Sunday, January 27, 2013

በቅ/ላሊበላ ገዳም በዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ቤቶች በቃጠሎ ወደሙ



አዲስ አድማስ ጋዜጣ፤ ጥር 18/2005 ዓ/ም

  • ·        ቤቶቹ ከቤተ መድኃኔዓለም እና ቤተ ዐማኑኤል አጠገብ የተሠሩ ነበሩ።

  • ·        በልደት ክብረ በዓል የቱሪስቶች ቁጥር መቀነሱ ኅብረተሰቡን አስደንግጧል።

በቅዱስ ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም ከዐሥራ አንዱ ውቅር አብያተ መቅደስ ጋር በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ አራት ጥንታውያን ቤቶች በእሳት ቃጠሎ መውደማቸው ተገለጸ፡፡ ባለፈው እሁድ ለሰኞ አጥቢያ መንሥኤው ባልታወቀ ምክንያት በተነሣው የእሳት ቃጠሎ የወደሙት አራት ቤቶች የሣር ክዳን ያላቸው ፎቅ ቤቶች ሲኾኑ፣ የላሊበላን ጥንታዊ የቤቶች አሠራር የሚያሳዩ በመኾናቸው እየተጠገኑ እንዲጠበቁ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ በቃጠሎው የወደሙት ጥንታውያኑ ቤቶች፤ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች መካከል በቅኔና ዜማ ትምህርት መስጫነት ሲያገለግሉ እንደቆዩ ተገልጧል፡፡ ገኛ ቦታቸውም ከዐሥራ አንዱ አብያተ መቅደስ መካከል በታላቁ ቤተ መድኃኔዓለም እና በቤተ ዐማኑኤል አጠገብ 20 - 30 ሜትር ርቀት ላይ መኾኑ፣ የገዳሙ አስተዳደር /ቤት ለቅርሶቹ ደኅንነት ትኩረት ሰጥቶ በቂ ጥበቃና ክብካቤ እንደማያደርግ በካህናቱ እና ምእመናኑ የሚነሡበትን ስጋቶችና ተቃውሞዎች ያጠናከረ ነው ተብሏል፡፡ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማው ነዋሪዎች እንደሚያስረዱት÷ የቃጠሎ አደጋው በደረሰበት ዕለት ሌሊት በሁለቱም አብያተ መቅደስ አካባቢ የገዳሙ ጥበቃ አባላት አልነበሩም፡፡

ከሙስና እና ብልሹ አሠራር ጋር ተያይዞ ጥያቄ የሚነሣባቸውና ላለፉት ስምንት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት የገዳሙ መምህርም ቃጠሎው በደረሰበት ስፍራ የተገኙት ከሁለት ቀናት በኋላ ነው፡፡ ቤቶቹ ሰው በማይኖርበትና ‹‹ኮር ዞን›› ተብሎ በዩኔስኮ በሚታወቀው ለቅርሶች የተለየ ስፍራ የሚገኙ ኾነው ሳለ የተከሠተው ይኸው አደጋ፣ ‹‹በአስተዳደሩ ላይ እየተጠናከሩ የመጡትን ተቃውሞዎች ትኩረት ለማስቀየስ የተፈጠረ›› አድርገው እንደሚወስዱት የስፍራው ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም በአንድ ጊዜ በተደረገው 160 በመቶ የቱሪስቶች ዋጋ ጭማሪ ሳቢያ ዘንድሮ በተከበረው የልደተ ክርስቶስ (ቤዛ ኵሉ) እና ጥምቀት በዓላት ላይ የተገኙት የውጭ ቱሪስቶች ፍሰት ቀንሶ መስተዋሉን የዜናው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

Saturday, January 26, 2013

አባ ሕዝቅኤል ለምን ስብሰባ ረግጠው ወጡ?

