቀደመችቱን የእስራኤል ቤተ መቅደስ ወርዱንና ቁመቱን፣ ስፋትና ርዝመቱን፣ ጽላቱንና ታቦቱን፣ ኤፉዱንና አልባሳተ ካህናቱን፣  መጋረጃዎቹንና ቀለማቱን፣ በአጠቃላይ የቤተ መቅደሱን ንዋያተ ቅድሳት የመረጠው እግዚአብሔር ራሱ ነበር እንጂ ምድራውያን ሰዎች አልነበሩም። ያቺ እግዚአብሔር ይገለጽባት የነበረችው ቤተ መቅደስ ዛሬ የለችም። በሙሴ የነበረው የመገናኛው ድንኳን እግዚአብሔር ራሱ ባዘዘው መሠረት የተሠራ ነው። (ዘጸ36:1) በሰሎሞን ዘመን ወደሕንጻ ቤተ መቅደስ ሲቀየር ለዳዊት ከወገቡ የሚወጣው ልጁ እንደሚሰራለት እግዚአብሔር ራሱ ተናግሮ ስለነበር እንጂ ሰሎሞን ከልቡ አንቅቶ የሰራው አልነበረም። (2ኛ ዜና 6:9) ይህ ሰሎሞን ያሠራው ቤተ መቅደስ የፈረሰበትን ታሪክ መጽሐፍ ቅዱሳችን ሲነግረን ሕዝቡ እንደአሳቡ፣ እንደፈቃዱና እንደትእዛዙ ባለመሄዱ የተነሳ የደረሰባቸውን መከራ እንዲህ ይተርክልናል።  “ሴዴቅያስም በነገሠ በዘጠኝኛው ዓመት በአሥረኛው ወር ከወሩም በአሥረኛው ቀን የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆርና ሠራዊቱ ሁሉ ወደ ኢየሩሳሌም መጥተው ከበቡአት፤ በዙሪያዋም ዕርድ ሠሩባት።  (2ኛ ነገሥት ምዕራፍ 25ን  ያንብቡ) ቤተ መቅደሱ በናቡከደነጾር ፈርሶ፣ ንዋያተ ቅድሳቱ ተዘርፎ፣ ሕዝቦ ለባርነት ተግዞ ከተወሰደ በኋላ ኢየሩሳሌም ዳዋ ወርሷት ነበር። “እናንተንም ከአሕዛብ መካከል እበትናችኋለሁ፥ ሰይፍንም አስመዝዝባችኋለሁ፤ ምድራችሁም የተፈታች ትሆናለች፥ ከተሞቻችሁም ባድማ ይሆናሉ።”   ዘሌ 26፥33 ያለው ቃል ተፈጽሟል። ሁለተኛው ቤተ መቅደስ ተመልሶ የተሠራው በታላቁ ሄሮድስ ሲሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሞቱ በተናገረበት አንቀጽ የ2ኛውንም ቤተ መቅደስ መፍረስ ሲተነብይ እንዲህ ብሎ ነበር። “ኢየሱስም መልሶ፦ ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ አላቸው።” ዮሐ 2፥19 አይሁዶችም ሲመልሱለት፣ "ወይቤልዎ ፡ አይሁድ ፡ በአርብዓ ፡ ወስድስቱ ፡ ዓመት ፡ ተሐንጸ ፡ ዝንቱ ፡ ቤተ ፡ መቅደስ ፡ ወአንተሰ ፡ በሠሉስ ፡ መዋዕል ፡ ታነሥኦ?" ይህ ቤተ መቅደስ ለማነጽ 46 ዓመት ፈጀ፣ አንተ በሦስት ቀን መልሰህ ትሰራዋለህን? ብለው ጠይቀውታል። ዋናው መልእክቱ ለሰውነቱ ቤተ መቅደስ ቢሆንም ከሕንጻው ቤተ መቅደስም መፍረስ ትንቢት ነበር። ይህ በሄሮድስ የታነጸው ሁለተኛው ቤተ መቅደስ 46 ዓመት የፈጀ ሲሆን ሰሎሞን ካሰራው ቤተ መቅደስ የተለየ ነበር። ምክንያቱም እግዚአብሔር ያዘዘው ቃል ሥርዓት የሚፈጸምበትና የሚከናወንበት ቤተ መቅደስ አልነበረም። ታቦቱ የለም። ታቦቱና ጽላቱ በሌለበት የእግዚአብሔር ክብር አይታይም ማለት ነው። የቤተመቅደሱ ሥርዓት የሌለበት፣ ታቦቱና ጽላቱ የማይገኝበት፣ እግዚአብሔርም በሁለቱ ኪሩብ መካከል በሚታየው የክብር ደመና መካከል  ተገልጾ በአሮን የክህነት ማዕረግ ተሹመዋል የተባሉትንና በወቅቱ ሊቀካህናት የነበሩት ሐናንና ቀያፋን የሚያናግርበት ቤተ መቅደስ አልነበረም። የእግዚአብሔር ድምጽ የሚሰሙበት ቤተ መቅደስ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ስለኢየሱስ ድምጽ ይመጣላቸው ነበር። ከዚያ ይልቅ በዚህ በሄሮድስ ቤተ መቅደስ አደባባይ የሕዝቡ የኃጢአት ሥርየትና የደኅንነት መስዋዕት ሳይሆን ይቀርብ የነበረው የገንዘብ ለዋጮችና የርግብ ሻጮች ገበታ ነበር። ገንዘብ ለዋጮቹ ለበዓል ከተለያዩ ሀገራት የሚመጡትን ሰዎች ገንዘብ የሚመነዝሩ /money exchangers/ ሲሆኑ ርግብ ሻጮቹ ደግሞ ለበደል ሥርየት የሚሆኑ ርግቦችን ለሚመጡ ለእንግዶች የሚሸጡ የነጋዴዎች አደባባይ ሆኖ ነበር። ይህ ተግባር እግዚአብሔር አዝዞ በተሠራው በሰሎሞን ቤተ መቅደስ አደባባይ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ የሚለውን ቅጣት ያስከትል ነበር። ኢየሱስም፣ በዚህ ድርጊታቸው በተበሳጭቶ “ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች ተብሎ ተጽፎአል፥ እናንተ ግን የወንበዶች ዋሻ አደረጋችኋት አላቸው።” (ማቴ 21፥13) ይህ ቤተ መቅደስ እግዚአብሔር የማይከብርበት፣ ሥርዓተ መቅደሱ የማይፈጸምበት ስለነበረ መፍረስ ነበረበት። ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ቤተ መቅደሱ እንደሚፈርስ በተናገረው ቃል መሠረት ባረገ በዐርባኛው ዓመት፣ የሮማው ንጉሥ ጥጦስ በ70 ዓ/ ምህረት ገደማ ካፈረሰው በኋላ ላለፉት 2000 ዓመታት ቤተ መቅደስ የሚባል ታሪክ የለም። ከዚያ በኋላም  እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ስሩልኝ ያለው የተለየ ሕዝብና ሀገርም የለም። የቤተመቅደሱን ስፋትና ቁመት፣ የንዋያተ ቅድሳቱን ዝርዝርና ዓይነት የነገረው አንድም ሕዝብ ስለሌለ እግዚአብሔርን ለመገናኘት የምንሄድበት ቤተ መቅደስ በዓለም ላይ የትም ሀገር የለም። ልባቸው ያፈለቀውን፣ ኅሊናቸው ያሰበውን፣ ያላቸው የገንዘብ አቅም የፈቀደላቸውንና በሕንጻ አሠሪ ኮሚቴ በተፈቀደ ዲዛይን በተሠራ ሕንጻ ውስጥ እግዚአብሔርን ይገባበት ዘንድ በወይራና በቅብዐ ሜሮን ግንቡን ረጭተው እግዚአብሔር ሆይ ቀድሰነዋልና ና ግባበት እያሉ ሲጣሩ ውለው ቢያድሩ በዚያ በሰዎች ሃሳብ ሕንጻ ውስጥ እግዚአብሔር የለም። እግዚአብሔር እንደዚያ አድርገው እንዲሰሩለት ያዘዘው ሕዝብና ሀገር ስለሌለ፣ ሰዎች በልባቸው መሻት በሰሩት ቤተ መቅደስ ውስጥ በተሽሞነሞነ ጥሪና ልመና  የሚገባ አምላክ አለ ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል። የሚገባ ካለም ሌላ መንፈስ ይሆን ይሆናል እንጂ የሰማይ አምላክ አይደለም። ሐዋርያት 17፣ 24—25 "ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤ እርሱም ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣልና አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም"። አሁን ቤተ መቅደሱ አንተ ነህ። ይሄን አንተ ቤተ መቅደስ የሆነው ሰውነትህን አቆሽሸህ ስታበቃ ሕንጻውን ቀድሼዋለሁ ብትል ስህተትም፣ ክህደትም ነው። ለዚህም ነው፣ የቆሸሹ፣ ከኃጢአት ያልተመለሱ፣ ለመመለስም ፍላጎት የሌላቸው ዐመጸኞች ቤተ መቅደስ በሚሉት ሕንጻ ውስጥ ተሰግስገው መደበኛ ኑሮአቸውን የሚኖሩት። እግዚአብሔር እኔ ውስጥ የለም፣ እዚያ እኔ በሠራሁት ሕንጻ ውስጥ አምላኬ ስላለ ጥዋትና ማታ እየሄድኩ ኃጢአቴን ይቅር እንዲለኝ እነግረዋለሁ ብትል ሕንጻ ውስጥ ቁጭ ብሎ የአንተን ኃጢአት የሚሰማ የሰማይ አምላክ ስለሌለ መጀመሪያ ራስህን ቀድስ። ኢየሱስ ከኦሪቱ ቤተ መቅደስ አገልግሎት ይልቅ ወደበለጠው የአዲስ ኪዳን አገልግሎት የመጣው አንተን አማኙን ለመቀደስ እንጂ በድንጋይ የተሠራ ቤት ለመቀደስ አይደለም። “ኢየሱስም መለሰ አለውም፦ የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።”   — ዮሐንስ 14፥23 እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ ስለተባለ ቤተ መቅደሱ አንተ ራስህ ነህ። ቃሉን ጠብቅ፣ አብ ይወድሃል። ወልድም ይወድሃል። አንተም መኖሪያው ትሆናለህ። አንተ መኖሪያው ካልሆንክ የእግዚአብሔር መኖሪያ የሆነ ሌላ ሕንጻ የለም። ሕንጻው አንተ ነህ። ይሄንን ሕንጻ የሠራው ኢየሱስ ነው። (በቀጣይ ፅሑፋችን "ሰው የእግዚአብሔር መኖሪያ ሕንጻ መሆን እንዴት ይችላል?") የሚለውን እንመለከታለን።