ዘመነ ካሣ
             ከጀርመን
የማንም አሿሿሚ አልሆንም የሥልጣን ጥመኞችን አላገለግልምበማለት አራት ወራት የቀረውን የሲኖዶስ ዋና ጸሐፊነታቸውን የሚለቁ መሆናቸውን በደብዳቤ ገለጡ እየተባለ ሰሞኑን የሚወራላቸው አባ ሕዝቅኤል  ቀደም ሲልም ስብሰባ ረግጠው ቢወጡ የፈረሰው ቀኖና ይመለስ ብለው እንዳልሆነ መታወቅ አለበት።
አባ ሕዝቅኤልና በአዲስ አበባ የሚገኙት የሲኖዶስ አባለት ለእርቅና ለሰላም እንዲሁም ለሀያ ዓመታት የዘለቀውን የቤተ ክርስቲያን መለያየት ወደ አንድነት ለማምጣት በቅንነት እና ግልጽ በሆነ መንገድ ቢጓዙ ኖሮ ለዚህ ለከፋ መከፋፈል እንዲሁም ለመንግሥት ጣልቃ ገብነት ባልተዳረጉ ነበር ይልቁንም አባ ሕዝቅኤል  የመንግሥት ጣልቃ ገብነት አለ መባሉ ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው እንደሆነና ቅዱስ ሲኖዶስ ለምርጫ የሚያስፈልጉ ደንቦችን ከማውጣት በቀር መንግሥት ጣልቃ አልገባም በማለት በአደባባይ ተናግረው ጸሐይ የሞቀውን እውነት የካዱ አባት ናቸው አቡነ ገብርኤልም ይሕንኑ ሀቅ ክደው በአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ በሰጡት ቃል የአባ ሕዝቅኤልን ውሸት ደግመውታል።
ይልቁንም አባሕዝቅኤል በአፋቸው ስለ እርቅና ሰላም እያወሩ እሳቸውና መሰሎቻቸው  ከእኛም ወገን ይድረሰን ከሚሉት ግብረ አበሮቻቸው የሚፈልጉትን ፓትርያርክ ለማስመረጥ የሚሄዱበት መስመር እየተዘጋ በመንግሥት የሚደገፉት የነ አባ ሣሙኤል ክንድ እየበረታ ሲሄድ  ማንንም አሿሿሚ አይደለሁም፤ የሥልጣን ጥመኞችን አላገለግልም ማለቱ እና  አራት ወር የቀረውን የጸሀፊነት ሥልጣን እለቃለሁ ማለቱ ምክንያታዊነቱ  ፈጽሞ አይታይም።

Thursday, January 24, 2013

“አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት፣ አንድ ጥምቀት” ማለት ምን ማለት ነው?

የእግዚአብሔር መንግሥት የምትወረሰው አንዱን ጌታ በማመንና የእምነት አዋጅ የሆነውን «አንዲት ጥምቀት» በመጠመቅ እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል። ይሁን እንጂ ዓለምን ደግሞ ዛሬ ላይ ሆነን ስንመለከታት ብዙ ጌቶች፤ ብዙ ቤተ እምነቶችና ብዙ ጥምቀቶችን እያስተናገደች ትገኛለች። ይኼው የዓለሙ አንድ ዘርፍ የእምነት እንቅስቃሴ በኢትዮጵያችን ውስጥም የሚታይ ሲሆን የየራሳቸው ጌታ ያላቸው፤ በየራሳቸው ጥምቀት የሚያምኑ፤ ልዩ ልዩ ሃይማኖቶች መኖራቸው እርግጥ ነው። ከዚህ አንጻር ከእኔ በቀር «አንድ ጌታ፤ አንድ ሃይማኖት፤ አንድ ጥምቀት» በማለት በአደባባይ ለማወጅ የመናገር መብቱና ብቸኛ ውክልና  ያለው ሃይማኖት ኢትዮጵያ ውስጥ የለም ማለት ነው።  ምክንያቱም የሚያምነውን  እምነት በማይቀበሉ ሰዎች መካከል እኔ ነኝ እውነተኛው ብሎ ቢያውጅ አንድም ሌሎቹን ለማስቆጣት ወይም እነሱንም ለተመሳሳይ እንቅስቃሴ እንዲነሳሱ ከሚያደርግ በስተቀር የትክክለኛ እምነት ባለቤት መሆኑን በየትኛውም መልኩ አያረጋግጥምና ነው። «ጸብ ያለሽ በዳቦ ካልሆነ በስተቀር» ይህ ጥበብ ያለው የስብከት ዘዴም አይደለም። በአንድ የሙስሊም በዓል ላይ ታላላቆቹ የአላህ ነብያት መሐመድ፤ ዒሳ/ኢየሱስ/ እና ሙሴ (ሰዐወ) ናቸው የሚል ጽሁፍ ያለበት ቀይ ካናቴራ ሙስሊም ወጣቶች ለብሰው አይቻለሁ። ይህ እንግዲህ «ኢየሱስ ከነብይም በላይ አምላክ ነው» ለሚሉ አማኞች ስድብ  መሆኑ ነው።   በግሉ የሚያምንበትንና የራሱ ቤተ እምነት የሆነውን ዒሳ/ኢየሱስ/  ነብይ መሆኑን ካመነ በካናቴራ ላይ ጽፎ አደባባይ መውጣቱ ምን ለማምጣት ነው? ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናል። «ይህንን የማትቀበሉ ካላችሁ ጸብ ይዛችሁ ኑልኝ!» ብሎ ሁከት መጋበዝ ካልሆነ በስተቀር ምንም ፋይዳ የለውም።