Wednesday, March 9, 2022

የቤተ ክርስቲያኒቱ ጠላቶች በጉያዋ ናቸው!

ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በሦስት መንገድ ችግር ውስጥ ናቸው። 1ኛ/ ወደው ባልተወለዱበት ዘር ትግሬ በመሆናቸው በኦሮሙማው ኃይል የሚታዩት እንደጠላት ነው። 2ኛ/ የራሳቸው የአመራርና የሥልጣን አጠቃቀም ድክመት የተነሳ የመፈራትና የመከበር አቅማቸው አናሳ መሆኑ ሌላኛው ችግር ነው። 3ኛ/ ሊቃነ ጳጳሳቱ በራሳቸው የግል ኑሮ ምቾትና ምንግዴለሽነት የተነሳ ቤተ ክርስቲያኒቱን ስለረሷት ከፓትርያርኩ ጋር መቆም አልቻሉም። ወደፊትም ቢሆን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አሁን ባለችበት መንገድ ከተጓዘች በውስጥና በውጪ ጠላቶቿ እየተገዘገዘች የመውደቋ ነገር የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር መፍረሷ አይቀርም። የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ሦስት ምክር ያቀርባል። 1/የቀድሞው ፓትርያርክ ከዚህ ዓለም ስላረፉ አሁን ያሉት ፓትርያርክ ከእድሜ: ከህመምና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች የተነሳ በቂ ውሳኔ እየተሰጠ ባለመሆኑ ችግሮቹ ተደራራቢ እየሆኑ በመገኘታቸው ለቤተክርስቲያኒቱ ፈጣን አመራር መስጠት የሚችል ሰው በራሳቸው በፓትርያርኩ አቅራቢነት እንደራሴ ቢሾም: 2/ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜ መሆኑ ከድግስና ከተጋነነ ሪፖርት ውጪ ችግር ፈቺ ስላልሆነ የየአህጉረ ስብከቶቹን ችግር የሚያጠናና ለእንደራሴው ቢሮ የሚያቀርብ ቡድን ተሰይሞ በየችግሮቹ ዘርፍ ፈጣን ውሳኔ ቢሰጥባቸው: 3/ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የሚቆረቆሩ በሙያ: በልምድና በችሎታ ከልዩ ልዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የአማካሪ ቦርድ ቢቋቋም የተሻለ ይሆናል። ይህ አሰራር በግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያና ተግባራዊ ሆኖ ብዙ ችግር መቃለል ተችሏል። ከዚህ ውጪ አሁን ባሉት ጳጳሳት የሚፈታ የቤተ ክርስቲያን ችግር የለን። አይኖርምም። ራሳቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮች ናቸው። ፈሪሃ እግዚአብሔር የነበራቸውና በጥብዓት ይታገሉ የነበሩት ሁሉ በዐረፍተ ዘመን ሁሉን ትተው ሄደዋል። አሁን ካሉት ጳጳስ ተብዬ ወመኔዎች አንዱ የሆነው ቅዱስ ፓትርያርኩ ለመናገር ያሰቡትን ሃሳብ እንዳያስተላልፉ የዱርዬ ስራውን እንዴት ይሰራ እንደነበር ይህ ቪዲዮ ያሳያልና ተመልክታችሁ ፍረዱ! በፕሮቶኮል ደረጃ ከፓትርያርኩ ፊት መነጋገሪያ ማይክ አይነሳም። ማፊያው ጀነራል ሦስት መነጋገሪያ ፓትርያርኩ እንዳይነጋገሩ ሲያሸሽና ለአዳነች አቤቤ ሲሰጥ ተመልከቱ።

Saturday, September 30, 2017

ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን ምንድነው?



ከማኅበረ ቅዱሳን መሥራቾች አንዱ እንደሆነ የሚናገረው የሜሪላንዱ ኤፍሬም እሸቴ  ስለማቅ ጥንስስ እንደተረከው ብላቴ ጦር ካምፕ ውስጥ ተቀፍቅፈን፤ ዝዋይ ላይ በመፈልፈልና አዲስ አበባ ላይ ኅልውና አግኝተን ሕይወት ዘራን ሲል ይተርክልናል። የኅልውናቸውን መስራቾችና ፈልፋዮች ማንነት ኤፍሬም ዘለግ አድርጎ ሲገልፅ በኅብረተሰባዊት ኢትዮጵያ በመንደር ምሥረታ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ድርሻ የነበራቸው ሰዎች ሲሆኑ እነሱ ባሉበት የዳቦ ስም ወጥቶላቸው «ማኅበረ ቅዱሳን» እንደተባሉ «አደባባይ» በተሰኘው መካነ ጦማሩ በአንድ ፅሁፉ አውግቶናል። ለጠቅ አድርጎ: «ተማሪው በጋምቤላ፣ በመተከል፣ በወለጋ … ጎጆ ቤት ሲሠራ፣ ተፈናቃዩን ሲያቋቁም ቆይቶ ተመለሰ። በደህና ወጥቶ ለመመለስ ያልቀናውም ነበር። እነዚያ መንደር ሊመሠርቱ የወጡት ታላላቅ ወንድሞቻችን በየዛፉ ሥር፣ በየመንገዳቸው ጸሎተ ማርያም ማድረሳቸውን፣ ሲችሉም ተገናኝተው ቃለ እግዚአብሔር መስማታቸውን እንዳላስታጎሉ ሲናገሩ ሰምቻለሁ። እኛን ቃለ እግዚአብሔር ያስተማሩን የዚያ “መንደር መሥራች ትውልድ” አካላት የሆኑ ወንድሞች ናቸው። ወደ ዝዋይም የላኩን እነርሱ ናቸው። እኛ እና እነርሱ በአንድ ላይ ስንሆን ጊዜ በጋራ “ማቅ” ተባልን» ይለናል።
  በእርግጥ የዚያን ዘመን መንደር መሥራችና ትላልቅ ወንድሞች የተባሉት እነማን መሆናቸውን ባናውቅም ረጅም ህልም የነበራቸው: በእውቀትና በሥልጣን ትላልቅ ሰዎች እንደነበሩ መገመት ይቻላል። ለኤፍሬም ሆነ ለማቅ አባላት ትላልቅ ወንድሞች የተባሉት የማኅበሩ ፈጣሪዎችን ረጅም ዓላማ በግልጽ ያውቁት እንዳልነበር እርግጥ ቢሆንም አብዛኛው የማኅበሩን አባላት ያሰባሰባቸው ግን እምነታቸው ስለመሆኑ ከጥርጣሬ ላይ የሚወድቅ አይደለም። ብዙዎቹን የማኅበሩ ተከታይ ያደረጋቸው የቤተ ክርስቲያናቸው ቅናት ብቻ ነበር። ሲመሰረትም የወንድሞች ማኅበር «ማኅበረ ቅዱሳን» ከዚያ ከትንሹ ጅምር ተነስቶ ይህንን ያህል በመግዘፍ ሀገራዊ ማኅበርና የሲኖዶስ ጉባዔ የየዓመቱ የመነጋገሪያ አጀንዳ ይሆናል ብሎ የገመተ አይኖርም። ምናልባት ትላልቅ ወንድሞች የተባሉት እግር በእግር እየተከታተሉና እየኮተኮቱ ያሳደጉበትን  ኅቡእ አጀንዳ ራሳቸው ያውቁ እንደሆን እንጂ ዛሬም ድረስ ከጥቂቶች በስተቀር አብዛኛው የማኅበሩ አባላት እያገለገሉ ያሉት ቤተ ክርስቲያናቸውን እንደሆነ ያስባሉ።
 ነገር ግን ከአባላቱ መካከል በተለየ ተልእኮ ተመልምለው ረጅም አላማና ግቡን እንዲጨብጡ የተደረጉ አመራሮች በሂደት አልተፈጠሩም ማለት የማይቻልበት ምክንያት አንድ ተራ የፅዋ ማኅበር ከብላቴና ከዝዋይ ተነስቶና ግዝፈቱ እውን እየሆነ ሄዶ የጳጳሳቱን ጉባዔ ሲኖዶሱን ማነቃነቅና ለህልውናው ዘላቂነት እንዲቆሙ የማድረግ አቅም መጨበጥ መቻሉ ከበቂ በላይ አስረጂ ነው። ከዚህ ደረጃ ላይ  መድረሱ  እንዲደርስ የተፈለገበት ረጅም ህልምና ራእይ የለውም ማለት ጅልነት ነው። ኅልውናውን የሚያስጠብቅበትን የሕግ ማዕቀፍ በመጎናጸፍ፤ ማኅበሩን ለማሳደግ የሰው ኃይል በማደራጀት፤ የገንዘብ አቅሙን በማጎልበት፤ በአሰራር ውስጥ ጠልቆ በመግባት ራሱን የሚያስጠብቅበት ቅርጽና መዋቅር ቤተክርስቲያኒቱን መስሎና አኅሎ እየያዘ እንደመጣ እርምጃዎቹ ዋቢዎቻችን ናቸው። ዓላማና ግብ ሳይኖረው ኅልውናውን ማስጠበቅ እንደማያስፈልገው ይታወቃል።  እዚህ ይደርሳል ብለው ያልገመቱ ቢገኙም ሂደት ራሱ በሚፈጥረው ስኬት ከተነሳበት ሃሳብ ወጣ ባለ መልኩ ወደሚፈልግበት አዲስ ግብ ለመድረስ  ስትራቴጂ የለውም ማለት ሞኝነት ነው።  ታዲያ የት ሊደርስ ነው? ማኅበረ ቅዱሳን ተሰኝቶ እየደረጀ የሚሄደው?

የታላላቅ ወንድሞች ህልም ማኅበሩን ቅርፅና መልክ እየሰጡ ከትንሹ ትንሳዔው አንስቶ ያሳደጉት ስኬትን እያጎናፀፉ መድረስ ከሚፈልጉት ስውር ግብ ለማድረስ እንጂ በጽዋ ማኅበር ስር ታጥሮ እንዲቀር እንዳልነበር አሁን የደረሰበት ስኬት ያረጋግጥልናል። ዛሬ ከሲኖዶሱ ይልቅ ማኅበሩ ኃይል አለው። ከወዳጆቹ ጳጳሳት ተጠግቶ የበላቸውን እያከከ:ባልመሰላቸው ነገር ደግሞ እያስፈራራ ወይም በተአቅቦ አፋቸውን አስለጉሞ ማንም የማይደፍረውና የቤተ ክርስቲያኒቱ ያልታጠቀ ልዩ ኃይል መሆን ችሏል።
ማኅበረ ቅዱሳን በጥቂቶች አስተሳሰብ በእቅድ የተመሠረተ፤ በተራው አባል ግን በአጋጣሚ እግዚአብሔር ፈቅዶ የተቋቋመ ያህል የሚታሰብ ድርጅት መሆኑን ቢታሰብም እውነታው ግን ቤተ ክርስቲያንን ራሱ መውረስ ነው። መንግሥታዊ መንበሩንም አይመኝም ማለት የዋህነት ነው። አንዳንድ ነጥቦችን እያነሳን ማኅበሩን እንገምግም!

1/ማኅበረ ካኅናቱ ማቅን እንዴት ያየዋል?

ማኅበረ ቅዱሳን በማኅበረ ካህናቱ ዘንድ የሚታየው በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ሽብልቅ የገባ ዘመን አመጣሽ የጭዋ ማኅበር: ሰላይ: ነጋዴ: ስም አጥፊና የኃጢአት ጸሐፊ ዐቃቤ መልአክ ተደርጎ ነው። ይህ የአደባባይ ምስጢር ነው።  ማኅበሩ በቀጥታ ከማኅበረ ካህናቱ ጋር መጋጨት የማይፈልገው ምእመናኑ በአጠቃላይ የተያዙት በካህናቱ አባትነት ስለሆነ. ከስልታዊ አዋጭነቱ አንፃር ጉዳት የሚያስከትልበት መሆኑን በመገምገም ሲሆን በሂደት ግን ጉልበት ለማግኘትና ማኅበረ ካህናቱን ለመናድ በህግ ማሻሻያ ሰበብ በደንብና በመመሪያ. ሽፋን በአባ እስጢፋኖስ የአዲስ አበባ ሀ/ ስብከት ዘመነ ጵጵስና ሞክሮ ሳይሳካለት ቀርቷል። ጊዜ ለመግዛት ካልሆነ በስተቀር ነገ ያንኑ  በሲኖዶስ አስፀድቆ ካህናቱን ለመበታተን ዳግመኛ አይመለስም ማለት የዋህነት ይሆናል። በጥቅሉ ማኅበረ ቅዱሳንና ካህናቱ ዓይንና ናጫ ናቸው።

2/ ማኅበረ ቅዱሳንና የሰንበት ት/ ቤት ወጣቶች:

ወጣቶች ከእድሜአቸው አንፃር ነገሮችን የሚመለከቱበት መነፅር በአንድ አቅጣጫ የተወሰነ ነው። በተለይ ደግሞ ከእምነት አንፃር በሚገባቸው  ስስ ስሜት በኩል በወጣት ቋንቋ የሚነግራቸውን ቶሎ ይቀበሉታል። አሁን ባለው ሁኔታ ነጠላን በመስቀልኛ አጣፍቶ የራሱን ስብከት ለነገራቸው ማቅ ያላቸው ፍቅር ልዩ ነው።  የማኅበሩ ያልታጠቀ ኃይል የሰንበት ት/ቤት ወጣት ነው። ይህንን ኃይል መያዝ ማለት በየአጥቢያው ለማኅበሩ ህልውናና ስርፀት አስፈላጊ በር ለማስከፈት ጠቃሚ መሆኑን አሳምሮ ያውቃል። በዚያ ላይ ለማኅበሩ ህልውና አደጋ የሚፈጥር የአጥቢያ አስተዳዳሪ ወይም ማኅበረ ካህናት የማስወገጂያ ጦር ሆኖ ያገለግላል። በተለይ ደግሞ ሙሰኛና ነውር የተገኘበት ከሆነ ግፋ በለው የሚል አዋጅ የሚታወጀው በሰንበት ት/ ቤት ወጣት በኩል ነው። ስለሆነም የወጣቶቹን የሰንበት ት/ቤት ኃይል መቆጣጠር ማለት አጥቢያውን መቆጣጠር ማለት ነው። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ለጥምቀት በዓል አስፋልት በመጥረግ: ቄጠማ በመጎዝጎዝና ምንጣፍ በማንጠፍ መንፈሳዊ ቅናት መሰል ቅንቅን የወረሳቸውን የበጎ ፈቃድ ወጣቶችን ማኅበሩ "የጥምቀት ተመላሾች ማኅበር" በሚል ስም አዋቅሯቸው በራሱ መረብ ስር አስገብቷቸዋል። ነገር መፈለጊያ ጥቅስ በማልበስ "አንዲት ሃይማኖት: አንዲት ጥምቀት" የሚል ቲሸርት አስለብሶም በአደባባይ ጠብ ያለሽ በዳቦ ሲያሰኝም ነበር።  በሌላ በኩልም በአባልነት የያዛቸው የየአጥቢያውን ሰንበት ተማሪዎች ብቻ ሳይሆን የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን "ግቢ ጉባዔ" በሚል ሽፋን ለራሱ ዓላማ ስርፀት ከሚደክምባቸው ኃይሎች መካከል ተጠቃሾች ናቸው። ነገ በሚሰማሩበት የሥራና የሥልጣን ወንበር የማኅበሩ ወኪል የሚሆኑበትን መደላድል ዩኒቨርሲቲ ድረስ ገብቶ ይፈጥራል። ሌላው መረሳት የሌለበት ነገር ማኅበሩ የፖለቲካ ድርጅት የሆነ ያህል አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት በሚጠሉ ፖለቲከኞች ሁሉ እንደ አንድ አስፈላጊ አካል ሆኖ የመቆጠሩ ጉዳይ
መዘንጋት የለበትም። ለምን? ብሎ መጠየም ተገቢ ጉዳይ ነው።
እነዚህ አብሮነት ያገናኛቸው የእምነት ስምምነት ውል መኖሩ ሳይሆን የሚያቀራርባቸው ፖለቲካዊ ስልት መሆኑን ለማወቅ ብዙም ምርምር አይጠይቅም።

ማኅበሩ ከላይ ከፍተኛው የሥልጣን አካል የሆነውን ሲኖዶሱን ይዟል። ከታች አብዛኛውን የገንዘብ ምንጭና የጉልበት ኃይል የሆነውን ወጣቱን አቅፏል። በመካከል ያለው የካህናቱ ኃይል የሚደመጥበትና ማኅበሩን የሚቋቋምበት አቅም ስለሌለው አንገቱን ደፍቶ ቀርቷል።

3// ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ምዕመናን ያበረከተው ምንድነው?

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ መቅደሱ የክህነት አገልግሎት ላይ የተሰማራ ባለመሆኑ ለምዕመናኑ ከካህናቱ በተሻለ የሚሰጠው አገልግሎት ይኖራል ተብሎ አይታሰብም። ቤተ ክርስቲያኒቱ ሳትሰጥ የቀረችውና ማኅበሩ ሊያሟላው የሚችለው አንዳችም ነገር የለም።
 በየአድባራቱ ወይም በየገዳማቱ ከምዕመናን አባላቱና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶች ጋር ያለውን ቅርርብ በመጠቀም ዓላማና ግቡን ለማስረጽ በሚያደርገው ትግል ውስጥ ከካህናቱ በኩል ያለውን  ተቃውሞ ለመከላከል ሲል ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆር በመምሰል ስም በማጥፋት፤ በአድማና በህውከት ከቦታቸው እንዲነሱ፤ እንዲጠሉ በማስደረግ ወይም ዝም ጭጭ ብለው፤ አንገታቸውን ደፍተው እንዲኖሩ በሚያደርገው ተግባሩ ያተረፈው ነገር ቢኖር የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ወደሌሎች ቤተ እምነቶች መኮብለል ብቻ ነው። በሐረር፤ በድሬዳዋ፤ በደቡብ፤ በምዕራብና በምሥራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት እንደጎርፍ ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው የኮበሉለት ማኅበረ ቅዱሳን በየቦታው በፈጠው ሁከትና ብጥብጥ የተነሳ ነው።

   በእርግጥ አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ባሉበት መርጋት ትልቅ ሚና ተጫውቷል ቢሉም ተረትና እንቆቅልሽ ለማስተማር ካልሆነ በስተቀር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን የመተካት አንዳችም አቅም የሌለው ድርጅት መሆኑ ይታወቃል።
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከ1960 ዓ/ም በፊት ከ1% በታች የነበሩት የፕሮቴስታንት ቤተ እምነቶች እስከ 1984 ዓ/ም ድረስ 5.5% የደረሱ ሲሆን እስከ 1994 ዓ/ም ድረስ በዐሥር ዓመት ውስጥ ብቻ 10.2% ለመድረስ በቅተዋል። አሁን ባለው ስታስትስቲክ የፕሮቴስታንቱ ቁጥር ከሀገሪቱ ሕዝብ ውስጥ 18.6% ሲደርስ በተቃራኒው ደግሞ ከሀገሪቱ ሕዝብ 60% ገደማ የኦርቶዶክስ ቤተ እምነት ተከታይ የነበረው ቁጥር በአስደንጋጭ መጠን ወደ 43.5% ያሽቆለቆለው ባለፉት ዐሥርተ አመታት ውስጥ መሆኑ የሚያሳየን ነገር የማኅበረ ቅዱሳንን የስብከትና እንቅስቃሴ ምዕመናኑን ከመበተን ይልቅ በቤታቸው የማቆየት አቅም እንዳልነበረው አረጋጋጭ ነው። ውግዘትና ሁከት እንደውጤት ከተቆጠረ ማቅ በተገቢው ሰርቷል።   አንዳንዶች እንደሚያስወሩት ሰዎች ከነባር ቤተ እምነታቸው የኮበለሉት በስንዴና በአቡጀዲ ተገዝተው ሳይሆን መሬት ያለው እውነታ የሚነግረን ጊዜውን የሚመጥን አስተዳደርና ዘመኑን የሚዋጅ የወንጌል ቃል ትምህርት ስለሌለ ብቻ ነው። ለመሆኑ "ድንጋይ ዳቦ ነበረ" ከሚል ስብከት ያልተላቀቀው ማቅ ሁከትና ብጥብጥ ጨምሮበት ማን ባለበት ቆሞ ሕይወቱን በከንቱ ይገብራል?
ወደፕሮቴስታንቱ ጎራ ከኮበለለው 17% ገደማ የሚሆነው ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የወጣ እንጂ በዳንጎቴ ፋብሪካ የተመረተ የሰው ሲሚንቶ አይደለም። ማቅ እንኳን ከሌላ ቤተ እምነት ሰብኮና አሳምኖ ሊያመጣ ይቅርና ያሉት ተረጋግተው እንዳይኖሩ ሲሰራ የቆየ መሆኑ አይታበልም። የማኅበረ ቅዱሳን የተረትና እንቆቅልሽ አስተምህሮ ማንንም ሰብኮ መመለስ አይችልም።  ለጠያቂ ትውልድ የሚመጥን መልስ ሳይኖር ስመ ተሐድሶን መለጠፍና የስንዴ ሃይማኖት በማለት ማጣጣል ኩብለላውን ማስቆም አይቻልም። "አንድ ሳር ቢመዘዝ"  በሚል የሞኝ ተረት እያቅራሩ መኮፈስ የትም አያደርስም። ኢየሱስ ክርስቶስ ሥግው ቃል የሆነበት ምስጢር አንድ ሰው ፍለጋ ነው። ማቅና ደጋፊ ጳጳሳቱ ከአፋቸው የማይጠፋው ነገር በሰው ቁጥር መመካታቸው ቢሆንም ሳሩ ተመዞ ተመዞ እያለቀ መሆኑን አላቆመም።  ማኅበረ ቅዱሳን ኖሮ ቤተ ክርስቲያን ከተጠቀመችው ይልቅ ማኅበሩ በየቦታው በሚፈጥረው ሁከትና ግርግር የተጎዳችበት ይልቃል።
4// ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ያበረከተው አገልግሎት እውነት እንደሚወራው ነው?