 በሌላ በኩልም በአሁን ዘመን ታቦት ስለመኖሩ የማይቀበል  ቤተ እምነት እንዳለ እርግጥ ነው። ይኼው ቤተ እምነት በተራው « የዘመኑ ታቦት ጣዖት ነው» ብሎ ቢጽፍና ይህንኑ ይዞ አደባባይ ቢወጣ ያለምንም ጥርጥር አንዲት እርምጃ ሳይሄድ ወይ ይገደላል፤ አለያም ደሙ ይፈሳል እንጂ የሚያምንበትን በመጻፉ መብቱ ነው ብሎ የሚቀበለው ሰው አደባባይ ላይ አይገኝም።

ብዙ ኦሮሞዎች የኢሬቻን በዓል ያከብራሉ፤ ወንጌል አምናለሁ ለሚል ለሌላ ሰው ግን ኢሬቻን ለማክበር ዛፍ ስር መስገድና መስዋእት ማቅረብ ጣዖት ከማምለክ ጋር ሊያያዝ ይችላል። ይህንን የኢሬቻ አክባሪዎችን ስሜት የሚያስቆጣ ጽሁፍ በማንጠልጠል አደባባይ መውጣት ለነገር ካልሆነ በስተቀር የትኛውንም ነገር የሚያንጽና በማስተማር ሌላውን ለመለወጥ የሚሰጠው ፋይዳ አይኖርም። በተመሳሳይ መልኩ እነማኅበረ ቅዱሳንና ጎጋ ደጋፊዎቹ፤ መናፍቃን የሚሏቸውን ክፍሎች ለመሳደብ/ አስተምሮ ለመመለስ አይደለም/ በአንድ ወቅት «ያለድንግል ማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም» እና በሌላ ጊዜም «አንዲት ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት» የሚል ሸሚዝ ለብሰው በአደባባይ ሲንጎራደዱ ታይተው ነበር። ይኼው ድርጊት ዛሬም መቀጠሉ እየተነገረ ነው። የሌላውን ስስ ስሜት ለመኮርኮርና አምንበታለሁ የሚሉትን ጽኑ አቋም በአደባባይ በማንጸባረቅ እንደተቃዋሚ የሚቆጥሩትን ክፍል ልብ ለማቁሰል ካልሆነ በስተቀር ኢ-አማኝ የሆነውን ማንንም ሊለውጥ የሚችል ድርጊት አይደለም። ዋናው ነጥብ ለአደባባይ ጽሁፍ የሚመረጡት ጥቅሶችና ጽሁፎች በቤተ እምነቱ ውስጥ ካለው አጠቃላይ አቋም ውስጥ የሌላኛውን ወገን እምነት የሚመለከትና ስሜቱን ሰቅዞ በመያዝ ጠጣር መልእክት የሚያስተላልፈውን መምረጡ የራሱ የሆነ ዓላማና ግብ እንዳለው ለማወቅ አስቸጋሪ አይደለም። ያንን ጥቅስ ይዞ አደባባይ መገኘት ያስፈለገው የእምነቱ ተከታዮች ስለተሰወረባቸው ለመግለጽ ነው ወይስ የእምነቱ ተከታዮች ላልሆኑ ለሌሎች ክፍሎች ብትወዱም ብትጠሉም እኔ እንደዚህ እላለሁ ብሎ ለመንገር? የሚል ጥያቄን ያስከትላልና ነው።


ወንጌል ማስተማር፤ ያላመኑትን ማሳመንና የእኔ እውነት ትክክል ነው ወደሚሉት እምነት ሌላውን ለመቀየር ጥበብ የሚያስፈልገው አገልግሎት መሆኑ እሙን ነው። ወንጌልን መስበክ እንደባለ አእምሮ እንጂ በመታበይ ወይም ማን እንደእኔ በሚል ትምክህት ሊሆን አይችልምና። በዚህች ዓለም የስብከት ጥበብ ሳይሆን  እንደባለ አእምሮ መንፈሳዊ ብስለትና ሌላውን ደስ አሰኝቶ ሊለውጥ በሚችል መታደስ እንጂ በትእቢት አስተሳሰብ የሚደረግ ስብከት ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል። ወንጌልም አበክሮ የሚነግረን ይህንኑ ነው።

«እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ፥ እርሱም ለአእምሮ የሚመች አገልግሎታችሁ ነው። የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ።እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ የእምነትን መጠን እንዳካፈለው፥ እንደ ባለ አእምሮ እንዲያስብ እንጂ ማሰብ ከሚገባው አልፎ በትዕቢት እንዳያስብ በመካከላችሁ ላለው ለእያንዳንዱ በተሰጠኝ ጸጋ እናገራለሁ» ሮሜ 12፤1-3


ከዚህ ተነስተን በሰሞኑ የጥምቀት በዓል ላይ «አንድ ጌታ፤ አንድ ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት» የሚለውን ጥቅስ የለበሱ የጥምቀት ተመላሾች ማኅበር ወጣቶች ማንንም ሰብከው ሳይለውጡ /በእለቱ በዚህ ጥቅስ የተለወጡ አዲስ አማኞች ስለመኖራቸው አልሰማንም/ ወጣቶቹ የመታሰራቸው ዜና ተሰምቷል። ይህንን ተከትሎ የተለያዩ የድረ ገጽ ሚዲያዎች ዜናውን አስተጋብተዋል። በእርግጥ ጥቅሱ የወንጌል ቃል ነው። ቃሉም እውነት ነው። ነገር ግን ይህንን ጥቅስ ለብሰው አደባባይ የዋሉት ወጣቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው «አንድ ሃይማኖት ብቻ» መሆኑን ለማሳወቅ ወይስ ሌሎች ሃይማኖቶችን ለመስበክ? ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናል። ነገሩ በዓለ ጥምቀትን አስታኮ እውነተኛይቱ ሃይማኖት የእኔ ስለሆነ ሌሎቻችሁ ዋጋ የላችሁም ለማለት ካልሆነ በስተቀር እንደ ወንጌል አስተምህሮና እንደ ባለአእምሮ የተለወጠ ሰው፤ ሌላውን ደስ በማሰኘት ወደእውነት እንዲመጣ በመርዳት ለሌላው የሚተርፍ አንዳችም ጥቅም ያለው  አካሄድ አልነበረም። ይልቁንም ሌላው ወገን የራሱን አጸፋዊ ጥቅስ በመልስ ምት ይዞ እንዲመጣ የሚያደፋፍረው ይሆናል። ሌላው የሚያምንበት የራሱ እውነት ለእኔ ውሸት እንደሆነው ሁሉ፤ እኔም የማምንበት እውነት ለእርሱ ውሸት ስለሚሆን የኔን ትክክል ብዬ የማምንበትን እውነት ለማስተላለፍ የምጠቀምበት መንገድ ሌላውን የሚያርቅ ሳይሆን በመረጃና ማስረጃ  የማሳምንበት ሊሆን ይገባል።ምክንያቱም ሃይማኖት የሰዎችን ስሜትና አእምሮ የመቆጣጠር ትልቅ ኃይል ያለው ስለሆነ ማንም ለማስተማር ሲፈልግ ጥበብና ስልት ያለውን መንገድ መከተሉ የግድ ነው።

ሐዋርያው ጳውሎስ በአቴና ከተማ አርዮስፋጎስ አደባባይ ላይ ከድንጋይ በተሰራና «የማይታወቅ አምላክ » የሚል ጽሁፍ ለሰፈረበት ጣዖቱ አምላኪ ሕዝብ ያስተላለፈው የትምህርት መንገድ ትልቅ ግንዛቤ ይሰጠናል። በስብከቱ መነሻ የማይታወቀውን አምላክ፤ ይህ ድንጋይ ነው ብሎ ክብሩን አዋርዶ አልጀመረም። እናንተ ጣዖት አምላኪ ሕዝቦች ወዮላቸሁ ብሎ በማስፈራራትና ጆሮአቸውን ጭው በሚያደርግ ቃል አላስበረገገም። ይልቁንም እንዲህ በማለት ለድርጊታቸው ግምት ሰጥቶ እያዋዛ ወደሚፈልገው ጎዳና መራቸው እንጂ!

Wednesday, January 23, 2013

የውጪው ሲኖዶስ ድርድሩን ቅድሚያ ከመንግሥት ጋር ቢያደርግ ሳይሻል አይቀርም!

ከከፈለኝ ምስጋናው

 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በዘመንዋ ሁሉ ከነበሩ መንግሥታት ጋር እጅና ጓንት ሆና መቆየትዋ እውነት ነው። ከነገሥታቷና ከሹማምንቷ ጋር መሆንዋ በአንድ በኩል ጠቅሟታል። ይኸውም በፈለገችበት የሀገሪቱ አድማስ እንድትስፋፋ፤ በኢኮኖሚ አቅሟ እንድትደላደል፤ ተሰሚነት ያለው ድምጽ እንዲኖራት አግዟታል። በተቃራኒው ደግሞ ከመንግሥታት ጋር ተጠግታ መኖርዋ ራሷን ችላ እንዳትተዳደር፤ ሉዓላዊ የሆነ ሥልጣን እንዳይኖራትና ጉዳይዋን ባላት አቅም እንዳትፈታ በግልጽም፤ በቀጥታም ሲቆጣጠሯት መቆየታቸው አሁን ለደረሰችበት ፖለቲካንና ሃይማኖትን የማቀላቀል ዘመን ላይ እንድትደርስ አድርጓታል። ነገሥታቱ ሌላው ቀርቶ የአድባራትና የገዳማት አለቆችን እስከመሰየም ድረስ ግልጽ ሥልጣን እንደነበራቸው ታሪክ ይነግረናል። እስከ ደርግ መውደቅ ድረስ የጠቅላይ ቤተክህነቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ የሚሾምላት በቤተ መንግሥቱ ነበር። በዘመነ አፄ ኃ/ሥላሴ መነኮሳቱ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል ሆነው በማገልገል በሕዝባቸው ላይ የገባር ሥርዓት እንዲቀጥል ታማኝ አባል በመሆን የነገሥታቱ ባለሟልም ነበሩ።  

  በዚህም ይሁን በዚያ ከመንግሥታቱ ጋር መጣበቅዋ መልካም ገጽታዎችና አሉታዊ መልኮችም አብረዋት እንዲኖር ማድረጉም እውነት ነው።
ይህንኑ ተከትሎ 4ኛው ፓትርያርክ አባ መርቆሬዎስም እንደቀደመው ታሪክ ሁሉ በደርግ መንግሥት ድጋፍና ተቀባይነት ነበራቸው።  ደርግን የሚጠላ ደግሞ እርሳቸውን ቢጠላ አይደንቅም። መደገፍ እንዳለ መቃወምም ሰውኛ ጠባይ ነውና። ገለልተኛ መሆን በማይቻላቸው የቤተክርስቲያን መሪዎች የተነሳ  አንዱ ሄዶ አንዱ ሲመጣ መንግሥታት እንደምትመቻቸው ለማድረግ በመድከም ቁጥጥራቸው ለቤተክህነቷ ቅርብ ነው።  ከዚህም የተነሳ ለደርግ የነበራቸውን አቋም በመመልከትና በእሳቸው ላይ የነበረውን ጥላቻ በራሱ መንገድ ለመፍታት በመፈለግ  ከደርግ ውድቀት በኋላ ወደ ሥልጣን የመጣው የኢህአዴግ መንግሥት እንደቀደሙት መንግሥታት በቤተክርስቲያኒቱ ጉዳይ ላይ እጁን ማስገባቱ አልቀረም።  እውነት እውነቱን ስንነጋገር፤ የአባ መርቆሬዎስን ከሥልጣን መልቀቅ ይፈልግ የነበረው ተረኛው መንግሥት ብቻ ሳይሆን የመንበረ ፓትርያርኩ ብዙዎቹ ኃላፊዎችና ሊቃነ ጳጳሳቱም ጭምር እንደነበር በወቅቱ ከስልጣን የማባረር ተሳታፊዎችን ዘመቻና ግርግር ያስተዋለ አይዘነጋውም። 
  መንግሥትም ሆነ አባ መርቆሬዎስን ለመጣል ጊዜው አሁን ነው ባዮች የዘመቻው አባላት መጻኢውን የቤተክርስቲያን መከፋፈል ከግምት ውስጥ ባለማስገባታቸው የፈጸሙት ስህተት እስከአሁን ላለው ልዩነት ዳርጓል። ቤተክርስቲያን ነጻነቷን ሳታስደፍር እንዳትኖር መሪዎቿ ከመንግሥታት እየተለጠፉ ከመኖራቸው የተነሳ ደርግ መራሹ ቤተክህነት ወደኢህአዴግ መራሽ ተለውጧል። ለዚህ ድጋፍ ሥልጣን ናፋቂ አባላቶችዋ ከፍተኛ ድርሻ አላቸው።
በእርግጥ ቤተክህነት ውስጥ የተሰገሰገው እውነተኛ አማኝ ብቻ አይደለም።  በቆብና በቀሚስ ስር የተሸሸገ አደገኛ ፖለቲከኛም በመኖሩ መንግሥታት በሌላኛው  ዓይናቸውን ቤተክርስቲያኒቱን ቢከታተሏት ሊደንቀን አይገባም። በዘመነ ደርግ የፓርቲው አባላት ቤተክህነቱ ውስጥ ሥልጣን ሲኖራቸው ሌሎቹ ቀን እስኪያልፍ ሳይወዱ እየሳቁ ቀኑን ማሳለፋቸው አይዘነጋም።  የቤተክርስቲያኒቱ መለያየት ለሃይማኖታዊ ፖለቲከኞችም ሆነ ለግልጽ ፖለቲከኞች መሸሸጊያ  ዋሻ በመሆንዋ መንግሥታት በፖለቲካዊ ፍርሃት የተነሳ እጃቸውን እንዲያስገቡ በመደፋፈር ትንፋሿን ይቆጣጠራሉ።  የእግዚአብሔርን መንግሥት ብቻ የሚያገልግሉ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ መንግሥትንም አጣምረው የሚያገለግሉ ሞልተውባታል። ቤተክህነት ለሁለት ጌቶች ከተገዛች ደግሞ አንዱንም ማጣትዋ የግድ ነው። የሃይማኖተኛ ሰው ፖለቲካው ሃይማኖቱ ብቻ መሆን ነበረበት። ዛሬ የሚታየው ሃይማኖተኛ ግን ፖለቲካዊ ሃይማኖተኛ እንጂ ሃይማኖተኛ አማኝ አይደለም። 