ሲጀመር ጀምሮ ማኅበረ ቅዱሳን የካዝና ቋቱንና ኪሱን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አያሳይም። በሞዴላ ሞዴል ተጠቀም! ሂሳብህን አስመርምር! በምትሰራው ነገር ሁሉ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ ጠይቅ! መባሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥር የመሆኑ ማረጋገጫ  ካልሆነ በስተቀር ሀብትና ንብረቱን ስለመውረስ የሚያውጅ ድርጊት አልነበረም።  ቀደም ሲል ከእነአባ ሠረቀ ብርሃን ጋር ያጋጫቸው ይኸው ዘራፍ ባይነቱና ዘራፊነቱ ነበር።  ማኅበሩ የትኛውንም የቤተ ክርስቲያኒቱን ቁጥጥር መቀበል አይፈልግም። ለምን?

   ማኅበሩ ፈቃደኛ አለመሆኑ የሚያመለክተው ቢኖር አንድም ራሱ ብቻ አዋቂ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያኒቱን አሠራር ይንቃል፤ አለያም ምን እየሰራ እንዳለ እንዲታወቅበት አይፈልግም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን  አበረከትኩት የሚለው አገልግሎት የስም፤ የዝናና ራሱን በማሳደግ የሚጠቅምበት ስልታዊ እንቅስቃሴ ከመሆን የዘለለ አልነበረም ማለት ነው።
ለምሳሌ ጣሊያን ኢትዮጵያን ከወረረች በኋላ በመንገድ ሥራ፤ በውሃ ቧንቧ ግንባታ፤ በመብራት ዝርጋታ ላይ ተሰማርታ ነበር። ኢጣሊያ ያንን ማድረጓ ወረራዋን ፍትሃዊ ሊያሰኘው እንደማይችለው ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን ፈጸምኳቸው የሚላቸው አንዳንድ እንቅስቃሴዎች  የማኅበሩን ኢፍትሃዊ እርምጃዎችን ፍትሃዊ ሊያሰኙት በጭራሽ አይችሉም። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን ተመስርቶ ከተከናወኑት ሥራዎች ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማኅበሩ የደረሰባት ወከባና ሁከት ዐሥር እጅ ይልቃል። ደግሞስ በ25 ዓመት ዓመት እድሜው «ጧፍና ሻማ ረዳሁ» ከሚል በስተቀር የጧፍና ሻማ ማምረቻ ገነባሁ ሲል አልሰማንም። እንዲያውም ይህንን መንግሥት ለማጃጃል ካለው ገንዘብ ቀንሶ ቦንድ ገዛበት ሲባል ነበር።  በተዘዋዋሪ መንገድ ትመረመራለህ ከምትለው ቤተ ክርስቲያን ያለውን ገንዘብ የመደበቅ ባንዳነት ነው ። ለአብነት ት/ቤቶችና ለመምህራን ሠራሁ የሚለውም ቢሆን በአካፋ ከዛቀው በማንኪያ እያካፈለ ላለመሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱ ባደረገችው ምርመራ አልመሰከረችለትም።   በአጠቃላይ ማቅ በመኖሩ ቤተ ክርስቲያን ከኪሳራ በቀር ያተረፈችው ነገር የለም።

5/ከማኅበረ ቅዱሳን ጥፋት ዋነኛ ተጠያቂዎቹ ደጋፊ ጳጳሳቱ ናቸው!

በማኅበሩ ሁሉን አቀፍ ጥፋት ዋነኛ ባለእዳዎች ደጋፊ ጳጳሳቱ ናቸው። ይልቁንም የአማራ ጳጳሳት: በይበልጥም ሸዌ ጳጳሳት ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። በቅርቡ ባየሁት አንድ የፌስቡክ ገጽ ላይ አባ ቀውስጦስ የአዞ እንባ ሲያፈሱ ነበር።  ማኅበሩ ከሌለ እኛ የለንም የሚሉና ቤተክርስቲያኒቱን መንፈስ ቅዱስ ሳይሆን ማኅበሩ የሚጠብቃት አድርገው የደመደሙ አስመሳይ ጳጳስ ናቸው። ብዙዎቹ ጳጳሳት በዐውደ ምሕረት ስለቅድስና ይስበኩ እንጂ ቀርቦ ገመናቸውን ለመረመረ የሚሰቀጥጥ ነገር ይሰማል። ይህንን ገመና ለመሸፈን ለማኅበሩ "ተናገር በከንፈሬ ተቀመጥ በወንበሬ" ብለው እሱ እነሱን አስቀምጦ ሀገረ ስብከታቸውን ያስተዳድርላቸዋል። ከዚያም በላይ ወደ ቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳ አስቀርጾ ለሚያስገባ ማኅበር ጥብቅና የሚቆሙ: የራሳቸው ኅልውና ለማኅበሩ አሳልፈው የሰጡ ጳጳሳት ለቤተ ክርስቲያን መዳከም ተጠያቂዎች ናቸው። ፓትርያርኩን በህገ ቤተ ክርስቲያን ተጣሰ ሽፋን እጅ ከወርች አስረው አላሰራ እያሉ ያሉት ሞቴን ከማኅበሩ በፊት ያድርገው የሚሉ የክርስቶስን ሞት በማኅበሩ ጉልበት የተኩ
ጳጳሳት ናቸው። እነዚህ ሥጋውያንእንጂ መንፈሳውያን አይደሉም። ቤተ ክርስቲያን በማኅበረ ቅዱሳን ነው ተጠብቃ ያለችው ከማለት ሌላ ሞት አለ?
ከዚያም ባሻገር ጵጵስና ማዕርግ እንጂ ከኃጢአት የመንጻት የመጨረሻ ማረጋገጫ አይደለም።  በሚሊዮኖች ብር የሚገመት ቪላ የሚገነቡ፤  ከደሃይቱ ቤተ ክርስቲያን በሚወጣ ገንዘብ እንደውሃ በሚፈስ መኪና የሚሄዱት: ገንዘባቸው ባንክን ማጨናነቁ በሚነገርበት ሁኔታ ዓለም በቃኝ ብለዋል ብሎ ስለብቃት በመናገር ማንንም ማታለል አይቻልም። እንኳን በፈጣሪ ፊት በካህናቱ ዓይን ብዙው ገመና እየታወቀ በብፅእና ማዕርግ ተቀብሎ መኖሩ  የራስ ገመና ለማን ይነገራል? ተብሎ እንጂ የተከደነ: ያልተገለጠ: የተሰወረ : ያልታወቀ ኖሮ አይደለም። የዘር ቆጠራውና የወንዜ ልጅ ዜማው የሚገነው በነዚሁ በጳጳሳቱ ላይ ነው። ዘመድ ከመቅጠርና የዓይኑ ቀለም ያላማራቸውን ሰው ከማባረር ባሻገር ለህዝባቸው አገልግሎት የሚውል  ጤና ጣቢያ: የውሃ ቧንቧና ለልጆቻቸው ት/ቤት ሰርተዋል ተብሎ ዜና በማይነገርበት የልማት ዘመን ለከንቱ ማኅበር መቆም ለኦርቶዶክስ የቆሙ ያህል ከማሰብ የበለጠ ከንቱነት ሊኖር አይችልም።
ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳንን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በማሳደግ፤ በማግነን አሁን ላለበት ደረጃ በማድረስ በኩል ጳጳሳቱ ኃላፊነት አለባቸው። የትውልድም፤ የታሪክም ተጠያቂነት እንዲሁም በሆነውና በሚሆነው ነገር ሁሉ በእግአብሔር ፊት ባለእዳዎች ናቸው።
ጳጳሳቱ በተቀመጡበት የቤተ ክርስቲያን አመራር ወንበር ላይ መንፈሳዊ ይሁን ቁሳዊ ልማት የማምጣት፤ ሕዝቡን ወደ እድገትና ራስን ወደመቻል የሥራ አቅም የማሳደግ ኃላፊነት የተጣለባቸው ቢሆንም ይህንን ሲያደርጉ አይታዩም። ከዚህ ይልቅ በማኅበረ ቅዱሳን ባላ እየተደገፉ ስሙን ጳጳሳቱ ተሸክመው ሥራውን ለማኅበሩ በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱ ከነበረችበት ፈቀቅ እንዳትል አድርገዋታል። ቤተ ክርስቲያኒቱ ካሏት ሁለት ኮሌጆች በስተቀር በሀገረ ስብከት ደረጃ አንድም ጳጳስ ኮሌጅ ወይም ሴሚናሪ ት/ቤት ከፍቶ ማኅበረ ካህናቱን በሙያ: በክህሎት: በትምህርትና ዘመኑ ከደረሰበት የእውቀት መር አስተዳደር እያደረሱ እንዳልሆነ እናውቃለን።
 ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሁለት የተከፈለችውም ይሁን ክፍፍሉ ባለበት ቦታ ሁሉ ውስጧ የሚታወከው በጳጳሳቱ በራሳቸው መሆኑን ያየናቸው ተሞክሮዎች ያስረዱናል። መንፈሳዊነታቸውን ያሸነፈ ሥጋዊ ጳጳስነት ባያይል ኖሮ ቤተ ክርስቲያን ለሁለት አትከፈልም ነበር። ተከፍላም አትቀርም ነበር።

6/ ማኅበረ ቅዱሳንና የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ አይገናኙም!

ቤተክርስቲያን በመዋቅር የሊቃውንት ጉባዔ እንዳላት ይታወቃል። ይሁን እንጂ ይህ የሊቃውንት ጉባዔ የቤተ ክርስቲያኒቱን በዘመኑ ያሉ አስተምህሮዎች እየመረመረ ስህተቶችን እየለየ፤ በሐዋርያት መሠረት ላይ ያሉትን እያጸና እውነታኛውንና የቀደምት አበውን ትምህርት ሕዝቡን መመገብ ሲገባው እስከመኖሩ በማይታወቅበት ደረጃ ላይ መገኘቱ ያሳዝናል። ዛሬ ላይ የሊቃውንት ጉባዔውን ጉባዔ በአጅ አዙር በመረከብ በመመርመር ለስደትና ለውግዘት ተሰልፎ የሚገኘው ይህ ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ያልተማረው ሊቃውንት ጉባዔ ነው። በዚህ ማኅበር የተነሳ እውነት ተደፍቆ ተቀብሯል። ሊቃውንት ተሰደዋል። እነ "ሆድ አምላኩና እነልጆቼን ላሳድግበት" ብቻ ወንበር ይዘው ቀርተዋል። ይሁን እንጂ ይህ ድርጊት መቀጠሉ መልስ ያልተገኘላቸውን ጥያቄዎች ማስቀረት አይችልም። የተለመደው ባህላዊ እምነት ሳይነካ ባለበት ተሸፍኖ እንዲቀመጥ ማድረጉ ኩብለላውን አያቆምም። ትውልዱ የሚነገረውን ብቻ እየሰማ የሚነዳ ሳይሆን የሚጠይቅም በመሆኑ ከፊት እየሄደ የሚመራ ሊቃውንት ጉባዔ ያስፈልግ ነበር። እንዳለመታደል ሆኖ ይህ አልሆነም። አሁን በሚታየው ሁኔታም መቼም ይሆናል ተብሎ አይጠበቅም። በዚህ ላይ የተረት አባትና የአፄው ዘውግ አንጋች ማኅበረ ቅዱሳንና ጳጳሳቱ እያሉ የወንጌል እውነት ተገልጦ፤ የአበው አስተምህሮ አደባባይ ላይ ይነገራል ማለት ዘበት ነው። ተረትና እንቆቅልሽ፤ ባህልና ወግ እንደእምነት ተቀላቅሎ መኖራቸው ያበቃል ተብሎ አይታሰብም። ተኀድሶ የባህሪው የሆነው እግዚአብሔር ነገሮችን በሆነ መንገድ ይለውጥ እንደሆነ ወደሰማይ ማንጋገጥ የወቅቱ አማራጭ ሆኗል። በአጠቃላይ ሲታይ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይፈለግ የተገኘ፤ ሳይወደድ የቆየ፤ እየተጠላ ለመኖር የሚታገል በጥቂት አንጃ ጳጳሳት የሚደገፍና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሸክም የሆነ ድርጅት ነው።

"እርሱም። አሞጽ ሆይ፥ የምታየው ምንድር ነው? አለኝ። እኔም። የቃርሚያ ፍሬ የሞላበት ዕንቅብ ነው አልሁት። እግዚአብሔርም አለኝ። ፍጻሜ በሕዝቤ በእስራኤል ላይ መጥቶአል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ደግሞ አላልፋቸውም። "
(ትንቢተ አሞጽ 8: 2)