"ከፍሬአቸው ታውቁአቸዋላችሁ"

(በጮራ ቊጥር 5 ላይ የቀረበና ከድረ ገጹ የተወሰደ)
ምሁር ነኝ የሚሉ አረጋዊ ከሰዎች ጋር ሲነጋገሩ፥የእኛን ሃይማኖት የሚያህል ፈጽሞ የለምብለው የማውራት ልምድ ተጠናውቷቸዋል፡፡ እንዲህም ሲናገሩ ስመ ሃይማኖታቸውን እየጠሩ ነው፡፡ ቅያሬ የሌለውና የተጋነነው ከቃል ንግግር በቀር የሕይወት ምስክርነት ያልነበረው ወሬአቸው ወዳጆቻቸውንና ቤተ ሰባቸውን ጭምር አሰልችቷቸው ኖሮአል፡፡
አንድ ቀን ከአንድ ወዳጃቸው ጋር ይጨዋወቱ ነበር፡፡ እንደ ተለመደውየእኛን ሃይማኖት የሚያህል የለም፤ ብቻ ምን ያደርጋልሲሉ፤ በተከታዮች ብዛት ከሆነ እምነት ተከታዮች ይባልጣሉኮ! አለና መለሰላቸው፡፡ ትልቋ ልጃቸው ግንአባባ የእኛ ሃይማኖት ካለማመን የሚለይበትን አንድ ነጥብ ቢነግሩኝብትላቸው ምን ለማለት እንደ ፈለገች አልተረዱላትም፡፡ ልጅቷ የመደነጋገር ምልክት በአባቷ ፊት ላይ እንዳየች በሌላ የአገላለጽ ዘዬ ልታስረዳቸው ሞከረች፡፡ አባቷም ሲረዱ በጣም ተቈጡ፡፡
የአረጋዊው ምሁር አስተሳሰብ እምነታችን ጥሩ ነው፤ የእምነታችን ፍሬ ግን መራራ ነው፤ ወይም እምነታችን ፍሬ አልባ (መካን) ነው እንደ ማለት ነው፡፡ ሊሆን ግን አይችልም፡፡ አንድ ሰው ወይም ቡድን የተቀበለውና የሚመራበት የክርስትና እምነት ሕያው ከሆነ የቃል ምስክር ሳያስፈልገው ጣፋጭ ፍሬ አንዠርግጎ ይታያል፡፡