Monday, May 15, 2017

የውግዘት ፖለቲካና የቤተ ክርስቲያናችን እጣ ፋንታ


( ክፍል አንድ ) # በቀሲስ መላኩ
መግቢያ
ባለፉት ሃያዎቹ ዓመታት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ
ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ አይታ የማታውቃቸው ሦስት አበይት
ክስተቶች ታይተውባታል። የመጀመሪያው አንደኛው፥ ከፍተኛ
የሆነ የሕዝብ ፍልሰት ነው። በአዲስ አበባ ያሉት አባቶች
በግልጥ ያስቀመጡት ይፋዊ አኀዙ ሰባት ሚሊየን ይባል
እንጂ፥ ከአስር እስከ አስራ አምስት ሚሊየን የሚሆኑ የቤተ
ክርስቲያኒቱ አባላት ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው ወደ ሌሎች
ቤተ እምነቶችና ተቋሞች ሄደዋል። ሁለተኛው ዓቢይ
ክስተት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሦስት መከፈሏ ነው።
የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ አራተኛው ፓትርያክ ብፁዕ
ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከመንበራቸው ከተሰደዱበት
ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስደት ያለው ቅዱስ
ሲኖዶስ፥ በአገር ቤት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ እና ገለለተኛ
በሚል ተከፍላለች። ሦስተኛው እና ቤተ ክርስቲያኒቱ
በታሪኳ አይታው በማታውቀው መንገድ የተከሰቱ ነገሮች
ቢኖሩ በተለይ አዲስ አበባ ባሉት አባቶች ዘንድ፥ «
ውግዘት» እንደ ታላቅ መሣሪያ መያዙ ነው።
በዚህ በያዝነው በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች ተቀራርበው
አሳባቸውን በሚካፈሉበት ዘመን፥ አብያተ ክርስቲያናት
ያለፈ ውግዘታቸውን በይቅርታና በመግባባት አስተካከለው፥
አንድ በሚያደርጋቸው ነገር ላይ ለመነጋገር እየጣሩ ነው።
በቅርቡ የሮም ፖፕና የእስክንድርያው ፓትርያርክ አንዳቸው
የአንዳቸውን ምእመን ዳግም እንዳያጠምቁ
መፈራረማቸው ይታወቃል። ሆኖም ግን ባለፉት 25
ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ ባሉት አባቶች አማካይነት፥
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በሺዎች የሚቆጠሩ
ምዕመናኖቿን እና አገልጋዮቿን አውግዛለች። ከአንድ
ቢሊየን አባላት በላይ ያላት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን
ባለፉት አንድ መቶ አመታት ያወገዘቻቸውና በአዲስ አበባ
ያሉት አባቶች ያወገዙትን ስንመለከት በቍጥር የእኛው
በልጦ እናገኛለን። በአንድ በኩል የምዕመናኑ በሚሊየኖች
ወደ ሌሎች የእምነት ተቋማት መሄድ በሌላ በኵል ደግሞ
ጳጳሳትን ሳይቀር ምእመናንን ጨምሮ በመቶ ሺዎች
የሚቆጠሩ ምእመናንን ማውገዝ ከየት መጣ ለምንድነው
ይህ ክስተት በእኛ ዘመን የተደጋገመው? ከዚህ ውግዘት
በስተጀርባ ያሉት እነማን ናቸው? ተጠቃሚዎቹስ እነማን
ናቸው የሚለውን ለመመለስ በመጀመሪያ ስለውግዘት
በሚገባ ማወቅ ይኖርብናል።
ሀ. ውግዘት ምንድነው?
ውግዘት ቃሉ፥ ወገዘ ከሚለው ግሥ እንደሚገኝ እና
ፍቺውም መገዘት መለየት መካድ መርገም ማለት እንደሆነ
የሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ
ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ይናገራል። ከዚህ ከቃሉ አንጻር
በምንመለከትበት ጊዜ፥ ቃሉ የሚያመለክተን ከዚህ በፊት
ከአንድ አካል ጋር አንድነት (communion) የነበረውን
እንዲለይ (excommuncate) ማድረግ ነው። ይህን
ግልጥ ለማድረግ ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእንዴት
ያለ መንገድ እንደተቀመጠ በማየት ትርጉሙን
እንመለከታለን።
1.ውግዘት እርግማን ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ሲጽፍላቸው
«ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥
ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥
የተረገመ ይሁን። አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን
ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም
ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን።» ይላቸዋል። ( ገላ ፩፥፰-
፱) ግእዙም « አትሙሰ መልአክ እምሰማይ ለእመ
መሀረክሙ ካልአ እምዘ መሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።
በከመ እቤ ቀዳሚ ወይእዜኒ ካዕበ እብል ለእመቦ
ዘመሀረክሙ እምዘመሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።»
አስተውሉ አማርኛው « የተረገመ ይሁን የሚለውን ግእዙ
የተወገዘ ይሁን ይለዋል። ይህ ውግዘት ወይም እርግማን
ምን ማለት እንደሆነ እንመልከት፥ አዲስ ኪዳን
ለመጀመሪያ ጊዜ የተጻፈበትን የግሪኩን ቃል
በምንመለከትበት ጊዜ፥ የተወገዘ ይሁን አናቴማ ኤስቶ
(ἀνάθεμα ἔστω ) ይለዋል። አናቴማ ቃሉ በብሉይ
ኪዳን « እርም»፥ «ለእሳት የተሰጠ» ማለት ነው። ለምሳሌ
ኢያሱ በኢያሪኮ የተገኘው ሁሉ እርም እንዲሆን ሲያዝ
አካን የተባለው ሰው « እርም ከሆነው ነገር ወሰደ»
ይለናል። ኢያሱ7፥1። እንዲህ ዓይነት ብዙ ጥቅሶች
በብሉይ ኪዳን እናገኛለን። በአዲስ ኪዳንም ይህንኑ ቃል
ሳይስት፥ አናቴማ ( ውግዘት እርግማን) ማለት
በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ በገላያ መልእክቱ ላይ በሐዋርያት
ከተሰበከው የጸጋ ወንጌል የተለየ ወንጌልን የሚሰብክ
በዚህ የእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ እንደሚወድቅ ሲናገር
እናያለን።
2. ውግዘት ለሰይጣን አልፎ መሰጠት ነው።
አሁንም ወደ ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ስንመጣ
በ1ቆሮ5፥5 ላይ «መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን
ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን
እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ሲል እናገኛለን። ቅዱስ ጳውሎስ
በዚህ ስፍራ ሐዋርያዊ ውግዘቱን ያሳረፈበት ሰው፥ በሥነ
ምግባር ውድቀት ውስጥ የተገኘ ማለትም የአባቱን ሚስት
ያገባ ሰው ነው። ሐዋርያው ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች
ሲናገር «ይህን ሥራ የሠራው ከመካከላችሁ ይወገድ። እኔ
ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ
ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን
እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም
አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን
ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን፥ መንፈሱ በጌታ
በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት
ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ይላል።
ይህ የቅዱስ ጳውሎስ ቃል ስለ ውግዘት ሦስት ዋና ዋና
ነገሮችን ያሳየናል። አንደኛ፥ ይህ ነገር በጉባኤ በጥንቃቄ
የሚታይ ነው። ጉባኤው የክርስቶስ ጌትነት የከበረበት
ጉባኤ መሆን አለበት። የሐዋርያው ሥልጣን የከበረበት
መሆን አለበት። « እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» በዚህ ዘመን ያለውን
በውግዘት ዙሪያ የሚከናወነው፥ ተመሳሳይነቱ ከፖለቲካ
አደባባዮች ጋር ነው። አንደኛ ከብሮ የሚታየው ክርስቶስ
ሳይሆን የሰዎች የተንኮለኛነት ችሎታ ነው። ለምሳሌ
ባለፉት ሃያ አምስት አመታት በኢትዮጵያ ያሉት አባቶች
በአመት ሁለት ጊዜ ሲሰበሰቡ፥ ከስብሰባቸው በፊት፥
የተቃውሞ ሰልፍ፥ የክስ ደብዳቤዎች፥ ዘመቻዎች፥
ይካሄድባቸዋል። ወደስብሰባው የሚሄዱ አባቶች
ስብሰባው ከመጀመሩ በፊት ተወጋዡ ማን
እንደሚሆን፥ውሳኔው ምን መሆን እንዳለበት ተነግሮአቸውና
ተጽእኖ ተደርጎባቸው ነው የሚገቡት። ነገሮችን ከምንም
ነገር ነጻ በሆነ መንገድ ለማየት የሚሞክሩ አባቶች፥
በስድብ በስም ማጥፋት ጥላሸት ይቀባባቸዋል። በዚህ
ምክንያት አንዳንዶች ዝምታን ሲመርጡ አንዳንዶች
ለተጽእኖው ያጎበድዳሉ። ቅዱስ ጳውሎስ « ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» ሲል « ብርታታችንና
ጉልበታችን የሚሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ይሆናል» ማለቱ
ነው። እውነት የምትነግሠውና ሐሰት ሥፍራን የምታጣው፥
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይልና በመንፈስ ቅዱስ
መሪነት ስንጓዝ ነውና።
ቅዱስ ጳውሎስ ሌላ ታላቅ ነገር ያነሣል። ይኸውም
ውግዘት ምን ያህል አስፈሪ ነገር እንደሆነ የሚያመለክት
ነው። አንድ ሰው ከእድር ቢለይ፥ ሌላ እድር ውስጥ
ይገባል። ወይም በዘመናዊው ዓለም ሌላ ዘዴ ሊጠቀም
ይችላል። ( ላይፍ ኢንሹራንስ ሊገባ ይችላል።)ፋንታ
( ክፍል አንድ ) # በቀሲስ መላኩ
መግቢያ
ባለፉት ሃያዎቹ ዓመታት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ
ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ አይታ የማታውቃቸው ሦስት አበይት
ክስተቶች ታይተውባታል። የመጀመሪያው አንደኛው፥ ከፍተኛ
የሆነ የሕዝብ ፍልሰት ነው። በአዲስ አበባ ያሉት አባቶች
በግልጥ ያስቀመጡት ይፋዊ አኀዙ ሰባት ሚሊየን ይባል
እንጂ፥ ከአስር እስከ አስራ አምስት ሚሊየን የሚሆኑ የቤተ
ክርስቲያኒቱ አባላት ቤተ ክርስቲያኒቱን ትተው ወደ ሌሎች
ቤተ እምነቶችና ተቋሞች ሄደዋል። ሁለተኛው ዓቢይ
ክስተት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሦስት መከፈሏ ነው።
የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ አራተኛው ፓትርያክ ብፁዕ
ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከመንበራቸው ከተሰደዱበት
ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስደት ያለው ቅዱስ
ሲኖዶስ፥ በአገር ቤት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ እና ገለለተኛ
በሚል ተከፍላለች። ሦስተኛው እና ቤተ ክርስቲያኒቱ
በታሪኳ አይታው በማታውቀው መንገድ የተከሰቱ ነገሮች
ቢኖሩ በተለይ አዲስ አበባ ባሉት አባቶች ዘንድ፥ «
ውግዘት» እንደ ታላቅ መሣሪያ መያዙ ነው።
በዚህ በያዝነው በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች ተቀራርበው
አሳባቸውን በሚካፈሉበት ዘመን፥ አብያተ ክርስቲያናት
ያለፈ ውግዘታቸውን በይቅርታና በመግባባት አስተካከለው፥
አንድ በሚያደርጋቸው ነገር ላይ ለመነጋገር እየጣሩ ነው።
በቅርቡ የሮም ፖፕና የእስክንድርያው ፓትርያርክ አንዳቸው
የአንዳቸውን ምእመን ዳግም እንዳያጠምቁ
መፈራረማቸው ይታወቃል። ሆኖም ግን ባለፉት 25
ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ ባሉት አባቶች አማካይነት፥
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በሺዎች የሚቆጠሩ
ምዕመናኖቿን እና አገልጋዮቿን አውግዛለች። ከአንድ
ቢሊየን አባላት በላይ ያላት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን
ባለፉት አንድ መቶ አመታት ያወገዘቻቸውና በአዲስ አበባ
ያሉት አባቶች ያወገዙትን ስንመለከት በቍጥር የእኛው
በልጦ እናገኛለን። በአንድ በኩል የምዕመናኑ በሚሊየኖች
ወደ ሌሎች የእምነት ተቋማት መሄድ በሌላ በኵል ደግሞ
ጳጳሳትን ሳይቀር ምእመናንን ጨምሮ በመቶ ሺዎች
የሚቆጠሩ ምእመናንን ማውገዝ ከየት መጣ ለምንድነው
ይህ ክስተት በእኛ ዘመን የተደጋገመው? ከዚህ ውግዘት
በስተጀርባ ያሉት እነማን ናቸው? ተጠቃሚዎቹስ እነማን
ናቸው የሚለውን ለመመለስ በመጀመሪያ ስለውግዘት
በሚገባ ማወቅ ይኖርብናል።
ሀ. ውግዘት ምንድነው?
ውግዘት ቃሉ፥ ወገዘ ከሚለው ግሥ እንደሚገኝ እና
ፍቺውም መገዘት መለየት መካድ መርገም ማለት እንደሆነ
የሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ
ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ይናገራል። ከዚህ ከቃሉ አንጻር
በምንመለከትበት ጊዜ፥ ቃሉ የሚያመለክተን ከዚህ በፊት
ከአንድ አካል ጋር አንድነት (communion) የነበረውን
እንዲለይ (excommuncate) ማድረግ ነው። ይህን
ግልጥ ለማድረግ ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእንዴት
ያለ መንገድ እንደተቀመጠ በማየት ትርጉሙን
እንመለከታለን።
1.ውግዘት እርግማን ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ሲጽፍላቸው
«ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥
ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥
የተረገመ ይሁን። አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን
ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም
ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን።» ይላቸዋል። ( ገላ ፩፥፰-
፱) ግእዙም « አትሙሰ መልአክ እምሰማይ ለእመ
መሀረክሙ ካልአ እምዘ መሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።
በከመ እቤ ቀዳሚ ወይእዜኒ ካዕበ እብል ለእመቦ
ዘመሀረክሙ እምዘመሀርናክሙ ውጉዘ ለይኩን።»
አስተውሉ አማርኛው « የተረገመ ይሁን የሚለውን ግእዙ
የተወገዘ ይሁን ይለዋል። ይህ ውግዘት ወይም እርግማን
ምን ማለት እንደሆነ እንመልከት፥ አዲስ ኪዳን
ለመጀመሪያ ጊዜ የተጻፈበትን የግሪኩን ቃል
በምንመለከትበት ጊዜ፥ የተወገዘ ይሁን አናቴማ ኤስቶ
(ἀνάθεμα ἔστω ) ይለዋል። አናቴማ ቃሉ በብሉይ
ኪዳን « እርም»፥ «ለእሳት የተሰጠ» ማለት ነው። ለምሳሌ
ኢያሱ በኢያሪኮ የተገኘው ሁሉ እርም እንዲሆን ሲያዝ
አካን የተባለው ሰው « እርም ከሆነው ነገር ወሰደ»
ይለናል። ኢያሱ7፥1። እንዲህ ዓይነት ብዙ ጥቅሶች
በብሉይ ኪዳን እናገኛለን። በአዲስ ኪዳንም ይህንኑ ቃል
ሳይስት፥ አናቴማ ( ውግዘት እርግማን) ማለት
በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ መውደቅ ማለት ነው።
ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ በገላያ መልእክቱ ላይ በሐዋርያት
ከተሰበከው የጸጋ ወንጌል የተለየ ወንጌልን የሚሰብክ
በዚህ የእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ እንደሚወድቅ ሲናገር
እናያለን።
2. ውግዘት ለሰይጣን አልፎ መሰጠት ነው።
አሁንም ወደ ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ስንመጣ
በ1ቆሮ5፥5 ላይ «መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን
ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን
እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ሲል እናገኛለን። ቅዱስ ጳውሎስ
በዚህ ስፍራ ሐዋርያዊ ውግዘቱን ያሳረፈበት ሰው፥ በሥነ
ምግባር ውድቀት ውስጥ የተገኘ ማለትም የአባቱን ሚስት
ያገባ ሰው ነው። ሐዋርያው ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች
ሲናገር «ይህን ሥራ የሠራው ከመካከላችሁ ይወገድ። እኔ
ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ
ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን
እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም
አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን
ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን፥ መንፈሱ በጌታ
በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት
ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው።» ይላል።
ይህ የቅዱስ ጳውሎስ ቃል ስለ ውግዘት ሦስት ዋና ዋና
ነገሮችን ያሳየናል። አንደኛ፥ ይህ ነገር በጉባኤ በጥንቃቄ
የሚታይ ነው። ጉባኤው የክርስቶስ ጌትነት የከበረበት
ጉባኤ መሆን አለበት። የሐዋርያው ሥልጣን የከበረበት
መሆን አለበት። « እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» በዚህ ዘመን ያለውን
በውግዘት ዙሪያ የሚከናወነው፥ ተመሳሳይነቱ ከፖለቲካ
አደባባዮች ጋር ነው። አንደኛ ከብሮ የሚታየው ክርስቶስ
ሳይሆን የሰዎች የተንኮለኛነት ችሎታ ነው። ለምሳሌ
ባለፉት ሃያ አምስት አመታት በኢትዮጵያ ያሉት አባቶች
በአመት ሁለት ጊዜ ሲሰበሰቡ፥ ከስብሰባቸው በፊት፥
የተቃውሞ ሰልፍ፥ የክስ ደብዳቤዎች፥ ዘመቻዎች፥
ይካሄድባቸዋል። ወደስብሰባው የሚሄዱ አባቶች
ስብሰባው ከመጀመሩ በፊት ተወጋዡ ማን
እንደሚሆን፥ውሳኔው ምን መሆን እንዳለበት ተነግሮአቸውና
ተጽእኖ ተደርጎባቸው ነው የሚገቡት። ነገሮችን ከምንም
ነገር ነጻ በሆነ መንገድ ለማየት የሚሞክሩ አባቶች፥
በስድብ በስም ማጥፋት ጥላሸት ይቀባባቸዋል። በዚህ
ምክንያት አንዳንዶች ዝምታን ሲመርጡ አንዳንዶች
ለተጽእኖው ያጎበድዳሉ። ቅዱስ ጳውሎስ « ከኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን» ሲል « ብርታታችንና
ጉልበታችን የሚሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ይሆናል» ማለቱ
ነው። እውነት የምትነግሠውና ሐሰት ሥፍራን የምታጣው፥
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይልና በመንፈስ ቅዱስ
መሪነት ስንጓዝ ነውና።
ቅዱስ ጳውሎስ ሌላ ታላቅ ነገር ያነሣል። ይኸውም
ውግዘት ምን ያህል አስፈሪ ነገር እንደሆነ የሚያመለክት
ነው። አንድ ሰው ከእድር ቢለይ፥ ሌላ እድር ውስጥ
ይገባል። ወይም በዘመናዊው ዓለም ሌላ ዘዴ ሊጠቀም
ይችላል። ( ላይፍ ኢንሹራንስ ሊገባ ይችላል።)